Search

ስብከቶች፤

ርዕስ 9፡ ሮሜ (በሮሜ መጽሐፍ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[Chapter 9-2] አስቀድሞ መወሰን በእግዚአብሄር ጽድቅ ውስጥ እንደታቀደ ማወቅ አለብን፡፡ ‹‹ሮሜ 9፡9-33››

‹‹ሮሜ 9፡9-33›› 
‹‹ይህ በዚህ ጊዜ እመጣለሁ፤ ለሳራም ልጅ ይሆንላታል የሚል የተስፋ ቃል ነውና፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፤ ነገር ግን ርብቃ ደግሞ ከአንዱ ከአባታችን ከይስሐቅ በጸነሰች ጊዜ ልጆቹ ገና ሳይወለዱ በጎ ወይም ምንም ሳያደርጉ ከጠሪው እንጂ ከሥራ ሳይሆን በምርጫ የሚሆን የእግዚአብሄር አሳብ ይጸና ዘንድ ለእርስዋ ታላቁ ለታናሹ ይገዛል ተባለላት፡፡ ያዕቆብን ወደድሁ ኤሳውን ግን ጠላሁ ተብሎ እንደተጻፈ ነው፡፡ እንግዲህ ምን እንላለን? በእግዚአብሄር ዘንድ ዓመጻ አለ ወይ? አይደለም፡፡ ለሙሴ የምምረውን ሁሉ እምረዋለሁ፤ ለምራራለትም እራራለታለሁ ይላልና፡፡ እንግዲህ ምህረት ለወደደ ወይም ለሮጠ አይደለም፤ ከሚምር ከእግዚአብሄር ነው እንጂ፡፡ መጽሐፍ ፈርዖንን ሐይሌን በአንተ አሳይ ዘንድ ስሜም በምድር ሁሉ ይነገር ዘንድ ለዚህ አስነሳሁህ ይላልና፡፡ እንግዲህ የሚወደውን ይምረዋል፤ የሚወደውንም እልከኛ ያደርገዋል፡፡ እንግዲህ ስለምን እስከ አሁን ድረስ ይነቀፋል? ፈቃዱንስ የሚቃወም ማነው? ትለኝ ይሆናል፡፡ ነገር ግን አንተ ሰው ሆይ ለእግዚአብሄር የምትመልስ አንተ ማን ነህ? ሥራ ሠሪውን ስለምን እንዲህ አድርገህ ሠራኸኝ ይለዋልን? ወይም ሸክላ ሠሪ ከአንዱ ጭቃ ክፍል አንዱን ዕቃ ለክብር አንዱንም ለውርደት ሊሠራ በጭቃ ላይ ሥልጣን የለውምን? ነገር ግን እግዚአብሄር ቁጣውን ሊያሳይ ሐይሉንም ሊገልጥ ወዶ አስቀድሞ ለክብር ባዘጋጃቸው በምህረት ዕቃዎች ላይ የክብሩን ባለጠግነት ይገልጥ ዘንድ ለጥፋት የተዘጋጁትን የቁጣ ዕቃዎች በብዙ ትዕግስት ከቻለ እንዴት ነው? የምህረቱ ዕቃዎችም ከአይሁድ ብቻ አይደሉም፡፡ ነገር ግን ከአሕዛብ ደግሞ የጠራን እኛ ነን፡፡ እንዲሁ ደግሞ በሆሴዕ ሕዝቤ ያልሆነውን ሕዝቤ ብዬ እጠራለሁ፡፡ ያልተወደደችውንም የተወደደች ብዬ እጠራለሁ፡፡ እናንተ ሕዝቤ አይደላችሁም በተባለላቸውም ስፍራ በዚያ የሕያው እግዚአብሄር ልጆች ተብለው ይጠራሉ ይላል፡፡ ኢሳይያስም የእስራኤል ልጆች ቁጥር ምንም እንደ ባህር አሸዋ ቢሆን ቅሬታው ይድናል፡፡ ጌታ ነገሩን ፈጽሞና ቆርጦ በምድር ላይ ያደርገዋልና ብሎ ስለ እስራኤል ይጮሃል፡፡ ኢሳይያስም እንደዚሁ፡- ጌታ ጸባዖት ዘር ባያስቀርልን እንደ ሰዶም በሆንን ገሞራንም በመሰልን ነበር ብሎ አስቀድሞ ተናገረ፡፡ እንግዲህ ምን እንላለን? ጽድቅን ያልተከተሉት አህዛብ ጽድቅን አገኙ፡፡ እርሱ ግን ከእምነት የሆነ ጽድቅ ነው፡፡ እስራኤል ግን የጽድቅን ሕግ እየተከተሉ ወደ ሕግ አልደረሱም፡፡ ይህስ ስለ ምንድር ነው? በሥራ እንጂ በእምነት ጽድቅን ስላልተከተሉ ነው፡፡ እነሆ በጽዮን የእንቅፋት ድንጋይና የማሰናከያ ዓለት እኖራለሁ፤ በእርሱም የሚያምን አያፍርም ተብሎ እንደተጻፈ በእንቅፋት ድንጋይ ተሰናከሉ፡፡
                   
 

በእግዚአብሄር የታቀደው እውነተኛው አስቀደሞ መወሰን ምንድነው? 

 
አሁን ‹‹በእግዚአብሄር የታቀደው አስቀድሞ መወሰን ምን እንደሆነ›› ለማወቅ ትኩረታችንን እንመልስ፡፡ አስቀድሞ መወሰን ማለት በግልጽ ምን ማለት እንደሆነ ለመረዳት የተጻፈውን ቃል የእግዚአብሄር ቃል አድርገን መመልከትና በእምነታችን ውስጥ አንዳች የተሳሳተ ነገር ካለም ራሳችንን ማረም አለብን፡፡ ስለዚህ በመጀመሪያ እግዚአብሄር ኤሳውን ጠልቶ ያዕቆብን ለምን እንደወደደው መረዳት አለብን፡፡ በአሁኑ ዘመን ያለው ክርስትና አስቀድሞ የመወሰን መረዳት ከመጽሐፍ ቅዱስ ያፈነገጠ እንደሆነ ወይም እንዳልሆነም ማወቅ ያስፈልገናል፡፡ ሁላችንም እግዚአብሄር ያጸናውን አስቀድሞ መወሰን በትክክል መረዳት አለብን፡፡
 
እኛ ክርስቲያኖች ከእግዚአብሄር ዘንድ በረከቶችን ለማግኘት የእግዚአብሄር አስቀድሞ መወሰን እንዴት ከፈቃዱ ጋር እንደሚጣጣም ማወቅ ያስፈልገናል፡፡ ስለ እግዚአብሄር ዕቅድ ሲታሰብ ብዙዎቹ የዘመኑ ክርስቲያኖች ዕጣ ፈንታዎቻቸው ከመወለዳቸው በፊት አስቀድመው እንደተወሰኑና ከእምነታቸው ጋር ምንም ተያያዥነት እንደሌለው ያስባሉ፡፡ ይህ የያዕቆብና የኤሳው ዕጣ ፈንታዎች ያለ ቅድመ ሁኔታና በአንድዮሽ በእግዚአብሄር ተወስኖ ነበር የማለት ያህል ነው፡፡ ጉዳዩ ግን ይህ አይደለም፡፡ በእግዚአብሄር መወደድ ወይም አለመወደዳችን የሚወሰነው በእርሱ ጽድቅ በማመናችን ወይም አለማመናችን ነው፡፡ እግዚአብሄር በእቅዱ ውስጥ የሰጠን እውነት ይህ ነው፡፡
            
 
የእግዚአብሄርን ቅድመ ውሳኔ በትክክል ለመረዳት ከፈለጋችሁ የራሳችሁን አስተሳሰብ መጣልና 
በእግዚአብሄር ጽድቅ ላይ ማተኮር አለባችሁ፡፡ 
 
ብዙ ሰዎች በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በተገለጠው የእግዚአብሄር ጽድቅ ስለማያስቡና ስለማያምኑ የእግዚአብሄርን ፍቅር እነርሱ በመረጡት በማናቸውም መንገድ ሊያስቡት ያዘነብላሉ፡፡ እንዲያውም አንዳንዶች የእግዚአብሄር ፍቅር ቅን አይደለም ብለው ያስባሉ፡፡ ይህ ትክክለኛው የአስተሳሰብ መንገድ እንዳልሆነ መገንዘብ አለባቸው፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል የተገለጠውን የእግዚአብሄርን የጽድቅ እቅድ ሳናስብ በተሳሳተ መንገድ የደረስንባቸውን የእምነት ጭብጦች መጣል ያስፈልገናል፡፡ እግዚአብሄር አንዳንዶችን እየወደደ ሌሎችን እንደሚጠላ ብቻ የምታስቡ ከሆነ ይህ በራሳችሁ የተሳሳተ እሳቤ የተፈጠረ የተሳሳተ አይነት እምነት መሆኑን መገንዘብ አለባችሁ፡፡
 
የሰዎች አእምሮ በተሳሳቱ አስተሳሰቦች ተጠቅቷል፡፡ የዘመኑ ክርስቲያኖች ብዙዎቹ አእምሮዋቸው ብዙውን ጊዜ በተሳሳቱ እሳቤዎች የተሞላ በመሆኑ ትክክለኛ እምነት የላቸውም፡፡ የማይረቡ እሳቤዎቻችሁን ጥላችሁ የእግዚአብሄርን ቃል በመከተልና በእርሱ ጽድቅ በማመን እምነታችሁን በትክክለኛው ጎዳና ላይ እንድታኖሩት የሚያስፈልጋችሁ ለዚህ ነው፡፡
 
አስቀድሞ መወሰን የታቀደው በእግዚአብሄር ጽድቅ ውስጥ በመሆኑ በትክክል ሊስተዋልና ሊታመን የሚችለው በእርሱ ጽድቅ ስናምን ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ በእርሱ ዕቅድና ጽድቅ እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡ የእግዚአብሄር እቅድ በእርሱ ጽድቅ ውስጥ ባለው ፍቅር የሚያምኑትን ሰዎች በጽድቅ ማልበስ ነው፡፡
 
ስለዚህ የእርሱ ቅድሚያ ውሳኔ ምዕመናኖችን በኢየሱስ ጥምቀትና በስቅለቱ የተከፈለውን የሐጢያቶች ስርየት ደህንነት በማልበስ የራሱ ሕዝብ ማድረግ ነው፡፡ በጽድቁ ውስጥ በታቀደው እውነት በማመን ከእግዚአብሄር ጋር ትክክለኛ ግንኙነት መፍጠር አለብን፡፡ እግዚአብሄር እንደ ያዕቆብ ያሉትን የፍቅሩ ዕቃዎች ሲያደርጋቸው እንደ ኤሳው ያሉትን ደግሞ የቁጣው ዕቃዎች አድርጎዋቸዋል፡፡
 
 

የእግዚአብሄር ቅድመ ውሳኔ የአርባ ቀን ዕድል ጉዳይ አይደለም፡፡ 

 
በእግዚአብሄር ዕቅድ ውስጥ ያለው አስቀድሞ መወሰን በእርሱ ጽድቅ ውስጥ የጸና ነው፡፡ የእግዚአብሄር ዕቅድ ያለ ምንም ዕቅድ በዘፈቀደ የተደነገገ ነገር አይደለም፡፡ እያንዳንዱ ሰው ሕይወቱ በዕጣ ፈንታ የሚመራ ይመስል ከመወለዱ በፊት ያለ ቅድመ ሁኔታ ተመርጦ ከነበረ በኢየሱስ ጽድቅ በማመን እንዴት ከሐጢያት መዳን ይችላል? አንድ ሰው ዕጣ ፈንታው ከመወለዱ በፊት በዚህ መንገድ ከተወሰነ በእግዚአብሄር መወደድ አለመወደዱም አስቀድሞ የታቀደና አስቀድሞ የተወሰነ ውጤት ከሆነ እግዚአብሄር ቅን ነው ብሎ የሚያስብና በዚህ አይነት አምላክ የሚያምን ማን ነው?
 
የአምላካችን ዕቅድ ግን ግብታዊም ሆነ አምባገነናዊ አይደለም፡፡ በጽድቅ እኛን ከሐጢያቶቻችን የሚያድነንና ሕዝቡ የሚያደርገን ዕቅድ ነው፡፡ እግዚአብሄር በዚህ ዕቅድ ውስጥ ጽድቁን ሰጠን፡፡ በዚህ የጽድቅ ፍቅር ውስጥም የራሱን ይቅርታ ሰጠን፡፡ በጽድቁ ፍቅር የሚያምኑትንም ፍቅሩን ሊያለብሳቸው በዚህ የማያምኑትንም በቁጣው ሊያጠፋቸው ተዘጋጅቷል፡፡
በተሳሳተ መረዳት የእግዚአብሄርን ቅድመ ውሳኔ ለሚጠሉ ሰዎች የሚከተለውን መናገር እወዳለሁ፡፡ የእግዚአብሄር እቅድ የእርሱ ፍጥረት የሆንነውን እኛን የራሱ ሕዝብ ማድረግ ነው፡፡ ስለዚህ ለቅድመ ውሳኔው አመስጋኞች ልንሆን ይገባናል፡፡ እነርሱን የሚያጥላሉ ብስጩ ሰዎች ከመሆን ይልቅ በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምኑ አመስጋኝ ሰዎች መሆን ይሻለናል፡፡ ኢየሱስን አዳኙ አድርጎ የሚያምን እያንዳንዱ ሰው በእርሱ ጽድቅ ውስጥ የታቀደውን የእግዚአብሄር ቅድመ ውሳኔ በትክክል መረዳትና ማመን አለበት፡፡
         
 
የእግዚአብሄር እውነተኛ ቅድመ ውሳኔ በጠሪው በእርሱ የጸና ነው፡፡ 
 
ከሮሜ 9፡9 የተወሰደው የዛሬው ምንባብ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ይህ በዚህ ጊዜ እመጣለሁ፤ ለሳራም ልጅ ይሆንላታል የሚል የተስፋ ቃል ነውና፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፤ ነገር ግን ርብቃ ደግሞ ከአንዱ ከአባታችን ከይስሐቅ በጸነሰች ጊዜ ልጆቹ ገና ሳይወለዱ በጎ ወይም ምንም ሳያደርጉ ከጠሪው እንጂ ከሥራ ሳይሆን በምርጫ የሚሆን የእግዚአብሄር አሳብ ይጸና ዘንድ ለእርስዋ ታላቁ ለታናሹ ይገዛል ተባለላት፡፡ ያዕቆብን ወደድሁ ኤሳውን ግን ጠላሁ ተብሎ እንደተጻፈ ነው፡፡››
 
ይህ ምንባብ የእግዚአብሄር ቅድመ ውሳኔ በእግዚአብሄር የጽድቅ ፍቅር ውስጥ የታቀደ የፍቅር ቅድመ ውሳኔ እንደሆነ ይነግረናል፡፡ በዘፍጥረት 18፡10 ላይ እንደታየው የሳራ ልጅ መውለድ በሰው ዘንድ የማይቻል ቢሆንም አብርሃም ግን በእግዚአብሄር ተስፋ ቃል አመነ፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሄር ቃሉን ሰጥቶታልና፡፡ እግዚአብሄር አብርሃምን ያጸደቀው እንዲህ ነው፡፡ እግዚአብሄር ልጁን ይስሐቅን የሰጠው በእርሱ ስላመነ ነበር፡፡ እግዚአብሄርም እምነቱን አጽንቶለታል፡፡
 
ስለዚህ በእግዚአብሄር ጽድቅ ስለማመን ስንናገር በእግዚአብሄር ቃል ስለማመን እየተናገርን ነው፡፡ ስለ እግዚአብሄር ዕቅድና ቅድመ ውሳኔ የምናደርገው ውይይት በቃሉ ላይ ባለን እምነት መመራት አለበት፡፡ ለምሳሌ ከዚህ ውጪ የሚያደርጉ ሰዎች አሉ -- የእግዚአብሄርን ጽድቅ የመፈለግ ተግባራቸውን ሲጸልዩ ወይም ሕልም ሲያልሙ አይተናል በሚሉዋቸው ምመናቦች ወይም ምልክቶች የሚደናበሩ ሰዎች -- በእምነታቸው ትልቅ ስህተት እየሰሩ ነው፡፡
     
ጳውሎስ ጨምሮ ይህንን ያክላል፡- ‹‹ነገር ግን ርብቃ ደግሞ ከአንዱ ከአባታችን ከይስሐቅ በጸነሰች ጊዜ ልጆቹ ገና ሳይወለዱ በጎ ወይም ምንም ሳያደርጉ ከጠሪው እንጂ ከሥራ ሳይሆን በምርጫ የሚሆን የእግዚአብሄር አሳብ ይጸና ዘንድ ለእርስዋ ታላቁ ለታናሹ ይገዛል ተባለላት፡፡››
 
መጽሐፍ ቅዱስ ይስሐቅ የራሱ ልጅ ላልነበረው ወደ እግዚአብሄር እንደጸለየና እግዚአብሄርም መንታዎችን እንደሰጠው ይነግረናል፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ ውስጥ የታቀደው የእግዚአብሄር ቅድመ ውሳኔ በእግዚአብሄር ከተወደዱ ሰዎች ጋር የተወሰነ ግንኙነት እንዳለው ማየት እንችላለን፡፡
 
እዚህ ላይ ቁጥር 11ን መድገም ተገቢ ነው፡፡ ‹‹ልጆቹ ገና ሳይወለዱ በጎ ወይም ምንም ሳያደርጉ ከጠሪው እንጂ ከሥራ ሳይሆን በምርጫ የሚሆን የእግዚአብሄር አሳብ ይጸና ዘንድ፡፡›› በእግዚአብሄር ዕቅድ ውስጥ የቅድመ ውሳኔንና የምርጫን እውነት ለመረዳት ቁልፉ ‹‹ከጠሪው›› የሆነው የእግዚአብሄር አሳብ የጸና መሆኑ ነው፡፡ በእግዚአብሄር ዕቅድ ውስጥ ባለው የቅድመ ውሳኔ መሰረት በያዕቆብና በኤሳው መካከል እግዚአብሄር ያዕቆብን ጠርቶ ወደደው፡፡
 
በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር ሰዎችን ሲጠራና ሲወድድ ልክ እንደ ያዕቆብ ከጽድቅ የራቁትን ሰዎች ጠርቶ ይወድዳቸዋል፡፡ እግዚአብሄር ራሱን ጻድቅ እንደሆነ ያሰበውንና በትዕቢት የተሞላውን ኤሳውን አልጠራም፡፡ በእቅዱ ውስጥ በተቀመጠው የእግዚአብሄር ቅድመ ውሳኔ ውስጥ እግዚአብሄር እንደ ያዕቆብ ያሉ ሰዎችን የመምረጡ አሳብ ሐጢያተኞችን ከሐጢያት አርነት በማውጣት የራሱ ልጆች ለማድረግ ነው፡፡ የተጠሩትን በፍቅር የሚሸፍናቸው እግዚአብሄር ነው፡፡ በያዕቆብና በኤሳው መካከልም የተጠራው ያዕቆብ ነበር፡፡
 
በእርሱ ዕቅድ ውስጥ ያለውን የእግዚአብሄር ጽድቅ ማወቅና ማመን አለብን፡፡ ያዕቆብ የሚያመለክተው እግዚአብሄር በጽድቅ ውስጥ ምህረት ያደረገለትን ሐጢያተኛ ሲሆን ኤሳው የሚያመለክተው የእግዚአብሄርን የጽድቅ ፍቅር ችላ ብሎ የራሱን ጽድቅ የሚከተለውን ሰው ነው፡፡ ‹‹ከጠሪው›› የእግዚአብሄር አሳብ መጽናት በእርሱ ዕቅድ ውስጥ ያለውን ቅድመ ውሳኔ በሚመለከት የእግዚአብሄር ቃል የሚገልጠውን ቁልፍ መረዳት የሆነው ለዚህ ነው፡፡
 
በራሳችን አስተሳሰቦች ከተፈጠሩት ምናባዊ እምነቶች ራሳችንን ነጻ ማውጣት አለብን፡፡ እግዚአብሄር በራሱ ጽድቅ ውስጥ ያዕቆብን ብቻ ወድዶ ኤሳውን ጠልቷል፡፡ እግዚአብሄር ስለ ዕቅዱና ቅድመ ውሳኔው የሰጠው ማብራሪያ የእግዚአብሄር አሳብ ‹‹ከጠሪው›› ዘንድ የጸና በመሆኑ እወጃ አማካይነት ለእያንዳንዱ ሰው ቀርቦዋል፡፡ እግዚአብሄር ያዕቆብን ሲወድድና ኤሳውን ሲጠላ የቅድመ ውሳኔው አላማ ለደህንነት ባለው ዕቅዱ መሰረት የእግዚአብሄርን ጽድቅ መፈጸም ነበር፡፡
 
ብዙ ሌሎች ሃይማኖቶች እንደሚሉት በእግዚአብሄር የተወደዳችሁትና የዳናችሁት በበጎ ምግባሮች አይደለም፡፡ ከሐጢያቶቻችሁ ድናችሁ የእርሱ ልጆች የምትሆኑት በዕቅዱና በጽድቁ ስታምኑ ብቻ ነው፡፡
        
 
እግዚአብሄር ተሳስቷልን? 
 
እግዚአብሄር በእርሱ ጽድቅ የሚያምኑትንና የሚወዱትን ይወድዳል፡፡ በሌላ አነጋገር አባታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ውስጥ ሆነው በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምኑትን ለመውደድና ልጆቹ ለማድረግ የመወሰኑ እውነታ ምንም ስህተት የለበትም፡፡ የእግዚአብሄር ዕቅድ እንደ ያዕቆብ ያሉ ሰዎችን መውደድ እንጂ ሁሉንም በኢየሱስ ክርስቶስ መውደድ አልነበረም፡፡
 
ስለዚህ ያዕቆብን ወይም ኤሳውን ሆነን እንደሆነ ራሳችንን መጠየቅ አለብን፡፡ ነገር ግን በራሳቸው በጎ ምግባሮችና በራሳቸው ጽድቅ የተሞሉ ሰዎችም ቢሆኑ በእግዚአብሄር መወደድ ይፈልጋሉ፡፡ ነገር ግን በተሳሳተው ጎዳና ላይ ከመሮጥ ሊያቆማቸው የሚችል ማንም የለም፡፡ ስለዚህ እነዚህ ሁለት አይነት ሰዎች አሁን እየተነጋገርን እንኳን በእግዚአብሄር ተወድደው ወይም ተጠልተው ሁልጊዜም ይኖራሉ፡፡
     
በእርሱ የጽድቅ ፍቅርና ለደህንነታችን ባለው ዕቅዱ በማመን እግዚአብሄርን ማመስገንና ክብሩን ማወደስ አለብን፡፡ የምናምንበት የውሃውና የመንፈሱ ወንገልም በሚገርም ሁኔታ የእግዚአብሄርን ጽድቅ የሚያንጸባርቅ ስለመሆኑ እውነታም እግዚአብሄርን ልናመሰግነው ይገባናል፡፡ ሰው የእግዚአብሄርን ፍቅር ለመልበስ በመጀመሪያ በእግዚአብሄር ፊት ድካሞቹን ማወቅና በእርሱ ጽድቅ ማመን እንዳለበትም መረዳት ይገባዋል፡፡
 
ችግሩ ብዙ ክርስቲያኖች የእግዚአብሄርን ጽድቅ በፈጸመው የኢየሱስ ጥምቀትና የመስቀሉ እውነት ማመን ባለመቻላቸው እግዚአብሄር የተወሰኑ ሰዎችን እንደሚወድና ሌሎችን ግን እንደተዋቸው በተሳሳተ መንገድ የሚያምኑ መሆናቸው ነው፡፡
 
በጣም አስቸጋሪው ደግሞ የዚህ ዓይነቱ ትክክለኛ ያልሆነ እምነት እየገነነ መሄዱና በታላቅ አመኔታም ለሌሎች መሰበኩ ነው፡፡ በፍጥነት እየተሰራጨ ነው፡፡ እግዚአብሄር ባቀደው ዕቅዱ መሰረት በቅድመ ውሳኔው የተገለጠውን የእግዚአብሄር ፍቅር በተሳሳተ መንገድ የተረዱ ብዙ ሰዎችን ማፍራቱ ነው፡፡ እግዚአብሄር በያዕቆብና በኤሳው ታሪክ ሊያሳየን የፈለገው ነገር ቢኖር የእርሱ ልጆች ለመሆን የሚያስፈልገው የሰው ጽድቅ ሳይሆን በዕቅዱ መሰረት አስድሞ የተወሰነውን የእግዚአብሄር ጽድቅ ፍቅር በማመን ብቻ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር ለአብርሃም ቃል የገባለትን ልጅ ለሳራ እንደሰጣት መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል፡፡ ዛሬም ቢሆን የእርሱ ልጆች መሆን የሚችሉት በእግዚአብሄር ጽድቅ ፍቅርና ቃል እምነት ያላቸው ሰዎች ብቻ እንደሆኑ ይህ ይነግረናል፡፡ እንዲህ ዓይነት ልጆች ለመሆን በእግዚአብሄር ጽድቅና በዕቅዱ ባለን እምነት የተሰጠውን እውነት መረዳት ይኖርብናል፡፡ በዚህ እውነት ለማመንም በእግዚአብሄር ፍቅርና ጽድቅ ማመን አለብን፡፡
 
ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ ያለው ፍቅር፣ እግዚአብሄር ለእኛ ያለው ዕቅድ፣ ለሁላችንም የተሰጠው ፍጹም እውነትና ፍቅር ነው፡፡ ኢየሱስ እኛን ለማዳን በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወስዶ በመስቀል ላይ ሞተ፡፡ በእርሱ ለምናምነውም የዘላለምን ሕይወት ሊሰጠን ከሙታን ተነሳ፡፡
         
ይህ እውነት ሃይማኖተኛ በመሆንና የራሳችንን ጥረቶች በማሳየት የእግዚአብሄር ልጆች እንሆናለን ማለት ሳይሆን የእግዚአብሄር ልጆች ለመሆን ብቸኛው መንገድ እርሱ በነገረንና ባቀደልን የእግዚአብሄር ጽድቅ ቃለ ፍቅር በማመን ነው ማለት ነው፡፡ የእርሱን ፍቅር የለበሱት በእግዚአብሄር ፍቅርና ጽድቅ የሚያምኑ ሰዎች ብቻ መሆናቸውን መረዳት አለብን፡፡
 
ታዲያ ባህሪያችን ምን መሆን ይኖርበታል? በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀሉ ደም ማመን ነው፡፡ እግዚአብሄር እንዲምረን ልንጠይቀው ይገባናል፡፡ ሁላችንም ሐጢያተኞች ስለሆንን በፊቱ የእርሱ ሕዝብ ተብለን መጠራት እንደማይገባን መገንዘብ አለብን፡፡ የእርሱ ልጆች መሆን የምንችለው እርሱ ለእኛ ባለው ዕቅድ  -- የእርሱን የጽድቅ ፍቅር እናውቅ ዘንድ -- ብቻ መሆኑን መረዳት አለብን፡፡
 
በእግዚአብሄር የተጠሉ ሰዎች የተጠሉት የእርሱ ፍቅርና ጽድቅ ስለማያስፈልጋቸውና ስለማያምኑበትም ነው፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር አስቀድሞ ለእኛ የወሰነውን የፍቅር ዕቅዱን የሚያውቁና የሚያምኑ ሰዎች በእርሱ ሲወደዱ የእርሱን ፍቅር የሚንቁና የሚክዱ ደግሞ በእግዚአብሄር ይጠላሉ፡፡
    
 
የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል የሚያምኑ እነማን ናቸው? 
 
እግዚአብሄር የሰጠን የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል የእርሱን ጽድቅ የሚገልጥ ብቸኛው እውነት ነው፡፡ ታዲያ ይህንን በልባቸው የሚቀበሉ ሰዎች ምን ዓይነት ሰዎች ናቸው? እነዚህ ዕጣ ፈንታዎቻቸው በዘላለም ጥፋት ላይ ያረፉና በእግዚአብሄርና በቃሉ ፊትም ሐጢያተኞች መሆናቸውን በመረዳት የእርሱን ምህረት የሚለምኑ ሰዎች ናቸው፡፡ ‹‹አቤቱ እኔ ፈጽሞ በሕጎችህ መኖር የማልችል ሐጢያተኛ ነኝ፡፡ ልቤን ለአንተ ሰጥቼ አሰረክቤያለሁ፡፡›› እግዚአብሄር በጽድቁ የፍቅሩን የሐጢያቶች ስርየት የሰጣቸው ሰዎች እነዚህ ናቸው፡፡ የእግዚአብሄርን ጽድቅ በሚገልጠው ወንጌል ማመን ለሐጢያተኞች ሁሉ ታላቅ ጠቀሜታ አለው፡፡
እግዚአብሄር ሕጉን የሰጠን እያንዳንዱን ሐረግ እንድንታዘዝ አይደለም፡፡ ይህ እውነት በብዙዎች ዘንድ በተሳሳተ መንገድ ተስተውሎዋል፡፡ በፋንታው የሕጉ ዓላማ የእኛን ሐጢያተኝነት ወደ መረዳት መምራት ነው፡፡ ታዲያ ሐጢያተኞች ሕጉን ለመከተል የሚሞክሩት ለምንድነው? ምክንያቱም የእያንዳንዱ ሐጢያተኛ ደመ ነፍስ ከሐጢያቶቹ መዳንና መንጻት ስለሚፈልግ ነው፡፡
         
ነገር ግን ማንም ሕጎቹን በሙሉ መታዘዝ አይችልም፡፡ ሙከራዎቹ ሐጢያቶቻቸውን በአልሞት ባይ ተጋዳይነት ለመሸፈን የሚደረጉ ደመነፍሳዊ ማስመሰያዎችና ተራ ማታለያዎች ናቸው፡፡ ይህ በእግዚአብሄር ፊት አስመሳይ እምነት ነው፡፡ ሐጢያተኞች ይህን አታላይ እምነት አስወግደው የእግዚአብሄርን ጽድቅ ወደ ማመን መመለስና ፍቅሩን መልበስ የሚገባቸው ለዚህ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር ይህንን ፍቅር ሊያለብሰን በዮሐንስ ተጠምቆ የዓለምን ሐጢያቶች በጫንቃው ላይ በመሸከምና በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰስ ሐጢያቶችን በሙሉ እንዲደመስስ ኢየሱስን ወደ ምድር ላከው፡፡ እፍዚአብሄር በእርሱ የጽድቅ ፍቅር የሚያምኑትን ሰዎች እምነት አውቆዋል፡፡ የእግዚአብሄር ጽድቅ ፍጸሜ በሆነው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል በማመን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ በዳንን ጊዜ የእርሱን ፍቅር ለብሰናል፡፡ እግዚአብሄር በዕቅዱ ውስጥ ያስቀመጠው የተስፋው እውነት ይህ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር በራሳቸው ላይ ብቻ የሚደገፉትን ሰዎች ይጠላል፡፡ እነዚህን የመሰሉ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ እናንተ ግን የእግዚአብሄርን ፍቅርና ጽድቅ በፈጸመው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል በበማመን ከሐጢያቶቻችሁ ሁሉ መዳን አለባችሁ፡፡ ያን ጊዜ እርሱ ለሚጠራቸው ተጠብቆ የቆየውን የእርሱን ፍቅር በእርግጥ ትለብሳላችሁ፡፡ ሰዎች የእግዚአብሄርን ፍቅርና ይቅርታ ለማግኘት ብዙውን ጊዜ ነገሮችን በራሳቸው ለማድረግ ይሞክራሉ፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ጽድቅ ምንም እምነት ሳይኖር እነዚህ ጥረቶች ከንቱዎች ናቸው፡፡
       
እግዚአብሄር ፍቅሩን ያለብሰው ዘንድ የጠራው ያዕቆብን እንጂ ኤሳውን አይደለም፡፡ ያዕቆብ በእግዚአብሄር ፊት ብልጣ ብልጥ፣ ተንኮለኛና ውሸታም ነበር፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ፍቅርና ጽድቅ በማመኑ ከእምነት አባቶች አንዱ ሆነ፡፡ እኛም እንደዚሁ ለመዳናችን የእግዚአብሄር ጽድቅ ፍጻሜ በሆነው የኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ በማመን የእግዚአብሄርን ፍቅር መቀበል መቀበል አለብን፡፡ ኤሳው በራሱ አደን ከአባቱ በረከትን ለማግኘት ስለሞከረ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ማግኘት ለማይችሉት ሰዎች ምሳሌ ሆነ፡፡ ይህንን ጉዳይ በጥንቃቄ ለማሰብ የተወሰነ ጊዜ መውሰድ ያስፈልገናል፡፡ በዚህ ዓለም ላይ ኤሳውን የሚመስል ማነው? እኛስ እንደ እርሱ አይደለንምን?
 
እንደ ያዕቆብ ያሉ ሰዎች የእግዚአብሄርን የጽድቅ ፍቅር የተቀበሉ ናቸው፡፡ እኛም ልክ እንደ ያዕቆብ ደካሞችና ክፉዎች ነን፡፡ በሥራችን ሳይሆን በእርሱ ጥሪ ለመጽናት ከመወለዳችን በፊት የጠራን እግዚአብሄር የእርሱን ፍቅር ለመቀበል በፍቅሩና በጽድቁ እንድናምን ነግሮናል፡፡ እግዚአብሄር በዕቅዱ ውስጥ የእግዚአብሄርን ጽድቅ የፈጸመውን ኢየሱስን ስለ ሁላችን ላከው፡፡
እግዚአብሄር በመጀመሪያ ሲጠራን ጻድቃንን ሳይሆን ሐጢያተኞችን ለመጥራት መጣ፡፡ እግዚአብሄር የሚጠላቸው በራሳቸው ጽድቅ እንደተሞሉ የሚያስቡትንና በእርሱ የምህረት ፍቅር የማያምኑትን ነው፡፡ እግዚአብሄር በልቡ ይህንን እውነት አስቀድሞ ወሰነ፡፡ ስለዚህ በግልጽ እንዲህ አለ፡- ‹‹እንግዲህ ምን እንላለን? በእግዚአብሄር ዘንድ ዓመጻ አለ ወይ? አይደለም!›› (ሮሜ 9፡14)
     
 
እንደ ያዕቆብ ያሉ ሰዎች በእግዚአብሄር የተወደዱ ናቸው፡፡
 
እግዚአብሄር ሲመለከታችሁ በእርግጥ ምህረትን የሚያደርግላችሁ ዓይነት ሰዎች ናችሁን? እግዚአብሄር የሚራራለትን ሊራራለት የሚጠላውንም ሊጠላ የፈለገበት ምክንያት ምንድነው? እግዚአብሄር እንዴት በድሎናል እንላለን?
 
በዚህ ምድር ላይ እጅግ ብዙ ሰዎች ይኖራሉ፡፡ አንዳንዶቹ በእግዚአብሄር የተወደዱ ሲሆኑ ሌሎቹ ግን አይደሉም፡፡ ይህ ማለት እግዚአብሄር በድሎዋቸዋል ማት ነውን?
 
እግዚአብሄር በእርሱ ጽድቅ ላይ የተነሱትን ሰዎች ሐጢያቶች የሚኮንን ቅን አምላክ ነው፡፡ በእርሱ ጽድቅ ውስጥ የተገለጠውን የእግዚአብሄር ዕቅድ በእምነት በመረዳት በዚህ ጉዳይ ላይ የተሳሳቱ መረዳቶችን ማስወገድ አለብን፡፡ ልባቸው ልክ እንደ ፈርዖን የደነደነ ብዙ የተሳሳቱ ክርስቲያኖች አሉ፡፡ ይህ ምዕራፍ በቁጥር 17 ላይ እንደሚያብራራው የዚህ ዓይነት ሰዎች በእግዚአብሄር የተጠሉ ናቸው፡፡ ‹‹መጽሐፍ ፈርዖንን ሐይሌን በአንተ አሳይ ዘንድ ስሜም በምድር ሁሉ ይነገር ዘንድ ለዚህ አስነሳሁህ ይላልና፡፡››
 
ሁላችንም በእግዚአብሄር ፊት ብቃት ያለን አይደለንም፡፡ ስለዚህ እንደ ፈርዖን መሆን የለብንም፡፡ እግዚአብሄር እንደ ፈርዖን ደንዳኖች የሆንነውን ሰዎች ለደህንነታችን ስንል በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ባለማመናችን ሊጠላን ይገባል? አዎ፤ እንደ ፈርዖን ያሉ ሰዎች እግዚአብሄርን የሚቃወሙ ናቸው፡፡ እንደ እነዚህ ያሉ ሰዎች በራሳቸው ጽድቅ ይመካሉ፤ ይደገፉማል፡፡ የራሳቸው ጽድቅ ግን ከሐጢያቶቻቸው ሊያድናቸው አይችልም፡፡
 
ፈርዖን በምን ላይ ተደገፈ? በናይል ወንዝ ታመነ፤ ተደገፈም፡፡ የተትረፈረፈ የውሃ አቅርቦት እስካለው ድረስ ሁሉም ነገር ጥሩ ይሆናል፡፡ እግዚአብሄር እንደ ፈርዖን ያሉ ሰዎችን የሚጠላው ለዚህ ነው፡፡ ልቡ ልክ እንደ ፈርዖን ልብ የደነደነ ማንኛውም ሰው በእግዚአብሄር ይጠላል፤ ይኮነንማል፡፡ እርሱን መምሰል አይገባችሁም፡፡ እግዚአብሄር በነጻ የሰጣችሁን የምህረት ፍቅር በመቀበል የእርሱ ልጆች መሆን ትችላላችሁ፡፡
     
 
ከእግዚአብሄር የጽድቅ ዕቅድ ጋር በደስታ ትስማማላችሁን? 
 
ልባችሁ በእርሱ ዕቅድ ውስጥ አስቀድሞ የተወሰነላችሁን የእግዚአብሄር የጽድቅ ፍቅር ለመቀበል ተዘጋጅቷልን? በኢየሱስ ቢያምኑም የእግዚአብሄርን ዕቅድ በተሳሳተ መንድ በመረዳታቸው ምክንያት የሚሰቃዩ አንዳንድ ሰዎች አሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች ‹‹በኢየሱስ አምናለሁ፤ ነገር ግን እግዚአብሄር በእርግጥ አልመረጠኝምን? ካልመረጠኝ እምነቴ ምን ጥቅም አለው? ታዲያ ምን ማድረግ ይገባኛል? በኢየሱስ ማመኔን ማቆም አልችልም፡፡ ምን ላድርግ? ከልቤ በኢየሱስ አምናለሁ፡፡ ነገር ግን በእርሱ ምርጫ ውስጥ ከሌለሁ ምን ይፈጠራል?›› በማለት ይጨነቃሉ፡፡ 
‹‹በኢየሱስ ስለማምንና በቤተክርስቲያን አገልግሎቶች ላይ ስለምገኝ እግዚአብሄር የመረጠኝ መሆን አለበት፡፡ በእርግጥ ነገሩ እንደዚያ ነው፡፡ ሰማይ በእርግጥም መርጦኛል!›› ብለው ራሳቸውን ለማጽናናት ይሞክራሉ፡፡ በሐጢያት ሲወድቁ ግን ‹‹እግዚአብሄር አልመረጠኝም ማለት ነው! አሁን በኢየሱስ ማመኔን የማቆምበት ጊዜ ይሆን ይሆናል!›› በማለት እንደገና ይታወካሉ፡፡ በሌላ አነጋገር በራሳቸው ያስባሉ፡፡ ሁሉንም ነገር በራሳቸው ይደመድማሉ፡፡ ሁሉንም ነገር በራሳቸው ይጨርሳሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች ስለ እግዚአብሄር ዕቅድ ያላቸውን መረዳት ደግመው ማሰብና ኢየሱስን አዳኛቸው አድርገው ለማመንም ወደ ትክክለኛ ግንዛቤ ላይ መድረስ ያስፈልጋቸዋል፡፡
 
በሌላ በኩል የእግዚአብሄርን ቃል ከማመን ይልቅ የሥነ መለኮት ምሁራንን ትምህርቶች አብዝተው የሚያምኑ ሰዎች ‹‹እግዚአብሄር ታላቁ ለታናሹ ይገዛል፡፡ ከመወለዳቸውም በፊት ያዕቆብን እንደወደደና ኤሳውን እንደጠላ አልተናገረምን? አሁን በኢየሱስ ስለምናምን ከመወለዳችን በፊትም ቢሆን ለመዳን የተወሰንን መሆን አለብን›› ይሉ ይሆናል፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ ግን በእግዚአብሄር የታቀደው ቅድመ ውሳኔ ‹‹ከሥራ ሳይሆን ከጠሪው ዘንድ ጸንቶ እንደሚቆም›› ይናገራል፡፡
 
ሕጉን መከተል ሰውን የእግዚአብሄር ልጅ አያደርገውም፡፡ እኛ የእርሱ ልጆች መሆን የምንችለው በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ በተገለጠው በእግዚአብሄር ጽድቅ በማመን ብቻ ነው፡፡
 
የሥነ መለኮት ምሁራኖች በደነገጉዋቸው ትምህርቶች ምክንያት ብዙ ሰዎች የእግዚአብሄር ጽድቅ መገለጫ የሆነውን የኢየሱስ ጥምቀትና ደሙን ደህንነታቸው አድርገው ማመን አልቻሉም፡፡ የእርሱን ጽድቅ የሚያሳየውን የወንጌሉን ፍቅር ሰምተው በእርሱ የማያምኑ ሰዎች ልክ እንደ ፈርዖን ናቸው፡፡ እግዚአብሄር በኢየሱስ ክርስቶስ በተገለጠው የእግዚአብሄር ጽድቅ ሳያምኑ በራሳቸው ፍላጎት መሰረት በኢየሱስ በማመን የእግዚአብሄር ልጆች ለመሆን የሚሞክሩ ሰዎችን ይጠላል፡፡
 
በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በተገለጠው የእግዚአብሄር የጽድቅ ፍቅር ካላመናችሁ ታምኑ ዘንድ ጊዜው አሁን ነው፡፡ ያን ጊዜ የእግዚአብሄርን ፍቅር ትለብሳላችሁ፡፡ ቀድሞ ሁላችንም ልክ እንደ ኤሳው ነበርን፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር የጽድቅ ፍቅር በማመን ከሐጢያቶቻችን በአንድ ጊዜ ዳንን፡፡ በእርሱ ጽድቅ በማመን የእግዚአብሄርን የተባረከ ፍቅር ተቀብለናል፡፡
 
እግዚአብሄር በእርሱ የጽድቅ ፍቅር ለሚያምኑ ልጆቹ የመሆንን በረከት እስራኤሎችን አህዛቦች እንዲያገኙት ፈቀዶዋል፡፡ እግዚአብሄር ‹‹ሕዝቤ ያልሆነውን ሕዝቤ ብዬ ያልተወደደችውንም የተወደደችው ብዬ እጠራለሁ›› ባለው መሰረት የኢየሱስን ጥምቀትና የደሙን ወንጌል በዚህ ለምናምነው ሰዎችም የጽድቅ ፍቅሩን ሰጥቶናል፡፡
 
‹‹እናንተ ሕዝቤ አይደላችሁም በተባለላቸውም ሥፍራ በዚያ የሕያው እግዚአብሄር ልጆች ተብለው ይጠራሉ ይላል›› የሚለው ይህ ምንባብ ዛሬ ለእኛ የተፈጸመ የእግዚአብሄር ፍቅር ቃል ነው፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ፊት ጎዶሎዎች ስለሆንን እግዚአብሄር ሥጋ ለብሶ በመምጣት እንዳዳነንና የጽድቁ ፍቅርም ለእኛ እንዲደርስ በማድረግ እንዳዳነን መረዳት እንችላለን፡፡
 
እናንተና እኔ በእግዚአብሄር ፊት ከሐጢያቶቻችን ሁሉ መዳናችን በእግዚአብሄር ጽድቅ ውስጥ የታቀደ የሚያድን ፍቅር ነው፡፡ ልባችንን ሳናደነድን በእግዚአብሄር ጽድቅ ፍቅር በማመን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ መዳናችን የተገኘው በእውነት በማመናችን ብቻ ነው፡፡ ከዚህ የእምነት መንገድ ውጪ የሐጢያቶችን ስርየት ለመቀበል የሚያስችል ሌላ መንገድ የለም፡፡ ሁላችንም የደነደነ ልብ ይዘን ተወልደናል፡፡ የእግዚአብሄር ቃል ግን ልባችንንና ድንዳኔያችንን ማሸነፍ ይችላል፡፡ ያን ጊዜ ልባችን በእግዚአብሄር ሰላም ይሞላል፡፡ በእግዚአብሄር ብታምኑ የእግዚአብሄር ጽድቅ የእናንተ ይሆናል፡፡
  
እኛ የምንሰብከውና የእግዚአብሄርን ጽድቅ የወንጌል እውነት ባይኖር ኖሮ በዚህ ዓለም ላይ የሚኖር እያንዳንዱ ሰው ይጠፋ ነበር፡፡ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል የሚያሰራጩ ሰዎች ባይኖሩ ኖሮ የሰው ዘር በሙሉ ያለ ተስፋ ይሆን ነበር፡፡ የእግዚአብሄርን የጽድቅ ፍቅር የለበሱ ሰዎች ባይኖሩ ኖሮ ዓለም ከዚህ ቀደም ጠፍቶ እያንዳንዱ ሰውም በሐጢያቶቹ ተኮንኖ ነበር፡፡ እግዚአብሄር ግን በጽድቁ ፍቅር የምናምነውን እኛን በዚህ ምድር ላይ አስቀረን፡፡ ብዙ ድክመቶችና ጉድለቶች እያሉብን በእኛ በኩል በመስራቱ እግዚአብሄርን እናመሰግነዋለን፡፡
 
የእግዚአብሄርን የጽድቅ ፍቅር የለበሰው እምነት ከኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ካፈሰሰው ደሙ ጽድቅ የተገኘ ነው፡፡ በእግዚአብሄር ጽድቅ የሚያምን እምን በኢየሱስ ጥምቀትና ደም በሚያምን ልብ ውስጥ ይገኛል፡፡ ከሐጢያቶቻችን የዳንነው በእርሱ ጽድቅ ባለን እምነት ነው፡፡ ይህ እውነት እግዚአብሄር ለእኛ ያስቀመጠው ዕቅድ፣ ቅድመ ውሳኔና ምርጫ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል የእርሱን ጽድቅ በሚፈጽመው የአምላክ ቃል የሚያምን ሁሉ ከሐጢያቶቹ እንደሚያድን ተናግሮዋል፡፡ ሰው የሚጠፋው የእግዚአብሄር ጽድቅ ሐጢያቶቹን ስላሰወገደለት ሳይሆን ልቡ በመደንደኑ በዚያ ስላላመነ ነው፡፡
 
ልባችንን በእግዚአብሄር ቃል ፊት ትሁት ማድረግና በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ማመን አለብን፡፡ ልባችን በእርሱ ፊት መንበርከክ አለበት፡፡ እኛ በእግዚአብሄር የጽድቅ ፍቅር በማመን ተባርከናል፡፡ በብዙ ምህረትን ስላደረገልን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ድነናል፡፡ እኛ በእግዚአብሄር ጽድቅ የምናምን ሰዎች የምናፍርበት ምንም ነገር የለም፡፡ በተቃራኒው በእርሱ ጽድቅ የምንኮራበት በቂ ምክንያት አለን፡፡
 
እግዚአብሄር ሙሉ በሙሉ ከሐጢያቶቻችን ያዳነን በፊቱ ጉድለት ያለብን ሰዎች ሆነን ስለቀረብን ነው፡፡ ለዚህ ደህንነት ጌታ የተመሰገነ ይሁን! በእግዚአብሄር ለመወደድ በእርሱ ጽድቅ ማመን መቻል አለብን፡፡
 
ይህንን የእግዚአብሄር ጽድቅ ታውቁታላችሁን? ካወቃችሁት እመኑበት፡፡ ያን ጊዜ የእግዚአብሄር የጽድቅ ፍቅር ወደ ልባችሁ ይመጣል፡፡ እርሱ ለእናንተ ባቀደላችሁ የእግዚአብሄር የጽድቅ ፍቅር ላይ ያላችሁ እምነት ከተሳሳተ መረዳት ነጻ ይሁን፡፡
 
እግዚአብሄር ለእናንተ ያስቀመጠው የደህንነት ፍቅር ወደ ልባችሁ ይግባ፡፡ ሃሌሉያ! በጽድቁ ልጆቹ ላደረገልን ስላሴ አምላክ ምስጋናን አቀርባለሁ፡፡