Search

ስብከቶች፤

ርዕስ 9፡ ሮሜ (በሮሜ መጽሐፍ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[Chapter 8-13] ጻድቃንን ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለያቸዋል? ‹‹ሮሜ 8፡35-39››

‹‹ሮሜ 8፡35-39›› 
‹‹ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ ወይስ ጭንቀት ወይስ ስደት ወይስ ራብ ወይስ ራቁትነት ወይስ ፍርሃት ወይስ ሰይፍ ነውን? ስለ አንተ ቀኑን ሁሉ እንገደላለን፤ እንደሚታረዱ በጎች ተቆጠርን ተብሎ እንደተጻፈ ነው፡፡ በዚህ ሁሉ ግን በወደደን በእርሱ ከአሸናፊዎች እንበልጣለን፡፡ ሞት ቢሆን ሕይወትም ቢሆን መላእክትም ቢሆኑ ግዛትም ቢሆን ያለውም ቢሆን የሚመጣውም ቢሆን ሐይላትም ቢሆኑ ከፍታም ቢሆን ዝቅታም ቢሆን ልዩ ፍጥረትም ቢሆን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ካለ ከእግዚአብሄር ፍቅር ሊለየን እንዳችል ተረድቻለሁ፡፡››
   
 
ቁጥር 35 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ ወይስ ጭንቀት ወይስ ስደት ወይስ ራብ ወይስ ራቁትነት ወይስ ፍርሃት ወይስ ሰይፍ ነውን?›› በውስጡ የእግዚአብሄርን ጽድቅ በያዘው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ለሚያምኑ ሰዎች ከተሰጠው የክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? ስደትና መከራ ያንን ፍቅር ይቆርጣሉን? የሰባቱ ዓመት ታላቅ መከራ ከዚያ ፍቅር ሊለየን ይችላልን? በእርግጥ አይችልም!
 
በዚህ ዓለም ላይ ያለ መከራ ወይም ጭንቀት ከሐጢያቶቻችን ካዳነን የጌታችን ፍቅር ሊለዩን አይችሉም፡፡ ስልቹ ሆነን ብቻችንን መሆን ስንፈልግ እንኳን አንድ ሰው ይመጣና ኢየሱስ ከሐጢያቶቻችን አድኖን እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ሲጠይቀን ኢየሱስ በእርግጥም እንዳዳነንና እኛም ሐጢያት አልባ እንደሆንን ምላሽ እንሰጣለን፡፡ ልባችን ምንም ያህል ቢታክትና ቢታወክም እርሱ አሁንም አደኖናል፡፡ እርሱ አሁንም ዘላለማዊ አዳኛችን ነው፡፡ በጣም ብንደክም ወይም ሰውነታችንን መቆጣጠር እስኪያቅተን ድረስ ብንታመም ለእግዚአብሄር ጽድቅ ያለንን አመስጋኝነት መናገር እንችላለን፡፡ መታከት እኛን ከሐጢያቶቻችን ካዳነን የእግዚአብሄር ጽድቅ ሊለየን አይችልም፡፡
 
ስደት፣ ራብ፣ ራቁትነት፣ ፍርሃት፣ ሰይፍ ከእግዚአብሄር ጽድቅ ሊለየን አይችልም፡፡ አንዳንድ ጊዜ በሃይማኖት ሰዎች ስንገለልና ስንኮነን ስደት ይገጥመናል፡፡ ስደታችን ከጓደኞቻችን፣ ከዘመዶቻችን፣ ከጎረቤቶቻችን ይመጣል፡፡ የራሳችን ቤተሰብ አባሎችም ቢሆኑ መናፍቃን እንደሆንን በመክሰስ ይተዉናል፡፡ እነዚህ ስደቶች ከኢየሱስ ክርስቶስ ደህንነት ሊለዩን ይችላሉን? በእርግጥም አይችሉም!
 
ምንም ያህል ክፉኛ ብንሰደድም እኛን ካዳነን የእግዚአብሄር ጽድቅ ሊለየን አይችልም፡፡ የእግዚአብሄር ጽድቅ ሐጢያት አልባ ስላደረገንና ይህም የማይቀየር እውነት ስለሆነ ማንምና ምንም ነገር ከእግዚአብሄር ፍቅር ሊለየን አይችልም፡፡
 
መንፈሳዊ ወይም ሥጋዊ ራብ ሊለየን አይችልም፡፡ እኛ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ስለምናምን የእግዚአብሄር ጽድቅ ማለትም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ሐጢያት አልባ ባደረገን በጌታችን እምነት ሁልጊዜም በልባችን ውስጥ አለ፡፡ ይህ እምነት በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምን እምነትና በረከት ነው፡፡ ‹‹ጌታ ሐጢያቶቼ በሙሉ እንዲወገዱ ስላደረገ ሐጢያት የለብኝም! እግዚአብሄር ጻድቅና ሐጢያት አልባ አድርጎ ሙሉ በሙሉ የራሱን ጽድቅ አልብሶኛል!›› ራቡ ምንም ያህል የከፋ ቢሆንም በእግዚአብሄር ጽድቅ ላይ ያለን እምነት የማይጠፋው ለዚህ ነው፡፡
    
 

በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚገኝ የእግዚአብሄር ጽድቅ፡፡ 

 
ሰው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እስካላመነ ድረስ በልቡ ውስጥ ሐጢያት ይኖራል፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምን ሰው ግን ሐጢያት የለበትም፡፡ ጌታችን ዛፍን በፍሬው እንደምናውቀው የተናገረው ለዚህ ነው፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ የማያምኑ ሰዎች ኢምንት ችግር፣ ስደት፣ ራብ ወይም መከራ ሲገጥማቸው በኢየሱስ ላይ ያላቸውን እምነት ይተዋሉ፡፡
 
‹‹ኢየሱስ በሐጢያቶቼ ፋንታ በመስቀል ላይ ቢኮነንም የተወገደው የአዳም ሐጢያት ብቻ ነው፤ እኔ በየቀኑ ለምሰራቸው ሌሎች ሐጢያቶች ቀን በቀን ይቅርታን መለመን አለብን›› ብለው የሚያስቡ ሰዎች አሉ፡፡ የዚህ አይነት እምነት ያላቸው ሰዎች በእርግጥም ኢየሱስ ሐጢያቶቻቸውን በሙሉ እንደወሰደላቸው ባለማመን በእግዚአብሄር ላይ ሐጢያት እየሰሩ ስለሆነ በሒደት ራሳቸውን በመኮነን ያበላሻሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች ኢየሱስን የሚክዱና በእግዚአብሄር ጽድቅ የማያምኑ ሰዎች ናቸው፡፡
 
በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ሰዎች ግን ምንም አይነት ሁኔታዎች ቢገጥሙዋቸውም በእግዚአብሄር ጽድቅ ስለሚያምኑ ‹‹እግዚአብሄር በእርግጥም ከዓለም ሐጢያቶች በሙሉ አድኖኛል፡፡ እኔ ሐጢያት የለብኝም!›› በማለት እምነታቸውን አጥብቀው ይይዛሉ፡፡ በመጨረሻው የመንፈሳዊ ረሃብ ዘመናችን ሞት ቢገጥመን እንኳን እግዚአብሄር ሐጢያት አልባ እንዳደረገንና እኛም የእርሱ ሕዝብ እንደሆንን ፈጽሞ አንክድም፡፡ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ የወሰደው የእግዚአብሄር ጽድቅ እምነታችን ሆኖ አሁንም በልባችን ውስጥ ይቀራል፡፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ይህን ያህል ታላቅና ብርቱ ነው፡፡ በሕይወታችን ውስጥ ምንም አይነት ችግሮች ቢገጥሙንም የእግዚአብሄር ጽድቅ በክርስቶስ ውስጥ ስላለ በፍጹም ከክርስቶስ ፍቅር አንነጠልም፡፡
 
ከላይ ባለው ምንባብ ውስጥ ‹‹ራቁትነት›› ማለት ምን ማለት ነው? ራቁትነት የሚያመላክተው ንብረቶቻችንን ሁሉ ማጣትን ነው፡፡ በመካከለኛው ዘመን በአውሮፓ አገሮች በአንድ መንደር ወይም ከተማ ውስጥ ችግር ሲፈጠር ብዙውን ጊዜ ሰዎች ለችግሮቹ ሁሉ ተወቃሽ ለማድረግ ጠንቋዮችን በማደን ሥራ ይጠመዱ ነበር፡፡ ሰዎች ያላቸውን ሁሉ ይወስዱባቸውና መናፍቃን ናችሁ ብለው ይኮንኑዋቸዋል፡፡ ጳውሎስ ‹‹ራቁትነት›› የሚለውን ቃል እዚህ ላይ የተጠቀመው ለዚህ ነው፡፡
 
በዚያ ዘመን በአንድ ወይም በሁለት ምስክሮች ብቻ አንድን ሰው መክሰስ ይቻል ነበር፡፡ የተከሰሰው ሰውም በእንጨት ላይ እንዲቃጠል ይፈረድበታል፡፡ ንብረቶቹም ሁሉ ይወረሳሉ፡፡ ስሙም ይዘነጋል፡፡
 
እኛም እንዲህ ባለ ሁኔታ ራቁታችንን ብንሰደድ፤ ያለንን ሁሉ አጥተን ለሞት ተላልፈን ብንሰጥ እንኳን ለእኛ ባለው ፍቅሩ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ የወሰደው የእግዚአብሄር ጽድቅ ፈጽሞ ከእኛ አይጠፋም፡፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ይህን ያህል ምሉዕ ነው፡፡
 
ፍርሃትም ሆነ ሰይፍ ከክርስቶስ ፍቅር ሊለዩን አይችሉም፡፡ በሰይፍ ላይ ብንወድቅና በእርሱም የምንገደል ቢሆን እንኳን እኛ የምናምን ሰዎች ሐጢያት የለብንም፡፡ በጥንቷ ቤተክርስቲያን ውስጥ የነበሩ ብዙዎቹ ክርስቲያኖች ሮምን አቃጥላችኋል በሚል በሐሰት ተከሰው ለአንበሶች ምግብ እንዲሆኑ በትልቅ አዳራሽ ውስጥ በሕዝብ ፊት ተገድለዋል፡፡ እነርሱ እየሞቱ ሳሉ እንኳን ያዳናቸውን ጌታ ያመሰግኑ ነበር፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ስለነበሩ ማመስገን ችለው ነበር፡፡ እግዚአበሄር እንወደዳቸውና ሐጢያቶቻቸውን በሙሉ እንደወሰደላቸው የሚናገረውን እውነት በማመን የዳኑ ሰዎች እየተገደሉና በአንበሶች እየተበሉ እንኳን ጌታን ማመስገን ችለዋል፡፡
 
ይህ ጉልበት የተገኘው ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በወሰደው የእግዚአብሄር ጽድቅና በፍቅሩ ከማመን ነው፡፡ እንዲህ ያለው ጉልበት ሊገኝ የሚችለው እግዚአብሄር በውስጣችን ስላለ፣ ስለሚናገረን፣ ስለሚያበረታን፣ ስለሚጠብቀንና ስለሚያጽናናን ነው፡፡ ፍርሃት ቢሆን ሰይፍ ዛቻ ቢሆን ሰማዕትነት ከእግዚአብሄር ፍቅር ሊለየን አይችልም፡፡
 
በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ፤ በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምኑና የክርስቶስ ሕዝብ የሆኑ ሰዎች ናቸው፡፡ አንዳንድ ሰዎች ግን የመስቀል ላይ ሞቱን ብቻ ተመልክተው በተቀበላቸው መከራዎች በማዘንና በማልቀስ የክርስቶስን ፍጹም ፍቅር ተራ ወደሆነ ስሜታዊ ፍቅር ለውጠውታል፡፡ የሰዎች ስሜቶች ግን በአንድ ምሽት ሊለወጡ ይችላሉ፡፡
 
ስሜቶቻችን በየማለዳውና በየምሽቱ ቢለዋወጡም ጌታ እኛን ያዳነበት ፍቅር በማናቸውም ነገር ሊለወጥ ወይም ሊቀየር አይችልም፡፡ የእርሱ ፍቅር ለዘላለም የማይለወጥ ነው፡፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ይህን ያህል ብርቱ ነው፡፡ የእግዚአብሄር ጽድቅ ይህን ያህል ትልቅ ነው፡፡ ካዳነንና ፍጹም የሆነውን ፍቅሩን ካለበሰን ጌታችን ሊለየን የሚችል የለም፡፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ሐይል ይህ ነው፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ ላይ ያለን እምነት ጉልበትም ይህ ነው፡፡
 
‹‹ወንጌል›› ለሚለው ቃል የግሪኩ ቃል ‹‹ኢዋጂሊዮን›› ነው፡፡ የእግዚአብሄር ዱናሚስ እንዳለውም ተነግሮዋል፡፡ ይህ የግሪክ ቃል ‹‹ድማሚት›› የሚለውን ቃል ያገኘንበት ጉልበት፣ ሐይል ወይም አቅም ማለት ነው፡፡ አንድ እፍኝ ድማሚት አንድን ቤት ከስር ከመሰረቱ ነቅሎ ለማፈራረስ በቂ ነው፡፡ ከጦር መርከብ የተተኮሰ ቶምሃውክ ሚሳኤል አንድ ትልቅ በሲሚንቶ የተገነባን ሕንጻ ማውደምና አመድ ማድረግ ይችላል፡፡ ሕንጻው ምንም ያህል የተመሸገ ቢሆንም የሚሳኤሉን የማጥፋት ሐይል መቋቋም አይችልም፡፡
 
ሁለት የሕዝብ መጓጓዣ አውሮፕላኖች በኒውዮርክ የሚገኙትን መንታዎቹን የንግድ ማዕከል ሕንጻዎች አውድመዋል፡፡ አውሮፕላኖቹ ሕንጻዎቹን ሲገጩ ምን ተፈጠረ? በአውሮፕላኖቹ ፍንዳታ የተቀጣጠለው እሳት ነዳጁን በመመገቡ እጅግ ከፍተኛ በመሆኑ አውሮፕላኖቹ ጥሰው በገቡባቸው ወለሎች ላይ ያለውን እያንዳንዱን ነገር አቀለጠው፡፡ የወለሎቹ የብረት መዋቅሮችና ሕንጻውን ደግፈው ያቆሙት አምዶች በሙሉ ስለቀለጡ ወለሎቹ ድንገት ተደረመሱ፡፡ ሕንጻዎቹ እነዚህን የእየተደረመሱ ያሉ ወለሎች ክብደት መሸም ባለመቻላቸው በመጨረሻ ሙሉ በሙሉ ተሰነጣጠቁ፡፡ ወለሎቹ በዝግታ ተደርምሰው ቢሆን ኖሮ ሕንጻዎቹ አይደረመሱም ነበር፡፡ ነገር ግን ወለሎቹ በድንገትና በፍጥነት ስለወደቁ አምዶቹና ሌሎቹ ደጋፊ መዋቅሮች ተደረመሱ፡፡ ሁላችንም እንዳየነው ሕንጻዎቹም በሙሉ በሰከንዶች ጊዜ ውስጥ ፈራረሱ፡፡
 
የእግዚአብሄር ወንጌል ሐይል የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ሐይል ይህ ነው፡፡ ይህ በውስጡ የእርሱ ጽድቅ ያለበት ሐይልም ጭምር ነው፡፡ ምናልባት የእግዚአብሄርን ጽድቅ ለማብራራት ይህንን አሳዛኝ አደጋ መጠቀም ተገቢ አይሆን ይሆናል፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ጽድቅ የተሰጠው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ሐይል ሐጢያቶችን በሙሉ ፈጽሞ መጥረግ የሚችል አይነት ድማሚት ነው፡፡ የእግዚአብሄር ጽድቅ ጌታችን ወደዚህ ምድር መጥቶ ሐጢያቶቻችንን በመውሰድ፣ በመጠመቅ፣ በመስቀል ላይ በመሞትና ከሙታን በመነሳት እኛን ማዳኑ ነው፡፡
 
የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ኢየሱስ ከዓለም ፍጥረት ጀምሮ እስከ ፍጻሜው ድረስ የሰው ዘር የሰራቸውን ሐጢያቶች በሙሉ የወሰደበት የእግዚአብሄር ጽድቅ ነው፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ ወንጌል ባላቸው እምነት ድነው በእርሱ የተወደዱትን ሰዎች ምንም ነገር ከእግዚአብሄር ሊነጥላቸው የማይችለው ለዚህ ነው፡፡ የጳውሎስም እምነት እንደዚሁ በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምን እምነት ነበር፡፡
 
ታዲያ እኛ በመስቀሉ ደም ወንጌል ብቻ የእግዚአብሄር ጽድቅ መቀበል እንችላለን? አንችልም፡፡ በመስቀሉ ደም ብቻ ማመን የእግዚአብሄር ጽድቅ ሊሰጠን አይችልም፡፡ ከዚህ ውጪ የሚያስቡ ሰዎች ትንሽ ሲናወጡ በኢየሱስ ላይ ያላቸውን እምነት ይተዋሉ፡፡
 
ለምሳሌ ምድራዊ ሐብታቸው ሲወሰድ ወይም በሃይማኖታቸው ምክንያት በሥራ ቦታቸው ችግሮች ሲገጥሙዋቸው በቀላሉ እምነታቸውን ለመተው ይዳዳሉ፡፡ ይህ የማይቀር ዕዳ ነው፡፡ ብዙ ክርስቲያኖችንም ይመለከታል፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ባለማመን በልባቸው ውስጥ መንፈስ ቅዱስ የሌላቸውና ከሐጢያቶቻቸው ያልዳኑ ሰዎች ኢምንት ዛቻ ሲገጥማቸው በቀላሉ ምርኮኛ ይሆናሉ፡፡
 
የዘመኑ ክርስትና በዚህ ዓለም ላይ እንዲህ ደካማ የሆነው በዚህ በመስቀሉ ደም በተገደበ እምነት የተነሳ ነው፡፡ የዚህ አይነቱ እምነት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የእግዚአብሄርን ጽድቅ ያልተቀበለ እምነት ነው፡፡
 
የእግዚአብሄርን ጽድቅ በመቀበል ከሐጢያቶቹ ሁሉ የዳነ ምዕመን ብዙ ነፍሳቶችን ማዳን ይችላል፡፡ እርሱ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ስለሚያምንና መንፈስ ቅዱስ ስላለው እግዚአብሄርም በቃሉ ከእርሱ ጋር ስለሆነ ያ ሰው ብዙ መንፈሳዊ ሥራዎችን ሊሰራና ብዙ የጠፉ ነፍሳቶችን ወደ እግዚአብሄር ሊመልስ ይችላል፡፡ ይህ በእግዚአብሄር ጽድቅና በእግዚአብሄር የተሰጠው የውሃና የመንፈስ ወንጌል የሚያምን እምነት እንጂ በሥራዎቻችን የሚያምን እምነት ስላልሆነ የእግዚአብሄርን ሥራዎች መስራት የምንችለው በእርሱ በኩል ነው፡፡
 
ቁጥር 36 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ስለ አንተ ቀኑን ሁሉ እንገደላለን፤ እንደሚታረዱ በጎች ተቆጠርን ተብሎ እንደተጻፈ ነው፡፡›› በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በሚያምኑት መካከል በዚህ ምድር ላይ ሲኖሩ በዚህ ሁኔታ የተስተናገዱ አሉ፡፡ እንዲያውም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ሰዎች ብዙውን ጊዜ በሌሎች በተለይም ራሳቸውን ክርስቲያኖች ብለው በሚጠሩና የተሳሳተ እምነት ባላቸው ሰዎች ተጠልተዋል፡፡
 
በሌላ አነጋገር ዳግም የተወለዱ ክርስቲያኖች ከቡዲስቶች ይልቅ በአስመሳይ ክርስቲያኖች ይበልጥ ተጠልተዋል፡፡ ‹‹ስለ አንተ ቀኑን ሁሉ እንገደላለን፤ እንደሚታረዱ በጎች ተቆጠርን ተብሎ እንደተጻፈ ነው›› የሚለው ይህ ምንባብ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ለሚያምኑ ምዕመናን የተነገረ የእግዚአብሄር ቃል ነው፡፡ ጌታችንም እንኳን በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ሞቱ የአብን ፈቃድ በመታዘዙ ‹‹ለመታረድ እንደሚነዳ ጠቦት ተቆጠረ፡፡›› ጌታ ወደዚህ ምድር በመምጣትና እንዲህ ያለ ሕይወት በመኖር አዳነን፡፡
           
 

የእግዚአብሄር ጽድቅ በዓለም ሐጢያቶች ሁሉ ላይ አሸናፊ ሆንዋል፡፡

 
ቁጥር 37 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በዚህ ሁሉ ግን በወደደን በእርሱ ከአሸናፊዎች እንበልጣለን፡፡›› እነዚህን ሁሉ ነገሮች ማሸነፍ የምንችለው እንዴት ነው? ድላችንን የምናገኘው በእግዚአብሄር ፍቅር ላይ ባለን እምነታችን ሐይል ነው፡፡
 
በㅌውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የማያምን ሰው ግን በልቡ ውስጥ ያለው ሐጢያት ብቻ ነው፡፡ ሐጢያት ያለባቸው ሰዎች እምነትና ደህንነት ከስሜቶቻቸው የተነሳ ላይና ታች ስለሌለው ሐይል የላቸውም፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ሰዎች ግን ሐይል አላቸው፡፡ በራሳቸው ሐይል የላቸውም፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር የተሰጣቸው የወንጌል ሐይል አላቸው፡፡ በዚህ ሐይልም ስደቶችንና መከራዎችን ሁሉ መቋቋምና ማሸነፍ ይችላሉ፡፡ ጻድቃን ሐጢያተኞችን በመቃወም መንፈሳዊ ጦርነት ማድረግና የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ለእነርሱ መስበክ አለባቸው፡፡ ጻድቃን ለወንጌል እየተሰደዱ መኖርን የተፈጥሮ ዕጣ ፈንታቸው አድርገው መታገስ አለባቸው፡፡ የእኛ ዕጣ ፈንታ ለጌታ የሚኖር ሕይወትን መኖር ነው፡፡
 
አንድ የምሥራቃውያን ምሳሌ እንዲህ ይላል፡- ‹‹አንድ ሰው ለአንድ ቀን ማንበብ ካቆመ የሚቆጠቁጡ ቃሎችን ይናገራል፡፡›› እኛስ ታዲያ? እኛም እንደዚሁ ለእግዚአብሄርና ለወንጌሉ ሳንኖር አንድ ቀን ብናሳልፍ ወደ መበላሸት እናመራለን፡፡ እስከ ዕለተ ሞታችን ድረስ ሕይወታችንን መኖር ያለብን እንዲህ ነው፡፡ ነገር ግን ለክርስቶስ ብንኖር፣ ለእግዚአብሄር ራሳችንን መስዋዕት ብናደርግና ብንሰደድ፣ በክፋት መንፈሳውያን ሐይሎች ላይ መንፈሳዊ ጦርነትን ብናውጅ ልባችን በመንፈሳዊ ምግብ ስለሚሞላ ወደፊት የምንገሰግስበትን አዲስ ጉልበት እናገኛለን፡፡
 
ክርስቲያኖች ከወደቁ የሚወድቁት ለጌታ ባለመኖራቸው ነው፡፡ ለጌታ ስንኖር ግን መንፈሳዊ ጉልበቶቻችን ይበልጥ ይበረታሉ፡፡ ሥጋዊ ጤንነታችንና ብርታቶቻችንም እንደዚሁ ይጠነክራሉ፡፡
 
ቁጥር 38-9 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሞት ቢሆን ሕይወትም ቢሆን መላእክትም ቢሆኑ ግዛትም ቢሆን ያለውም ቢሆን የሚመጣውም ቢሆን ሐይላትም ቢሆኑ ከፍታም ቢሆን ዝቅታም ቢሆን ልዩ ፍጥረትም ቢሆን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ካለ ከእግዚአብሄር ፍቅር ሊለየን እንዳችል ተረድቻለሁ፡፡›› ጳውሎስ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምን አማኝ በመሆኑ ይህንን ተረድቶዋል፡፡ ይኸው እውነት እኛንም ይመለከተናል፡፡ ሞትም ሆነ ሕይወት ከክርስቶስ ሊለየን አይችልም፡፡
 
በጥንት ዘመናት ዓለማዊ ሥልጣንን የያዙ እንደ ሮም ንጉሠ ነገሥታት ሁሉንም ዓይነት ማባበያዎች ከፍተኛ ሥልጣኖችን፣ ሚስቶችንና ንብረቶችን በማቅረብ ክርስቲያኖች እምነታቸውን እንዲያወግዙና እንደ እነርሱ አማኞች የሆኑትንም ለባለሥልጣኖች እንዲያጋልጡ ሊያሳምኑዋቸው ሞክረዋል፡፡ ነገር ግን ወንጌል የሚያምኑ እውነተኛ ምዕመናን በሥልጣን፣ በሐብት ወይም በክብር ተደልለው በጭራሽ አልተንበረከከም፡፡
 
እምነት ዓለም ሊያቀርብ በሚችለው ነገር የሚለወጥ ነገር አይደለም፡፡ አንድ ሰው ባዶ ቼክ አሳይቶን ‹‹ወንጌልን ማሰራጨትህን ብታቆም ይህንን ቼክ እሰጥሃለሁ›› ቢለን ወደፊት ባለን ተስፋና በእግዚአብሄር ላይ ባለን ጠንካራ እምነት ‹‹ለራሰህ ያሰፈልግሃል፡፡ ስለዚህ ተጠቀምበት፡፡ ለእኔ ይህ ተራ ወረቀት እንጂ ምንም ነገር አይደለም›› ብለን መመለስ እንችላለን፡፡
 
 
የእግዚአብሄር ጽድቅ ያለው ወንጌል የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ብቻ ነው፡፡
   
ብዙ ሰዎች ‹‹በመስቀሉ ደም ማመናችን ብቻውን ትክክለኛ እምነት ነው፡፡ እኛም እምነትህን እንቀበለዋለን፡፡ አንተን መናፍቅ ነህ ብለን መክሰሳችንን ከማቆማችንም በላይ በእርግጥ እናግዝሃለን›› ብለውኛል፡፡ በተለይ እነዚህ የሃይማኖት መሪዎች ተብዬዎች ከእኔ እንዲህ ያለ ማመቻመችን ፈለጉ፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሄር ጽድቅ በቃሉ ሲመዘን ግልጽና ተጨባጭ ነው፡፡ የተሳሳተው ተሳስቷል፡፡ እውነት የሆነውም እውነት ነው፡፡ ለተሳሳተ እምነት እውቅናን መስጠት በራሱ በእግዚአብሄር ላይ ማመጽ ነው፡፡ ስለዚህ እኔ እምነታቸውን የማልደግፍ ከመሆኔም በላይ ውሸቶቹንም በማጋለጥ መቀጠል ይኖርብኛል፡፡
 
‹‹በመስቀሉ ደም ብቻ ታምናላችሁን? እንግዲያውስ በልባችሁ ውስጥ ሐጢያት አለ፡፡ ለሲዖል ታጭታችኋል፡፡ እኔ በጣም ኮስታራና የማልንበረከክ መሆኔን ብታስቡ እንኳን ላደርገው የምችለው ነገር የለም፡፡ እውነት እውነት ነው፡፡›› እነዚህን ቃሎች በመናገሬ ሰዎች ይርቁኛል፡፡ ሊቀርቡኝ እንደማይችሉ በጣም ግልጽ ነው፡፡ ብዙ ሰዎች እንደ እነርሱ እየመሰልኋቸው ሊቀርቡኝ ይፈልጋሉ፡፡ ነገር ግን በየጊዜው ‹‹እናንተ በእግዚአብሄር ስም እየነገዳችሁ የምትኖሩ ሐሰተኛ እረኞችና አጭበርባሪዎች ናቸሁ፡፡ ተራ ሌቦች ናችሁ›› ብዬ እናገራቸዋለሁ፡፡ እንደዚህ እየተናገርሁ ማን ይወደኛል? ነገር ግን የማይሆነው አይሆንም፡፡ በአቋሜ ጽኑና የማልንገዳደገድ የሆንሁት ለዚህ ነው፡፡
በመስቀሉ ደም ብቻ ባምን እንዲህና እንዲያ ሥልጣን እንደሚሰጡኝ በሚናገሩ ሰዎችም ተፈትኛለሁ፡፡ ነገር ግን ከላይ የተጠቀሰው ምንባብ እንደሚለው ‹‹የሚመጣውም ቢሆን ሐይላትም ቢሆን ከፍታም ቢሆን ዝቅታም ቢሆን፡፡›› ምንም ሥልጣን፣ ከፍታ ወይም ዝቅታ አያስፈልገንም፡፡ አንዳንድ አጭበርባሪዎች አለን እንደሚሉት የፈውስ ሐይልም አያስፈልገንም፡፡ ዳገም የተወለድን ሰዎች እንዲህ ያሉ ነገሮች አያስፈልጉንም፤ እንዲያውም አንወዳቸውም፡፡
 
ምንባቡ ማንም ሌላ ፍጥረት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ካለው የእግዚአብሄር ፍቅር ሊለየን እንደማይችልም ይናገራል፡፡ በዚህ ዩኒቨርስ ውስጥ እንግዳ ፍጡራን ቢኖሩ እንኳን ካዳነን የእግዚአብሄር ፍቅር ሊለዩን አይችሉም፡፡
 
በሕዋ ውስጥ ፍጥረታት እንዳሉ የሚያምኑ ክርስቲያኖች አሉ፡፡ በመጋቢዎች መካከልም ቢሆኑ ብዙዎች በእነርሱ መኖር ያምናሉ፡፡ ነገር ግን እንግዳ ፍጡር የሚባል ነገር የለም፡፡ በሴሚናሪ ውስጥ ስማር በነበረ ጊዜ ግሪክ ከሚያስተምሩት ከፕሮፌሰሮቼ አንዱ እንግዳ ፍጡራን ስለመኖራቸው ያምን ነበር፡፡ ስለዚህ ‹‹እምነትህን ከመጽሐፍ ቅዱስ በሚገኝ መረጃ መደገፍ ትችላለህን?›› በማለት ጠየቅሁት፡፡ በእርግጥ ለጥያቄዬ የሚሆን አንዳች መልስ አላቀረበልኝም፡፡ እንግዳ ፍጡራን የሚባሉ ፈጽሞ የሉም፡፡ እግዚአብሄር ዓለምን እንዲሁ ስለወደደ አንድያ ልጁን ሰጠን፡፡ በእርግጥም እንግዳ ፍጡራኖች ያሉ ከሆኑ ኢየሱስ በዚህ ምድር ላይ ብቻ መወለድ ባላስፈለገው ነበር፡፡
 
እጅግ ብዙ መዋዕለ ንዋይ ካፈሰስንና ምርምር ካደረግን በኋላ ጨረቃ ላይ መድረስ ችለናል፡፡ የምርምር መሳሪያዎቻችንንም ማርስ ላይ ሳይቀር አርፈዋል፡፡ ነገር ግን ከምድር ውጪ ሕይወት ስለ መኖሩ የሚጠቁም አንድም መረጃ አላገኘንም፡፡ የሰው ዘር ሳይንሳዊና ቴክኖሎጂያዊ ችሎታዎች ምንም ያህል የመጠቁ ቢሆኑ ዩኒቨርስንም ምንም ያህል በስፋት ብንመረምር በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ተመስርቼ በሕዋ ላይ የሚኖሩ ፍጡራን በጭራሽ እንደማይኖሩ በድፍረት መናገር እችላለሁ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ምንም ሌላ ፍጥረት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ክርስቶስ ካለው ፍቅር ሊለየን እንደማይችል ይነግረናል፡፡ ታዲያ ይህ የእግዚአብሄር ፍቅር ምንድነው? ይህ ፍቅር የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ የእግዚአብሄር ፍቅር ይህ ነው፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ያዳነንና ሐጢያት አልባ ያደረገን ደህንነት የእግዚአብሄር ፍቅር ነው፡፡ ከዚህ ፍቅር ምንም ነገር ሊለየን አይችልም፡፡
 
ጳውሎስ በምዕራፍ 9 ላይ እንደገና ስለ እምነት ይናገራል፡፡ ነገር ግን የእምነት ጫፍ ላይ የተደረሰው በምዕራፍ 8 መደምደሚያው ላይ ነው፡፡ የሮሜ መጽሐፍ ከምዕራፍ 1 እስከ 8 ድረስ አንድ ርዕሰ ጉዳይ ይዘረዝራል፡፡ ምዕራፍ 8 የመደምደሚያ ምዕራፍ በመሆኑ የእምነት ጫፍ ላይ የተደረሰው እዚህ ላይ ነው፡፡ በምዕራፍ 8 ላይ የእግዚአብሄር ቃል እንደሚያሳየን ከእግዚአብሄር ፍቅር የማይነጠሉት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑት ብቻ ነው፡፡
 
ነገር ግን እንደዚህ የማያምኑ ሰዎች በጭራሽ አያምኑም፡፡ ምናልባት ለጊዜው ይኖሩ ይሆናል፡፡ ነገር ግን እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ ለእምነታቸው ሊቆሙ ወይም ለእርሱ ሊኖሩ አይችሉም፡፡ ለ10 እና ለ20 ዓመት በሃይማኖት ይኖሩ ይሆናል፡፡ እምነታቸው ግን ውሎ አድሮ ስለሚበሰብስና ስለሚሞት ፈጽሞ ከእግዚአብሄር እንዲነጠሉና ከእርሱም ጋር ምንም ግንኙነት እንዳይኖራቸው ያደርጋቸዋል፡፡ ሥራ አልጎደለባቸውም፡፡ ነገር ግን በልባቸው ውስጥ ለክርስቶስ ያላቸው ፍቅር ከእነርሱ ይጠፋል፡፡ እነርሱ በልቡናቸው ውስጥ መንፈስ ስለሌላቸው በልባቸው ውስጥ ለጌታ ፍቅር የላቸውም፡፡ በአጭሩ በልባቸው ውስጥ ሐጢያት አለ፡፡
 
ቀናቶች እየነጎዱ ሲሄዱ ጌታችን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እኛን ያዳነበት የደህንነት ፍቅር ምን ያህል ጥልቅና ፍጹም እንደሆነ ይበልጥ ተረድቻለሁ፡፡ ጌታን ለመጀመሪያ ጊዜ ስገናኘው ለክርስቶስ ፍቅር ያለኝ ጥልቅ የሆነ ምስጋና ወደ ወደ ሐይቅ የተወረወረ ድንጋይ ትንሽና ብዙም የማይቆዩ ማዕበሎችን እንደሚፈጥር ጸጥ ያለና የተረጋጋ ነበር፡፡ ምላሼ ኢየሱስ ሐጢያቶቼን በሙሉ የመውሰዱንና እኔም በዚህ መንገድ ሐጢያት አልባ የመሆኔን እውነታ በጸጥታ መረዳቴ ብቻ ነበር፡፡ ነገር ግን ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ወንጌልን የመስበክ ሕይወትን ስኖር በልቤ ውስጥ ያሉት ማዕበሎች ልክ ቦምብ በልቤ ውስጥ የፈነዳ ይመስል ባልታሰበ መልኩ እየተለቁና እየጠለቁ ሄዱ፡፡
በመስቀሉ ደም ብቻ ማመን አለባችሁ ያለው ማነው? ጳውሎስ እንዲህ ብሎዋልን? ጳውሎስ በሮሜ ውስጥ በግልጽና በማያሻማ መልኩ ስለ ውሃውና መንፈሱ ወንጌል ተናግሮዋል፡- ‹‹ወይሰ ከክርስቶስ ኢየሱስ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ የተጠነቅን ሁላችን ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ እንደተጠመቅን አታውቁምን? እንግዲህ ክርስቶስ በአብ ክብር ከሙታን እንደተነሳ እንዲሁ እኛም በአዲስ ሕይወት እንድንመላለስ ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ በጥምቀት ከእርሱ ጋር ተቀበርን፡፡›› (ሮሜ 6፡3-4)
 
ይህ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ፈጽሞ ታላቅና ፍጹም አይደለምን? እምነቱ ምንም ያህል ትንሽ ቢሆንም አንድ ሰው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምን ከሆነ ከሐጢያቱ ይድናል፡፡ ምንም ያህል ጉድለቶች ቢኖሩባችሁም እምነታችሁ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ሙሉ ሆንዋል፡፡ ምንም ያህል ደካማ ብትሆኑም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ላይ ባላችሁ እምነት ድናችኋል፡፡ በራሳችን ጉልበት ባይኖረንም ለእግዚአብሄርና ከእግዚአብሄር ጋር ከኖርን ርኩሰቱ ሁሉ ከልባችን ውስጥ ይወገዳል፡፡
 
ነገር ግን ገና ከመነሻው የማያምኑ ሰዎች ይህንን ወንጌል ሰምተው ለ10 ዓመት ቢኖሩበትም በመጨረሻ በእግዚአብሄር ላይ ይነሱበትና ትተውት ይሄዳሉ፡፡ ዓይኖቻቸውን በመጨፈንና ጆሮዎቻቸውን በመዝጋት እውነትን ለማየትም ሆነ ለመስማት የወሰኑ ሰዎች በራሳቸው እጅ የእግዚአብሄርን በረከት አሻፈረኝ ማለታቸውና ወደ ሲዖል በመንጎዳቸው በጣም ተሞኝተዋል፡፡ በኢየሱስ ጥምቀት ባይሆን ኖሮ የመስቀል ላይ ሞት የሚባል ነገር ባይኖርም እነርሱ ግን በሐጢያቶቻቸው በየቀኑ ክርስቶስን ይሰቅሉታል፡፡
 
በእያንዳንዱ የሚያልፍ ቀን ይህ ወንጌል ምን ያህል ታላቅና ፍጹም እንደሆነ እገነዘባለሁ፡፡ በጣም በደከምሁ ቁጥር በዚህ ወንጌል የተገለጠው የጌታችን ፍቅር ምን ያህል ድንቅና ምሉዕ እንደሆነ በመረዳት ለዚህ አብዝቼ አመሰግነዋለሁ፡፡ ይህንን ወንጌል አብዝቼ በሰበክሁ ቁጥር ድምጼ ይበልጥ ይጮሃል፡፡ ይህንን ወንጌል በሰበክሁ ቁጥር ይበልጥ ብርቱ እሆናለሁ፡፡ ይህንን እውነተኛ ወንጌል አብዝቼ በሰበክሁ ቁጥር ይበልጥ እተማመናለሁ፡፡
 
ዳግም ብትወለዱም የእግዚአብሄርን ቃል የማትሰሙና እርሱን የማታገለግሉ ከሆናችሁ በአእምሮዋችሁ ውስጥ አረሞች መብቀል ይጀምራሉ፡፡ ከእነዚህ አረሞች የተነሳም አእምሮዋችሁ ባድማ ይሆናል፡፡ ይህ ሲሆን ደግማችሁ የምስጋና መዝሙራችሁን በመዘመር የሆዋን አስቡት፡፡ ለእግዚአብሄር የምስጋና መዝሙሮችን ስትዘምሩ አእምሮዋችሁ ዳግም መንፈሳችሁን ይቀሰቅሰዋል፡፡
 
አእምሮዋችሁን ርኩስ ከሆነ ከማንኛውም ነገር ለማጽዳት ልትንጡት ይገባችኋል፡፡ ልባችሁንም በእግዚአብሄር ቃል በመሙላት ዳግመኛ አድሱት፡፡ ልባችን አስቀድሞም ነጽቷል፡፡ ነገር ግን የዓለም ርኩሰቶች ወደ አእምሮዋችን ገብተው ሊያደናግሩንና ሊበጠብጡን ሲሞክሩ የጌታን ምስጋናዎች በመዘመር ልባችንን እያደስንና ዳግመኛ እያስነሳነው ደግመን እግዚአብሄርን ልናመልከውና ወደ እርሱ ልንጸልይ እንችላለን፡፡
 
ራሳችንን የትም ቦታ እናግኘው እግዚአብሄርን ማመስገን አስደሳችና ትፍስህታዊ ልምምድ ነው፡፡ በዳኑት ሰዎች አእምሮ ውስጥ ሐጢያት የለም፡፡ ስለዚህ ከአእምሮዋቸው ውስጥ ምስጋናና ደስታ መፍለቃቸው የተለመደ ነው፡፡ በደስታ ከሰከረው ልባችን ውስጥ የሚፈልቁት የምስጋና መዝሙሮች በአእምሮዋችን ውስጥ የበቀሉትን አረሞች ሊያስወግዱዋቸው ይችላል፡፡
 
አንዳንድ ጊዜ ድክመቶቻችን ይገለጣሉ፡፡ አሰተሳሰቦቻችንና ስሜቶቻችን በተለያዩ ገጠመኞች ውስጥ በቀላሉ ስለሚቀያየሩ በክርስቶስ ወንድሞች ከሆኑት ጋር አብረን ስንሆን ደስተኞችና ጥሩ ስሜት የሚሰማን ብንሆንም ብቻችንን ስንሆን ቆሻሻና የረከሱ አስተሳሰቦች ይኖሩን ይሆናል፡፡ ጳውሎስ ‹‹እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ! ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሥጋ ማን ያድነኛል? በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን ለእግዚአብሄር ምስጋና ይሁን!›› ብሎ የጮኸው ለዚህ ነው፡፡
             
ጳውሎስ በሥጋው ደካማ ቢሆንም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ድኖ ምሉዕ ሆነ፡፡ እንዲህ የሆነው ብቸኛው ሰው ጳውሎስ ብቻ ነበር? እኔም እንደ ጳውሎስ ነኝ፡፡ እናንተም ደግሞ እንደ እርሱ አይደላችሁምን?
 
ዓለማዊ ሰዎች ሲሰባሰቡ ወንዶቹ አዘውትረው መጠጣት፣ ብዙውን ጊዜም ስለ ራሳቸው ማውራት፣ ማን ዕድገት እንዳገኘና ወ.ዘ.ተ ሲነጋገሩ ሴቶቹ ደግሞ በባሎቻቸው፣ በልጆቻቸው፣ በቤታቸውና ወ.ዘ.ተ ሲኮፈሱ ይባትላሉ፡፡ ነገር ግን በጻድቃን መካከል የሚደረጉት ንግግሮች ከዓለም ሰዎች ንግግሮች በጥራት የተለዩ ናቸው፡፡ ምግባችንን አብረን ስንበላ እንኳን በመላው ዓለም በሕንድ፣ በጃፓን በአውሮፓ በአፍሪካ በአሜሪካና ወ.ዘ.ተ ስለዳኑት ነፍሳቶች በማውራት እግዚአብሄርን እናመሰግናለን፡፡ ከአእምሮዋችን ጋርም ሕብረትን እናደርጋለን፡፡
 
የሮሜን መጽሐፍ ስናንብ የጳውሎስን እምነት ልንለማመድና በልባችን ውስጥ ልናኖረው እንችላለን፡፡ እግዚአብሄር የሰጠው ደህንነትም ምን ያህል ታላቅ እንደሆነም መረዳት እንችላለን፡፡ የወንጌል ዕጹብ ድቅነትም ሊታወቀን ይችላል፡፡ ምንባቦቹን ተረድተን በጥቅሱ ውስጥ የተደበቁትን ፍቺዎች ማግኘት እንችላለን፡፡ የጌታችን ደህንነት ምን ያህል ምሉዕና ፍጹም እንደሆነ ስለምንገነዘብ የእርሱን ጽድቅ ከማመስገን የእርሱን ጽድቅ ከማመስገን መቆጠብ አንችልም፡፡
 
መላው ዓለም አሁኑኑ ቢለወጥ እንኳን ከሐጢያቶቻችን ያዳነን የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ሳይለወጥ ይጸናል፡፡ የክርስቶስ ፍቅር ስላዳነን፣ ይህ ፍቅር በፍጹም ስላልተወንና አሁንም በውስጣችን ስላለ እኛ ማድረግ የሚኖርብን ልባችንን ከዓለም መልሰን እንደገና በእግዚአብሄር ላይ ማተኮር ነው፡፡ እኛ ደካሞች ነን፡፡ ከዚህ ድክመት የተነሳ አንዳንድ ጊዜ በዓለም መንገዶች ላይ እንወድቃለን፡፡ ነገር ግን ይህ በሚሆንበት ጊዜ ሁሉ እኛ ማድረግ የሚገባን አእምሮዋችንን ወደ እግዚአብሄር በመመለስ ጌታችን ያዳነን በመሆኑ እውነት ማመን ብቻ ነው፡፡ ሥጋችን ስላልተቀየረ የምንኖረው በሐጢያት ሕግ ነው፡፡ ስለዚህ ሥጋችንን ያለ ማቋረጥ መካድና መንፈሳዊ አሳቦችን በማሰብ ሕይወታችንን መኖር አለብን፡፡ አረሞች በልባችን ውስጥ መብቀላቸውን እንዲያቆሙ ሁልጊዜም ወደ እግዚአብሄር መመለስና ጽድቁን ማመስገን ይገባናል፡፡
አሁን ይህ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ምን ያህል ብርቱ እንደሆነ ተገነዘባችሁን? የሮሜ መጽሐፍ በሙሉ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ላይ የተመሰረተ በመሆኑ መጀመሪያ በዚህ ወንጌል ሳናምን የእግዚአብሄርን ቃል መክፈት አንችልም፡፡
 
የዚህን ቃል ምስጢሮች ከፍተን ማየት እንችል ዘንድ ስለፈቀደልን ጌታን አመሰግናለሁ፡፡ የክርስቶስ ፍቅር ከሆነው የእግዚአብሄር ጽድቅ ሊለየን የሚችል የለም፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ ማመን ከፈለጋችሁ ለቤዛነታችሁና ለደህንነታችሁ በዮሐንስ በሆነው የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ታመኑ፡፡ ያን ጊዜ እናንተም ደግሞ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ትቀበላላችሁ፡፡
 
የጌታችን ጽድቅ በረከቶች ከእናንተ ጋር ይሁኑ፡፡