Search

ስብከቶች፤

ርዕስ 9፡ ሮሜ (በሮሜ መጽሐፍ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[Chapter 1-5] እውነትን በአመጻ የሚከለክሉ ሰዎች፡፡ ‹‹ ሮሜ 1፡18-25 ››

‹‹ ሮሜ 1፡18-25 ››
‹‹እውነትን በአመጻ በሚከለክሉ ሰዎች በሐጢያተኝነታቸውና በአመጻቸው ሁሉ ላይ የእግዚአብሄር ቁጣ ከሰማይ ይገለጣልና፡፡ እግዚአብሄር ስለገለጠላቸው ስለ እግዚአብሄር ሊታወቅ የሚቻለው በእነርሱ ዘንድ ግልጥ ነውና፡፡ የማይታየው ባህሪይ እርሱም የዘላለም ሐይሉ ደግሞም አምላክነቱ ከአለም ፍጥረት ጀምሮ ከተሰሩት ታውቆ ግልጥ ሆኖ ይታያልና፡፡ ስለዚህም እግዚአብሄርን እያወቁ እንደ እግዚአብሄርነቱ መጠን ስላላከበሩትና ስላላመሰገኑት የሚያመካኙት አጡ፡፡ ነገር ግን በአሳባቸው ከንቱ ሆኑ፡፡ የማያስተውለውም ልባቸው ጨለመ፡፡ ጥበበኞች ነን ሲሉ ደነቆሩ፡፡ የማይጠፋውንም የእግዚአብሄር ክብር በሚጠፋ ሰውና በወፎች፣ አራት እግር ባላቸውም በሚንቀሳቀሱትም መልክ መስለው ለወጡ፡፡ ስለዚህ እርስ በርሳቸው ሥጋቸውን ሊያዋርዱ እግዚአብሄር በልባቸው ፍትወት ወደ ርኩስነት አሳልፎ ሰጣቸው፡፡ ይህም የእግዚአብሄርን እውነት በውሸት ስለለወጡ በፈጣሪም ፋንታ የተፈጠረውን ስላመለኩና ስላገለገሉ ነው፡፡ እርሱም ለዘላለም የተባረከ ነው፤ አሜን፡፡››
 

 
የእግዚአብሄር ቁጣ የተገለጠው በማን ላይ ነው?
 

ሐዋርያው ጳውሎስ እኛ የምንሰብከውን ያንኑ ወንጌል እንደሰበከ ማየት እንችላለን፡፡ የእግዚአብሄር ቁጣ የተገለጠው በማን ላይ ነው? የእግዚአብሄር ፍርድ የተገለጠው እውንትን በአመፃ በሚከለክሉ ሐጢያተኞች ማለትም ሐጢያቶች ባሉባቸውና በራሳቸው አስተሳሰቦች እውነትን በሚያደናቅፉት ላይ ነው፡፡
 
ሐዋርያው ጳውሎስ የእግዚአብሄር ቁጣ በመጀመሪያ እውነትን በአመጻ በሚከለክሉ ሰዎች ላይ እንደሚገለጥ በግልጽ ይናገራል፡፡ እነዚያ ሰዎች በእግዚአብሄር ይፈረድባቸዋል፡፡ የእግዚአብሄር ቁጣ ምን አይነት ቁጣ ይሆናል? የእግዚአብሄር ቁጣ ሥጋቸውንና መንፈሳቸውን ወደ ሲዖል ያወርደዋል፡፡
 
የሚኮነነው ሥጋ ብቻ ነው ብለን ማሰብ የለብንም፡፡ ምክንያቱም ሰዎች መንፈስም አላቸውና፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሄርን እውነት በምድራዊ አስተሳሰቦቻቸው የሚያደናቅፉ ናቸው፡፡ የእግዚአብሄር ቁጣና ፍርዱ በልባቸው ድንዳኔ ሐጢያትን በሚሰሩና እግዚአብሄርን በማይፈሩ ሰዎች ላይ ይገለጣል፡፡
 
የሚኮነነው ሥጋ ብቻ ነው ብለን ማሰብ የለብንም፡፡ ምክንያቱም ሰዎች መንፈስም አላቸውና፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር ሥጋንና መንፈስን ይኮነናል፡፡ እነዚህ የእግዚአብሄርን እውነት በምድራዊ አስተሳሰቦቻቸው የሚያደናቅፉ ናቸው፡፡ የእግዚአብሄር ቁጣና ፍርድ በልባቸው ድንዳኔ ሐጢያትን በሚሰሩና እግዚአብሄርን በማይፈሩ ሰዎች ይገለጣል፡፡
ሐዋርያው ጳውሎስ በሮሜ 1፡17 ላይ ‹‹ጻድቅ በእምነት ይኖራል›› ይላል፡፡ የእግዚአብሄር ፍርድና ቁጣም በሐጢያቶቻቸው እውነትን በሚያደናቅፉት ላይ እንደሚገለጥም ተናግሮዋል፡፡
 

 
የማያምኑ ሰዎች ከእግዚአብሄር ቁጣ በታች ናቸው፡፡

 
እግዚአብሄር የደህንነትን እውነት ለዓለም ሰጥቶዋል፡፡ የእግዚአብሄር እውነትና ፍቅር በምድር ላይ ሰፍነዋል፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሄርን እውነትና ፍቅር ቸል በማለት የሚቀርብ ማማኻኛ የለም፡፡ እግዚአብሄር በእውነት ወንጌል የማያምኑትንና እርሱን የሚቃወሙትን ሁሉ ይፈርድባቸዋል፡፡
 
የእውነተኛውን ወንጌል ፍቅር ስላልተቀበሉ ሰዎች እናስብ፡፡ እግዚአብሄር የፈጠረውን ማለትም ውሃውን፣ ሳሩን፣ ዛፎችን፣ ሰማይን፣ አእዋፋትንና ወ.ዘ.ተ እናያለን፡፡ እነዚህ ነገሮች እግዚአብሄር ሳይፈጥራቸው እንዴት ሊኖሩ ቻሉ? መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹እያንዳንዱ ቤት በአንድ ሰው ተዘጋጅቷል፡፡ ሁሉን ያዘጋጀ ግን እግዚአብሄር ነው፡፡›› (ዕብራውያን 3፡4) በእግዚአብሄርና በእውነት ቃል አለማመናቸው የእነርሱ ስህተት አይደለምን?
 
ስለዚህ በእግዚአብሄር የሐጢያት ይቅርታ ጸጋ የሚያምኑ ሰዎች በእግዚአብሄር ቢኮነኑ ተገቢ ነው፡፡ በዝግመተ ለውጥ ላይ የሙጥኝ ብለዋል፡፡ አጽናፈ ዓለማት የተገኙት በዝግመተ ለውጥ ነው በማለት ይከራከራሉ፡፡ በመጀመሪያ ከ15 ቢሊዮን ዓመታት በፊት ቢግ ባንግ የተባለ ፍንዳታ ነበር፤ ከዚያም አንድ ሕያው ፍጡር ብቅ አለ ይላሉ፡፡ ይህ የመጀመሪያው የሕይወት እውነታ ተለውጦ ወደ አሦች፣ ወደ እንስሶችና ውሎ አድሮም ወደ ሰዎች እያዘገመ ተለወጠ ይላሉ፡፡ ይህ ጽንሰ አሳብ እውነት ቢሆን ኖሮ የሰው ዘርም ውሎ አድሮ ከአንድ ወይም ሁለት ሺህ ዓመታቶች በኋላ ወደ ሌላ የሕይወት ቅርጽ ይለወጥ ነበር፡፡
 
‹‹የማይታየው ባህሪይ እርሱም የዘላለም ሐይሉ ደግሞም አምላክነቱ ከአለም ፍጥረት ጀምሮ ከተሰሩት ታውቆ ግልጥ ሆኖ ይታያልና፡፡ ስለዚህም እግዚአብሄርን እያወቁ እንደ እግዚአብሄርነቱ መጠን ስላላከበሩትና ስላላመሰገኑት የሚያመካኙት አጡ፡፡›› (ሮሜ 1፡20) ሰዎች የተፈጥሮን ድንቆችና ምስጢሮች በሚመለከቱበት ጊዜ እግዚአብሄር ሕያው እንደሆነ በግልጥ ማየት ቢችሉም እግዚአብሄርን ይክዱታል፤ አይቀበሉትምም፡፡ የማያምኑ ሰዎች ከእግዚአብሄር ቁጣ በታች ናቸው፡፡ ብዙ ሰዎች እግዚአብሄርን አላከበሩትም ወይም አላመሰገኑትም፡፡ ስለዚህ በአሳባቸው ከንቱዎች ሆኑ፡፡ ገልቱ ልባቸውም ጨለመ፡፡ ጥበበኞች ነን ሲሉ ሞኞች ሆኑ፡፡ የማይጠፋውንም የእግዚአብሄር ክብር በሚጠፉ ሰዎች፣ በወፎች፣ አራት እግር ባላቸው በሚንቀሳቀሱት መልክ ለወጡ፡፡ በኢየሱስ ቢያምኑ ወይም ባያምኑ የእግዚአብሄር ፍርድ እነዚህን ሰዎች እንደሚጠብቃቸው ግልጽ ነው፡፡
 
 
እግዚአብሄር የማያምኑ ሰዎችን ለርኩሰት አሳልፎ ሰጥቶዋቸዋል፡፡
 
‹‹ስለዚህ እርስ በርሳቸው ሥጋቸውን ሊያዋርዱ እግዚአብሄር በልባቸው ፍትወት ወደ ርኩስነት አሳልፎ ሰጣቸው፡፡ ይህም የእግዚአብሄርን እውነት በውሸት ስለለወጡ፣ በፈጣሪም ፋንታ የተፈጠረውን ስላመለኩና ስላገለገሉ ነው፡፡ እርሱም ለዘላለም የተባረከ ነው፤ አሜን፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር ለሚያስነውር ምኞት አሳልፎ ሰጣቸው፡፡ ሴቶቻቸውም ለባህሪያቸው የሚገባውን ሥራ ለባህሪያቸው በማይገባው ለወጡ፡፡ እንዲሁም ወንዶች ደግሞ ለባህሪያቸው የሚገባውን ሴቶችን መገናኘት ትተው እርስ በርሳቸው በፍትወታቸው ተቃጠሉ፡፡ ወንዶችም በወንዶች ነውር አድርገው በስህተታቸው የሚገባውን ብድራት በራሳቸው ተቀበሉ፡፡›› (ሮሜ 1፡24-27)
 
ይህ ምንባብ ምን ለማለት እየሞከረ ነው? እግዚአብሄር ፍጥረታትን የሚያመልኩትንና የሚያገለግሉትን እንደ ውዴታቸው ለሐጢያት አሳልፎ ይሰጣቸዋል፡፡ ለሰይጣንም አሳልፎ ይሰጣቸዋል፡፡ እግዚአብሄር ሰይጣን እንደፈለገው ያደርግ ዘንድ ይፈቅድለታል፡፡ ስለዘዚህ በእግዚአብሄር ማመንና መዳን ይገባናል፡፡ ‹‹ሴቶቻቸውም ለባህሪያቸው የሚገባውን ሥራ ለባህሪያቸው በማይገባው ለወጡ፡፡ እንዲሁም ወንዶች ደግሞ ለባህሪያቸው የሚገባውን ሴቶችን መገናኘት ትተው እርስ በርሳቸው በፍትወታቸው ተቃጠሉ፡፡›› ይህ እግዚአብሄርን መካድ ነው፡፡ ኤድስን ያመጣውም ይኸው ነው፡፡
 
እግዚአብሄር የተፈጥሮ ስርዓትን ሰጠ፡፡ ወንድ ከሴት ጋር መኖር ይገባዋል፡፡ ነገር ግን ወንዶች ከወንዶች ጋር ሴቶችም ከሴቶች ጋር ግንኙነት የመፍጠራቸው እውነታ እግዚአብሄር የሰጠውን የተፈጥሮ ስርዓት እንደካዱ ያሳያል፡፡ የሮሜ መጽሐፍ የተጻፈው ከ1,900 ዓመታት በፊት ነው፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ ተፈጥሮአዊ የጾታ ስርዓቶቻቸውን የሚተዉ ብልሹ ለሆነው የጾታ ግንኙነታቸው ቅጣታቸውን እንደሚቀበሉ ተንብዮአል፡፡ በዚህ ዘመን የእግዚአብሄር ቃል በተጨባጭ እየታየ ነው፡፡ ኤድስ በተለይም በግብረ ሰዶማውያን ዘንድ እየተስፋፋ እንዳለ እናውቃለን፡፡
 
ከጾታ ግንኙነት ጋር ለተዛመዱት ሐጢያቶቻቸው ቅጣትን መቀበላቸው ፈጽሞ ተገቢ ነው፡፡ የእግዚአብሄር ቁጣ ተፈጥሮአዊውን የጾታ ስርዓት በሚለውጡ ሰዎች ላይ ይገለጣል፡፡ የኤድስን ቅጣት መቀበላቸው ተገቢ ነው፡፡ ይህ ደዌ በእርግጥም የመጣው እግዚአብሄርን ባለማመን ነው፡፡ እግዚአብሄር የማያምኑትን ሰዎች ለማይረባ አእምሮ አሳልፎ ሰጥቶዋቸዋል፡፡ በሌላ አነጋገር ይህ በእርግጥም የእግዚአብሄር እርግማን ነው፡፡
 
 
እነርሱ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ተቃውመዋል፡፡
 
እግዚአብሄርን በአእምሮዋቸው መያዝ የማይወዱ ሰዎች የሚከተሉትን ይመስላሉ፡፡ ‹‹አመጻ ሁሉ፣ ግፍ፣ መመኘት፣ ክፋት ሞላባቸው፡፡ ቅናትን፣ ነፍስ መግደልን፣ ክርክርን፣ ተንኮልን፣ ክፉ ጠባይን ተሞሉ፡፡ የሚያሾከሹኩ፣ ሐሜተኞች፣ አምላክን የሚጠሉ፣ የሚያንገላቱ፣ ትዕቢተኞች፣ ትምክህተኞች፣ ክፋትን የሚፈላልጉ፣ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፣ የማያስተውሉ፣ ውል የሚያፈርሱ፣ ፍቅር የሌላቸው፣ ምህረት ያጡ ናቸው፡፡ እንደነዚህ የሚያደርጉት ሞት ይገባቸዋል የሚለውን የእግዚአብሄርን ሕግ እያወቁ እነዚህን ከሚያደርጉ ጋር ይስማማሉ እንጂ አድራጊዎች ብቻ አይደሉም፡፡›› (ሮሜ 1፡29-32)
 
‹‹እነዚህን የሚያደርጉ›› ሰዎች ተመሳሳይ ክፋትን ለሚያደርጉ ምን ይፈይዱላቸዋል? እነርሱን ‹‹ይደግፉዋቸዋል፡፡›› እግዚአብሄርን የሚቃወሙ ሰዎች የእግዚአብሄርን ቃል በሚታዘዙ ጻድቃኖች ላይ ምን ያደርጉባቸዋል? ‹‹እናንተ መናፍቃን ናችሁ›› በማለት ጻድቃንን ያሳድዳሉ፡፡ ጻድቃን በኢየሱስ ካመኑ በኋላ ስለ ጽድቅ ይሰደዳሉ፡፡ እነርሱ ብሩካን ናቸው፡፡
 
ሰዎች በሥጋ ለሚቅበዘበዙ ሰዎች ያዝኑላቸዋል፡፡ ሆኖም ሌሎች በኢየሱስ አምነው የሐጢያት ይቅርታን በማግኘት ጻድቃን እንዳይሆኑ ሲቃወሙና ሲከለክሉዋቸው ማየታችንን መናገር እንግዳ ነገር ነው፡፡ ይህ የሐጢያት ባርያ ሆኖ እንደ መኖር ነው፡፡ ምክንያቱም እነርሱ በእግዚአብሄር አያምኑም፤ የእውነትንም ቃል አይታዘዙምና፡፡
 
ስለዚህ የማያምኑ ሰዎችና ሰይጣን በኢየሱስ ክርስቶስ እንድናምን ቢፈቅዱልንም ፈጽሞ መቀደስም ሆነ ፍጹም የሆነ የሐጢያት ይቅርታ ሊኖረን እንደማይገባ ይናገራሉ፡፡ የማያምኑ ሰዎችና ሕግ ተላላፊዎች በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያቶች ቢኖሩም ሰማይ ለመግባት ሲሉ በኢየሱስ ማመን እንዳለባቸው ያስባሉ፤ ይናገራሉም፡፡ ሐጢያተኞች ሆነው በኢየሱስ ሲያምኑ የእፎይታ ስሜት የሚሰማቸው ለዚህ ነው፡፡ እግዚአብሄርን የማያውቁና የማያምኑ ሰዎች ክርስቲያኖች በፍጹም በእውቀታቸው እግዚአብሄርን ስላልተቀበሉት ይቃወሙታል፡፡ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ይቃወማሉ፡፡ ሰይጣንንና ሐጢያቶችንም ሁሉ ያመልካሉ፡፡ ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች በኢየሱስ ቢያምኑም ልክ እንደዚያው ናቸው፡፡ ዳግም ያልተወለዱ እጅግ ብዙ የስም ክርስቲያኖች አሉ፡፡ በልባቸው ውስጥ ሐጢያቶች ይዘው በኢየሱስ የሚያምኑ ሰዎች የእግዚአብሄርን የእውነት ቃል ስለማይታዘዙ በኢየሱስ ክርስቶስ እውነት በማመን የሐጢያት ስርየት አግኝተው የተቀደሱ ክርስቲያኖችን ይቃወማሉ፡፡
 
 
ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች ዳግም የወለዱትን ይቃወማሉ፡፡
 
ሐዋርያው ጳውሎስ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እውነትን በአመጻ በሚከለክሉ ሰዎች ላይ የእግዚአብሄር ቁጣ እንደሚገለጥ ተናግሮዋል፡፡ የእግዚአብሄር ቁጣ በርኩሰትና በአመጻ ሁሉ ላይ ከሰማይ እንደሚገለጥም ተናግሮዋል፡፡ እያንዳንዱ ነገር የሚከናወነው በእውነት አማካይነት ነው፡፡ እውነቱም ጌታ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ የደመሰሰ መሆኑ ነው፡፡ የእግዚአብሄር ፍርድ እውነትን በሚቃወሙና በሚያደናቅፉ ላይ ይገለጣል፡፡ ዳግም ያልተወለዱ ምዕመናን በሙሉ በእግዚአብሄር እንደሚፈረድባቸው ከእግዚአብሄር ቃል ተምረናል፡፡ እግዚአብሄር በኢየሱስ ቢያምኑም ዳግም ያልተወለዱትን ይፈርድባቸዋል፡፡
 
ዳግም ያልተወለዱ ምዕመናን ሐሜትን በተሞሉ ልቦች ዳግም በተወለዱት ላይ ማላገጥ ይወዳሉ፡፡ እነዚህ ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ እግዚአብሄር ወደ ሲዖል ያባርራቸዋል፡፡ እነርሱ በሐሜት የተሞሉ ናቸው፡፡ እርስ በርሳቸው ያሾከሹካሉ፡፡ የሐጢያት ይቅርታ ባገኙ ጻድቃን ላይ አብረው የሚያሾከሹኩ ሐጢያተኞች ሊፈረድባቸው ይገባል፡፡ ምን ማለቴ እንደሆነ ገባችሁ? ልናዝንላቸው ይገባል፡፡ እነርሱ ‹‹ሐጢያቶች የሌሉባቸው መሆኑ እንግዳ ነገር ነው፡፡ ይህ እንግዳ ነገር ይመስላል›› በማለት እያሾከሾኩ እርሱን የተቃወሙ መሆናቸውን ሳያውቁ በሐጢያቶቻቸው እግዚአብሄርን ይቃወማሉ፡፡
 
የእግዚአብሄር ቁጣ በክፋታቸው እርሱን በሚቃወሙት ላይ ይገለጣል፡፡ እነዚያ ሰዎች ክፋትን በሚያደርጉ ሰዎች ይደሰታሉ፡፡ ሐሜተኞችና ተሳዳቢዎች ትክክለኞች ናቸው ብለው ይቀበላሉ፡፡ ጻድቁን ያሙታል፤ ይጠሉትማል፡፡ በራሳቸው ይመካሉ፡፡ አብረውም ክፋትን ያሴራሉ፡፡ እንዴት ክፋትን እንደሚያሴሩ ታውቃላችሁን? እርስ በርሳቸው ተባብረው ክፋትን ይፈጽማሉ፡፡ ‹‹በኢየሱስ በሚገባ እንመን፡፡ ትክክለኛ እምነት ይኑረን፡፡ የዓለም ብርሃን እንሁን›› በሚሉ ጥሩ መፈክሮች ጻድቃኖችን ይቃወማሉ፡፡ በጋራ ሆነው እነዚህን ሐጢያቶች ይፈጽማሉ፡፡ ምክንያቱም ለብቻ ሐጢያት መስራት ቀልድ አይደለምና፡፡
 
ስለዚህ እግዚአብሄር በመዝሙረ ዳዊት 2፡4 ላይ እንዲህ ይላል፡- ‹‹በሰማይ የሚኖር እርሱ ይስቀል፡፡ ጌታም ይሳለቅባቸዋል፡፡›› ምክንያቱም የምድር ነገሥታት በእግዚአብሄር ላይ ተነስተዋልና፡፡ ‹ኦ! ይህ አስቂኝ ነው፡፡ እናንተ እኔን የሚቃወም ተግዳሮት ብታደርጉም ምንም የሚሆን ነገር አይኖርም፡፡ እናንተ ሰዎች ይፈረደብኝ ዘንድ በጉቦ አባብላችሁኛል፡፡› ይህ በጣም አስቂኝ ስለሆነ እግዚአብሄር የፍርዱን ቀን በመጠባበቅ ላይ ነው፡፡
 
 
በጻድቁ ላይ የሚፈርዱ ሰዎች በእግዚአብሄር ይፈረድባቸዋል፡፡
 
የእግዚአብሄርን እውነት የሚቃወሙና ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች ሐጢያቶችን ያደርጋሉ፡፡ ዳግም የተወለዱትም ቢሆኑ በሥጋቸው ውስጥ ክፋትና አለፍጽምናዎች አሉባቸው፡፡ ነገር ግን ይህ በመሰረቱ የተለየ ነው፡፡ እኛ በእግዚአብሄርና በእውነት እናምናለን፡፡ በእግዚአብሄር አማካይነት የሐጢያት ስርየትን አግኝተናል፡፡ እነርሱ ግን በጭራሽ በእግዚአብሄር አያምኑም፡፡ እነዚህ ሰዎች ‹‹የእግዚአብሄርን ጽድቅና እውነት›› የሚቃወሙ ናቸው፡፡ ‹‹ስለዚህ አንተ የምትፈርድ ሰው ሁሉ ሆይ የምታማካኘው የለህም፡፡ በሌላው በምትፈርድበት ነገር ራስህን ትኮንናለህና አንተው ፈራጁ እነዚያን ታደርጋለህ፡፡›› (ሮሜ 2፡1)
 
ሐዋርያው ጳውሎስ ዳግም ላልተወለዱትና ሕጉን ለሚያከብሩት አይሁዶችና ክርስቲያኖች ይናገራል፡፡ እነርሱ ‹‹አትግደል፣ አታመንዝር፣ አትስረቅ፣ እግዚአብሄርን ብቻ አምልክ›› በማለት ሌሎችን ይኮንናሉ፡፡ እነርሱ ራሳቸው ግን ሕጉን አይጠብቁም፡፡ በቅንነት የሚፈርድ እግዚአብሄር ብቻ ነው፡፡ በእግዚአብሄር ቃል መሰረት መፍረድ የሚችሉትም ዳግም የተወለዱት የእርሱ ልጆች ብቻ ናቸው፡፡
 
የዚህ አይነት ሰዎች ሊፈረድባቸው ይገባል፡፡ ምክንያቱም ጻድቁን በማንአለብኝነት ኮንነውታልና፡፡ እግዚአብሄር ዳግም ያልተወለዱትን ሁሉ ማለትም አይሁዶችንና ሕግ አጥባቂ ክርስቲያኖችን ይፈርድባቸዋል፡፡ የእግዚአብሄር ቁጣ ዳግም ሳይወለዱ ሕግን በመጠበቅ የሃይማኖት ኑሮን የሚኖሩትንና እግዚአብሄርን ባይታዘዙ ሲዖል እንደሚወርዱ እግዚአብሄር እንደተናገረው ቢያደርጉ ደግሞ ሰማይ እንደሚሄዱ በሚያምኑ ሰዎች ላይ ይገለጣል፡፡ የእምነት ሰው በኢየሱስ ክርስቶስ ካመነ በኋላ የጸደቀ ሰው ነው፡፡ መለየት አለብን፡፡ ዳግም ሳይወለዱ በእግዚአብሄር የሚያምኑና የሃይማኖት ሕይወትን የሚኖሩ ሰዎች በራሳቸው መስፈርት መሰረት በጻድቃን ላይ ይፈርዳሉ፡፡
 
ሆኖም እግዚአብሄር በእርግጥ ይፈርድባቸዋል፡፡ በራሳቸው መስፈርት መሰረት በራሳቸው ላይ እየፈረዱ መሆናቸውን አያውቁም፡፡ የሐጢያት ይቅርታን ሳትቀበሉ የተሳሳተ እምነት ይዛችሁ የእግዚአብሄርን እውነት ጸጋ ሳታገኙ በጻድቃን ላይ የምትፈርዱ ሰዎች ሆይ ከእግዚአብሄር ፍርድ የምታመልጡ ይመስላችኋልን? እነዚያ ሰዎች በእግዚአብሄር ይፈረድባቸዋል፡፡
 
 
የእግዚአብሄር ፍርድ ጻድቅ ነው፡፡
 
‹‹እንደዚህም በሚያደርጉት ላይ የእግዚአብሄር ፍርድ እውነተኛ እንደሆነ እናውቃለን፡፡›› (ሮሜ 2፡2) በኢየሱስ ቢያምኑም ዳግም ሳይወለዱ በሌሎች ላይ በሚፈርዱ ሰዎች የእግዚአብሄር ፍርድ እውነተኛ እንደሆነ እናውቃለን፡፡ እግዚአብሄር እነዚህን ሰዎች ወደ ሲዖል እንሚያወርዳቸውና በራሱ እውነት መሰረትም እደሚፈርድባቸው ማወቅ አለብን፡፡
 
እግዚአብሄር ሐጢያተኞችን ሲዖል የሚሰዳቸው የእርሱ እውነት ትክክል ስለሆነና የእግዚአብሄር ፍርድ እውነታ ስለሆነ ነው፡፡ አንድ ሰው ወደ ሲዖል መሄድ ወይም አለመሄዱ የሚወሰነው ‹‹እግዚአብሄር እንዳንዶችን ይወዳል፤ ሌሎችን ግን ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ ይጠላል›› ብሎ በሚሰብከው አስቀድሞ የመወሰን ትምህርት አይደለም፡፡ እግዚአብሄር ከዓለም ፍጥረት በፊት ሰዎችን በኢየሱስ ክርስቶስ መርጦዋቸዋል፡፡ (ኤፌሶን 1፡4)
 
ኢየሱስ ክርስቶስ ሐጢያቶቹን በሙሉ እንደደመሰሰለት የሚያምን ሰው ሁሉ የሐጢያት ስርየትን ይቀበላል፡፡ እግዚአብሄር ቀድሞውኑም የወሰነው ይህንን ነው፡፡ ስለዚህ ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች ሁሉ በኢየሱስ ቢያምኑም ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ በእግዚአብሄር ፍርድ መሰረት ወደ ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ እውነቱ ይህ ነው፡፡
 
ሐጢያተኞችን ወደ ሲዖል የሚያወርደው የእግዚአብሄር ፍርድ ትክክል ነው፡፡ ለምን? ምክንያቱም እነርሱ ታላቁን የእግዚአብሄር ፍቅር ንቀዋል፡፡ የእግዚአብሄርንም ማዳን አልተቀበሉም፡፡ በእርሱም አላመኑምና እንደ እውነቱ ከሆነ ዳግም ያልተወለዱትን ወደ ሲዖል መላኩ ለእግዚአብሄር ተገቢ ነው፡፡
 
አንዳንዶች ‹‹እግዚአብሄር ለምን ወንጌልን አልሰበከልኝም?›› ይሉ ይሆናል፡፡ አልሰበከም እንዴ? እግዚአብሄር ብዙ ጊዜ ወንጌልን ሰብኮላችኋል፡፡ አይኖቻችሁን በደንብ ከፍታችሁ ደህንነትን ለማግኘት ሞክሩ፡፡ በዚህ ዓለም ላይ ወንጌል የሚሰብኩ ጥቂት ቤተክርስቲያኖች አሉ፡፡ ሆኖም እውነቱን ከልባችሁ ብትፈልጉ ልታገኙት ትችላላችሁ፡፡ እኔም እውነትን ለማግኘት ከልቤ ጥሬያለሁ! ስብከት ከሰበክሁ በኋላ ገና ዳግም ያልተወለድሁ ሆኜ በነበረ ጊዜ ‹‹አምላክ ሆይ ልክ እንደዚህ ቃልህን ለሰዎች ብሰብክም እኔ በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኛ ነኝ፡፡ ለሰዎች የነገርኋቸውም ለራሴ የምነግረውን ነው፡፡ እኔ ሐጢያተኛ ነኝ፤ እባክህ ተገናኘኝ፤ እባክህ አድነኝ›› ብዬ ጸለይሁ፡፡
 
እውነትን ለማግኘት ምን ያህል እንደሞከርሁ አላውቅም፡፡ እግዚአብሄር እርሱን የሚሻውን ሁሉ ይገናኘዋል፡፡ እግዚአብሄር እርሱን የማይሹትንም እንኳን መቤዠት ይፈልጋል፡፡ ‹‹ሕዝቤ ያልሆነውን ሕዝቤ ብዬ ያልተወደደችውንም የተወደደች ብዬ እጠራለሁ፡፡›› (ሮሜ 9፡25) እግዚአብሄር እኛን ለማዳን ወደዚህ ምድር የመጣ አዳኛችን እንደሆነ ተናግሮዋል፡፡ እግዚአብሄርን ከልባቸው የሚሹ ሰዎች በእርግጥም ያገኙታል፡፡ ሌሎች ደግሞ እግዚአብሄርን ባይፈልጉትም የወንጌል ሰባኪዎች ወደ እነርሱ መጥተው ወንጌልን በሰበኩላቸው ጊዜ ጌታን የመገናኘት እድል አግኝተዋል፡፡ አንዳንዶች በወንጌል ይደሰታሉ፡፡ ሌሎች ግን አይደሰቱም፡፡ ወደ ሲዖል የሚወርዱ ሰዎች መጨረሻቸው እዚያው ይሆናል፡፡ ምክንያቱም የምስራቹን አልተቀበሉትምና፡፡
 
በእግዚአብሄር እውነት መሰረት ወደ ሲዖል መውረድ የሚገባቸው ሰዎች መጨረሻቸው ሲዖል መሆኑ ተገቢ ነው፡፡ ወደ መንግሥተ ሰማይ መግባት የሚገባቸው ሰዎች አንዳች የሚታወቅ ተግባር ባይኖራቸውም እዚያ የሚደርሱት በትክክለኛው መስፈርት መሰረት በኢየሱስ በማመን ነው፡፡ ይህ የሚሆነው በእግዚአብሄር ቅን ፍርድ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር ለአንዳንድ ሰዎች በማዳላት ላይ ተመስርቶ በዘፈቀደ አንዱን ሲዖል ሌላውን ደግሞ መንግሥተ ሰማያት አያስገባም፡፡ በፋንታው በቀናው ፍርዱ መሰረት በእውነት ይፈርዳል፡፡ ስለዚህ ወንጌልን መስበክ አለብን፡፡ ‹‹አንተም እንደዚህ በሚያደርጉ የምትፈርድ ያንም የምታደርግ ሰው ሆይ አንተ ከእግዚአብሄር ፍርድ የምታመልጥ ይመስልሃልን? ወይስ የእግዚአብሄር ቸርነት ወደ ንስሐ እንዲመራህ ሳታውቅ የቸርነቱንና የመቻሉን የትዕግስቱንም ባለጠግነት ትንቃለህን?›› (ሮሜ 2፡3-4)
 
 
ኢየሱስ ቀድሞውኑም በፍቅሩ አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ደምስሶዋል፡፡
 
ሐዋርያው ጳውሎስ የኢየሱስንም ፍቅር ሆነ ዳግም መወለድን ላልተቀበሉ ሐጢያተኞች፣ ለአይሁዶችና ለሕግ አጥባቂ ክርስቲያኖች እንደሚፈረድባቸው ይነግራቸዋል፡፡ እነርሱ ወደ ሲዖል ለመውረድ የታጩ ናቸው፡፡ ነገር ግን ወንጌል ምንድነው? በሮሜ 2፡4 ላይ እግዚአብሄር እንዲህ ይላል፡- ‹‹ወይስ የእግዚአብሄር ቸርነት ወደ ንስሐ እንዲመራህ ሳታውቅ የቸርነቱንና የመቻሉን የትዕግስቱንም ባለጠግነት ትንቃለህን?›› (ሮሜ 2፡4) የእግዚአብሄር ፍቅር ለሰዎች ሁሉ በትክክል ተገልጦዋል፡፡ በቅንነትም ተሰጥቷል፡፡
 
ማንም ሰው ከእግዚአብሄር የደህንነት ጸጋ አልተገለለም፡፡ ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ደምስሶዋል፡፡ ኢየሱስ ፈጽሞ ቀድሶናል፡፡ ለሐጢቶቻችን ይቅርታ ወደ እርሱ በምንጸልይበት ጊዜ ሁሉ የአዳምን ሐጢያት ብቻ ደምስሶ በየቀኑ የምንሰራቸውን ሐጢያቶች ይቅር የሚል ብቻ ነውን? አይደለም፡፡ ጌታ ቀድሞውኑም የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ደምስሶዋል፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄርን የሚቃወሙ ሰዎች የእርሱን ቸርነትና ፍቅር ንቀዋል፡፡ ‹‹ኢየሱስ ያዳነን እንዴት ነበር? በተደጋጋሚ ሐጢያት እየሰራሁ እንዴት ሐጢያት የለብኝም ማለት እችላለሁ? ይህ ስሜት የማይሰጥ ነው፡፡ እርሱ አዳኝና ጌታ አምላክ ቢሆንም እኔ በተደጋጋሚ ሐጢያት እየሰራሁ እግዚአብሄር ሐጢያቶቼን ሁሉ እንዴት ሊደመስሳቸው ቻለ?››
 
ሰዎች በሥጋቸው ልክ እንደዚህ ያስባሉ፡፡ እግዚአብሄር ግን ቀድሞውኑም በፍቅሩ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ አንጽቶዋል፡፡ ጌታ ወደ ዓለም መጣና ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ደመሰሳቸው፡፡ ጌታ የሰዎችን እንከኖችና ድካሞች ያውቃል፡፡ (ሥጋ ደጋግሞ ሐጢያት ከመስራት በቀር ሌላ የሚያውቀው ነገር የለም፡፡) ስለዚህ እርሱ በጥምቀቱና ደሙን በመስቀል ላይ በማፍሰስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ደምስሶዋል፡፡ ጌታ የሥጋን ድካሞች በሚገባ ያውቃል፡፡ ‹‹ያዳንኋችሁ እስክትሞቱ ድረስ ደጋግማችሁ ሐጢያት እንደምትሰሩ በማወቄ ነው፡፡››
 
ጌታ የዓለምን ሐጢያቶች አንጽቷል፡፡ ጌታ እኛን በመቤዠት ሁላችንንም ተቀብሎናል፡፡ ጌታ ለሐጢያተኞች የሐጢያትን ዋጋ ከፍሎ በሐይሉና በጽድቁ ቀድሶዋቸዋል፡፡ (ኢየሱስ በዮርዳኖስ ወንዝ በአጥማቂው ዮሐንስ ተጠምቋል፡፡) ጌታ እንድንባረክና ልጆቹም እንድንሆን ፈቅዶዋል፡፡ የሐጢያቶቻችንን ዋጋ በሕይወቱ (ደሙ) በመክፈል መንግሥተ ሰማይ እንድንገባ አስችሎናል፡፡ ጌታ ሐጢያተኞችን ወደ ጻድቃን ልጆቹ ቀይሮዋቸዋል፡፡
 
 
የማያምኑ ሰዎች ንስሐ መግባትና ልቦቻቸውን ወደ ጌታ መመለስ አለባቸው፡፡
 
‹‹ወይስ የእግዚአብሄር ቸርነት ወደ ንስሐ እንዲመራህ ሳታውቅ የቸርነቱንና የመቻሉን የትዕግስቱንም ባለጠግነት ትንቃለህን?›› (ሮሜ 2፡4) እግዚአብሄር የአምላክን ቸርነት፣ ባለጠግነት፣ መቻልና ትዕግስት የሚንቁና የሚክዱ ወደ ሲዖል እንዲወርዱ በይኖባቸዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ያነጻና ወንጌልም በመላው ዓለም የተሰራጨ መሆኑ እውነት ነው፡፡ ነገር ግን ሰዎች በዚህ ስለማያምኑ አሁንም ቢሆን ወደ ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ መቻሉንና የቸርነቱን ባለጠግነት በመናቅ ወደ ሲዖል መውረድ ብንፈልግም ኢየሱስ ወደ ሲዖል ከመውረድ ሊከላከለን አድኖናል፡፡ ሲዖል መውረድ ብንፈልግም እርሱ አድኖናል፡፡
 
ስለዚህ ለመዳን በኢየሱስ ክርስቶስ ውሃና ደም ማመን አለብን፡፡ እመኑና ዳኑ፡፡ የእግዚአብሄርን ፍቅርና ደህንነት የሚንቁ ወደ ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ ሲዖል እግዚአብሄር የደህንነቱን ጸጋና የቸርነቱን ባለጠግነት ለሚንቁ ያዘጋጀው ስፍራ ነው፡፡ የማያምኑ ሰዎች ወደ ሲዖል የሚወርዱበትን ትኬት አስቀድመው ቆርጠዋል፡፡ ወደ ሲዖል ለመውረድ የታጩ ሰዎች ንስሐ መግባትና ልቦቻቸውን ወደ ጌታ መመለስ አለባቸው፡፡ በእውነተኛው ወንጌል ላይ እምነት እስከሌላችሁ ድረስ የእግዚአብሄርን መንግሥት ደህና ሰንብት ልትሉት ይገባል፡፡
 
 
ሰዎች የእግዚአብሄርን ፍቅር ስለሚንቁ ወደ ሲዖል ይወርዳሉ፡፡
 
‹‹ነገር ግን እንደ ጥንካሬህና ንስሐ እንደማይገባ ልብህ የእግዚአብሄር ቅን ፍርድ በሚገለጥበት በቁጣ ቀን ቁጣን በራስህ ላይ ታከማቻለህ፡፡›› (ሮሜ 2፡5) ንስሐ የማይገባ ልብ ያላቸውና ንስሐ የማይገቡ ሰዎች ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ አንዳንድ ሰዎች የእግዚአብሄርን ታላቅ ፍቅር በመናቃቸው ሲዖል ይገባሉ፡፡ እውነትን ግትር በሆነው ልባቸው የሚንቁና የራሳቸውን አስተሳሰቦች የሚከተሉ ሰዎች ወደ ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ ይህም የሐጢያታቸው ዋጋ ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ፍቅር ለመቀበል እምቢተኞች የሆኑና በሒደት ቅድስና ላይ ለመድረስ ሲሉ የንስሐ ጸሎቶችን የሚጸልዩ ሰዎች ውሎ አድሮ ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ እነርሱ የጌታን ፍቅር በመናቃቸው እስከ መገለጥ ቀን ድረስ የእግዚአብሄርን ቁጣና ጻድቅ ፍርዱን አከማችተዋል፡፡
 
እግዚአብሄር በመቤዠት እቅዱ ሰይጣን እኛን በሐጢያት ከማበላሸቱ በፊትም እንኳን ሐጢያተኞችን ለማዳንና ጻድቃን ለማድረግ ወስኖዋል፡፡ እግዚአብሄር እኛን ለማዳንና ለመቀደስ ልጁን ላከ፡፡ ሐጢያተኞች ግን ይህንን አልተቀበሉትም፡፡ የእግዚአብሄርን ፍቅር በመናቃቸው የእግዚአብሄርን ቁጣ እስከ አፍ ገደፉ ድረስ ስላከማቹ በቁጣው ቀንና የእርሱ ጻድቅ ፍርድ በሚገለጥበት ቀን ይፈረድባቸዋል፡፡ የእግዚአብሄር ጻድቅ ፍርድ በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያቶች ያሉባቸውን ሰዎች ወደ ሲዖል ያወርዳቸዋል፡፡
 
ለምን? ምክንያቱም እግዚአብሄር የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ አንጽቶ በዓለም ላይ ያለውን እያንዳንዱን ሰው በእምነት አድኖታልና፡፡ የማያምኑ ሰዎች በእርግጥም ወደ ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ እነርሱ ግትሮችና ወደ ሲዖል ለመውረድ የሚወዱ ስለሆኑ በመጨረሻ በውሳኔያቸው ይጸጸታሉ፡፡ ሐጢያተኞች የእግዚአብሄርን ትልቅ ፍቅር ካልተቀበሉ ወደ ሲዖል ይወርዳሉ፡፡
 
ሰዎች እግዚአብሄር በገዛ ሥልጣኑ በዘፈቀደ አንዳንድ ሰዎችን ወደ ሲዖል ስለሚያወርድና ሌሎችን ደግሞ መንግሥተ ሰማያት ስለሚያስገባ ምክንያታዊ አይደለም ብለው ያስባሉ፡፡ ይህ ግን እውነት አይደለም፡፡ እግዚአብሄር ሲዖልን ያዘጋጀው ፍቅሩንና እውነቱን በመካድ ግትሮች ለሆኑት ነው፡፡ ስለዚህ ለእነርሱ የሚሆን በቂ ስፍራ አለ፡፡
 
መጽሐፍ ቅዱስ ሲዖል በእሳትና በዲን የሚቃጠል እሳት ያለበት ስፍራ እንደሆነ ይናገራል፡፡ ሐጢያት መስራትን ለሚቀጥሉ ሰዎች የሚርመሰመሱ ቆሻሻ ትላትሎች የሚገኑበት ስፍራ ነው፡፡ እነርሱ ‹‹ሐጢያቶቼን ሁሉ አንጽቻለሁ፡፡ አንተ ግን ሐጢያት ቢኖርብህም ምንም አይደለም ብለኸኛል›› ብለው ያለቅሱ ይሆናል፡፡ እግዚአብሄር ግን ‹‹ሐጢያቶችህን ሁሉ አንጽቻለሁ፡፡ አንተ ግን ሐጢያት ቢኖርብህም ምንም አይደለም ብለሃል፡፡ ስለዚህ ትሎችን ስጦታ አድርጌ ሰጥቼሃለሁ፡፡ ወዳጆችህ ይሁኑ፡፡ ምክንያቱም የሐጢያት ይቅርታ ይኖርህ ዘንድ አልወደድህምና›› ይላቸዋል፡፡
‹‹ብትጠላውም ይህንኑ ጠይቀሃል፡፡ እኔ የጽድቅ ጌታ ነኝ፡፡ የምትፈልገውን ሰጥቼሃለሁ፡፡ በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት እንዲኖር ለሚወዱ ሁሉ ሲዖልን ሰጥቻቸዋለሁ፡፡›› ይህ ትክክለኛ የእግዚአብሄር ፍርድ ነው፡፡ ሰብዓዊ ፍጡራን በዚህ ምድር ላይ ሲኖሩ ሳለ ሐጢያት ይሰራሉ፡፡ ነገር ግን የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ያነጻውን የእግዚአብሄር የደህንነት ወንጌል ቸል ማለት የለባቸውም፡፡
 
ሰዎች ወደ ሲዖል የሚወርዱት ልበ ደንዳኖች ስለሆኑ ነው፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ግትሮች መሆን የለብንም፡፡ እርሱ ቀድሞውኑም የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ እንዳነጻ ማመን አለብን፡፡ ይህ የማይታይ ቢሆንም ማመን አለባችሁ፡፡
 
 
እግዚአብሄር ቀድሞውኑም እንደወደደን ነግሮናል፡፡
 
እግዚአብሄር ቀድሞውኑም እንደወደደን ነግሮናል፡፡ ‹‹ቀድሞውኑም ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ አንጽቻለሁ፡፡›› ይህንን እውነት ልታምኑት ይገባል፡፡ እግዚአብሄር ሰማያትንና ምድርን እንደፈጠረ ከተናገረ ልናምነው ይገባናል፡፡ ምክንያቱም የእግዚአብሄር ቃል እውነት ነውና፡፡ እምነት የሚጀምረው የእግዚአብሄርን ቃል በማመን ነው፡፡ ሰዎች አንድን ነገር የሚያምኑት በትንሽዋ ጭንቅላታቸው ከተረዱ ብቻ ነው፡፡ መረዳት ካልቻሉ አያምኑም፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያተኞችን ሁሉ ከሐጢያቶቻቸው እንዳዳናቸው የማያምኑ ሰዎች ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ እነርሱ አእምሮዋቸውን ያዘጋጁት ሲዖል ለመውረድ ነው፡፡
 
በአንድ ወቅት በይፋ ‹‹እስክሞት ድረስ በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኛ መሆኔን እናዘዛለሁ›› ብሎ የተናገረ አንድ የታወቀ ክርስቲያን ነበር፡፡ እርሱ ሞተ፡፡ በእርግጥም ወደ ሲዖል ወርዶዋል፡፡ እርሱ እግዚአብሄርን እንዲህ አለው፡- ‹‹በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኛ መሆኔንና በፊቱ ፈጽሞ ጻድቅ መሆን እንደማልችል አውጃለሁ፡፡›› እስከ ዕለተ ሞቱ ድረስ ሐጢያተኛ በመሆኑ ጸና፡፡ የመጨረሻ እስትንፋሱ እስኪወጣ ድረስ የእግዚአብሄርን ፍቅርና እውነት ናቀ፡፡ ከዚያም ጌታ እንዲህ አለ፡- ‹‹አንተ ለገዛ ራስህ እምነት በጣም ታማኝ ነህ! እንደ እምነትህም ወደ ሲዖል መውረድህ ተገቢ ነው፡፡ ሐጢያተኞች ፈጽሞ መንግሥተ ሰማይ ሊገቡ ስለማይችሉ ወደ ሲዖል እልክሃለሁ፡፡››
 
 
አምኜ ቢሆን ኖሮ!
 
‹‹እስከ ዕለተ ሞቴ ድረስ ሐጢያተኛ መሆኔን አውጃለሁ›› ያለው ሰው ወደ ሲዖል ወረደ፡፡ እነዚህን ሰዎች እግዚአብሄርም እንኳን ሊረዳቸው አይችልም፡፡ እነርሱ ከነገ በኋላ መጨረሻቸው ሲዖል ቢሆንም ሐጢያተኞች መሆናቸውን ያወጁ ብቻ ሳይሆኑ በእነርሱ የሚታመኑ ምዕመናኖችንም ‹‹እስክንሞት ድረስ ሐጢያተኞች ነን፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ስንቆምም ሐጢያተኞች እንሆናለን›› ብለው አስተምረዋቸዋል፡፡ ስለዚህ ብዙ ምዕመናኖች ይህንኑ የሃይማኖት መንገድ ተከትለዋል፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያተኞች ወደ ሲዖል እንደሚወርዱ ተናግሮዋል፡፡ ሆኖም ብዙ ክርስቲያኖች በዘመኑ ክርስትና ውስጥ ይህንን ትምህርት ተከትለዋል፡፡ እግዚአብሄር እነዚያ ሐጢያተኞች ‹‹አምኜ ቢሆን ኖሮ! ይህንን ብቻ አምኜው ቢሆን ኖሮ›› በማለት በሚንበለበለው የሲዖል እሳት ውስጥ ጥርሶቻቸውን እያፏጩ ለዘላለም እንደሚጸጸቱ ተናገረ፡፡
 
‹‹ኢየሱስ ሐጢያቶቼን በሙሉ ያጠበ የመሆኑን እውነታ አምኜና የራሴን አስተሳሰቦች ትቼ ቢሆን ኖሮ መንግሥተ ሰማይ በገባሁ ነበር!›› ‹‹አምኜ ቢሆን ኖሮ፣ እውነትን ተቀብዬ ቢሆን ኖሮ የእርሱ ልጅ በሆንሁ ነበር፡፡ ለምን እንደዚህ ግትር ሆንሁ…፡፡››
 
በዚያን ጊዜ እኛ ጻድቃኖች እግዚአብሄርን ‹‹አቤቱ ሐጢያተኞች አሁን እያደረጉ ያሉትን እባክህ አሳየን፡፡ እኛን ጻድቃኖችን አሳድደውናል›› ብለን እንጠይቀዋለን፡፡ ‹‹ልጆቼ ሆይ ይህ ለእናንተ ጥሩ አይደለም፡፡ በእነርሱ መካከል ዘመዶቻችሁን ስታዩ ልባችሁ ይሰበራል፡፡ እናንተ የምታውቁዋቸው ሰዎች ሲሰቃዩ በእርግጥ ማየት ትፈልጋላችሁን?›› ‹‹እባክህ አንድ ጊዜ አሳየን!›› እግዚአብሄር ደግ ስለሆነ ከዕለታት አንድ ቀን ያሳየን ይሆናል፡፡ ስለዚህ እንዳየነው አድርገን እንገምት፡፡ ‹‹አምኜ ቢሆን ኖሮ፤ አምኜ ቢሆን ኖሮ›› የሚሉ ብዙ ልቅሶዎች ይሰሙ ይሆናል፡፡ ያን ጊዜ ‹‹ይህ ጩኸት ምንድነው? እየዘመሩ ነውን?›› ብለን እንገረም ይሆናል፡፡ ‹‹እየዘመሩ ወይም እየተጸጸቱ መሆናቸውን በጥንቃቄ አድምጡ፡፡›› በዚያ እሳት ውስጥ ያሉ ወንዶችና ሴቶች በዜማ እየዘመሩና ‹‹አምኜ ቢሆን ኖሮ›› በማለት እየተጸጸቱ ነው፡፡
 
ግትር ሰዎች በትክክለኛው መንገድ ግትር እስካልሆኑ ድረስ ወደ ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ እውነትን አጥብቀን በመያዝ ረገድ ጽናት ያስፈልገናል፡፡ ሰው የሚያመነታ መሆን የለበትም፡፡ መጽናት ያለብን ከሆነ መጽናት አለብን፡፡ ሁላችንም በትክክለኛው መንገድ መጽናት ይኖርብናል፡፡ አስፈላጊ በሚሆንበት ጊዜም ጽናታችንን ማፍረስ ይኖርብናል፡፡
 
 
እግዚአብሄር ለእያንዳንዱ ሰው እንደ ሥራው መጠን ይከፍለዋል፡፡
 
እግዚአብሄር ‹‹ለእያንዳንዱ እንደ ሥራው ያስረክበዋል፡፡ በበጎ ሥራ በመጽናት ምስጋናንና ክብርን የማይጠፋንም ሕይወት ለሚፈልጉ የዘላለምን ሕይወት ይሰጣቸዋል፡፡›› (ሮሜ 2፡6-7) እግዚአብሄር ለእያንዳንዱ ሰው እንደ ሥራው መጠን ያስረክበዋል፡፡ እርሱን/እርስዋንም በዚያ መሰረት ይፈርድባቸዋል፡፡ ‹ማስረከብ› ማለት ‹ከምግባር ጋር የሚመጣጠን ሽልማት መስጠት› ማለት ነው፡፡› ክብርን፣ ውዳሴንና አለመሞትን እየፈለገ በጎ በማድረግ ለመቀጠል ትዕግስትን የሚጠቀም ምን አይነት ሰው ነው? እርሱ/እርስዋ በኢየሱስ ፍጹም የሆነ ደህንነት የሚያምኑ እንደዚህ ያሉ ሰዎች ናቸው፡፡
 
በዓለም ላይ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ እግዚአብሄር የዘላለምን ሕይወት የሚሰጠው ግን ሌሎች ሰዎች ምንም ቢናገሩም ስለ ጽድቅ ለሚታገሱትና በእርሱ እውነት ለሚያምኑት ነው፡፡ እግዚአብሄር ጻድቃን መሆን ለሚፈልጉት ለዘላለም የደስታ ሕይወትን መኖር ለሚፈልጉት ሰዎች የዘላለም መንግስቱን ክብር ይሰጣቸዋል፡፡ እነርሱ በጎ ነገርን በማድረግ ይቀጥላሉ፡፡ ክብርን፣ ምስጋናን፣ የማይጠፋ ሕይወትንም ይሻሉ፡፡ የእግዚአብሄር ልጆች መሆን ይፈልጋሉ፡፡ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ለመሻትም በጎ በማድረግ ይታገሳሉ፤ ይቀጥላሉም፡፡ እግዚአብሄር ለእነዚህ ሰዎች የዘላለምን ሕይወትን ይሰጣቸዋል፡፡ እግዚአብሄር ለዘላለም እንዲኖሩ ፈቅዶላቸዋል፡፡ ልጆቹም አድርጎዋቸዋል፡፡ የእግዚአብሄር ልጆች በመንግሥቱ ውስጥ አምላኮች ናቸው፡፡
 
‹‹ለአመጻ በሚታዘዙ እንጂ ለእውነት በማይታዘዙትና በአድመኞች ላይ ግን ቁጣና መቅሰፍት ይሆንባቸዋል፡፡›› (ሮሜ 2፡8) ‹‹በእነዚያ ላይ ግን›› የሚለው የሚያመላክተው ከብሩካኖቹ በተቃራኒ ያለውን የሕዝብ ቡድን ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ጽድቅ በማይታዘዙ፣ አድመኞች በሆኑና እውነትን በማይታዘዙ ላይ የእግዚአብሄር ቁጣ ይመጣባቸዋል፡፡ እግዚአብሄር ወደ ሲዖል ይልካቸዋል፡፡ ዳግም ያልተወለዱና እውነትን የማይታዘዙ ሰዎች እንደ አንድ ቡድን አድመኞችና የእውነት ተቃዋሚዎች ናቸው፡፡
 
ዳግም ያልተወለዱ ሰዎች አድመኞች ናቸው፡፡ አንጃዎችን መፍጠርም ይወዳሉ፡፡ በኮርያ ታሪክ ውስጥ የጥንት አያቶቻችን አንጃዎችን ፈጥረው በፖለቲካ ችግሮች እርስ በርሳቸው ይጣሉ ነበር፡፡ ገዢው ቡድን የሚወስነው ንጉሥ የሚሆነው ማነው በሚለው እውነታ መሰረት ነው፡፡ ከሊ ቤተሰቦች አንዱ ንጉሥ ከሆነ የሊ ቤተሰብ ሰዎች በከፍተኛ ማህበራዊ ሥልጣኖች ላይ ይቀመጣሉ፡፡ ሌሎቹ ግን ይባረራሉ ወይም ይሰደዳሉ፡፡ ነገር ግን ዙፋኑ ወደ ኪም ቤተሰቦች ሲሸጋገር ሁሉም ነገር ሙሉ በሙሉ ይቀየራል፡፡ ሰዎች አንጃዎችን የሚፈጥሩት ጥሩ ነገሮችን ለማድረግ ሳይሆን ለራሳቸው ጥቅም ነው፡፡
 
የዘመኑም ክርስትና ከዚህ ጋር ይመሳሰላል፡፡ እነርሱ የቤተክርስቲያን ድርጅቶችንና አንጃዎችን ያደራጃሉ፡፡ ለምን ዓላማ? እንደ አንድ ቡድን ሆነው እውነትን ለመቃወም! ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች ቢያነጻም በአንድ ድምጽ ሐጢያት እንዳለባቸው ይናገራሉ፡፡ ጻድቃን እንደሆኑና እንደዳኑ ያስመስላሉ፡፡ እውነትን ግን አይታዘዙም፡፡ ሐጢያት የመስራት መብት እንዳላቸው በመናገር ጻድቃኖችን መናፍቃን አድርገው ይኮንኑዋቸዋል፡፡ ጌታ በጻድቃን ላይ አድማ የሚመቱ ሐጢያተኞች መሳሳታቸውንና ሁሉም ሲዖል መውረድ እንዳለባቸው ይናገራል፡፡
 
እውነትንና እግዚአብሄርን የሚታዘዙ ሰዎች የጌታን ቃል ይታዘዛሉ፡፡ እኛ ጻድቃኖች የእግዚአብሄር ፍርድ እውነተኛ እንደሆነ እናምናለን፡፡
 
 
የክርስትና ድርጅቶች መንግሥተ ሰማይ ያስገቡናልን?
 
የቤተክርስቲያን ድርጅት አካሎች መንግሥተ ሰማይ ሊያስገቡን አይችሉም፡፡ ባለቤቴ ‹‹ሃይማኖት መንግሥተ ሰማይ ሊያስገባሽ አይችልም›› በማለት አማቷን አስቆጥታለች፡፡ በግልጽ አነጋገር እናቴ በዚህ አነጋገር ለምን እንደተቆጣች እስከ አሁን ድረስ አላውቅም፡፡ ሃይማኖት መንግሥተ ሰማይ ሊያስገባችሁ እንደሚችል ታስባላችሁን? እኛ በግል እንድንና በእግዚአብሄር ቃል በማመን መንግሥተ ሰማይ እንገባለን፡፡ የፕሪስባይቴርያን ቤተክርስቲያን የሃይማኖት አካሎች መንግሥተ ሰማይ ሊያስገቡዋችሁ ይችላሉን? የባፕቲስት ቤተክርስቲያን የእምነት አካል መንግሥተ ሰማይ ሊያስገባችሁ ይችላልን? የቅድስና ቤተክርስቲያንስ ይችላልን? የሰባተኛ ቀን አድቬንቲስት ቤተክርስቲያንስ ይችላልን? አይችልም፡፡ መንግሥተ ሰማይ መግባት የምንችለው ኢየሱስ ለእኛ ባዘጋጀው የሐጢያት ይቅርታ ስናምን ብቻ ነው፡፡
 
 
በእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ውስጥ መቆየት ይኖርብናል፡፡
 
ሐዋርያው ጳውሎስ በክርስቲያኖች ሁሉ መካከል ወደ ሲዖል የሚወርዱትን ሐጢያተኞች መንግሥተ ሰማይ ከሚገቡ ጻድቃኖች በግልጽ ለይቶዋቸዋል፡፡ ወንጌል ለሁሉም ለአይሁዶችና ለግሪኮችም እንደዚሁ እኩል ነው፡፡ እዚህ ላይ ግሪኮች የሚያመለክቱት አህዛቦችን ሲሆን አይሁዶች ደግሞ ክርስቲያኖችን ያመላክታሉ፡፡ እግዚአብሄር የሰዎችን ውጫዊ ገጽታ አይመለከትም፡፡ እግዚአብሄር የአምላክን ቃል በልቡ የሚያምነውን ሰው ይመለከታል፡፡ ኢየሱስ አምላክ እንደሆነ ታምናላችሁን? ኢየሱስ አዳኛችን እንደሆነ ታምናላችሁን? ኢየሱስ በጥምቀቱ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ እንደወሰደ ስናምን ብቻ መንግሥተ ሰማይ መግባት እንችላለን፡፡ ይህንን ማመን እንጂ መካድ የለብንም፡፡ በውስጣችን ያለው መንፈስ ቅዱስ እምነታችንን እንዳንክድ ይጠብቀናል፡፡ አደጋ በሚገጥመን ጊዜም ጠላቶቻችንን እንድናሸንፍ ይረዳናል፡፡ ጠንቃቆች መሆን ይኖርብናል፡፡
 
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስለ አራት አይነት መሬቶች የተነገረ ምሳሌ አለ፡፡ አንዳንዶቹ መሬቶች ግን መዳን የማይችሉትን ያመለክታሉ፡፡ በእነዚያ መሬቶች ላይ የተዘሩት ዘሮች በበቀሉ ጊዜ ወዲያውኑ ይሞታሉ፡፡ ይህ ሁኔታ ከሞተ ዘር ጋር ተመሳሳይነት አለው፡፡ ውጤቱም ተመሳሳይ ሲሆን ያም ሞት ነው፡፡ ታዲያ እምነታችንን በራሳችን መጠበቅ እንችላለን? አንችልም፡፡ እምነታችንን መጠበቅ የምንችለው በእውነተኛው የወይን ግንድ ላይ ሆነን ማንኛውንም ችግር የምንቋቋምበትን ጉልበትና ለእያንዳንዱ መንፈሳዊ በሽታም ፈውሱን ጌታ ሲሰጠን ብቻ ነው፡፡
 
ወይኑ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ነች፡፡ በእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ውስጥ ስንኖር ሳለ ጌታ በረከቶችን፣ ፈውሶችን፣ መጽናናቶችንና ስደትን የምንቋቋምበት እምነት ይሰጠናል፡፡ በወይኑ ግንድ የማንኖር ከሆንን ግን ምን ይገጥመናል? ፈጥነን እንሞታለን፡፡ ብዙ ችሎታዎችና ጉልበቶች ቢኖሩዋቸውም በፈቃዳቸው ከቤተክርስቲያን ጋር ካልተቆራኙ የጻድቃን ልቦች የሰይጣንን ጥቃቶች መቋቋም ስለማይችሉ ውሎ አድሮ ይታመማሉ፡፡ ይህንን አስተዋላችሁን? እነርሱ ቀስ በቀስ ይወድቃሉ፡፡ ይበልጡኑም አይረቤ ይሆናሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹እናንተ የምድር ጨው ናችሁ፡፡ ጨው አልጫ ቢሆን ግን በምን ይጣፍጣል? ወደ ውጭ ተጥሎ በሰው ከመረገጥ በቀር ወደፊት ለምንም አይጠቅምም፡፡›› (ማቴዎስ 5፡13)
 
ጻድቃኖች ከቤተክርስቲያን ውጪ የሚኖሩ ከሆኑ ለምንም አይጠቅሙም፡፡ ብርሃናቸውን ማብራትና መባረክ የሚችሉት በቤተክርስቲያን ውስጥ ሲኖሩ ነው፡፡ ነገር ግን ከቤተክርስቲያን ተለይተው ከዓለም ጋር ከተቀላቀሉ ዓለምን ማሸነፍ አይችሉም፡፡ እምነታችሁን ደግፋችሁ መያዝ የምትችሉት ለምን ያህል ጊዜ ነው? ከእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን የምትርቁትስ እስከ መቼ ነው? የእግዚአብሄር ባሮች እንኳን መላቅ አይችሉም፡፡ ነገር ግን በወይኑ ግንድ ላይ የምንጣበቅ ከሆነ ቤተሰባችንም ይድናል፡፡ በእኛ አማካይነትም ብዙ ሰዎች የሐጢያቶቻቸውን ስርየት ሊያገኙ ይችላሉ፡፡ ሎጥ ሥጋዊ ፍላጎቱን ከተከተለ በኋላ ወዴት ሄደ? ወደ ሰዶም ሄደ፡፡ እዚያም በምቾት ኖረ፡፡ ውጤቱስ ምን ነበር? እርሱ ተበላሸ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የሎጥ ዝርያዎች ሁሉ እንደጠፉ ይናገራል፡፡ ሞዓባውያንና አሞናውያን የመጡት ከሎጥ ሴት ልጆች ነበር፡፡
 
የእግዚአብሄር ተቃዋሚ የሆኑት ዘሮች ጻድቅ ሰው ከሆነው ከሎጥ የተወለዱት ለምን ነበር? ይህ የሆነው እርሱ ከቤተክርስቲያን ስለተለየ ነው፡፡ እኔ በማናቸውም አስቸጋሪ ወቅቶች ተስፋ የማልቆርጠው እግዚአብሄር ቤተክርስቲያኑን ስለመሰረተ ነው፡፡ እግዚአብሄር ጻድቃን የሚሰበሰቡበትን ቤተክርስቲያን ባርኮታል፡፡ ለእያንዳንዱ ቅዱስ ሰውም የቤተክርስቲያን ጌታና እረኛ ሆንዋል፡፡ ይህ የእርሱ ተስፋና ማረጋገጫ ነው፡፡
 
‹‹ያለ ሕግ ሐጢአት ያደረጉ ሁሉ ያለ ሕግ ደግሞ ይጠፋሉና፡፡ ሕግ ሳላቸው ሐጢአት ያደረጉ ሁሉ በሕግ ይፈረድባቸዋል፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ሕግን የሚያደርጉት ይጽድቃሉ እንጂ ሕግን የሚሰሙ ጻድቃን አይደሉምና፡፡ ሕግ የሌላቸው አህዛብ ከባህርያቸው የሕግን ትዕዛዝ ሲያደርጉ እነዚያ ሕግ ባይኖራቸው እንኳን ለራሳቸው ሕግ ናቸውና፡፡ እነርሱም ሕሊናቸው ሲመሰክርላቸው አሳባቸውም እርስ በርሳቸው ሲካሰስ ወይም ሲያመካኝ በልባቸው የተጻፈውን የሕግ ሥራ ያሳያሉ፡፡›› (ሮሜ 2፡12-15)
 
በዛሬው ዘመን ወደ ቤተክርስቲያን የማይሄዱ ሰዎች ሕጉን አያውቁም፡፡ ያን ጊዜ ሕሊናቸው ሕግ ይሆናል፡፡ በሕሊናቸው ትክክል ወይም ስህተት መሆኑን ቢያውቁም ክፉውን ነገር ያደርጋሉ፡፡ ይህ ሐጢያት ስለሆነ ከሐጢያት ለመዳን ጌታን መሻት አለባቸው፡፡ እግዚአብሄር ከልቡ ሊገናኘው የሚሻውን ሰው ይገናኘዋል፡፡
 
በእግዚአብሄር ፊት ምህረቱን መሻትና በእርሱ ማመን አለብን፡፡ ትምክህታችንን ትተን በእርሱ ማመን አለብን፡፡ በእምነት መኖር አለብን፡፡ የእግዚአብሄርን ቤተክርስቲያን መተው የለብንም፡፡ መለመን፣ ማመንና በቤተክርስቲያን ውስጥ መቆየት አለብን፡፡ ደካሞችና ጎዶሎዎች ብንሆንም በቤተክርስቲያን ውስጥ ስንቆይ እግዚአብሄር አያባርረንም፡፡
 
 
የአይሁድ ሐጢያቶች፡፡
 
አሁን ሐዋርያው ጳውሎስ መንግሥተ ሰማይ ከሚገቡት ከለያቸው በኋላ ለአይሁዶች ወንጌልን በሙላት መስበክ ጀመረ፡፡
 
‹‹አንተ ግን አይሁዳዊ ብትባል በሕግም ብትደገፍ፣ በእግዚአብሄርም ብትመካ፣ ፈቃዱንም ብታውቅ፣ ከሕግም ተምረህ የሚሻለውን ፈትነህ ብትወድ፣ በሕግም የእውቀትና የእውነት መልክ ስላለህ የዕውሮች መሪ፣ በጨለማም ላሉ ብርሃን፣ የሰነፎችም አስተማሪ፣ የሕፃናትም መምህር እንደሆንህ በራስህ ብትታመን እንግዲህ አንተ ሌላውን የምታስተምር ራስህን አታስተምርምን? አትስረቅ ብለህ የምትሰብክ ትሰርቃለህን? አታመንዝር የምትል ታመነዝራለህን? ጣዖትን የምትጸየፍ ቤተ መቅደስን ትዘርፋለህን?›› (ሮሜ 2፡17-22)
 
የሚከተለውን ማወቅ አለብን፡፡ እግዚአብሄር በመጀመሪያ የተናገረው ለአይሁዶች ነበር፡፡ ስለዚህ እነርሱ የእግዚአብሄር ቃልና የመስዋዕት ስርዓት ነበራቸው፡፡ መሲሁ በአይሁዶች በኩል እንደሚመጣም ተስፋ ሰጥቶዋቸዋል፡፡ በአይሁድ አገልጋዮቹ አማካይነትም ዕቅዱን አሳይቶዋቸዋል፡፡ ስለዚህ ሙሴና ነቢያቶች ሁሉ አይሁዶች ነበሩ፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሄርን ቃል በትጋት በማነብነብና በአእምሮዋቸው በማስታወስ እግዚአብሄርን ምን እንደሚያስደስተውና ሕጉም ምን እንደነበር መረዳታቸውን አሰቡ፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ ግን እንዲህ ይላል፡- ‹‹አንተ ግን አይሁዳዊ ብትባል በሕግም ብትደገፍ፣ በእግዚአብሄርም ብትመካ፣›› አይሁዶች በእግዚአብሄር ቢመኩና በቅንነትም መስዋዕቶችን ቢያቀርቡም አልዳኑም፡፡ ኢየሱስን አዳኛቸው አድርገው በሚገባ የማያምኑ ሰዎች ከአላማኒዎች ጋር ተመሳሳይ ናቸው፡፡ ይህ ማለት እግዚአብሄር በመስዋዕቱ ስርዓት ውስጥ እንደታየው የሚያድናቸው የመሆኑን የእግዚአብሄር ተስፋ አላመኑም፤ በአዳኙ ኢየሱስም አላመኑም ማለት ነው፡፡
 
አይሁዶች በአዳኙ ኢየሱስ ስለማያምኑ ወደ ሲዖል ይወርዳሉ፡፡ ደጋግመው በበጎች ራስ ላይ እጆቻቸውን መጫናቸው ጥቅም የለውም፡፡ በብሉይ ኪዳን ማብቂያ ላይ ባለው በሚልክያስ ዘመን ‹‹እጆችን መጫን›› ማለት ‹‹ሐጢያቶችን ማስተላለፍ›› መሆኑን ከልባቸው አላመኑም፡፡ በዳዊት ዘመን በሚገባ አምነውበት ይሆናል፡፡ ከሰሎሞን ዘመን ጀምሮ ግን እምነታቸው መንገዳደገድ ጀመረ፡፡ በተከፋፈለው መንግሥት ዘመን በቤተመቅደሱ ውስጥ የግብር ይውጣ መስዋዕቶችን እያቀረቡ እንደ በኣልና አሼራ ያሉትን አማልክቶች ያመልኩ ነበር፡፡ የግብር ይውጣ መስዋዕቶችን ማቅረብ በእግዚአብሄር ከአለማመን ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ እግዚአብሄር በቃሉ ስናምንና ስንኖር ይረካል፡፡
 
በመገናኛው ደንኳን የመስዋዕት ስርዓት ውስጥ የአንድ ግለሰብ ሐጢያቶች ለመስዋዕት ወደሚቀርበው እንስሳ የሚሻገረው እጆቹን በእርሱ ላይ ሲጭንበት ነው፡፡ ነገር ግን ስህተቱና ትክክለኛው የቱ እንደሆነ ቢያውቁም በዚያ አላመኑበትም፡፡ ሌሎች ሰዎችንም አላስተማሩም፡፡ ይህ የአይሁዶች ሐጢያት ነበር፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል እውነት አለማመን፣ ቃሉን በሚገባ አለማወቅና ቃሉን ለሌሎች ሰዎች አለመስበክ የአይሁዶች ሐጢያት ነበር፡፡
 
ይህ እግዚአብሄርን ከአለማመን ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ይህ አደገኛ ሐጢያት ነው፡፡ ‹‹አንተ ግን አይሁዳዊ ብትባል በሕግም ብትደገፍ፣ በእግዚአብሄርም ብትመካ፣ ፈቃዱንም ብታውቅ፣ ከሕግም ተምረህ የሚሻለውን ፈትነህ ብትወድ፣ በሕግም የእውቀትና የእውነት መልክ ስላለህ የዕውሮች መሪ፣ በጨለማም ላሉ ብርሃን፣ የሰነፎችም አስተማሪ፣ የሕፃናትም መምህር እንደሆንህ በራስህ ብትታመን፡፡›› ጳውሎስ በአይሁዶች መካከል ያለውን የአለማመን ሐጢያት ነቅሶ አውጥቶዋል፡፡
 
 
በልብ ውስጥ ሐጢያቶችን ይዞ ማመን እግዚአብሄርን ማርከስ ነው፡፡
 
ይህንኑ የአይሁዶች የጅል ስህተት ዛሬ ላሉት ለአብዛኞቹ ክርስቲያኖች ልናውለው እንችላለን፡፡ አይሁዶች ኢየሱስ ሐጢያቶቻቸውን በሙሉ በመደምሰስ እንደቀደሳቸው ከማያምኑት ሰዎች አይለዩም፡፡ ‹‹በሕግ የምትመካ ሕግን በመተላለፍ እግዚአብሄርን ታሳፍራለህን? በእናንተ ሰበብ የእግዚአብሄር ስም በአሕዛብ መካከል ይሰደባልና ተብሎ እንደተጻፈ፡፡›› (ሮሜ 2፡23-24) በተሳሳተ መንገድ በኢየሱስ የምናምን ከሆነ የእግዚአብሄርን ስም እናሳፍራለን፡፡ ኢየሱስ በትክክል ያደረገውን የማናምንና ዳግም ያልተወለድን ከሆንን የእግዚአብሄርን ስም እናሳፍራለን፡፡
 
ዳግም ሳይወለዱ በኢየሱስ ማመን እግዚአብሄርን ማሳፈር ነው፡፡ ‹‹ሕግን ብታደርግ መገረዝስ ይጠቅማል፡፡ ሕግን ተላላፊ ብትሆን ግን መገረዝህ አለመገረዝ ሆኖአል፡፡ እንግዲህ ያልተገረዘ ሰው የሕግን ስርአት ቢጠብቅ አለመገረዙ እንደ መገረዝ ሆኖ አይቆጠርለትምን? ከፍጥረቱም ያልተገረዘ ሕግን የሚፈጽም ሰው የሕግ መጽሐፍና መገረዝ ሳለህ ሕግን በምትተላለፈው በአንተ ይፈርድብሃል፡፡ በግልጥ አይሁዳዊ የሆነ አይሁዳዊ አይደለምና፡፡ በግልጥ በሥጋ የሚደረግ መገረዝም አይደለምና፡፡ ዳሩ ግን በስውር አይሁዳዊ የሆነ አይሁዳዊ ነው፡፡ መገረዝም በመንፈስ የሚደረግ የልብ መገረዝ ነው እንጂ በመጽሐፍ አይደለም፡፡ የእርሱ ምስጋና ከእግዚአብሄር ነው እንጂ ከሰው አይደለም፡፡›› (ሮሜ 2፡25-29) ሁላችንም የኢየሱስን ቃሎች በልቦቻችን መቀበል አለብን፡፡
 
 
መጀመሪያ የቀደመው የትኛው ነው ግርዘት ወይስ ሕግ?
 
መጀመሪያ የቀደመው የትኛው ነው ግርዘት ወይስ ሕግ? እግዚአብሄር በመጀመሪያ ለእስራኤል የሰጠው የቱን ነው? ግርዘትን ነው፡፡ እግዚአብሄር አብርሃምን እንዲገረዝ ነገረው፡፡ አብርሃም የ99 ዓመት ሰው ቢሆንም የራሱ ልጅ አልነበረውም፡፡ እግዚአብሄር ግን አብርሃም የ75 ዓመት ሰው በነበረ ጊዜ ልጅ እንደሚሰጠው ቃል ገብቶለት ነበር፡፡ እግዚአብሄር አብርሃምን ‹‹ወደ ውጭ ውጣ፡፡ በሰማይ ላይ እንዳሉት ከዋክብቶች ብዙ ዘሮችን እሰጥሃለሁ›› አለው፡፡ አብርሃም በእግዚአብሄር ቃል አምኖ 25 ዓመት ያህል ጠበቀ፡፡ በመጨረሻ ከ25 ዓመታት በኋላ ተስፋው ተፈጸመ፡፡ ስለዚህ ልጅ ያገኘው በ100 አመቱ ነበር፡፡ እየጠበቀ ሳለ ጥቂት ተስፋ ቢቆርጥና ብዙ ስህተቶችን ቢሰራም 25 ዓመት ያህል ጠበቀ፡፡ እግዚአብሄር በመንፈሳዊ መልኩ መንግሥተ ሰማይን የምታመላክተውን የተስፋይቱን ምድር ከንዓንን ለእርሱና ለልጆቹ እንደሚሰጣቸውም ቃል ገብቶ ነበር፡፡
 
እግዚአብሄር መንግሥተ ሰማይን ቃል ከገባ በኋላ ለአብርሃም በቤቱ ያለ እያንዳንዱ ወንድ እንዲገረዝ ነገረው፡፡ ግርዘት በእግዚአብሄርና በእነርሱ መካከል ለሚሆነው ቃል ኪዳን ምልክት እንደሆነም ነገረው፡፡ ስለዚህ አብርሃም ሸለፈቱን ተገረዘ፡፡ በቤቱ ያሉት ወንዶች በሙሉም ይህንን ስርዓት ፈጸሙ፡፡ ግርዘት ከምናምንበትና የእውነትን ወንጌል ከምንቀበልበት እምነት ጋር የእውነትን ወንጌል ከምንቀበልበት እምነት ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡
 
 
እስራኤሎች የልብ ግርዘትን ክደዋል፡፡
 
ነገር ግን እስራኤሎች የአብርሃም ዘሮች በመሆናቸውና በመገረዛቸው የተመኩ አሕዛቦችን ‹‹ተገርዛችኋልን?›› በማለት በማን አለብኝነት ጠየቁዋቸው፡፡ በልባችን መገረዝ አለብን፡፡ ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች መደምሰሱን የሚናገረውን ቃል ስንቀበልና በልቦቻችንን ስናምነው እንድናለን፡፡
 
ከእስራኤል የበለጠ የተወረረ አገር የለም፡፡ ለሁለት ሺህ አመታቶች ያህል አገር አልባ ሕዝብ ስለነበሩ ሐዘናቸው የጠለቀ ነበር፡፡ እግዚአብሄር እስራኤልን ጨፈለቀ፡፡ ለምን? ምክያቱም አላመኑምና፡፡
 
እግዚአብሄር እስራኤልን ቢወድና ሐጢያቶቻቸውን በሙሉ እንዳነጻ ያምኑ ዘንድ ቢፈልግም ባለማመናቸው ምክንያት የእግዚአብሄርን ስም አረከሱ፡፡ የእስራኤል እረኛ ሆኖ ጠላቶቻቸውን ሊያሸንፍ ፈለገ፡፡ ሊባርካቸው ሊወዳቸውና ሊያከብራቸው ፈለገ፡፡
 
ከልባቸው በእርሱ ቢያምኑና የሐጢያት ስርየትን ቢቀበሉ እግዚአብሄር ሰዎችን ሁሉ ሊያከብርና ልጆቹ ሊያደርጋቸው ቃል ገብቷል፡፡ በእስራኤል ምሳሌ መሰረት እግዚአብሄር ተስፋውን የማይቀበሉ ከሆነ ወደ ሲዖል እንደሚልካቸው የዓለምን ሕዝብ በሙሉ አስጠንቋቋል፡፡
 
እግዚአብሄር የእርሱን የእውነት ወንጌል የሚያምን ሁሉ በምግባሮቹ ብቃት ባይኖረው እንኳን በረከቶችን ሁሉ ሊቀበል እንደሚችል ቃል ገብቷል፡፡ የእግዚአብሄር ፍርድ ለማስወገድ ብቸኛው መንገድ በወንጌል ማመን ነው፡፡ በእርሱ እመኑ፡፡ ያን ጊዜ ትድናላችሁ፡፡ ከሲዖልም ትወጣላችሁ፡፡
 
የእግዚአብሄር ጸጋ በነፍሶቻችን ሁሉ ውስጥ እንዲሰርጽ እመኛለሁ፡፡