Search

ስብከቶች፤

ርዕስ 11፡ የመገናኛው ድንኳን

[11-7] የእምነትን መሠረት የጣሉት የመገናኛው ድንኳን የግንባታ ቁሶች:: ‹‹ ዘጸዓት 25፡1-9 ››

የእምነትን መሠረት የጣሉት የመገናኛው ድንኳን የግንባታ ቁሶች::
‹‹ ዘጸዓት 25፡1-9 ››
‹‹እግዚአብሄርም ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው፡- ስጦታ ያመጡልኝ ዘንድ ለእስራኤል ልጆች ተናገር፡፡ በገዛ እጁ ሊሰጠኝ በልቡ ከሚያምረው ሰው ሁሉ መባ ተቀበሉ፡፡ ከእነርሱም የምትቀበሉት መባ ይህ ነው፡፡ ወርቅ፣ ብር፣ ናስም፣ ሰማያዊና፣ ሐምራዊ፣ ቀይም ግምጃ፣ ጥሩ በፍታም፣ የፍየልም ጠጉር፣ ቀይ የአውራ በግ ቁርበት፣ የአቆስጣ ቁርበት፣ የግራርም እንጨት፣ የመብራትም ዘይት፣ ለቅብዓት ዘይትና ለጣፋጭ ዕጣን ቅመም፣ መረግድም፣ ለኤፉድና ለደረት ኪስ የሚደረግ ፈርጥ፡፡ በመካከላቸውም አድር ዘንድ መቅደስ ይስሩልኝ፡፡ እኔ እንደማሳይህ ሁሉ እንደ ማደሪያው ምሳሌ እንደ ዕቃውም ሁሉ ምሳሌ እንዲሁ ስሩት፡፡›› 
 
የመገናኛው ድንኳን
 
ምስኪን ሕይወቶች፡፡ 
 
‹‹የሕይወት ማህሌት›› በሚለው ሥነ ግጥሙ ሔነሪ ዋድስዎርዝ ሎንግፌሎው እንዲህ ሲል ጽፎዋል፡- ‹‹ሕይወት ባዶ ሕልም ነው ብላችሁ በሚያሳዝን ቃና አትንገሩኝ!›› 
 
ነገር ግን ስለዚህ ጉዳይ በእርግጥ የምታስቡ ከሆነ የሰብዓዊ ፍጡራን ሕይወት በእርግጥም አሳዛኝ ነው፡፡ የሰው ሁሉ ሕይወት በዚህ ዓለም ምድረ በዳ ላይ በብቸኝነትና በጊዜያዊነት ከኖረ በኋላ በከንቱ ወደ አፈር የሚመለስ ቢመስልም የመጨረሻው መዳረሻ ምድር አይደለም፡፡ የእያንዳንዱ ሰው ሕይወት የመጨረሻ ፍጻሜ በሐጢያት ምክንያት ዘላለማዊና አስፈሪ የሲዖል መከራ ነው፡፡ 
 
ሆኖም ሰዎች ስለ ሞታቸውና ከመቃብር ወዲያ ስላለው ሕይወት ብዙውን ጊዜ ግድ የላቸውም፡፡ ሰዎች በዚህም ምድር ላይ ሲኖሩ ያለ ምንም ዓላማ እንዲሁ እየኖሩ ያዳናቸውን አምላክ ሳይገናኙ ወደ ሲዖል ይነጉዳሉ፡፡ ሕይወት ይህ ነው፡፡ ሕይወት ማለት በእርግጥም ይህ ከሆነ ምንኛ ምስኪንና አሳዛኞች በሆንን ነበር?
 
መሲሁ እንደዚህ ያሉ ሕይወቶችን ይጠብቃል፡፡ ሰዎች ያለ ዓለም እንዲንጠራወዙና በጨለማ ውስጥ እንዲጠፉ በግድ የለሽነት ወደዚህ ክፍት ዓለም የተወረወሩ ከሆኑ በእርግጥም እየኖሩ ያሉት አሳዛኝና ምስኪን ሕይወት ነው፡፡ በዙሪያችን ያለውን በመመልከት ብቻ ሁላችንም ይህንን መረዳት እንችላለን፡፡ እነርሱ ብዙዎቹ በሕይወታቸው ውስጥ ብዙ ችግሮች ስለገጠሙዋቸው ቆም ለማለትና መለስ ብለው ወዴት ሲጓዙ እንደነበር ለማየት ዕድሉ እንኳን የላቸውም፡፡ ወላጆች ሁሉ ለልጆቻቸውና ለቤተሰባቸው እየኖሩ ቢለፉም ሐዘናቸውን የሚገልጡ ቃሎች ግን አይገኙም፡፡ የጸሐይ ግባታቸው ሲቃረብ በሕይወታቸው ውስጥ የሚቀር ምንም ነገር የለም፡፡ 
 
በዕንባ ይጥለቀለቃሉ፡፡ ብዙ ዘመን ካለፈና እነርሱም በመጨረሻ መለስ ብለው ወደኋላ የመመልከት ዕድል አግኝተው እንደዚያ ሲያደርጉ የሚሰማቸው ስሜት ቢኖር በቅርቡ የሆነው ይህ አውዳሚ ውድቀት ትዝታቸውን ይቀሰቅስባቸዋል፡፡ ከውድቀቱ ጋር ቅጠሎቹም በሙሉ ሲረግፉና አሰልቺውን ክረምት ሲጋፈጡ ሕይወታቸውም እንደዚሁ ፈጥኖ በዚህ መንገድ እንደሚከስም ይገነዘባሉ፡፡ ይህንን ለመረዳት ረጅም ጊዜ ስለፈጀባቸው ማዘናቸው አይቀርም፡፡ እነዚህ ሰዎች ጌታን ሳይገናኙ ወደ ሞት ተቃርበው ሳለ ምን ተስፋ አላቸው? መሲሁን ሳይገናኙ ወደ ሕይወታቸው ፍጻሜ የመጡ የዚህ ዓይነት ሰዎች ለዘላለም ምስኪኖች ናቸው፡፡ 
 
እኔም ራሴ ከጌታ ጋር ባልገናኝ ኖሮ አሳዛኝ ሕይወትን እኖር ነበር፡፡ እናንተስ? ጌታን ባትገናኙት ኖሮ መድረሻችሁ የት ይሆን ነበር? ዛሬ ሰዎች በዚህ ዓለም ላይ ጌታን መገናኘት ባለመቻላቸው ምክንያት ሐዘንተኞች ሆነዋል፡፡ 
 
ስለ እነዚህ ሰዎች ሳስብ ልቤ ይሰበራል፡፡ በጣም ብዙ ሰዎች በሐዘን ውስጥ ይኖራሉ፡፡ አሳሞች ወደ ፍጻሜያቸው እስኪመጡ ድረስ ራሳቸውን ይመግባሉ፡፡ የእኛ ሕይወት ግን ከእነዚህ አሳሞች የተለየ ነው፡፡ እኛ የአሁኑን ትተን የወደፊቱን ማሰብና መመልከት አለብን፡፡ ብዙ ሰዎች የመጨረሻ ቀኖቻቸውን የሚጋፈጡት በጸጸት ተሞልተው ነው፡፡ ዘላለማዊ የሆነ መንግሥተ ሰማይ እንዳለ ቢያውቁም ወደዚያ ለመግባት ብቃት የላቸውም፡፡ ምክንያቱም ሐጢያተኞች ሆነው ቀርተዋልና፡፡ በዚህ ዓይነት ጸጸት የተሞሉ ብዙ ሰዎች መኖራቸውን ማወቄ አሳዛኝ ስለሆነው ዕጣ ፈንታቸው እንዳለቅስ ያደርገኛል፡፡ 
 
እነዚህ ሕይወቶች በእግዚአብሄር ወደተዘጋጀው ጥሩ ስፍራ መሄድ እንደማይችሉና የሕይወታቸውን እውነተኛ ዓላማ ሳይፈጽሙም ከዚህ ዓለም እንደሚሰናበቱ ስናስብ ለዕጣ ፈንታቸው እናለቅሳለን፡፡ ሕይወት ብዙውን ጊዜ አዳጋችና አስቸጋሪ በሆነ ውቅያኖስ ላይ ከመጓዝ ጋር የሚመሳሰለው ለዚህ ነው፡፡ ሰዎች ሕይወትን ሲመለከቱ በሰብዓዊ ዓለም ምሬት ውስጥ በሕይወት ለመቆየት በመሞከር እንደዚህ ባለ ውቅያኖስ ውስጥ መኖርን ይመስላል ይላሉ፡፡ ምክንያቱም ከውልደታቸው አንስቶ እስከ ሞታቸው ድረስ ለመኖር ሲሉ እየተወራጩና እየጮሁ መሰቃየት አለባቸውና፡ 
 
ሕይወት ማለት ይህ እንደሆነ ራሳችንን ስናስታውስ የዚህን የመገናኛውን ድንኳን እውነት ለሰዎች ሁሉ ማብራራትና ጌታን እንዲገናኙ መርዳት ወሳኝ ጠቀሜታ ያላቸው ሥራዎች መሆናቸውን በእርግጠኝነት እንገነዘባለን፡፡ ለምን? ምክንያቱም እግዚአብሄር በመስዋዕቱ ጠቦት አማካይነት እነዚህን ሐጢያተኛ ሰዎች በራሱ በአምላክ ቤት ተገናኝቶዋቸው ከሐጢያቶቻቸው አድኖዋቸዋልና፡፡ የመገናኛው ድንኳን በምድረ በዳ የተሰራ የእግዚአብሄር ቤት ነው፡፡ በዚህ የእግዚአብሄር ቤት በሆነው የመገናኛው ድንኳን ውስጥ እግዚአብሄር በመስዋዕቱ ቁርባን በተፈጸመው የሐጢያት ስርየት ጸጋ አማካይነት ሐጢያተኛውን ይገናኘዋል፡፡ እግዚአብሄር እንዲህ ነግሮናል፡- ‹‹እኔ የማድርበትን ቤቴን እንድትሰሩ አደርጋችኋለሁ፡፡ በዚህ የመገናኛው ድንኳን ውስጥ በስርየት መክደኛው ላይም እገናኛችኋለሁ፡፡›› ለማንኛውም ሰው እግዚአብሄርን የመገናኘት ዕድል የሚሰጠው የእግዚአብሄር ቤት በሆነው በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ብቻ ነው፡፡ 
 
በመገናኛው ድንኳን እውነት ላይ ያለው ይህ እምነት በዚህ ዓለም ላይ ባለ በማንኛውም ነገር ሊለወጥ አይችልም፡፡ በማናቸውም ዋጋ ሊገዛ የማይችል እጅግ የከበረ ነገር ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ አዳኛችን መሆኑን የሚያምን የክርስቲያን እምነት ላለን ለእኛ ይበልጥ የተባረከ በሆነው መንገድ ላይ እንድንራመድ የሚያስችለን ስለ መገናኛው ድንኳን ትክክለኛ ዕውቀትና ተገቢ የሆነ እምነት ሲኖረን ነው፡፡ 
 
 
የተባረከውን ሕይወታችንን እየኖርን ነው፡፡ 
 
ልቤ አሁን እኛ እየኖርን ያለነውን የተባረከ ሕይወት እየኖረ ያለ ሌላ ሰው ይኖር እንደሆነ በማሰብ በሐሴት ተሞልቷል፡፡ ሕይወት አሳዛኝ ኑሮ ቢሆንም ብዙ ሰዎች ዕጣ ፈንታቸውን ሙሉ በሙሉ ሳያውቁ መኖራቸውን ቀጥለዋል፡፡ እግዚአብሄር ግን በእርሱ ፊት ሕይወታቸው ምን ያህል ቀልድ እንደሆነ እንዲገነዘቡና በልባቸው ንስሐ እንዲገቡ ይፈልጋል፡፡ በሌላ በኩል እነርሱ አሁንም እግዚአብሄር በነጻ የሰጣቸውን ሳያዳምጡና በልባቸውም ውስጥ ኢምንት ስፍራ እንኳን ሳይሰጡ ለመኖር እየሞከሩ ነው፡፡ 
 
ዘጸዓት እግዚአብሄር በፈርዖን ላይ ስላወረዳቸው አስር መቅሰፍቶች ይነግረናል፡፡ በግብጽ ምድር ላይ በጠቅላላው አስር መቅሰፍቶች ወረዱ፡፡ እግዚአብሄር ፈርዖንን የማይታዘዘው ከሆነ አስር መቅሰፍቶችን እንደሚያወርድበት ነገረው፡፡ ፈርዖን ግን እግዚአብሄር የነገረውን አልሰማም፡፡ በግትርነት የእርሱን ትዕዛዝ ተቃወመ፡፡ በመጨረሻም እግዚአብሄር የተናገረውን አስር መቅሰፍቶች በሙሉ ተቀበለ፡፡ ይህ የፈርዖን ግትርነት ድድብና ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ቅጣቶች ሁሉ ከተቀበለ በኋላ በመጨረሻ የእስራኤልን ሕዝብ የለቀቀው በሰይጣን ቁጥጥር ስር ስለወደቀ ነበር፡፡ ይህም በእያዳንዳችን ውስጥ የሚገኘውን የተሳሳተ ራስ ወዳድነታችንን የሚጠቁም ነው፡፡ 
 
ነገር ግን እንደዚህ ዓይነት ሰዎች በእግዚአብሄር በኩል በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የተቀመጠውን የሐጢያት ስርየት መቀበልና ከእርሱ ጋር በእምነት መኖር ይችላሉ፡፡ ሆኖም እነዚህ ሰዎች በጣም ግትሮች ስለሆኑ እንደ አህያ ባለ ግትርነት የእግዚአብሄርን እውነት በመናቅና ባለማመን ቀጥለዋል፡፡ ከእውነት አምላክ ጋር መገናኘት የተሳናቸው ሐጢያተኞች ሆነው የሚኖሩና በመጨረሻም የሚጠፉ ብዙ ሰዎች ያሉት ለዚህ ነው፡፡ ይህ እጅጉን ያሳዝነኛል፡፡ እጅግ ብዙ ሰዎች በእግዚአብሄር ፊት በጣም ግትሮች ናቸው፡፡ 
 
እነዚህ ሰዎች መከራ ሲገጥማቸው ለጥቂት ጊዜ እጃቸውን ቢሰጡም ነገር ግን የእግዚአብሄርን ፈቃድ በመናቅና ራስ ወዳድ መንገዶቻቸውን እንደገና በመጀመር ቀድሞ ወደነበሩበት ስፍራ ስለሚመለሱ ሁለተኛውን መቅሰፍታቸውን ይቀበላሉ፡፡ በዚህ በሁለተኛው መቅሰፍት በጥቂቱም ቢሆን እጃቸውን ይሰጣሉ፡፡ ይህ ግን ዘለቄታ የለውም፡፡ እንደገና በእግዚአብሄር ላይ ማመጽና እርሱን መቃወም ይጀምራሉ፡፡ ስለዚህ ሦስተኛው መቅሰፍት ይመጣባቸዋል፡፡ ከዚያም አራተኛው፣ አምስተኛው፣ ስድስተኛው፣ ሰባተኛው፣ ስምንተኛው፣ ዘጠነኛው መቅሰፍቶች ይከተላሉ፡፡ በመጨረሻም ከአስረኛው መቅሰፍት በኋላ እጃቸውን ይሰጡና ይጠፋሉ፡፡ 
 
የመጨረሻው መቅሰፍት ሲመጣ መሲሁ ለእነርሱ ያደረገላቸውን ባለማመናቸው የሲዖልን መከራ የሚቀበሉ ብዙ ሰዎች ይኖራሉ፡፡ የእነዚህ ሰዎች ሕይወት ምንኛ ገልቱ ነው? የሰው ሁሉ ሕይወት የሚያሳዝነው ለዚህ ነው፡፡ 
 
የሰዎች ሕይወት በእግዚአብሄር ፊት የሚያሳዝን ቢሆንም እግዚአብሄርን በመገናኛው ድንኳን ውስጥ መገናኘት ለእናንተ ታላቅ መሆኑን መገንዘብና በዚህ ግንዛቤ በመገናኛው ድንኳን ቃል መኖር አለባችሁ፡፡ 
 
 
እግዚአብሄር ከእኛ የሚጠይቃቸው መባዎች፡፡
 
እግዚአብሄር ሙሴን ወደ ሲና ተራራ እንዲወጣ አዘዘው፡፡ ሙሉውን የሕጉን ዝርዝርም ሰጠው፡፡ በመጀመሪያ ለሙሴ አስርቱን ትዕዛዛት ሰጠው፡፡ ‹‹በፊቴ ሌሎች አማልክት አይሁኑልህ፤ ስዕሎችን አታድርግ፤ አትስገድላቸውም፤ ስሜን በከንቱ አትጥራ፤ የሰንበትን ቀን ትቀድሰው ዘንድ አስብ፡፡ ወላጆችህን አክብር፡፡ አትግደል፤ አታመንዝር፤ አትስረቅ፤ በባልንጀራህ ላይ በሐሰት አትመስክር፡፡ አትመኝ፡፡›› በተጨማሪ እስራኤሎች በቀን ተቀን ሕይወታቸው ውስጥ የሚጠብቁዋቸውን ሌሎች ሕጎች ነገራቸው፡፡ በአጠቃላይ 613 የእግዚአብሄር ትዕዛዛትና ሕጎች ነበሩ፡፡ 
 
እነዚህ 613 ትዕዛዛቶች እስራኤላውያን ከብታቸው ሲጠፋ ምን እንደሚያደርጉ፣ የሌላ ሰው ከብት ጉድጓድ ውስጥ ቢወድቅ ምን እንደሚያደርጉ፣ እንዳያመነዝሩ፣ ባሮች ካሉዋቸው በሰባተኛው ዓመት ነጻ እንዲያወጡዋቸው፣ ሴት ገረድ ከነጠላ ወንድ ባርያ ጋር ተጋብታ ልጅ ቢወልዱ በሰባተኛው ዓመት ወንዱ ባርያ በፈቃዱ ነጻ መውጣት ከፈለገ ነጻ እንዲያወጡት ወ.ዘ.ረተፈ የሚያሳስቡ ጉዳዮች ነበሩ፡፡ እግዚአብሄር ለሙሴ እንደነገረው እስራኤሎች በቀን ተቀን ሕይወታቸው በእግዚአብሄር ፊት እነዚህን ሥነ ምግባራዊ ሕጎች በእምነት መጠበቅ ነበረባቸው፡፡ 
 
ከዚያም እግዚአብሄር ለሙሴ ከተራራው ወርዶ ሽማግሌዎችን እንዲሰበስብና የእርሱን ትዕዛዛቶች እንዲያውጅ ነገረው፡፡ የእስራኤል ሕዝብ የእግዚአብሄርን ቃል ከሰሙ በኋላ የእርሱን ትዕዛዛቶች በሙሉ እንደሚታዘዙ በደም መሐላ ማሉ፡፡ (ዘጸዓት 24፡1-4) 
 
ከዚያም እግዚአብሄር ሙሴን እንደገና ወደ ተራራው ጠራውና የመገናኛውን ድንኳን እንዲሰራ አዘዘው፡፡ 
 
እግዚአብሄር ለሙሴ ተናገረው፡- ‹‹እግዚአብሄርም ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው፡- ስጦታ ያመጡልኝ ዘንድ ለእስራኤል ልጆች ተናገር፡፡ በገዛ እጁ ሊሰጠኝ በልቡ ከሚያምረው ሰው ሁሉ መባ ተቀበሉ፡፡›› (ዘጸዓት 25፡2) ከዚያም መባውን ይዘረዝራል፡- ‹‹ከእነርሱም የምትቀበሉት መባ ይህ ነው፡፡ ወርቅ፣ ብር፣ ናስም፣ ሰማያዊና፣ ሐምራዊ፣ ቀይም ግምጃ፣ ጥሩ በፍታም፣ የፍየልም ጠጉር፣ ቀይ የአውራ በግ ቁርበት፣ የአቆስጣ ቁርበት፣ የግራርም እንጨት፣ የመብራትም ዘይት፣ ለቅብዓት ዘይትና ለጣፋጭ ዕጣን ቅመም፣ መረግድም፣ ለኤፉድና ለደረት ኪስ የሚደረግ ፈርጥ፡፡›› (ዘጸዓት 25፡3-7)
 
እግዚአብሄር እነዚህን መባዎች እንዲያመጡ ከነገራቸው ነገር በስተ ጀርባ ወሳኝ ዓላማ ነበር፡፡ ይህም ዓላማ የእስራኤልን ሕዝብ እዚያው ለመገናኘትና ሐጢያቶቻቸውን ለማስወገድ ሐጢያት የሌለበትንና እግዚአብሄር የሚያድርበትን የሚያበራ የአምላክ ቤት ለመገንባት ነበር፡፡ ነገር ግን ይህ ማለት እግዚአብሄር ልክ እንደ ዛሬዎቹ ቤተክርስቲያናት የመታሰቢያ ሕንጻ ለመገንባት ገንዘብ እንዲያመጡ ነግሮዋቸዋል ማለት አይደለም፡፡ የዘመኑ ክርስትና የሐሰት ነቢያቶች የራሳቸውን ፍትወት ለማርካት ብለው የቤተክርስቲያኖቻቸውን ሕንጻዎች ለመገንባት በሚሞክሩበት ጊዜ ይህንን ምንባብ በተሳሳተ መንገድ ወደ መጠቀም ያዘነብላሉ፡፡ 
 
በንጽጽር እግዚአብሄር ለእስራኤላውያን እነዚህን መባዎች እንዲያመጡለት የነገራቸው የራሱን ቤት ለመገንባት እንዲገለገልበትና እነርሱንም በዚያው ቤት ውስጥ አትረፍርፎ እንዲባርካቸው ነው፡፡ እንዲያውም እግዚአብሄር እነዚህን መባዎች የተቀበለው ከሐጢያቶቻችን ሊያድነንና ከኩነኔያችን ነጻ ሊያወጣን ነው፡፡ አሳዛኝ ሕይወት ስለምንኖር እግዚአብሄር ራሱ ሊገናኘን፣ ሐጢያቶቻችንን ሊያስወግድ፣ ሐጢያቶቻችንን ሊያከስምና የራሱ ሕዝብ ሊያደርገን ፈለገ፡፡ 
 
 
እግዚአብሄር እንዲቀርቡለት ያዘዛቸው መባዎች ያላቸው ስውር ትርጓሜ፡፡
 
ወደፊት ከመዝለቃችን በፊት እግዚአብሄር እንዲቀርቡለት ባዘዛቸው በእነዚህ መባዎች መንፈሳዊ ትርጉም ላይ በማሰላሰል የተወሰነ ጊዜ እንጠቀም፡፡ ከዚህ በኋላ በዚህ ብርሃን አማካይነት እምነታችንን እንመረምራለን፡፡ 
 
 
ወርቅ፣ ብርና ናስ፡፡ 
 
ከሁሉ በማስቀደም ወርቅ፣ ብርና ናስ የት ቦታ ጥቅም ላይ እንደዋሉ ማወቅ አለብን፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ወርቅ ለቅድስቱ ስፍራ፣ ለቅድስተ ቅዱሳኑና መቅረዙን፣ የሕብስቱን ገበታ፣ የዕጣኑን መሰውያ፣ የስርየት መክደኛውንና የምስክሩን ታቦት ጨምሮ በእነርሱ ውስጥ በሚገኙት ዕቃዎች ሁሉ ላይ ጥቅም ላይ ውሎዋል፡፡ ወርቅ በእግዚአብሄር ቃል ላይ ያለውን እምነት ያመለክታል፡፡ ብር የደህንነትን ጸጋ ያመለክታል፡፡ ይህም በመሲሁ ብቻ በተሰጠው የደህንነት ስጦታና ጌታችን ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወስዶ ስለ እኛ እንደተኮነነ የሚያምን እምነት ሊኖረን እንደሚገባ ይነግረናል፡፡ 
 
በንጽጽር ናስ ለመገናኛው ድንኳን ቋሚ ኩላቦች፣ ለካስማዎች፣ ለመታጠቢያው ሰንና ለሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ጥቅም ላይ ውሎዋል፡፡ ከናስ የተሰሩት ዕቃዎች በሙሉ በመሬት ውስጥ መጥለቅ ወይም መቀበር ነበረባቸው፡፡ ይህም የሰዎችን ሐጢያቶች ፍርድ ያመለክታል፡፡ ናስ እኛ የእግዚአብሄርን ሕግ መጠበቅ ስለተሳነንና ሐጢያቶችን ስለሰራን በእግዚአብሄር መኮነን እንደሚኖርብን ይነግረናል፡፡ 
 
ታዲያ የወርቁ፣ የብሩና የናሱ መንፈሳዊ ትርጉም ምንድነው? እነርሱ በእግዚአብሄር የተሰጠውን የደህንነት ስጦታ በመቀበል የእምነት መሰረቶችን ይጥላሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ሁላችንም ሕጉን ሙሉ በሙሉ መጠበቅ የማንችል ሐጢያተኞች እንደሆንንና በሐጢያቶቻችን ምክንያትም መሞት እንዳለብን ይነግረናል፡፡ በእኛ ሞት ፋንታ ጌታ ወደዚህ ምድር መጥቶ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የሚቀርበውን መስዋዕት ሆኖ በእኛ ምትክ ስለ ሐጢያቶቻችን ተኮነነ፡፡ 
 
ሐጢያተኞች የሐጢያቶቻቸውን ችግር ለማስወገድ ወደ መገናኛው ድንኳን ነውር የሌለበት እንስሳ በማምጣት በመስዋዕቱ ስርዓት መሰረት እጆቻቸውን በራሱ ላይ ጭነው ሐጢያቶቻቸውን ወደ እርሱ ያሻግራሉ፡፡ ከዚያም የእነርሱን ሐጢያቶች የተሸከመው መስዋዕት ይታረድና ደሙን ያፈስሳል፡፡ እንዲህ በማድረግ ለሲዖል የታጩት (ናስ) የእስራኤል ሕዝቦች የሐጢያቶቻቸውን ስርየት (ብር) ሊቀበሉና ከሐጢያት ኩነኔያቸው በእምነት (ወርቅ) ማምለጥ ይችሉ ነበር፡፡
 
 

ሰማያዊው፣ ሐምራዊው፣ ቀዩ ማግና ጥሩው በፍታ፡፡ 

ሰማያዊው፣ ሐምራዊው፣ ቀዩ ማግና ጥሩው በፍታ፡፡ 
 
አዘውትረው ጥቅም ላይ የዋሉት ቁሶች ሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግና ጥሩ በፍታ ነበሩ፡፡ እነዚህ ማጎች በመገናኛው ድንኳን አደባባይ ላይ ላለው የመግቢያ በር፣ ለቅድስቱ ስፍራ የመግቢያ በርና በቅድስቱና በቅድስተ ቅዱሳኑ መካከል ለሚከፍለው መጋረጃ ጥቅም ላይ ውለዋል፡፡ እነዚህ አራት ማጎች በዘፍጥረት 3፡15 ላይ ጌታ የሴቲቱ ዘር ሆኖ እንደሚመጣ በተተነበየው መሰረት ጌታችን በእርግጥም ወደዚህ ምድር መጥቶ በመጠመቅና በመሰቀል ሐጢያተኞችን ከሐጢያቶቻቸው እንደሚያድን ያሳያሉ፡፡ እግዚአብሄር ራሱ ያድነናል፡፡ 
 
እነዚህ አራት ማጎች ጥቅም ላይ የዋሉት በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በሮች ላይ ብቻ ሳይሆን በሊቀ ካህኑ ልብሶችና በመገናኛው ድንኳን የመጀመሪያ ሽፋን ላይም ጭምር ነበር፡፡ ይህም ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ የሰማያዊ፣ የሐምራዊና የቀዩን ማግ ሥራዎቹን በመፈጸም ከሐጢያቶቻችን እንደሚያድነን እግዚአብሄር የገባው ቃል ኪዳን ነበር፡፡ ጌታችንም ይህንን ኪዳን ጠብቆ ከዓለም ሐጢያቶች አዳነን፡፡ 
 
በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በሮች ላይ ወሳኙ ቀለም ሰማያዊው ማግ ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ መሲህ ሆኖ ወደዚህ ምድር በመጣ ጊዜ በመስቀል ላይ የሞተው ለምንድነው? ስለተጠመቀ ነው፡፡ ሰማያዊው ማግ የኢየሱስን ጥምቀት ያመለክታል፡፡ ሐምራዊው ማግ ኢየሱስ ንጉሥ መሆኑን ይነግረናል፡፡ ቀዩ ማግ ስቅለቱንና ያፈሰሰውን ደም ያመለክታል፡፡ ሰማያዊው፣ ሐምራዊው፣ ቀዩ ማግና ጥሩው በፍታ ኢየሱስ ክርስቶስ መሲህ ሆኖ ወደዚህ ምድር በመምጣትና ሐጢያቶቻችንን ሁሉ በራሱ ላይ በመውሰድ የሰጠንን የደህንነት ስጦታ የሚያዋቅሩ አስፈላጊ የግንባታ ቁሶች ናቸው፡፡ 
 
በዚህ ዓለም ላይ የሚኖሩ ብዙ ሰዎች ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሄር ልጅና በመሰረቱም ራሱ አምላክ በመሆኑ ላይ ያተኩራሉ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር በመገናኛው ድንኳን አማካይነት የዚህ ዓይነት ትምህርቶች ሙሉ እውነት ሊሆኑ እንደማይችሉ በግልጽ ይነግረናል፡፡ 
 
ሐዋርያው ጴጥሮስ በ1ኛ ጴጥሮስ 3፡21 ላይ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ይህም ውሃ ደግሞ ማለት ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድነናል፤ የሰውነትን እድፍ ማስወገድ አይደለም ለእግዚአብሄር የበጎ ሕሊና ልመና ነው እንጂ፡፡››
 
ይህም ኢየሱስ ክርስቶስ በሚያድነን ጥምቀቱ የደህንነት ተስፋውን እንደፈጸመና የእምነት መሰረቶችን እንደጣለ ይመሰክርልናል፡፡ መሲሃችን ማነው? መሲህ ማለት አዳኝ ማለት ነው፡፡ ይህም ኢየሱስ ወደዚህ ምድር መጥቶ ሐጢያቶቻችንንና የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በራሱ ላይ ለመውሰድ እንደተጠመቀና በእርግጥም በጥምቀቱ ሁሉንም በራሱ ላይ እንደወሰደ ይነግረናል፡፡
 
እግዚአብሄር እስራኤሎችን የመገናኛው ድንኳን አደባባይ የመግቢያ በር ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግ ፈትልና ከጥሩ በፍታ እንዲሰሩ ነገራቸው፡፡ የነገሥታት ንጉሥና የሰማይ ጌታ የሆነው አምላካችን የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር የመጣበት ዓላማ የእነዚህን የሰማያዊ፣ የሐምራዊ፣ የቀይ ማግና የጥሩ በፍታ እውነትን ለመፈጸም ነበር፡፡ ጌታችን የሰው ሥጋ ለብሶ በመምጣት ጽድቅን ሁሉ መፈጸም የሚያስችለውን ጥምቀት የሰው ዘር ወኪል ከሆነው ከአጥማቂው ዮሐንስ ተቀበለ፡፡
 
ይህም ሊቀ ካህኑ እጆቹን በራሱ ላይ በመጫን ወደ እርሱ የተሻገሩትን የእስራኤሎችን ሐጢያቶች ተቀብሎ ለእነዚህ ሐጢያቶች በምትካቸው ከተኮነነው የብሉይ ኪዳን መስዋዕት ጋር የተመሳሰለ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ልክ በብሉይ ኪዳን ላይ እንዳለው የመስዋዕት ጠቦት ኢየሱስም በአዲስ ኪዳን ለሐጢያተኞች ሐጢያቶች ሁሉ የመስዋዕት ጠቦት ሆኖ በመምጣት ተጠመቀ፤ ተሰቀለ፤ በዚያውም የዓለምን ሐጢያቶች ኩነኔ ሁሉ ተሸከመ፡፡ ኢየሱስ የእግዚአብሄር የመስዋዕት በግ ሆኖ በዮሐንስ በመጠመቅ የሰማያዊውን ማግ እውነት ፈጸመ፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ የሰውን ሐጢያቶች ሁሉ በአንድ ጊዜ በራሱ ላይ ወሰደ፡፡
 
አብዛኞቹ ክርስቲያኖች በሌሎች ዓለማዊ ሐይማኖቶች ውስጥ ከሚገኙ ሰዎች ይልቅ ወደ ክፉነት የተለወጡት የኢየሱስን ጥምቀት የሚያመለክተውን ይህን የሰማያዊ ማግ እውነት ማወቅና ማመን ባለመቻላቸው ነው፡፡ ስለዚህ በአንድ ጊዜ የሐጢያቶቻቸውን ስርየት አልተቀበሉም፡፡ ክርስቲያኖች ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በራሱ ላይ ለመውሰድ ሲል የተቀበለውን ጥምቀት ትክክለኛ ትርጉም የማያውቁ ከሆነ የእምነት መሰረቶቻቸው ከመጀመሪያውም በትክክል ሊመሰረት አይችልም፡፡
 
እርግጠኛ ለመሆን ሰማያዊው ማግ መሲህ ወደዚህ ምድር መጥቶ ሐጢያቶቻችንን በራሱ ላይ የተሸከመበት ዘዴና እውነት ነው፡፡ ቀዩ ማግም የኢየስስን ደም ያመለክታል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በጥምቀቱ በራሱ ላይ ስለወሰደ ነው፡፡ በመስቀል ላይ ስለ እኛ መስዋዕት መሆኑ ከንቱ ያልሆነውም ለዚህ ነው፡፡ እርሱን ደህንነታችንን ማጠናቀቅ የቻለው መሲሁ ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ ሙሉ በሙሉ የሐጢያት ኩነኔያችንን ሁሉ ስለተሸከመ ነው፡፡
 
ሐምራዊው ማግ ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክና የነገሥታት ንጉሥ መሆኑን ያመለክታል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የነገሥታት ንጉሥ (ሐምራዊው ማግ) ቢሆንም የሰው ዘር ወኪል በሆነው በአጥማቂው ዮሐንስ ባይጠመቅና በራሱ ላይ ባይወስድ ኖሮ (ሰማያዊ ማግ) በመስቀል ላይ በብዙ መከራና ስቃይ (ቀይ ማግ) ቢሞትም ሞቱ ከንቱ ይሆን ነበር፡፡ ያማረው ጥሩ በፍታ እግዚአብሄር በብሉይ ኪዳን የተናገረው የትንቢት ቃል ሁሉም በአዲስ ኪዳን ውስጥ ተፈጽሞዋል፡፡
 
 

ዘመኑ ክርስትና የሰማያዊው ማግ ትርጉም ጠፍቶታል፡፡ 

 
ሆኖም የዘመኑ ክርስትና ከአራቱ ማጎች መካከል ሰማየዊውን ማግ ቸል የማለትና የእግዚአብሄርን ቃል በዘፈቀደ በራሱ መንገድ የመተርጎም አዝማሚያ ይታይበታል፡፡ ይህ ታላቅ ሐጢያት በእርግጥም ይኮነናል፡፡
 
በመገናኛው ድንኳን አደባባይ የመግቢያ በር ጥቅም ላይ የዋሉት ሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግና ጥሩው በፍታ መሲሃችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ከሐጢያቶቻችን ለማዳን የሰው ሥጋ ለብሶ በመምጣት መጠመቅና መሰቀል የነበረበት የመሆኑን የደህንነት እውነት ይነግሩናል፡፡ ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ በራሱ ላይ ወስዶዋል፡፡
 
ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በራሱ ላይ የወሰደው እንዴት ነው? የወሰደው ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱ አማካይነት ነው፡፡ ኢየሱስ እውነተኛ አዳኛችን መሆን የቻለው ሐጢያቶቻችንን በራሱ ላይ መውሰድ ስለቻለ ብቻ ነው፡፡ የመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በሮች ከእነዚህ ከአራቱ ማጎች መፈተል የነበረበት ለዚህ ነው፡፡ እነዚህ ማጎች ወደዚህ ምድር የመጣው የተጠቀመው ደሙን በመስቀል ላይ ያፈሰሰውና ዳግመኛ ከሙታን የተነሳው ኢየሱስ ራሱ አምላክ እንደሆነ ይነግሩናልና፡፡
 
ስለዚህ የመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ከእነዚህ ከሰማያዊው፣ ከሐምራዊው፣ ከቀዩ ማግና ከጥሩው በፍታ ተሰራ፡፡ ኢየሱስ ወደ መንግሥተ ሰማይ የሚመራን የደህንነት በር ነው፡፡ ይህ በር ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ የተሰራ በር ነው፡፡ ኢየሱስ የሐጢያተኞች አዳኝ ነው፡፡ የኢየሱስ ጥምቀትና ስቅለቱ ሐጢያተኞችን ከሐጢያቶቻቸው ያዳነ የደህንነት ስጦታ ናቸው፡፡
የዘመኑ ክርስትና ከእውነተኛው አምላክ ጋር መገናኘት ያልቻለው ነገር ግን ከብዙዎቹ ዓለማዊ ሐይማኖቶች እንደ አንዱ ሆኖ የተቀየረው የኢየሱስን ጥምቀት በትክል መረዳት ስለተሳነው ነው፡፡ ስለዚህ እምነታችንን በሚመለከት በመጀመሪያ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ እውነት ላይ ጽኑ የእምነት መሰረት መጣል አለብን፡፡ ይህ የእምነት መሰረት ጌታችን ወደዚህ ምድር መጥቶ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ አማካይነት እናንተንና እኔን ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ ያዳነን የመሆኑ እውነታ ነው፡፡
 
ኢየሱስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱና በስቅለቱ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ያዳነንን የደህንነት ስጦታ አጠናቀቀ፡፡ ይበልጥ ግልጽ ለመሆን ኢየሱስ የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር በመምጣት በጥምቀቱ አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በራሱ ላይ ከወሰደ በኋላ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ለሐጢያቶቻችን ስርየት በመስጠት በመስቀል ላይ ሞቶ የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ ተሸከመ፡፡ በዚህ ሁኔታ በውሃውና በደሙ ያዳነን ይህ ኢየሱስ (1ኛ ዮሐንስ 5፡4-8) በዋናነት እኛን የፈጠረን የፍጥረት ጌታና እኛን ያዳነንን የደህንነት ስጦታ የሰጠን አምላክ ነው፡፡ ከሐጢያቶቻችን ሁሉና ከኩነኔ ያዳነን ይህ ኢየሱስ እውነተኛ አዳኛችን ሆንዋል፡፡ የመገናኛው ድንኳን ቁሳቁሶች የሚነግሩንም ይህንኑ ነው፡፡
 
ስለዚህ በእነዚህ ቁሶች በማመን እምነታችንን በጽናት መመስረት አለብን፡፡ መሲሃችንና አዳኛችን ሆኖ በመጣው በዚህ ኢየሱስ ስናምን በተቀበለው ጥምቀት፣ በመስቀል ላይ ስለ እኛ በተሸከመው ኩነኔ ሁሉና በሙታን ትንሳኤው በግልጽና በተጨባጭ ማመን አለብን፡፡ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ አማካይነት ከሐጢያቶቻችን ሁሉ የመዳንን ስጦታ የሰጠን አዳኝ ተራ ሰው ሳይሆን የሰውን ዘርና አጽናፈ ዓለማትን የፈጠረ ፈጣሪ ነበር፡፡ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ ላይ ያለንን እምነት ማወጅ ይገባናል፡፡ እምነታችንን በዚህ መንገድ ካላወጅን ኢየሱስን አዳኝ አድርጎ ማመን ብቻውን ዋጋ የለውም፡፡
 
በዝምታ ላይ የተመሰረተ የቃላት ጨዋታ ተጫውታችሁ ታውቃላችሁን? ይህ ጨዋታ የሚጀምረው አንድ አረፍተ ነገር የተጻፈበት ካርድ ከተሰጠው ሰው ነው፡፡ ግለሰቡ በመጀመሪያ በምስጢር አረፍተ ነገሩን ያነባል፡፡ ከዚያም ከንፈሩን በማንቀሳቀስ ብቻ በዝምታ አረፍተ ነገሩን ይናገራል፡፡ ከዚያም የከንፈር እንቅስቃሴውን ያነበበ ቀጣዩ ሰው ለሦስተኛው ሰው ያስተላልፋል፡፡ ይህም ደግሞ የሁለተኛውን ሰው የከንፈር እንቅስቃሴ አንብቦ በተመሳሳይ መንገድ ወደ አራተኛው ሰው ያስተላልፋል፡፡ የመጨረሻው ሰው ላይ እስኪደርስ ድረስም በዚሁ ይቀጥላል፡፡ የዚህ ጨዋታ ዓላማ የመጨረሻው ሰው በመጀመሪያ የተላለፈውን ትክክለኛ አረፍተ ነገር በትክክል እንዲናገር ማድረግ ነው፡፡ ይህ ጨዋታ የሚያስደስተው የመጀመሪያው አረፍተ ነገር ተዛብቶ መቅረቡ ሲታወቅ ነው፡፡ ለምሳሌ ጨዋታው የጀመረው ‹‹የአየር ማቀዝቀዣውን ክፍተው›› በሚል አረፍተ ነገር ከሆነ ለጥቂት ሰዎች ከተላለፈ በኋላ መለወጥ ይጀምራል፡፡ በመጨረሻም የመጨረሻው ሰው ‹‹አህያውን መልሰው›› በማለት ፈጽሞ የተለየ አረፍተ ነገር ተናግሮ ሊያጠናቅቅ ይችላል፡፡ 
ይህ የመጨረሻው ሰው ፈጽሞ የተለየ አረፍተ ነገር እንደተናገረ ሁሉ የዘመኑ ክርስትናም ይህንን በዝምታ ላይ የተመሰረተ ቃልን የማስተላለፍ ጨዋታ እየተጫወተ ይመስል ፈጽሞ ፈሩን የለቀቀ እምነት ይዞዋል፡፡ ነገሩ ለምን እንደዚህ ሆነ? የእምነቱን መሰረት በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ ላይ አልመሰረተም፡፡ የእምነት መሰረት በሚናወጥበት ጊዜ በኢየሱስ ምንም ያህል በግለት ብናምንና የእርሱን ትምህርቶችም ምንም ያህል በሕይወታችን ለመተግበር ብንሻም ይህንን ማድረግ አንችልም፡፡
 
እግዚአብሄር የመገናኛውን ድንኳን ለመስራት መባዎቻቸውን እንዲያመጡ ለእስራኤሎች በነገራቸው ጊዜ በመጀመሪያ ወርቅ፣ ብርና ናስ ከዚያም ሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግና ጥሩ በፍታ እንዲያመጡ ነገራቸው፡፡ እነዚህ የግንባታ ቁሶች በሙሉ ኢየሱስ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱ፣ በመስቀል ላይ እስከ ሞት ድረስ ባፈሰሰው ደሙና በትንሳኤው አማካይነት እንዳዳነን ያሳዩናል፡፡
ሰማያዊው ማግ ጥቅም ላይ የዋለው ለመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በሮች ሁሉ ብቻ ሳይሆን ለሊቀ ካህኑ ልብስና ለመገናኛው ድንኳን ሽፋኖችም ጭምር ነበር፡፡ ይህ ጌታችን እንዴት ወደዚህ ምድር እንደመጣና እናንተንና እኔን እንዴት በተጨባጭ ከሐጢያቶቻችን እንዳዳነን የሚነግረን ወንጌል ነው፡፡ ስለዚህ እነዚህ አራቱ የእምነት መሰረታዊ መዋቅሮች ማለትም ሰማያዊው፣ ሐምራዊው፣ ቀዩ ማግና ጥሩው በፍታ ምን ያህል ለእምነታችን አስፈላጊ እንደሆኑ ይነግረናል፡፡ እኛም በዚህ ቃል ላይ በመመስረት የእምነት መሰረታችንን በጽናት መመስረት አለብን፡፡ በእግዚአብሄር ማመን የምንችለው፣ የሐጢያቶቻችንን ስርየት የምንቀበለውና ከዚህ በኋላም ይህንን ቃል የሚያሰራጩ የእርሱ ልጆች የምንሆነው ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡ ጌታ ሲመጣም በዚህ እምነት በእግዚአብሄር ፊት በድፍረት የምንቆም የእርሱ ሕዝብ እንሆናለን፡፡
 
በኮርያ ከውጪ የሚመጣ ማንኛውም ነገር የተሻለ ነው ብሎ የማሰብ ዘመናዊነት አለ፡፡ ይህ ዝንባሌ በአገሬ የቃለ እግዚአብሄር ሊቃውንት መካከልም አለ፡፡ እነርሱ በምዕራባውያን የቃለ እግዚአብሄር ሊቃውንት ላይ ታላቅ እምነት ስላላቸው በእግዚአብሄር ቃሎች ላይ ከመደገፍ ይልቅ በእነርሱ ቃሎች ላይ ይደገፋሉ፡፡ እነርሱ ከዚህ ድንቁርና ነጻ መውጣት አለባቸው፡፡ በእግዚአብሄር በመተማመንና በእርሱ ላይ በመደገፍ በእግዚአብሄር ቃል ከልባቸው ማመን አለባቸው፡፡ ምክንያቱም ጌታችን የጥምቀቱና የደሙ እውነት እንደዚሁም እርሱ ራሱ አምላክ የመሆኑ እውነታ በዋናነት የደህንነታችን በር ሆኖዋልና፡፡ 
 
ሐዋርያው ጴጥሮስ ‹‹አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሄር ልጅ ነህ›› (ማቴዎስ 16፡16) በማለት እንዳወጀ ሁሉ እናንተም በእግዚአብሄር የምታምኑ ከሆነና ጌታ ወደዚህ ምድር የመጣው እናንተን ከሐጢያቶቻችሁ ለማዳን እንደሆነ የምታምኑ ከሆነ ጌታ እውነተኛ የደህንነት አምላካችን የሆነው በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በራሱ ላይ በመውሰድ፣ በመስቀል ላይ በመሞትና ዳግመኛም ከሙታን በመነሳት እንደሆነ ማወቅና ማመን አለባችሁ፡፡ የጌታችን ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ የደህንነትን ስጦታ እንድንቀበል ያስቻሉን የእምነት መሰረቶቻችን ናቸው፡፡ በእግዚአብሄር ቃል መሰረት በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ እምነት ማመን የማንችል ከሆነን ይህንን እንዴት እውነተኛ እምነት ነው ብለን ልንጠራው እንችላለን?
 
 
ሕጉ ሊመጣ ላለው መልካም ነገር ጥላ ነው፡፡ 
 
የመገናኛው ድንኳን የግንባታ ቁሶች ጌታችን ወደዚህ ምድር ሥጋ ለብሶ በመምጣት በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በራሱ ላይ እንደወሰደ፣ በስቅለቱም የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ እንደተሸከመ፣ ዳግመኛም ከሙታን እንደተነሳና አዳኛችን እንደሆነ ያሳዩናል፡፡ ጌታችን በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ የደህንነትን ስጦታ እንደሚሰጠን በብሉይ ኪዳን ውስጥ ቃል ገብቶልናል፡፡ ይህንን ኪዳን የሰጠን ለሐጢያተኞች ሲል የተጠመቀውና የተሰቀለው የነገሥታት ንጉሥ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ይህ አምላክ መሲህ አምላካችን ሆኖ መጣ፡፡ ስለዚህ ይህንን እውነት ሙሉ በሙሉ በማወቅና በማመን የእምነት መሰረታችንን መመስረት አለብን፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ሁላችንም የደህንነትን ስጦታ መቀበል አለብን፡፡
 
ወርቅ፣ ብርና ናስ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ጥቅም ላይ የዋሉ ቁሶች ናቸው፡፡ እነዚህ ቁሶች የእምነታችንን መሰረት ይጠቁማሉ፡፡ በእግዚአብሄር ፊት በሐጢያቶቻችን ምክንያት ወደ ሲዖል ከመጣል በስተቀር ሌላ ተስፋ አልነበረንም፡፡ ነገር ግን እንደ እኛ ላለን ሰዎች፣ ጌታችንን ለምናምን ሰዎች የደህንነትን ስጦታ ሰጠን፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ዘር ሁሉ መስዋዕት ለመሆን በዮሐንስ ተጠመቀ፤ ተሰቀለም፡፡ ሙሉ በሙሉም ከሐጢያቶቻችን አዳነን፡፡ እኛ ሲዖልን የምናርቅበት መንገድ አልነበረም፡፡ ምክንያቱም የምናውቀው ነገር ቢኖር ለሐጢያቶቻችን ለመኮነን የታጨን መሆናችንን ብቻ ነበር፡፡ ሐጢያቶቻችን ሁሉ እንዴት እንደሚወገዱ የምናውቅበት እምነትም አልነበረንም፡፡ በእግዚአብሄር ግን የደህንነት ስጦታ አገኘን፡፡ ኢየሱስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ በራሱ ላይ ወሰደ፡፡ በመስቀል ላይም ሞተ፡፡ ከዚያም የሐጢያቶቻችንንና የኩነኔ ችግሮቻችንን ሁሉ አቃለለ፡፡ ይህ የደህንነት ስጦታ ነው፡፡
 
ከሐጢያቶቻችን የዳንነው እግዚአብሄር የደህንነታችንን ስጦታ እንደሰጠን በሚያምነው እምነታችን ነው፡፡ እግዚአብሄር የወርቅ፣ የብርና የናስ እምነት እንድናቀርብለት የተናገረው ለዚህ ነው፡፡ ምክንያቱም እርሱ የደህንነት ስጦታን በመስጠት ለሲዖል የታጩትን ሙሉ በሙሉ አድኖዋቸዋልና፡፡ በዚህ የደህንነት ስጦታ በማመን በእግዚአብሄር ፊት ሙሉ በሙሉ የዳንነው ጌታችን በእርግጥም ወደዚህ ምድር መጥቶ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በራሱ ላይ በመውሰድ ኩነኔያችንን በመሸከሙ ነው፡፡
 
አሁን ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም የሆነ አዳኛችን ሆንዋል፡፡ ስለዚህ በደህንነት ስጦታው ላይ ባለን እምነት ጸንተን መቆም አለብን፡፡ ምክንያቱም ሰማያዊው፣ ሐምራዊው፣ ቀዩ ማግና ጥሩው በፍታ የእምነት ስጦታዎች ናቸውና፡፡ እግዚአብሄር ምንም ነገር ሳናውቅ እንዲያው በዘፈቀደና በዕውር ድንብር እንድናምን አይፈልግም፡፡
 
 
የፍየል ጠጉር፣ የቀይ አውራ በግ ቁርበትና የአቆስጣ ቁርበት፡፡ 
 
የፍየል ጠጉር፣ የቀይ አውራ በግ ቁርበትና የአቆስጣ ቁርበት፡፡ 
 
እነዚህ የመገናኛውን ድንኳን ለመሸፈን የሚያገለግሉ ሽፋኖች ነበሩ፡፡ የመጀመሪያው ሽፋን ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ የተሰራ ሲሆን ሁለተኛ ሽፋን በሆነው በፍየል ጠጉር የተለበጠ ነበር፡፡ ይህም ደግሞ በቀይ አውራ በግ ቁርበት ተሸፍኖ ነበር፡፡ በመጨረሻም ጣሪያው በአቆስጣ ቁርበት ተለብጦ ነበር፡፡ በዚህ መንገድ የመገናኛውን ድንኳን አራት የተለያዩ ሽፋኖች ሸፍነውት ነበር፡፡
 
በመገናኛው ድንኳን ላይ በመጨረሻ የተደረገው ሽፋን የአቆስጣው ቁርበት ነበር፡፡ ስለዚህ በመገናኛው ድንኳን ሽፋን የፊት ገጽታ ላይ የሚታየው የአቆስጣ ቁርበት ነበር፡፡ አቆስጣ በባህር ውስጥ የሚኖር እንስሳ ነው፡፡ የቁርበቱ መጠን የአንድ ሰው ቁመት ወይም ከዚያ ጥቂት ያነሰ ያክላል፡፡ ቁርበቱም ውሃ አያስገባም፡፡ የአቆስጣ ቁርበት ለመገናኛው የጣሪያ ሽፋንም ጥቅም ላይ የዋለው ለዚህ ነው፡፡ ከዚህ የተነሳ የመገናኛው ድንኳን የውጪ ገጽታ መስህብነት ያልነበረው ለዚህ ነው፡፡ በእርግጥም ለማየት የሚያጓጓ አልነበረም፡፡ ይህም ኢየሱስ ለእኛ ሲል ወደዚህ ምድር በመጣ ጊዜ በእርግጥም በገጽታው እንወደው ዘንድ የሚያምር ደም ግባት ይዞ እንዳልነበር ይነግረናል፡፡
 
የቀዩ አውራ በግ ቁርበት ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ ስለ ሐጢያት መስዋዕት መሆኑን ሲነግረን የፍየሉ ጠጉር ደግሞ የመስዋዕት ጠቦታችን ሆኖ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችንን በራሱ ላይ እንደተሸከመና በመስቀል ላይ እንደተሰዋ ይነግረናል፡፡ 
 
በሌላ አነጋገር የመገናኛው ድንኳን መሸፈኛ ቁሳቁሶች የእምነታችን መሰረቶች ናቸው፡፡ እነዚህ እውነቶች ፈጽሞ ሊረሱ የማይችሉ የእምነት የግንባታ ቁሶች ናቸው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የደህንነትን ስጦታ ይሰጠን ዘንድ የመስዋዕት ጠቦታችን ሆኖ ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ በብሉይ ኪዳን እግዚአብሄር የእስራኤሎችን ሐጢያቶች ለማስተሰረይ የመስዋዕት ስርዓትን ደነገገ፡፡ ነውር የሌለባቸውን የመስዋዕት እንስሶች (ፍየሎች፣ ጠቦቶች ወይም ኮርማዎች) በእጆች መጫን ወደ እነርሱ የተሻገሩትን የእስራኤሎች ሐጢያቶች ተቀብለው በእነርሱ ምትክ በመታረድ ደማቸውን አፍስሰው ይቃጠሉ ነበር፡፡ በዚህም ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ያድኑዋቸው ነበር፡፡
 
ኢየሱስ ክርስቶስ የመስዋዕት ጠቦት ሆኖ ወደዚህ ምድር በመምጣት በጥምቀቱ አማካይነት ማለትም በእጆች መጫን ሐጢያቶቻችንን በራሱ ላይ ወሰደ፡፡ የመስዋዕት ጠቦቱ በእጆች መጫን የእስራኤሎችን ሐጢያቶች በመቀበሉ ታርዶ ደሙ እንደሚፈስስና በሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ላይ እንደሚቃጠል ሁሉ ኢየሱስ ክርስቶስም እንደዚሁ በመጠመቅና በመስቀል ላይ በመሞት የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ ሁሉ ተሸክሞ ከዓለም ሐጢያቶች አዳነን፡፡
 
የመስዋዕቱን ጠቦት ደም በሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ቀንዶች ላይ በመቀባት ስሞች ከፍርድ መጽሐፍ እንደሚደመሰሱ ሁሉ ኢየሱስም በመጠመቁና ደሙን በማፍሰሱ ዘላለማዊ ስርየታችንን በደሙ በመፈጸም የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ደመሰሰ፡፡ ልክ እንደዚሁ የመገናኛው ድንኳን ቁሶች በሙሉ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስና ስለ አገልግሎቶቹ ይናገራሉ፡፡ በዚህ መንገድ ከዓለም ሐጢያቶች እንዳዳነን ይነግሩናል፡፡ ከብሉይ ኪዳን አንስቶ እስከ አዲስ ኪዳን ድረስ ኢየሱስ ከሐጢያቶቻችን ያዳነንና ሙሉ በሙሉ ከስህተቶቻችን ነጻ ያወጣን የመሆኑ ቃል ምሉዕ እምነት ነው፡፡
 
ብዙዎቹ የዘመኑ ክርስቲያኖች ኢየሱስ ክርስቶስ የመስዋዕት ጠቦታችን ሆኖ ወደዚህ ምድር በመምጣት ሐጢያቶቻችንን በጥምቀቱ በራሱ ላይ መውሰዱን አያምኑም፡፡ ነገር ግን በፋንታው በመስቀል ላይ መሞቱን ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ ያምናሉ፡፡ እንደዚህ ያለው የክርስትና እምነት ሰማያዊውን ማግ ትቶ ከቀዩና ከሐምራዊው ማግ ብቻ የተሰራ ሕገ ወጥ የመገናኛው ድንኳን አደባባይ የመግቢያ በር ነው፡፡ እነርሱ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊና ከቀዩ ማግ የተሰራውን መሸፈኛ አስፈላጊነት ማየት የማይችል የተሳሳተ እምነት ይዘዋል፡፡ የሚፈልጉት ነገር ቢኖር ከቀዩ አውራ በግና ከአቆስጣ ቁርባኖች የተሰሩትን እነዚህን ሁለት ሽፋኞች ብቻ እንደሆነ ያምናሉ፡፡
 
በመላው ዓለም ላይ በስዕል መልክ የቀረቡ የመገናኛውን ድንኳን ስዕሎች በምንመለከትበት ጊዜ አብዛኞቹ የሰማያዊውን ማግ ጥቂት ዱካ እንኳን ማግኘት በማንችልበት መንገድ የተሳሉ መሆናቸውን እናገኛለን፡፡ እነዚህን ስዕሎች የሳሉት ሰዎች የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ስለማያውቁ በስዕሎቻቸው ውስጥ የመገናኛው ድንኳን አደባባይ የመግቢያ በር በቀይና በነጭ ቀለማቶች የተሞሉ ናቸው፡፡ ነገር ግን እንደዚህ ዓይነቱ እምነት በእግዚአብሄር ፊት በፍጹም ትክክለኛ እምነት ሊሆን አይችልም፡፡
 
ለመገናኛው ድንኳን አደባባይ የመግቢያ በር በእጅጉ ጥቅም ላይ የዋለው ሰማያዊው ማግ ሲሆን ከእርሱ ቀጥሎ ሐምራዊው ማግ፣ ከዚያም ቀዩ ማግ፣ በመጨረሻም ነጩ ማግ ናቸው፡፡ ስለዚህ የአደባባዩ የመግቢያ በር ሲታይ እነዚህ አራቱም ቀለማቶች በአንድ ጊዜ መታየት አለባቸው፡፡ ነገር ግን በዚህ ዓለም ላይ እምነታቸው ሙሉ በሙሉ የኢየሱስን ጥምቀት ከማወቅ ውጪ የሆኑ ብዙ ሰዎች ያሉ በመሆናቸው ለመገናኛው ድንኳን ጥቅም ላይ የዋሉትን አራት ቀለማት ያላቸውን ማጎች ቸል ብለው የራሳቸውን የመገናኛ ድንኳን የመግቢያ በር በሁለቱ ማጎች ብቻ ሰርተዋል፡፡
 
እንዲህ በማድረጋቸውም አስቀድሞም ውሱን የሆነ የእግዚአብሄር ዕውቀት የነበራቸውንና ቃሉን የማያውቁትን ብዙ ሰዎች እያሳቱ ነው፡፡ እነዚህ ሁሉ ሐሰተኛ ነቢያት ናቸው፡፡ ኢየሱስ ራሱ ስለ እነዚህ ሰዎች ሲናገር ዲያብሎስ በስንዴው መካከል የዘራቸው እንክርዳዶች መሆናቸውን ተናግሮዋል፡፡ (ማቴዎስ 13፡25) በሌላ አነጋገር እነርሱ ሰማያዊውን ማግ ከመገናኛው ድንኳን አደባባይ የመግቢያ በር በማስወገድ ውሸቶችን የሚያሰራጩ ሰዎች ሆነዋል፡፡ ብዙ ሰዎች በኢየሱስ እያመኑም ሐጢያተኞች ሆነው የቀሩት ለዚህ ነው፡፡ በኢየሱስ ቢያምኑም በሐጢያቶቻቸው ምክንያት ሁሉም ለጥፋት የታጩ የሆኑት ለዚህ ነው፡፡
የእምነት መሰረታችን በጽናት መቆም አለበት፡፡ የሐይማኖት ሕይወታችሁ ሕገ ወጥ በሆነ የእምነት መሰረት ላይ ተመስርቶ ሳለ ረጅም የሐይማኖት ሕይወትን መኖር ምን እርባና አለው? የተሳሳተ እምነት በቅጽበት ይወድቃል፡፡ ቤታችን ምንም ያህል ያማረ ቢሆን ይህንን ቤት የገነባነው እንከን ባለው የእምነት መሰረት ላይ ከሆነ ምን እርባና ይኖረዋል? እግዚአብሄርን ምንም ያህል በትጋት ብታገለግሉት የእምነት መሰረታችሁ እንከን ካለበት ቤታችሁን የገነባችሁት በአሸዋ ላይ ብቻ ነው፡፡ ማዕበል ሲመጣ፣ ነፋስ ሲነፍስና ጎርፍ ሲጎርፍ ሁሉም በአንድ ጊዜ ይወድቃል፡፡
መሰረቱ ጽኑ የሆነ እምነትስ? ምንም ያህል ቢናወጥ ፈጽሞ አይወድቅም፡፡ እግዚአብሄር በሰማያዊ፣ በሐምራዊ፣ በቀይ ማግና በጥሩ በፍታ በተፈተለ የእውነት ዓለት ላይ የተመሰረተ ቤት ፈጽሞ እንደማያወድቅ ነግሮናል፡፡ ነገሩ በእርግጥም እንደዚህ ነው፡፡ በዓለት ላይ የተመሰረተ እምነት ምንድነው? በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ እውነት የሚያምን እምነት ነው፡፡ የዚህ ዓይነት የእምነት ቤት የገነቡ ሰዎች እምነት በፍጹም አይወድቅም፡፡ እምነታችንን ጽኑና ጠንካራ መሰረት ሊኖረው የሚገባ መሆኑ ወሳኝ የሆነው ለዚህ ነው፡፡ ጌታ ለእኛ ያደረገልንን ነገር በትክክል ሳናውቅ የምናምን ከሆነ የዚህ ዓይነቱ እምነት በእግዚአብሄር ወደማይፈልግ ሐሰተኛ የሐይማኖት እምነት ይለውጣል፡፡
 
 
የግራር እንጨት፣ ዘይትና ሽቱዎች፡፡ 
 
የመገናኛው ድንኳን ቋሚዎች፣ የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ፣ የመቅደሱ ሳንቃዎችና ዕቃዎች በሙሉ የተሰሩት ከግራር እንጨት ነበር፡፡ እንጨት በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ብዙውን ጊዜ የሚያመለክተው ሰብዓዊ ፍጡራንን ነው፡፡ (መሳፍንት 9፡8-15፤ማርቆስ 8፡24) እንጨቱ እዚህ ላይ ሰብዓዊ ተፈጥሮዋችንንም ያመለክታል፡፡ ይህ የግራር እንጨት ለቋሚዎቹ ለሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያና ለራሱ ለመገናኛው ድንኳን ጥቅም ላይ መዋሉ የግራር እንጨት ሥሮች ሁልጊዜም በመሬት ውስጥ የተቀበሩ እንደነበሩ ሁሉ እኛም ሁልጊዜ ሐጢያት ከመስራት በስተቀር ሌላ የምናደርገው ነገር እንደሌለ ይነግረናል፡፡ ሰዎች ሁሉ ሁልጊዜ ዓመጸኞች በመሆንና ሐጢያትን በመስራት የሚቀጥሉ መሆናቸውን ማመን አለባቸው፡፡
 
የግራሩ እንጨት የኢየሱስ ክርስቶስን ሰብዓዊነትንም ያመለክታል፡፡ የሰው ሥጋ ለብሶ የመጣው መሲህ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ተሸክሞ ለሰው ዘር ሁሉ ሲል በይፋ ተኮነነ፡፡ እርሱ ራሱ አምላክ ነው፡፡ ስለዚህ ታቦቱ፣ የሕብስቱ ገበታ፣ የዕጣኑ መሰውያና የመገናኛው ድንኳን ሳንቃዎች በሙሉ ከግራር እንጨት የተሰሩና በንጹህ ወርቅ የተለበጡ ነበሩ፡፡
 
ለመብራት የሚሆነው ዘይት፣ ለቅብዓ ቅዱስ የሚሆኑት ሽቱዎችና ጣፋጩ ዕጣን ለኢየሱስ ክርስቶስ የምናቀርበውን እምነታችንን ያመለክታሉ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ እናንተንና እኔን ያዳነ መሲሃችን ነው፡፡ ‹‹ኢየሱስ›› የሚለው ስም ትርጉም ‹‹ሕዝቡን ከሐጢያቶቻቸው የሚያድናቸው›› ማለት ሲሆን ‹‹ክርስቶስ›› የሚለው ስም ደግሞ ‹‹ቅቡዕ›› ማለት ነው፡፡ ስለዚህ እኛን ያዳነን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ አምላክና የሰማይ ሊቀ ካህን እንደሆነ ይህ ይነግረናል፡፡ ጌታችን የእግዚአብሄርን ፈቃድ በመታዘዝ የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር መጣ፤ ተጠመቀ፤ ስለ እኛም ራሱን በመስቀል ላይ መስዋዕት አደረገ፡፡ የደህንነትንም ስጦታ ሰጠን፡፡ ደህንነትን የሰጠን ኢየሱስ የተረከበው የሊቀ ካህን ሚና በእርግጥም እጅግ ያማረ ሥራ ነው፡፡
 
 
በሊቀ ካህኑ ኤፉድና በደረቱ ኪስ ላይ የተጠለፉት የመረግድ ዕንቁዎችና ሌሎች ዕንቁዎች፡፡ 
 
በሊቀ ካህኑ ኤፉድና የደረት ኪስ ላይ የሚጠለፉ አስራ ሁለት የተለያዩ የከበሩ ድንጋዮች ተጠቅሰዋል፡፡ በመጀመሪያ ሊቀ ካህኑ ሸሚዞችን ይለብሳል፡፡ ከዚያም ሰማያዊ ቀሚስ ይለበሳል፡፡ ከቀሚሱ በላይ በመስዋዕት ስርዓት ወቅት የሚለብሰውን ኤፉድ ያጠልቃል፡፡ በዚህ ላይ አስራ ሁለት የከበሩ ድንጋዮች ያሉበትን የደረት ኪስ ይደርባል፡፡ ይህም የሊቀ ካህኑ ሚና የእስራኤልን ሕዝብና በመላው ዓለም የሚገኙ ሌሎች ሕዝቦችን በሙሉ በዕቅፉ ይዞ በእግዚአብሄር ፊት እንደሚቀርብና የእነርሱን መስዋዕቶች እንደሚያቀርብ ያሳያል፡፡
 
ዘላለማዊው የሰማይ ሊቀ ካህን ኢየሱስም እንደዚሁ የዓለምን ሕዝቦች ሁሉ በዕቅፉ ይዞ ሐጢያቶቻችንን በጥምቀቱ በራሱ ላይ በመውሰድና በእኛ ፈንታ መስዋዕት በመሆን ሕዝቡን ለእግዚአብሄር አብ ቀድሶዋል፡፡ በደረቱ ኪስ ላይ ያሉት አስራ ሁለቱ የከበሩ ድንጋዮች የዚህን ዓለም ሕዝቦች ሁሉ ያመለክታሉ፡፡ እነዚህን ድንጋዮች የተሸከመው ሊቀ ካህንም የዓለምን ሕዝብ በሙሉ ያዳነውንና በዕቅፉ የያዘውን ኢየሱስ ክርስቶስን ያመለክታል፡፡
 
አምላካችን ለመገናኛው ድንኳን ግንባታ እንዲያመጡለት ለእስራኤሎች የተናገራቸው መባዎች እነዚህ ነበሩ፡፡ እግዚአብሄር ማደሪያው የሆነውን ይህንን የመገናኛውን ድንኳን በእነዚህ መባዎች እንዲሰሩ በነገራቸው እውነታ ውስጥ መንፈሳዊ ትርጉም አለ፡፡ የእስራኤል ሕዝብ እግዚአብሄር የሰጣቸውን ሕግ መጠበቅ ስላልቻሉ ሁልጊዜም ሐጢያተኞች ነበሩ፡፡ እግዚአብሄር በሙሴ በኩል የመገናኛውን ድንኳን እንዲሰሩ የነገራቸውና በመገናኛው ድንኳን ውስጥም የመስዋዕቱን ስርዓት የሰጣቸው ለዚህ ነበር፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ በሚቀርቡት መስዋዕቶች አማካይነት የሐጢያት ስርየት ይሰጥ ነበር፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር መባዎቻቸውን በመቀበል፣ ቤቱን ለመገንባትም እነዚህን መባዎች ሁሉ በመጠቀምና በመስዋዕቱ ስርዓት መጠይቆች መሰረትም መስዋዕቶቻቸውን እንዲያቀርቡ በማድረግ የእስራኤሎችን ሐጢያቶች በሙሉ ደመሰሰ፡፡ እግዚአብሄር ከእስራኤል ሕዝብ ጋር በመገናኛው ድንኳን ውስጥ መኖር የቻለው በዚህ መንገድ ነው፡፡
 
ነገር ግን በዚህ ምድር ላይ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ የማያምኑ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ እግዚአብሄር ወርቅ፣ ብርና ናስ እንዲያቀርቡለት ሲነግራቸው በእነዚህ መባዎች የተመለከተውን እውነት የማያምኑት ለምንድነው?
 
እኛ በሐጢያቶቻችን ምክንያት ለሲዖል የታጨን አልነበርንምን? በፍጹም ለሲዖል የታጫችሁ እንዳልነበራችሁ ባለማመናችሁ ክርስትና ከዚህ ዓለም ብዙ ሐይማኖቶች አንዱ እንደሆነ አድርጋችሁ አምናችኋልን? እስከ አሁን ድረስ ያመናችሁት እንደዚህ ከሆነ ንስሐ መግባትና ወደ ሰማያዊው፣ ሐምራዊው፣ ቀዩ ማግና ጥሩው በፍታ እምነት መመለስ አለባችሁ፡፡ ጥብቅ በሆኑት የእግዚአብሄር ትዕዛዛት ፊትም በሐጢያት የተሞላችሁና ከእነዚህ ሐጢያቶች የተነሳም ለሲዖል የታጫችሁ እንደሆናችሁ ማወቅና በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ማመን አለባችሁ፡፡
 
አሁን በእውነት ወንጌል ማመን አለባችሁ፡፡ ለሲዖል የታጫችሁ ሆናችሁ ሳለ ጌታችን መሲህ ሆኖ ወደዚህ ምድር በመምጣት በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችሁን ወሰደ፡፡ እነዚህንም ሐጢያቶች ወደ መስቀል ወስዶ በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰስ ራሱን መስዋዕት አደረገ፡፡ በዚህም እናንተንና እኔን ከሐጢያቶቻችንና ከኩነኔያችን አዳነን፡፡ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ሳናምን የእምነት መሰረታችንን ፈጽሞ ሙሉ በሙሉ መመስረት አንችልም፡፡
 
 
ስለ እምነታችን መሰረት ማሰብ አለብን፡፡ 
 
እግዚአብሄር የሰማያዊው፣ የሐምራዊውና የቀዩ ማግ እምነት እንዲኖረን ነግሮናል፡፡ ይህ የሰማያዊው፣ የሐምራዊውና የቀዩ ማግ እምነት እንዳለንና እንደሌለን ወይም የምናምነው ሰማያዊውን ማግ ትተን በቀዩና በሐምራዊው ማግ በተገለጠው እውነት ብቻ እንደሆነ ራሳችንን መጠየቅ አለብን፡፡
 
ራሳችንን ተመልክተን ለእኛ የሚጥመንን የተሳሳተ እምነት ለእግዚአብሄር እያቀርብን መሆን አለመሆናችንን ማየት ያስፈልገናል፡፡ እግዚአብሄር ሰማያዊውን፣ ሐምራዊውንና ቀዩን ማግ እንድናመጣለት ሲነግረን በማናቸውም አጋጣሚ ጥቁር ቀለም ያለውን የናይሎን ማግ አላቀረብንለትምን? ‹‹አቤቱ አንተ የጠየቅኸው ማግ ለመገናኛው ድንኳን የሚረባ አይመስልም፡፡ በዝናብ በስብሶ ይቀደዳል፡፡ ይህንን ፈልጎ ማግኘትና እዚህ ማምጣቱ በጣም አድካሚ ነው፡፡ በፋንታው ይህንን የናይሎን ማግ ሞክረው፡፡ በደንብ ከጠበቅኸው ቢያንስ ለ50 ዓመታት ምናልባትም ለ100 ዓመታት እንደሚቆይ ዋስትና ልሰጥህ እችላለሁ፡፡ ለ200 ዓመታት ያህልም አይበሰብስም፡፡ ይህ ግሩም አይደለምን?››
 
በማናቸውም አጋጣሚ ለእግዚአብሄር የምንነግረው ይህንን አይደለምን? ራሳችንን በደንብ ተመልክተን የዚህ ዓይነት ራስ ወዳድና በባዕድ አምልኮ ላይ የተመሰረተ እምነት ለእግዚአብሄር እያቀረብን እንደሆነና እንዳልሆነ በማጤን አሁኑኑ ንስሐ መግባት አለብን፡፡ በሌላ አነጋገር መመለስ አለብን፡፡
 
በመካከላችን ራሳቸውን ጥሩ ክርስቲያኖች አድርገው የሚያስቡ ብዙዎች አሉ፡፡ ነገር ግን ጠጋ ብለው ሲያዩዋቸው ዕውቀታቸው የተሳሳተ ሰለሆነ እምነታቸውም የተሳሳተ ነው፡፡
 
 
በዘመኑ ክርስትና ውስጥ የገነነው ረቂቅ መንፈሳዊነት፡፡ 
 
ክርስቲያኖች በጥቅሉ በረቂቅ መንፈሳዊነት አብዝተው ያምናሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች የእግዚአብሄር ቃል በትክክል ምን እንደሚል አያውቁም፡፡ መሲሁ የሰጣቸውን የእውነት ቃል ስለማያውቁ እንደ ራሳቸው ስሜት ጌታን በመከተል ያምናሉ፡፡ የዚህ ዓይነት ስሜት የእውነት ክፍል እንደሆነም አምነው ተቀብለዋል፡፡ በራሳቸው ስሜት ወደ እግዚአብሄር በትጋት ስለሚጸልዩና በጸሎቶቻቸው ውስጥ የሚሰሙዋቸውን ስሜቶቻቸውን በታማኝነት ስለሚከተሉ እውነተኛው የእግዚአብሄር እምነት በትክክል ምን ማለት እንደሆነ ለይተው ማወቅ አይችሉም፡፡
 
በራስ አስተሳሰብ ውስጥ ያለ ሆኖ በስፋት በሚዋልል ስሜት ማመን የረቂቅ መንፈሳዊነት እምነት ነው፡፡ ሰዎች በሚጾሙበት፣ የማለዳ ጸሎት በሚጸልዩበት፣ በሚያመሰግኑበት፣ በሚያምኑበት፣ ለመጸለይ ወደ ተራራ በሚወጡበት፣ ሐጢያት በሚሰሩበት፣ የንስሐ ጸሎቶችን በሚጸልዩበትና ወ.ዘ.ተረፈ ወቅት በሚያገኙት ስሜት ተነድተው በእግዚአብሄር የሚያምኑ ሰዎች ሁሉም ረቂቅ መንፈሳዊያን ናቸው፡፡ በሌላ አነጋገር በራስ ስሜት እየተመሩ የእምነትን ሕይወት በመምራት መሲሁ የተናገረለት የሰማያዊው፣ የሐምራዊውና የቀዩ ማግ እምነት አይደለም፡፡
 
ምናልባትም 99.9 ከመቶ የሚሆኑት የዘመኑ ክርስቲያኖች በታሪካዊ መልኩ ረቂቅ መንፈሳውያን ነበሩ፡፡ በሌላ አነጋገር ከጥንቷ ቤተክርስቲያን በስተቀር መላው የክርስቲያን ዓለም በሙሉ ረቂቅ መንፈሳዊነትን ሲከተል እንደነበር መናገሩ ማጋነን አይደለም፡፡ የሰማያዊው፣ የሐምራዊውና የቀዩ ማግ እምነት የሌላቸው ስሜቶቻቸው በራሳቸው እምነት እንደሆኑ በማሰብ ተታልለዋል፡፡ በጸሎቶቻቸው ወቅት እግዚአብሄርን እንዳዩትና እንደተገናኙት ይናገራሉ፡፡ በሚያመሰግኑበት ጊዜ ሁሉም ምን ያህል የደስታ ስሜት እንደሚሰማቸው ይነግረናል፡፡
 
‹‹በዚህ የምስጋና ጉባኤ ውስጥ ተሰብስበናል፡፡ እጆቻችንን ከፍ አድርገን በአንድነት ለሐጢያቶቻችን ንስሐ ገብተናል፡፡ መስቀሉን ይዘን ከበታቹ አንዳች ስርዓትን ፈጽመናል፡፡ ከዚያም ልቦቻችን በእሳት ተቀጣጠሉ፡፡ ክርስቶስንም አብዝተን ወደድነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ስላፈሰሰው ደሙ ብዙ ውዳሴ በልባችን ውስጥ አለ፡፡ እርሱ ደሙን ያፈሰሰው ለዚህ እንደሆነ በመገንዘባችንም ጌታ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ እንዳስወገደ በግለት እናምናለን፡፡ ልምምዱን ወደነዋል›› ይላሉ፡፡ ነገር ግን አንድ ቀን ስሜቶቻቸው ሲበርዱ ‹‹ያ ሁሉ ስሜት ደረቀ፤ እኛም በልቦቻችን ውስጥ ሐጢያት አለብን›› ይላሉ፡፡ የዚህ ዓይነቱ እምነት የረቂቅ መንፈሳዊነት እምነት ነው፡፡
 
የሐይማኖት ወይም የአንጃ ልዩነቶች ቢኖሩም እያንዳንዱ ክርስቲያን በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ እውነት የሚያምነው እምነት ያስፈልገዋል፡፡ እግዚአብሄር የተናገረለት ይህ የሰማያዊው፣ የሐምራዊውና የቀዩ ማግ እምነት የሌላቸው ሰዎች ሁሉ እምነት ረቂቅ መንፈሳዊነትና ባዕድ አምልኮ ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ለእግዚአብሄር እየሰጡ ያሉት የሰማያዊውን፣ የሐምራዊውንና የቀዩን ማግ እምነት ሳይሆን የናይሎኑን ማግ እምነት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር በጣም የዘቀጠውንና እግዚአብሄርም ሊመለከተው የሚጸየፈውን አንዳች የረቂቅ መንፈሳዊነትን እምነት ነው፡፡
 
በወደብ ላይ ጀልባዎችን ለማሰር የሚያገለግሉ ወፋፍራም ገመዶችን አይታችሁ ታውቃላችሁን? ረቂቅ መንፈሳውያን የዚህ ዓይነቱን ቁስ በደስታ ለእግዚአብሄር ያቀርባሉ፡፡ ጌታችን ሰማያዊውን፣ ሐምራዊውን፣ ቀዩን ማግና ጥሩውን በፍታ እንድናመጣለት ሲነግረን አንዳንድ ሰዎች ግን ‹‹አቤቱ ይህንን እምነት ተቀበል!›› በማለት ይህንን ወፍራም ገመድ ለእግዚአብሄር ያቀርቡለታል፡፡ አንዳንድ ሰዎችም ትላልቅ መርከቦችን እርስ በርስና ከወደቡ ጋር ለማሰር የሚጠቀሙባቸውን የብረት ሰንሰለቶች ያቀርቡለታል፡፡ እነዚህን ወፋፍራም የብረት ሰንሰለቶች ጠቅልለው እንዲቀበላቸው በመጠየቅ በጌታ እግር ፊት ያስቀምጡታል፡፡
 
እግዚአበሄር ግን የሰማያዊውን፣ የሐምራዊውንና የቀዩን ማግ እምነት እንድናቀርብ ነግሮናል፡፡ የብረት ሰንሰለቶችን እንድናቀርብለት አልነገረንም፡፡ ነገር ግን ብዙ ሰዎች በዓይኖቻቸው ፊት የተሻሉ የመሰሉዋቸውን ወይም በቀላሉ የሚያገኙዋቸውን ለእርሱ ያቀርቡለታል፡፡ የብረት ሰንሰለቶችን፣ ገመድን፣ የናይሎን ማግን ወይም ሥራ ስሮችን ይዘው ወደ እግዚአብሄር የሚቀርቡ ሰዎች ቢኖሩም እግዚአብሄር የሚቀበለው ግን የሰማያዊውን፣ የሐምራዊውንና የቀዩን ማግ መባ ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር የሚቀበለው ብቸኛው እምነት የሰማያዊው፣ የሐምራዊውና የቀዩ ማግ እምነት እንዲሆን ወስኖዋል፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ፊት ይህንን የሰማያዊውን፣ የሐምራዊውንና የቀዩን ማግ እምነት ማቅረብ አለብን፡፡
 
 
መሲሁ ማንኛውንም መባ አይቀበልም፡፡ 
 
እስራኤሎች ወርቅ፣ ብር፣ ናስ፣ በኤፉዱና በደረቱ ኪስ ላይ የሚሆኑትንም አስራ ሁለት የከበሩ ድንጋዮች ለእግዚአብሄር ማቅረብ ነበረባቸው፡፡ ነገር ግን መዳብን ወይም ብረትን ለእግዚአብሄር የሚያቀርቡ አንዳንድ ሰዎች አሉ፡፡ ኢየሱስ ሁሉንም ዓይነት ነገሮችን የሚቀበል ይመስል ዳግመኛ ለአገልግሎት የሚውሉ ቆሻሻዎችን የሚይዝ የቆሻሻ ማጠራቀሚያ እያስተዳደረ ነውን? በፍጹም አይደለም!
 
ኢየሱስ ማንኛውንም ዓይነት ቆሻሻ የሚረከብ ዓይነት ሰው አይደለም፡፡ እናንተ የምታመጡለትን ማንኛውንም የማያገለግል ዕቃ ወስዶ ዳግመኛ እንዲያገለግል ለማድረግ የሚያስችል ማጠራቀሚያ የሚያስተዳድር አይደለም፡፡ ኢየሱስ ሐጢያቶቸችንን ይቅር የሚለውን የሰማያዊ፣ የሐምራዊና የቀይ ማግ ምህረቱን ሊሰጠንና እውነተኛ ፍቅሩን ሊለግሰን የሚሻ መሲህ ነው፡፡ ኢየሱስ የፍቅር ንጉሥ ነው፡፡ ኢየሱስ በእርግጥም እውነተኛ መሲሃችን ነው፡፡ ይህ መሲህ የተወሰኑ ባህሪያቶች ፈጽመው አስፈላጊ እንደሆኑ በማብራራት ከእኛ የሚፈልገውን እምነት አስቀምጦልናል፡፡ እርሱ ቃል የገባልንን የሚሰጠን ይህንን እምነት ይዘን በእግዚአብሄር ፊት ስንቀርብ ብቻ ነው፡፡
 
ነገር ግን ስለ እግዚአብሄር በተሳሳተ ዕውቀት ላይ የተመሰረተ የተሳሳተ እምነት ባላቸው መካከል ግትርነታቸው ከመጠን በላይ የሆነ አንዳንዶች አሉ፡፡ በእግዚአብሄር ፊት በግትርነቱ እንደጸናው ፈርዖን ክፉዎችና ዓመጸኞች ናቸው፡፡ ሙሴ ‹‹የሆዋ ራሱን ገልጦዋል፤ ሕዝቡ ነጻ ይውጡ›› ባለው ጊዜ ፈርዖን ‹‹ይህ የሆዋ ማነው?›› በማለት ተሳለቀ፡፡
 
የእግዚአብሄር ሕልውና በተብራራለት ጊዜ ራስ ወዳድነቱ የሚያስከፍለውን ዋጋና የሚያገኛቸውን ጥቅሞች ካሰላ በኋላ ፈጥኖ ለእግዚአብሄር እጁን ቢሰጥ ይሻለው ነበር፡፡ አሁንም ፈጽሞ የማያምንና በግትርነቱ የሚጸና ከሆነ ለጥቂት ጊዜ ሥልጣኑን ማቆየት ይሞክር ይሆናል፡፡ ነገር ግን ከሁለት መቅሰፍቶች በኋላ ተስፋ ይቆርጣል፡፡ ፈርዖን ጓጉንቸሮች መላውን አገሪቱን ሸፍነው ሳለ በግትርነቱ በመጽናትና የእግዚአብሄርን ቃል ባለመታዘዝ መቀጠሉ ምንኛ ደደብነትና አሳዛኝ ነው?
 
የፈርዖንን ቤተ መንግሥት የወረሩት ጓጉንቸሮች ብቻ ሳይሆኑ ቅማሎችም ጭምር ነበሩ፡፡ አንድ ሰው በግራም በቀኝም ቢመለከት መላው የግብጽ ምድር ሁሉ በቅማል ተሞልቶ ነበር፡፡ ፈርዖን ግን እጁን አልሰጠም፡፡ ሁሉም ስፍራ በቅማል ተሞልቶ እያለ ሰው እንዴት ሊኖር ቻለ? በዚህ ሁኔታ ላይ ሳለ ‹‹በእግዚአብሄር ላይ ስላመጽሁ እውነተኛው ንጉሥ ማን እንደሆነ እያሳየኝ ነው፤ እኔ በዚህ ምድር ላይ የመንግሥቴ ንጉሥ ሆኜ ይሆናል፤ ነገር ግን ከእርሱ ጋር ስነጻጸር ምናምን ነኝ፡፡ እኔ በዚህ ምድር እጅግ ታላቅ የሆነችው አገር ንጉሥ ብሆንም፣ በመላው ዓለም ላይም ሥልጣን ያለኝ ብሆንም እግዚአብሄር ግን ከእኔም በላይ ብርቱ ነው፡፡ በዓመጻዬ ምክንያት እነዚህን መቅሰፍቶች እያወረደብኝ ነው›› ብሎ ግንዛቤ መውሰድ ነበረበት፡፡ እጁን መስጠት የሚኖርበት በዚህ መንገድ ነበር፡፡
 
ፈርዖን ማድረግ የነበረበት ብልህ ነገር ግትርነቱ የሚያስከፍለውን ዋጋ ለራሱ ከተመለከተ በኋላ በፍጥነት እጁን መስጠት ነበር፡፡ ፈርዖን ምንም ያህል ብርቱ የነበረ ቢሆንም እግዚአብሄርን የሚቃወምበት መንገድ እንዳልነበረ ድምዳሜ ላይ ቢደርስ ማድረግ የነበረበት ነገር ቢኖር ‹‹እሺ፤ እግዚአብሄር አንተ የመጀመሪያውን ስፍራ ትወስዳለህ፤ እኔም ሁለተኛው ቦታ እወስዳለሁ›› በማለት እጁን ለእግዚአብሄር መስጠት ነበር፡፡
 
ከዚህ የተነሳ ግብጻውያን አንዳች ነገር ማድረግ አልቻሉም፡፡ ሰው ሁሉ ያለ ርህራሄ በቅማል እየተሰቃየ ባለበት ሁኔታ ቅማሉን ከማስወገድ በስተቀር ሌላ ነገር ማድረግ እንዴት ይችላል? ሁላችንም እነዚህ ምስኪን ግብጻውያን ቅማልን ለማስወገድ እየሞከሩ ችቦዎችን ይዘው ሲሽከረከሩ ምናልባትም በሒደቱ የራሳቸውን ቤቶች አቃጥለው የተቃጠሉት ቅማሎች ግማት መንደሮችን ሲያዳርስ ማሰብ እንችላለን፡፡
 
ሰው ሊያደርጋቸው የሚችላቸው ነገሮች አሉ፡፡ ሰው ሊያደርጋቸው የማይችላቸውም ነገሮች አሉ፡፡ እግዚአብሄር የሠራዊት ጌታ ስለሆነ በሕይወትና በሞት፣ በደስታና በሐዘን፣ በበረከቶችና በእርግማኖች ላይ የሚሰለጥነው እርሱ ነው፡፡ ነገሩ እንደዚህ በሚሆንበት ጊዜ በራሳችን ከመተማመንና እግዚአብሄርን ለመቃወም ከመሞከር ይልቅ ሁላችንም ረጋ ብለን በማሰብ ግትርነታችንን ለመተው ስነ አመክኖአዊ ድምዳሜ ላይ መድረስ አለብን፡፡ የራሳችንን መንገድ የሙጥኝ ብለን በመያዝ በሌሎች ላይ የበላይ ለመሆን እንሞክራለን፡፡ መሲሁን በሚመለከት ግን ይህ የሚሆን አይደለም፡፡
 
በእግዚአብሄር ፊት ምን ዓይነት ሰዎች መሆን እንደሚገባን ማሰብ አለብን፡፡ እግዚአብሄርን የምንቃወም እንሁን ወይም ልባችን በእርግጥም ገርና የዋህ ይሁን አጥብቀን ማሰብ አለብን፡፡ ሁለችንም በእግዚአብሄር ፊት ገሮች መሆን ያለብን ስለመሆኑ ወሳኝ ድምዳሜ ላይ መድረስ አለብን፡፡ በሰዎች ፊት በግትርነታችን እንቀጥል ይሆናል፡፡ አንዳንድ ጊዜም ውጤቶቹን እንቀበላለን፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ግን ልባችን ሙሉ በሙሉ ገር መሆን አለበት፡፡
 
‹‹እግዚአብሄር ሆይ ተሳስቻለሁ፡፡›› ይህንን የሚያምኑ ትክክለኛውን መንገድ የሚመርጡ ናቸው፡፡ እነዚህ ከተረገመው ሕይወታቸው የዳኑ ሰዎች ናቸው፡፡ በሐጢያቶቻቸው ምክንያት እግዚአብሄርን የተዉት በእግዚአብሄር ክንዶች የሚታቀፉበትና ሕይወት ሰጪ ውሃውን የሚጎነጩበት መንገድ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ዳግመኛ በመወለድ ነው፡፡ ሕይወታችን ያለ ምንም ዓላማ ባዶና ደረቅ በሆነው ምድሩ ላይ እየተንጠራወዘ በዚህ ዓለም ምድረ በዳ ላይ እንዳለ ፍሬ ባክኖ ወደ አፈርነት ሊለወጥ ከተዘጋጀ ከዚህ ሕይወት ምን ልንጠብቅ እንችላለን?
 
ወደ አፈር ለምንመለሰውና ወደ እሳት ባህር ለመጣል ለታጨነው ለእኛ የመዳኛው ብቸኛው መንገድ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የሐጢያቶቻችንን ስርየት መቀበል ነው፡፡ እግዚአብሄርን በመቃወማቸውና በሐጢያቶቻቸው የተነሳ ለዘላለም ጥፋት የታጩ ተስፋ ቢስ ሕይወቶች በምህረት ፍቅሩና በደህንነት ፍቅሩ እንደገና በእግዚአብሄር ፊት በተዓምራዊ መንገድ ነፍስ ይዘራሉ፡፡ ስለዚህ ሁላችንም ይህንን ደህንነት መልበስ አለብን፡፡
 
ሟች የሆነ ማንኛውም ሰው እንዴት እግዚአብሄርን ሊገዳደር ይችላል? እግዚአብሄር ይህንንና ያንን መባ እንድናመጣ ከነገረን ሁላችንም ቃሉን መታዘዝ አለብን፡፡ እግዚአብሄር ምን ዓይነት መባዎችን ልናመጣለት እንደሚያስፈልገን የተናገረበትን ከላይ ያለውን ምንባብ ስንመለከት ሁላችንም ‹‹አሃ እግዚአብሄር ወደ እርሱ እንድናመጣለት የጠየቀን የእምነት ዓይነት ይህ ነው›› በማለት ግንዛቤ መውሰድ አለብን፡፡
 
በሊቀ ካህኑ የደረት ኪስ ላይ አስራ ሁለት የከበሩ ድንጋዮች መደረግ ነበረባቸው፡፡ ከፍርዱ የደረት ኪስ በታችም ሊቀ ካህኑ በእስራኤል ሕዝብ ላይ ትክክለኛ ፍርድ ይፈርድ ዘንድ ቃል በቃል ብርሃናት ወይም ፍጻሜታት የሚል ትርጉም ያላቸው ኡሪምና ቱሚም መደረግ ነበረባቸው፡፡
 
ይህም በውስጣቸውና በእግዚአብሄር ቃል ላይ ያለውን የመንፈስ ቅዱስን ብርሃን በማብራት በመንፈሳዊ የእምነት ልጆቻቸው ላይ የጽድቅ ፍርድን ማሳለፍ የሚችሉት የእግዚአብሄር ባሮች ብቻ መሆናቸውን የሚጠቁም ነው፡፡
 
አሁን በእግዚአብሄር ፊት ተጨባጩ እውነትና እውነተኛው ደህንነት የሰማያዊው፣ የሐምራዊውና የቀዩ ማግ እውነት መሆኑን ሁላችንም መረዳት አለብን፡፡ የሰማያዊው፣ የሐምራዊውና የቀዩ ማግ እውነት ሕይወትን የሚሰጠን እውነተኛ ደህንነት ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ደህንነታችንን የሚያዋቅር ሌላ ምንም ነገር የለም፡፡ ይህ ሁሉ ግልጽና እውነት ሆኖ በእግዚአብሄር ቃል ላይ የተመሰረተ ነው፡፡
 
 

የመገናኛው ድንኳን ቁሶች በሙሉ ሰው ከሐጢያት ከሚድንበት ደህንነት ጋር ተዛምደዋል፡፡ 

 
ነገር ግን ሰዎች በስፍናቸው አሁንም ለማመን እምቢተኞች ናቸው፡፡ ታዲያ ምን ይገጥማቸዋል? መቼም ቢሆን በፍጹም አይድኑም፡፡ እኛ በእግዚአብሄር ፊት ስንፍናችንን መጣል አለብን፡፡ ልባችንንም ባዶ ማድረግ አለብን፡፡ በእግዚአብሄር ፊት የራሳችንን አስተሳሰቦችና ግትርነት ማስወገድ አለብን፡፡ ቃሉን መታዘዝና ልባችንንም ለእርሱ መስጠት አለብን፡፡ ራስ ወዳድ የሆኑትን መንገዶቻችንን የሙጥኝ ብለን ይዘን እግዚአብሄርን በፍጹም መቃወም የለብንም፡፡ ይህንን በሌሎች ሰዎች ፊት እናደርግ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ክርስቲያኖች በመሆናችን ቢያንስ ይህንን በእግዚአብሄር ፊት ማድረግ አንችልም፡፡ ሞኞች የሆኑ ሰዎች ግን እግዚአብሄርን እየተቃወሙ በሰዎች ፊት ብቻ ገሮች ይሆናሉ፡፡ ችግራቸው ይህ ነው፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ራሳችንን ዘርረን እግዚአብሄር የነገረን ሁሉ ትክክል እንደሆነ ማመን አለብን፡፡
 
በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ ቃል ማመንና መታመንም ይገባናል፡፡ እምነት በእግዚአብሄር ቃል መታመን ነው፡፡ ራሳችንን በእግዚአብሄር ፊት ስንዘርር፣ ችግሮቻችንን ሁሉ በፊቱ ስንናገርና የእርሱን እርዳታ በመለመን ከእርሱ ጋር ስንጣበቅ እግዚአብሄር እንደሚመልስልን የተረጋገጠ ነው፡፡ ያን ጊዜ እርሱ ለእኛ ያደረገልንን ከምስጋና ጋር መቀበል አለብን፡፡ እምነት ማለት ይህ ነው፡፡ ታዲያ ለእግዚአብሄር ከሰማያዊው፣ ከሐምራዊውና ከቀዩ ማግ የተለየ የዓሣ ማጥመጃ መንጠቆዎች ወይም የብረት ሰንሰለቶች ማቅረብ ምንኛ ዕብደት ነው? በእግዚአብሄር ፊት የማይረባ ማግ በማቅረብ ‹‹የእኔ እምነት ይህ ነው፡፡ በብረቱ የማምነው እንደዚህ ነው፡፡ በተለየ መንገድ ጠብቄ ያቆየሁት ጽኑ እምነት ይህ ነው›› ማለት በአጭሩ እምነት አይደለም፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ፊት ራስን ማሞኘት ነው፡፡
 
ሰው በመሲሁ ፊት ግትርነቱን መተው አለበት፡፡ በሌላ አነጋገር ሰው በእግዚአብሄር ፊት ፈቃዱን ማለዘብ አለበት፡፡ ሁላችንም በእግዚአብሄር ፊት ራሳችንን ማወቅ አለብን፡፡ እግዚአብሄር ለእኛ በተናገረውና እርሱ ለእኛ በወሰነው መሰረት ማወቅ አለብን፡፡ ትክክለኛው የክርስቲያኖች እምነት ይህ ነው፡፡ የታመነው ሰው ትክክለኛ አቋምና ልብ በእግዚአብሄር ቃል መሰረት መታዘዝና ማመን ነው፡፡ በእግዚአብሄር ፊት በአእምሮዋችን ልንይዘው የሚገባን ይህንን ነው፡፡
 
በመካከላችን ስለ ክንውኖቻችን እንኩራራለን፡፡ እርስ በርሳችን እንፎካከራለን፡፡ እርስ በርሳችን እንወዳደራለን፡፡ እርስ በርሳችንም እንፋለማለን፡፡ በእግዚአብሄር መለኪያ ሁሉም ተመሳሳይ ሆኖ ሳለ የዚህ ዓይነቱ ፉክክር የማይረባ ምግባር ቢሆንም በሰብዓዊ ፍጡራን መካከል ግን ይህ ሁልጊዜም የምንሳተፍበትና ብዙም ምርጫ የማናገኝበት ነገር ነው፡፡
 
ውሾችም እንኳን ባለቤቶቻቸው እነማን እንደሆኑ ያውቃሉ፡፡ ለባለቤቶቻቸው በመገዛትም ይታዘዙዋቸዋል፡፡ በሌላ አነጋገር ውሾችም እንኳን አሳዳሪዎቻቸውን ይታዘዛሉ፤ ድምጻቸውንም ያውቃሉ፡፡ አሳዳሪዎቻቸውንም ብቻ ይከተላሉ፡፡ ውሾች በአሳዳሪዎቻቸው ሲገሰጹ ስህተቶቻቸውን አውቀው በመታዘዝ አንገቶቻቸውን ይደፋሉ፡፡ ሁሉንም ዓይነት አስደሳች ምግባሮች በማድረግ ከአሳዳሪዎቻቸው ጋር ወደ መስማማት ለመመለስ ይሞክራሉ፡፡ እንስሶች እንኳን ይህንን እያደረጉ ሰዎች ግን የራሳቸው አስተሳሰብ የፈጠረውን እምነት በመውሰድ እግዚአብሄርን በመፈታተን ቀጥለዋል፡፡ በሌላ አነጋገር በራሳቸው መንገዶችና አስተሳሰቦች ላይ ሙጭጭ የሚሉትን ያህል በእግዚአብሄር ላይም ሙጭጭ በማለት ቀጥለዋል፡፡
 
እግዚአብሄር በዚህ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ የሰው ዘር ሐጢያቶች በሙሉ እንዲወገዱ አድርጓል፡፡ እርሱ የነገረን ነገር ቢኖር በጌታችን ሥራዎች የሚያምን እምነት እንዲኖረን ነው፡፡ ነገር ግን ሰዎች አሁንም ድረስ ራስ ወዳድ ሆነው እግዚአብሄርን እየተገዳደሩት ነው፡፡
 
እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወደ እርሱ እንድናመጣ ነግሮናል፡፡ ሁሉንም በሰማያዊው፣ በሐሐምራዊውና በቀዩ ማግ በማስወገድም የሐጢያትን ስርየት ሰጥቶናል፡፡ እግዚአብሄር የሰማያዊውን፣ የሐምራዊውንና የቀዩን ማግ እምነት እንድናመጣ ሲነግረን ሰዎች አሁንም በዚህ ባለማመን የራሳቸውን መምህር እየናቁ ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ይረገማሉ፡፡
እነርሱ ለመሲሁ የሚፈልገውን ሳይሆን የማይፈልገውን ነገር ሲያቀርቡለት ይቆጣል፡፡ እነርሱ በእግዚአብሄር ፊት ግትርነታቸውን በማምጣት ‹‹እስከዚህ ድረስ እምነቴን ጠብቄያለሁ፡፡ ጥሩ አድርጌ ለሰራሁት ሥራ አመስግነኝ!›› በማለት ይነዘንዙታል፡፡ ይህ እምነታቸው በዚህ ሁሉ ዘመን ውስጥ የማይረባ ሆኖ ሳለ እምነታቸውን ስለጠበቁ እግዚአብሄር ያመሰግናቸዋልን?
 
በሕይወታችን ውስጥ ግትርነት በተገቢ መንገድ የሚያስፈልግባቸው ጊዜያቶች ሊኖር ይችላል፡፡ ነገር ግን የተሳሳተ እምነት ግትርነት በእግዚአብሄር ፊት ፈጽሞ የማይረባ ነው፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን በማስወገድ ረገድ ሰማያዊውን፣ ሐምራዊውንና ቀዩን ማግ ተጠቅሞዋል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሄር ሐምራዊውን ማግ እንደተጠቀመ፣ ቀይ ማግን ብቻም እንደተጠቀመ፣ የብረት ሰንሰለቶችንም እንደተጠቀመ አይናገርም፡፡ የናይሎን ማግ ስለ መጠቀሙም አልተጠቀሰም፡፡ መሲሁ በእግዚአብሄር ቤትና ለእኛ በተሰጠን በደህንነት ሕጉ ውስጥ የሰማያዊ፣ የሐምራዊና የቀይ ማግ እምነትን ጠይቋል፡፡
 
ክርስቲያኖች በኢየሱስ ክርስቶስ የሚያምኑና እርሱን የሚከተሉ ናቸው፡፡ እኛም እንደዚሁ ክርስቲያኖች ነን፡፡ ነገር ግን የሐጢያቶቻቸውን ስርየት ሳይቀበሉ ኢየሱስን አዳኛቸው አድርገው የሚያምኑና የሰማያዊው፣ የሐምራዊውና የቀዩ ማግ እምነት የሌላቸው ክርስቲያኖች ለሲዖል የታጩ አስመሳይ ናቸው፡፡ ምክንያቱም የሚያምኑት በራሳቸው መንገድ መሰረት ነው፡፡ እግዚአብሄር እነዚህን ሰዎች ይተዋቸዋል፡፡ ምክንያቱም ሐይማኖተኞች እንጂ እውነተኛ ክርስቲያኖች አይደሉም፡፡
 
ቢያንስ በእግዚአብሄር ፊት ሁላችንም እውነተኞች መሆንና የራሳችንን ማንነት በትክክል ማወቅ አለብን፡፡ በየቅጽበቱ፣ በየደቂቃውና በየሰከንዱ በሐጢያቶቻችን ምክንያት ለሲዖል የታጨን መሆናችነን መናዘዝ አለብን፡፡ በመሲሁ ፊት ሁላችንም የሰማያዊው፣ የሐምራዊውና የቀዩ ማግ እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡ እንደዚህ ማመን ትክክለኛ ነገር ነው፡፡ በምንናዘዝበት ጊዜ ሁሉ መሲሁ ስለ እኛ ያደረገልንን፤ እኛን ከሐጢያት ለማዳን መጠመቁን በስቅለቱም ለገዛ ሐጢያቶቻችን መኮነኑን ማስታወስና በየጊዜውም ደህንነታችንን መረዳት አለብን፡፡ እግዚአብሄር ከእኛ የሚፈልገው እምነት ይህ ነው፡፡
 
መሲሁ እንድናደርግ የነገረንን በትክክል እስካላደረግን ድረስ እግዚአብሄርን በጭራሽ ልናስደስተው አንችልም፡፡ ለምን? ምክንያቱም እርሱ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ ዘላለማዊ አዳኛችን እንደሆነ ሁሉ እኛም እግዚአብሄር ለእኛ ያደረገውን ነገር በየቅጽበቱ ማመን ያስፈልገናል፡፡ የሰማያዊው፣ የሐምራዊውና የቀዩ ማግ እምነት እውነት ስለሆነ በየቀኑ ለምንሰራቸው ሐጢያቶቻችን ስርየት ይህ እምነት ይበልጥ አስፈላጊ ነው፡፡
 
 
እኛ የጥረቶቻችንን ውጤቶች ሰጥተነው ቢሆን ኖሮ እግዚአብሄር ይደሰት ነበርን?
 
ለእግዚአብሄር የምድርን ነገሮች ሰጥተነው ቢሆን ኖሮ በላያችን ላይ የእርሱን ቁጣ እያከማቸን ብቻ ሳይሆን እርሱን በመገዳደርም ትልቅ ሐጢያት እየሰራን ይሆን ነበር፡፡ የዚህ ዓይነቱ እምነት ክህደት ነው፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሄርን የሚቃወም ነውና፡፡ በዚህ ምድር ላይ ያለው ነገር ምንም ያህል ውድና የከበረ ቢሆንም እግዚአብሄርን ሊያስደስተው አይችልም፡፡ የዚህን ዓለም ቁስ ነገሮች ለእግዚአብሄር ማቅረብ እግዚአብሄር የሚያመሰግነው ትክክለኛ እምነት አይደለም፡፡ በዓለም አተያይ ምንም ያህል ጥሩ ቢሆኑም እግዚአብሄር እንደ እነዚህ ያሉ ቁሳዊ ነገሮችን አይቀበልም፡፡ እግዚአብሄር በተጨባጭ ከእኛ የሚፈልገው ዓይነት እምነት ሊኖረንና ይህንንም እምነት ልንሰጠው ይገባናል፡፡
 
እምነታችን በተጻፈው የእግዚአብሄር ቃል የሚያምን መሆን አለበት፡፡ እግዚአብሄር ከእኛ የጠየቃቸውን መባዎች በትክክል የሚያቀርብ እምነት መሆን አለበት፡፡ በሚያልፈው በእያንዳንዱ ቅጽበት እግዚአብሄር ያደረገልንን ነገር መረዳት አለብን፡፡ ድካሞቻችንንና አለመብቃቶቻችንንም ማመን አለብን፡፡ እግዚአብሄር ለእኛ የሰጠንን የተትረፈረፉ በረከቶች ማስታወስ አለብን፡፡ ለእኛ ያደረገውን ነገር በትከክል ማወቅና ማመን አለብን፡፡ እርሱ በፈቃዱ ተገናኝቶናልና፡፡
 
በረቂቅ መንፈሳዊነት ላይ የተመሰረቱ እምነቶችን ሁሉ መጣል አለብን፡፡ እምነታችን እግዚአብሄር በተናገረው ቃል የሚያምን ብቻ መሆን አለበት፡፡ ለእግዚአብሄር ልንሰጠው የሚገባን የዚህን እምነት መባዎች ነው፡፡ እግዚአብሄር የሚደሰተው፣ የሚገናኘንና እምነታችንን የሚቀበለው ከትክክለኛ እምነት የመነጩ መባዎችን ስንሰጠው ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር ለእኛ ያዘጋጃቸውን በረከቶች ሁሉ የሚሰጠን ይህንን ስናደርግ ነው፡፡
 
በቃሉ ላይ ስንመሰረት ‹‹እግዚአብሄር በትክክል ከእኛ የሚፈልገው እምነት ምንድነው? እርሱ የሚፈልገው ጸሎት ምን ዓይነት ጸሎት ነው?›› ብለን ማሰብ አለብን፡፡ ያን ጊዜ እግዚአብሄር ከእኛ የሚፈልገው ጸሎት የእምነት ጸሎትን እንደሆነ እንገነዘባለን፡፡ ጌታችን በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ ውስጥ ባለው የደህንነት እምነት እግዚአብሄር ባደረገው ውስጥ ያለውን የእምነት ጸሎት ከእኛ ይፈልጋል፡፡ እግዚአብሄር ከእኛ የሚፈልገው ነገር በእምነት የሆነውን ይህንን የምስጋና ጸሎት ነው፡፡ እኛ ልንሰጠው የምንሞክረውን ወይም በእግሩ ሥር የምናስቀምጥለትን ማንኛውንም የራሳችንን ፈጠራ በጭራሽ አይቀበልም፡፡ እኛ በፍጹም ይህንን ማድረግ እንደማይኖርብን መገንዘብ አለብን፡፡
 
የኢየሱስ ጥምቀት
 
የኢየሱስ መስቀል
 
እግዚአብሄር ‹‹አይደለም፤ አይደለም፡፡ እኔ ለእናንተ የምፈልገው እምነት ያ አይደለም፡፡ እኔ ለእናንተ ተጠምቄያለሁ፤ ተሰቅያለሁ፤ ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ ለማስወገድም ጥምቀትን ወስጃለሁ፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት ለእነዚህ ሐጢያቶች ተኮንኜ በመስቀል ላይ ከመሞቴ በፊት ሐጢያቶቻችሁን በራሴ ላይ መውሰድ ስለነበረበኝ ነው፡፡ እኔ አዳኛችሁ ነኝ፡፡ ደግሞም አምላካችሁም ነኝ፡፡ እኔ የነገሥታት ንጉሥ ነኝ፡፡ ነገር ግን እኔ አምላካችሁ በመሆኔ ወደዚህ ምድር መጥቼ ሁሉን ፈጸምሁ፡፡ ከልባችሁ በእኔ እንድታምኑ፣ በልባችሁ ውስጥም የእኔን ሥልጣን እንድትቀበሉና እኔ እውነተኛ አምላካችሁ መሆኔን ከሙሉ ልባችሁ እንድትታዘዙ እፈልጋለሁ›› ብሎ እየነገረን ነው፡፡ እግዚአብሄር ሰማያዊውን፣ ሐምራዊውን፣ ቀዩን ማግና ጥሩውን በፍታ የሰጠን ይህንን አስቦ ነው፡፡ እግዚአብሄር ከእኛ የሚፈልገው እምነትም ይኸው ነው፡፡
በትክክል ይህ የሰማያዊው፣ የሐምራዊውና የቀዩ ማግ እምነት ያስፈልገናል፡፡ ለራሳችሁ እንዲህ ብላችሁ ታስቡ ይሆናል፡፡ ‹‹አሁንም መኖር ይቻላል፡፡ አሁንም ደህና ነኝ፡፡ ነገሮች ጥሩ ይሆናሉ፤ ካልተሰበረ ለምን እጠግነዋለሁ? በዚህ መንገድ በትክክል የማምነው ለምንድነው? በዚህ መንገድ ወይም በዚያ መንገድ ባምን ባላምን ሁሉም ተመሳሳይ አይደሉምን?›› ተመሳሳይ አይደሉም! በልባችሁ ውስጥ ከዚህ ውጪ የሆነ እምነት ካለ ፈጽሞ አልዳናችሁም፡፡ ምክንያቱም በእነዚህ ዓይነት ልቦች ውስጥ አሁንም ሐጢያት ይገኛልና ልባችሁን ዘወር አድርጋችሁ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ከልብ ወደሚያምን እምነት መመለስ አለባችሁ፡፡
 
በእውነተኛው ወንጌል የሚያምኑ ሰዎች ልብና የማያምኑ ሰዎች ልብ በመሰረቱ እርስ በርስ የተለያዩ ናቸው፡፡ እግዚአብሄርም ይህንን ያውቃል፡፡ እኛም ዳግመኛ የተወለድነው እናውቃለን፡፡ ራሳችሁን ስታውቁ መመለስ አለባችሁ፡፡ ‹‹አቤቱ እኔ በእርግጥም ሐጢያተኛ ነኝ፡፡ እባክህ አድነኝ፡፡›› ልባችሁን በዚህ መንገድ ስትመልሱ፣ ደህንነታችሁን ስትሹ እግዚአብሄር በእውነቱ ይገናኛችኋል፡፡
 
 

ጌታችን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖናል፡፡ 

 
ጌታችን የተጠመቀውና የተሰቀለው ለእኛ ነው፡፡ በማቴዎስ 3፡15 ላይ እንደተጻፈው ጌታ ለእኛ ያደረገው ይህ ነው፡፡ እኛም እናምንበታለን፤ ለዚህም እናመሰግነዋለን፡፡ ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችን ሁሉ ወደ እርሱ ተሻገሩ፡፡ እርሱ በተሰቀለ ጊዜ እነዚህን ሐጢያቶች በሙሉ ወደ መስቀል የወሰዳቸው ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ስለወሰደ ነው፡፡ እርሱ የተኮነነው ለእኛ ሐጢያቶች ብቻ ሳይሆን ለመላው ዓለም ሐጢያቶችም ጭምር ነው፡፡
 
ጌታችን ለመገናኛው ድንኳን ግንባታ የሚውሉትን ቁሳቁሶች እንድናመጣለት ሲነግረን ወይም ማንኛውንም ነገር በሚነግረን ጊዜ ሁሉ ሁልጊዜም ተራን ይከተላል፡፡ ሁልጊዜም ‹‹ሰማያዊ፣ ሐምራዊና ቀይ ማግ አምጡልኝ›› በማለት ይነግረናል፡፡ ሰማያዊው ማግ ሁልጊዜም በመጀመሪያ ይመጣል፡፡ ይህንን ተከትሎም በእግዚአብሄር ቃል እንድናምን የሚነግረንን ያማረውን በፍታ ይጠቅሳል፡፡ በመጀመሪያ በመስቀሉ ቃል ከዚያም በኢየሱስ ጥምቀት ማመን በመጀመሪያ ዕይታ ትክክል መስሎ ሊታይ ይችላል፡፡ ይህ ግን በእርግጥም ስህተት ነው፡፡ ኢየሱስ በመስቀል ላይ ደሙን ያፈሰሰው በመጀመሪያ ስለተጠመቀ ነው፡፡ እንደገና እነግራችኋለሁ፤ በመጀመሪያ በመስቀሉ ደም ከዚያም በጥምቀቱ ማመን በፍጹም ትክክል አይደለም፡፡ እግዚአብሄር በፍጹም ይህንን እምነት አይፈቅድም፡፡
 
ጌታችን የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር በመምጣት 30 ዓመት ሲሞላው ሐጢያቶቻችንን ሁሉ በራሱ ላይ ለመውሰድ በመጀመሪያ ተጠመቀ፡፡ ይህንን ካደረገ በኋላ እነዚህን የዓለም ሐጢያቶች በመስቀል ላይ በመሸከም በስቅለት ተኮነነ፡፡ ከዚያም እንደገና ከሙታን ተነስቶ አዳኛችን ሆነ፡፡ ስለዚህ እርሱ ሥራዎቹን በፈጸመበት ስርዓት መሰረት ጌታ ለእኛ ባደረገው ነገር ማመን ያለብን በዚህ መንገድ ነው፡፡ እምነታችን ግራ ሳይጋባና ሳይናወጥ ጽኑ ሆኖ የሚቆመው ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡ ወንጌልን ለሌሎች በምናሰራጭበት ጊዜም የምናሰራጨው በዚህ መሰረት ይሆናል፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሄርን በሚያስደስተውና እርሱ ባስቀመጠው መሰረት ማመን አለብን፡፡
 
እግዚአብሄር እንድታመጡለት የሚጠይቃችሁ የእምነት መባዎች ምንድናቸው? የሰማያዊውን፣ የሐምራዊውን፣ የቀዩን ማግና የጥሩውን በፍታ እምነት እንድታቀርቡ አልነገራችሁምን? እንዲያው በአጋጣሚ የተገላቢጦሹን አምናችሁ አታውቁምን? ‹‹በዚህ መንገድ አመንሁ ወይም በዚህ መንገድ የሚያመጣው ነገር የለም፡፡ አሁንም አምናለሁ፡፡ የሚያስፈልገውም ይኸው ነው፡፡ በመጀመሪያ በቀዩ ማግ አምናለሁ፡፡ ከዚያም በሰማያዊው ማግ፣ በመጨረሻም በሐምራዊው ማግ አምናለሁ፡፡›› የምታምኑት እንደዚህ ከሆነ እንደገና ማመን አለባችሁ፡፡ እግዚአብሄር ይህንን የተገላቢጦሽ እምነታችሁን አይቀበለውም፡፡
 
አምላካችን የፍትህና የእውነት አምላክ ነው፡፡ ስለዚህ የተሳሳተ እምነትን አይቀበልም፡፡ እምነት ስርዓቱ ከተዛባ ሊቆም ስለማይችል እግዚአብሄር ቢፈልግም እንኳን ይህንን እምነት አይደግፍም፡፡ የቤቱን ግንባታ ከጨረስን በኋላ መሰረትን ልንጥል ሙከራ ማድረግ አንችልም፡፡ ኢየሱስ የተሰቀለው ሐጢያቶቻችንን በጥምቀቱ ስለወሰደ ነው፡፡
 
ስለዚህ እግዚአብሄር በነገረን መሰረት ማመን አለብን፡፡ ለትክክለኛው እምነት የማዕዘን ድንጋይ የሚቆመው በዚህ መንገድ ነው፡፡ እግዚአብሄር በትክክል በቅንነትና በጽድቅ ስላዳነን በራሳችን ፈቃድ የእርሱን ስርዓት ማፋለስ አንችልም፡፡ በመጀመሪያ በመስቀሉ ደም ከዚያም በኢየሱስ ጥምቀት የምናምን ከሆነ ይህ እምነት በአጭሩ ስህተት ነው፡፡ እንደዚህ በሚያምኑ ሰዎች ልቦች ውስጥም ሐጢያት አለ፡፡ ምክንያቱም እምነታቸው የተገላቢጦሽ ስለሆነ ሐጢያቶቻቸው አልተወገዱም፡፡ ይህ በእርግጥም የሚያስገርም ነው፡፡ አስገራሚው እውነት ይህ ነው፡፡
 
ብዙዎቻችን በመሲሁ ስናምን የከረምነው ኢየሱስ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ብቻ ነው፡፡ ‹‹ኢየሱስ ሐጢያቶቼን በሙሉ ወስዶ በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰስ ከነኔዬን ሁሉ ተሸከመ፡፡ ስለዚህ ሙሉ በሙሉ ድነናል፡፡ ደህንነታችን የመጣው ስለ እኛ በመስቀል ላይ ከሞተው ከክርስቶስ ነው፡፡ በዚህ የሚያምን ሁሉ አሁን ድኖዋል›› ብለን አምነናል፡፡ ከዚያም የኢየሱስን ጥምቀት እውነተኛ ትርጉም ተረዳን፡፡ ስለዚህ በተሳሳተው እምነታችን ላይ የእውነትን እምነት ጨመርን፡፡ ከዚያ ምን ተከሰተ? ሐጢያቶቻችን በጭራሽ አልተወገዱም፡፡ የዚህ ዓይነቱ እምነት በዕውቀትና በሐይማኖት ትምህርት ላይ የተመሰረተ ብቻ ስለሆነ እውነተኛና ተጨባጭ የልባችን እምነት ሊሆን አልቻለም፡፡
 
እምነታችሁ ይህን መሰል ከሆነ በፍጥነት መመለስና መለወጥ አለባችሁ፡፡ ከሁሉ በፊት እምነታችሁ ትክክል እንዳልነበረ በግልጽ ማመን አለባችሁ፡፡ ከዚያም ፈጥናችሁ የእምነት መሰረታችሁን ማደስ ይኖርባችኋል፡፡ ማድረግ የሚኖርባችሁ ስርዓቱን እንደገና መለወጥ ነው፡፡ ‹‹ኢየሱስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በአጥማቂው ዮሐንስ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቆ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ወሰደ፡፡ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ የተሻገሩት ስለተጠመቀ ነው፡፡ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ በዚህ መንገድ ወደ ኢየሱስ ስለተሻገሩ ሐጢያቶቼ በሙሉ ወደ ኢየሱስ ተሻግረዋል፡፡ ከዚያም ለሐጢያቶቼ ደመወዝ ይሆን ዘንድ ደሙን በመስቀል ላይ አፈሰሰ፡፡›› ማመን የሚገባችሁ እንዲህ ነው፡፡
 
‹‹በዚህ መንገድ ወይም ወይም በዚያ መንገድ ባምን ማን ያገባዋል? ዋናው ጉዳይ በእነዚህ በአራቱ የጌታ አገልግሎቶች ማመን ነው፡፡ በዚህ ስርዓት መሰረት ካልሆነ በስተቀር ተብሎ ለምን ግትር ይኮናል?›› እንዲያው በአጋጣሚ ይህንን አመለካከት የሙጥኝ ብላችሁ ይዛችሁ አታውቁምን? እንግዲያውስ ይህንን እውነት በልባችሁ መያዝ ይገባችኋል? ኢየሱስ በመስቀል ላይ የሞተው ከተጠመቀ በኋላ ነው፡፡ ልምኑበት የሚገባው እውነት ይህ ነው፡፡
 
መንፈስ ቅዱስ ኢፍትሃዊነትን በጭራሽ አይደግፍም፡፡ እግዚአብሄር መንፈስ ቅዱስ እምነታችንን የሚደግፈው መሲሁ በዚህ ምድር ላይ ያደረገልንን ስናምን ብቻ ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ‹‹ስለዚህ በእነዚህ አራት የኢየሱስ ሥራዎች በሙሉ አምናችኋል፡፡ አሜን፡፡ በትክክል አመናችሁም በተገላቢጦሽ አመናችሁም በዚህ መንገድ ወይም በዚያ መንገድ አመናችሁ በማንኛውም መንገድ እስካመናችሁ ድረስ ጥሩ ነው፡፡ አሜን፤ እሺ እንግዲያውስ ልጆቼ ናችሁ›› አይለንም፡፡
 
መሲሁ ኢየሱስ በእግዚአብሄር አብ ፈቃድ መሰረት ወደዚህ ምድር መጥቶ እግዚአብሄር ያዘዘውን ነገር አደረገ፡፡ በዚህ ምድር ላይ የሕይወቱን 33 ዓመታት የኖረው በዚህ መንገድ ነው፡፡ እርሱ ወደዚህ ምድር መጥቶ በመጠመቅ፣ በመሰቀል፣ በትንሳኤ በመነሳትና ወደ ሰማይ በማረግ የደህንነት ሥራውን አጠናቀቀ፡፡ መንፈስ ቅዱስንም ሰጥቶናል፡፡
 
እግዚአብሄር መንፈስ ቅዱስ የሐጢያት ስርየትን በተቀበልነው ልብ ውስጥ ይኖራል፡፡ በማንነታቸው እግዚአብሄር ለእነርሱ ባደረገላቸው ነገር የሚያምኑትን እምነት ይደግፋል፡፡ በራሳችን አስተሳሰቦች በፍጹም ማመን የማንችለው ለዚህ ነው፡፡ እናንተና እኔ ከልባችን በኢየሱስ ብናምን በተገላቢጦሽ ስርዓት ያመናችሁበት አጋጣሚ አልነበረምን? እንደዚያ ከሆነ ዳግመኛ በትክክል ማመን አለባችሁ፡፡
 
እንደዚህ ስታደርጉ መንፈስ ቅዱስ በልባችሁ ውስጥ ይሰራል፡፡ በድካሞች የተሞላን ብንሆንም መንፈስ ቅዱስ ልባችንን አርግቦታል፡፡ ከእኛ ጋር ነው፡፡ በእርሱ ፊት ስንቀርብም ጸጋውን ይሰጠናል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ሐይልን ይሰጠናል፡፡ ብርታትን ይሰጠናል፤ ያጽናናናል፤ ይባርከናል፤ ብሩህ ፍጻሜና ተስፋን ሰጥቶናል፡፡ የምናምነውንም ወደ እርሱ የዘላለም መንግሥት ለመግባት የሚያስችለንን ብቃት እንዳናጣ ከእምነት ወደ እምነት ይመራናል፡፡
 
እግዚአብሄር እንድናደርገው በሚፈልገው ነገር ወይም መባዎቻችንን ወደ እርሱ እንድናመጣ በነገረን ነገር ስናምን የሚያስፈልገን ይህ ነው፡፡ ማለትም እርሱ በውሃና በመንፈስ ያዳነን መሆኑን ማመን አለብን፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ያሉት ዕቃዎች በሙሉ አስፈላጊ ናቸው፡፡ ምክንያቱም ሁሉም ከውሃና ከመንፈስ የመወለድን ምስጢር ይነግሩናልና፡፡ በሌላ አነጋገር በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ባሉት ብዙ ነገሮች አማካይነት እግዚአብሄር ስለ አንድ ነገር -- ስለ ውሃውና መንፈሱ ወንጌል ሊነግረን ፈልጎዋል፡፡
 
 
የእምነታችን መሰረት በጣም ወሳኝ ነው፡፡
 
በመጀመሪያ የእምነታችንን መሰረት በጽናት ሳንመሰርት የእምነት ቤታችንን ብንሰራ በኢየሱስ ለረጅም ጊዜ ብናምንም ብዙ ሐጢያቶችን እናከማቻለን፡፡ ብዙ የንስሐ ጸሎቶችን እንጸልያለን፡፡ በይበልጥ ደግሞ ግብዝ ሐጢያተኞች እንሆናለን፡፡ ነገር ግን ጌታችን በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ ባዳነን የደህንነት ስጦታ ስናምን ሁላችንም የእግዚአብሄር ፍጹም ልጆች መሆን እንችላለን፡፡ ስለዚህ ሁላችንም በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ እውነት ማመን አለብን፡፡ በዚህ መንገድ ሁላችንም የእግዚአብሄር ልጆች እንሆናለን፡፡
 
የእምነት መሰረታቸው ምሉዕ የሆኑ ሰዎች ራሳቸው ድካሞች ቢኖራቸውም ሁልጊዜም ክህነቱን በብሩህ ብርሃን መስራት ይችላሉ፡ በሌላ አነጋገር እነዚህን የክህነት ተግባራቶች በሙሉ መፈጸም የሚችሉት የሐጢያት ስርየት እንዲያገኙ ወደ እግዚአብሄር በመጸለይና ይህንን ወንጌል በእግዚአብሄር ፊት በማገልገል የዚህን ዓለም ሰዎች በሙሉ ከልባቸው በዕቅፎቻቸው ውስጥ በመያዝ ነው፡፡
 
በንጽጽር የእምነት መሰረታቸው ግልጽ ያልሆነ ሰዎች ጊዜ በነጎደ ቁጥር ይበልጥ ግብዞች ይሆናሉ፡፡ ክፉዎች ይሆናሉ፡፡ ይበልጥ ግብዝ የሆኑ ሐይማኖተኞች ይሆናሉ፡፡ ጌታችን ዛፍን በፍሬው እንደምናውቅ ስለነገረን የእነዚህ ሰዎች ፍሬ አስጸያፊ፣ የረከሰና ግብዝ ነው፡፡ ነገር ግን ዳግመኛ የተወለድን ሰዎች በፍጹም ግብዞች አይደለንም፡፡ ሁሉም እውነተኞች ናቸው፡፡ ድካሞች ቢኖሩባቸውም ከልባቸው እውነተኞች ናቸው፡፡ ድካሞቻቸውንና ስህተቶቻቸውን ያውቃሉ፡፡ ሁልጊዜም ብሩህ በሆነው ብርሃን ውስጥ ይኖራሉ፡፡ ጌታችንን ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ለመደምሰስ ስለተጠመቀና ስለተሰቀለ፣ በዚህ መንገድም ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንዲወገዱ ስላደረገ በዚህ እውነት በማመን የሐጢያቶቻችንን ስርየት አግኝተናል፡፡ የማንበቃ ብንሆንም፣ ሐጢያቶችንና ስህተቶችን ብንሰራም፣ ደካሞች ብንሆንም የእምነት መሰረታችን ጠንካራ ስለሆነ ሕይወታችን አሁንም ብሩህ ነው፡፡ ምክንያቱም ልባችን ሁልጊዜም ሐጢያት አልባ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ከድካሞቻችን የተነሳ ልንስት እንችላለን፡፡ ነገር ግን በእርግጥም ሐጢያት አልባ ስለሆነን ሌሎችንና ራሳችንን ወደ ጥፋት ለመስደድ አንስትም፡፡ የማንበቃ ብንሆንም ደረጃ በደረጃ ወደፊት እየተጓዝንና ወንጌልንም በብዙ እያገለገልን እግዚአብሄርን በሚያስደስተው መንገድ ላይ እንጓዛለን፡፡ ይህ ሁሉ የተከናወነው ኢየሱስ ፈጽሞ ስላዳነን ነው፡፡
 
መሲሃችንና አዳኛችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ መንገድ በሁለቱ ማጎች ሙሉ በሙሉ ባያድነን ኖሮ በጭራሽ መዳን አንችልም ነበር፡፡ የዳንነው እርሱ ስላዳነን ነው፡፡ የምናምነው፣ ወንጌልን የምናሰራጨውና እርሱን በእምነታችን የምናመሰግነው ለዚህ ነው፡፡ እግዚአብሄርን የምናመሰግነው በእምነታችን ነው፡፡ እርሱን የምናገለግለው በእምነታችን ነው፡፡ እርሱን የምንከተለውም በእምነታችን ነው፡፡ በሌላ አነጋገር እኛ እግዚአብሄርን የምናስደስተው በእምነታችን ነው፡፡ እኛ የእምነት መሰረታችን ጽኑ ሆኖ የቆመልን ሰዎች ነን፡፡
 
የእምነት መሰረታቸው በትክክል ያልተመሰረተ ሰዎች እንደገና ሊመሰርቱት ይገባቸዋል፡፡ ዕብራውያን 6፡1-2 እንደዚህ የሚለው ለዚህ ነው፡- ‹‹ስለዚህ የክርስቶስን ነገር መጀመሪያ የሚናገረውን ቃል ትተን ወደ ፍጻሜ እንሂድ፤ መሰረትን ደግመን አንመስርት፡፡ እርሱም ከሞተ ሥራ ንስሐና በእግዚአብሄር እምነት፣ ስለ ጥምቀቶችና እጆችንም ስለ መጫን፣ ስለ ሙታንም ትንሳኤ፣ ስለ ዘላለም ፍርድም ትምህርትም ነው፡፡››
 
ይህ ምንባብ ምን ይነግረናል? ‹‹ኢየሱስ ለምን ተጠመቀ?›› ‹‹ይህ ጥምቀት በብሉይ ኪዳን ለነበረው የእጆች መጫን አካል ነውን?›› ‹‹የዘላለም ፍርድስ ምንድነው?›› የሚሉትን ጥያቄዎች እንድናውቅ፣ በግልጽ እንድናረጋግጥና ጽኑ መሰረትን እንድንመሰርት ይነግረናል፡፡ በእነዚህ ነገሮች ተናውጠን መሰረታችንን ዳግመኛ እንዳንመሰርት ይነግረናል፡፡ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ የሚያምን እምነት ጌታችን ደህንነታችንን ፈጽሞ እንዳጠናቀቀው የሚያምን ሙሉ እምነት ነው፡፡ በዚህ የእምነት መሰረት ላይ በጽናት መቆም አለብን፡፡ ከዚያ ተነስተንም መሮጥ አለብን፡፡ የእምነትን ሩጫ መሮጥ አለብን፡፡
 
አንዳንድ ሰዎች ከላይ የተጠቀሰውን የዕብራውያን ምንባብ ሐጢያቶቻችን በጥምቀቱ አማካይነት ወደ ኢየሱስ ተሻግረዋል ብለን እንደገና መናገር የለብንም ማለቱ ነው፤ ምንባቡ የሚነግረን የእምነትን መሰረት እንደገና መገንባት አያስፈልገንም እያለ ነው በማለት ይተረጉሙታል፡፡ ነገር ግን የእምነት መሰረታችን ከመጀመሪያውም በትክክል ተገንብቶ ቢሆን ኖሮ እግዚአብሄር ዳግመኛ እንድንመሰርተው ይነግረን ነበርን? ይህ ምንባብ የሚነግረን ትክክለኛ የእምነት መሰረት ያላቸው ደግሞ ይበልጥ ጽኑና ጠንካራ በማድረግ ወደፊት መሮጥ እንደሚገባቸው ነው፡፡
 
እግዚአብሄር እኛን ለማዳን ሙሴን የመገናኛውን ድንኳን እንዲሰራና ከሕዝቡም መባዎችን እንዲቀበል አዘዘው፡፡ የእስራኤልንም ሕዝብ ወርቅ፣ ብር፣ ናስ፣ ሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግ፣ ጥሩ በፍታ፣ የፍየል ጠጉር፣ የቀይ አውራ በግ ቁርበት፣ የአቆስጣ ቁርበትና የግራር እንጨት እንዲያመጡለት አዘዛቸው፡፡ በእነዚህ ቁሳቁሶች ውስጥ እንደተገለጠው ጌታችን እናንተንና እኔን ከዓለም ሐጢያቶች ለማዳን በእርግጥም የደህንነትን ስጦታ ሰጥቶናል፡፡ እግዚአብሄር በዚህ መንገድ ለእስራኤሎች እነዚህን መባዎች እንዲያቀርቡለት፣ የመገናኛውን ድንኳን እንዲሰሩ፣ የመስዋዕት ስርዓቱን እንዲመሰርቱ ነገራቸው፡፡ በዚህ የመስዋዕት ስርዓት መጠየቆች መሰረትም የመስዋዕት መባዎቻቸውን ያቀረቡትን እስራኤሎች ሐጢያቶች ይቅር አለ፡፡
 
 
እምነታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የሆነውን የደህንነታችንን ፍጹም ፍጻሜ በሚተነብየው በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በማመን ሙሉ ሆንዋል፡፡
 
እኛ በኢየሱስ ክርስቶስ በተፈጸመው ፍጹም እምነት ማመን ሳንችል ቀርተን ፈጥነን የእምነታችንን መሰረት በጽናት ካልመሰረትን እምነታችን ሁልጊዜም ይናወጣል፡፡ ጌታችን ሙሉ በሙሉ ያዳነን የመሆኑን እውነታ ካላወቅን፣ ካልተረዳንና ካላመንን በጥረቶቻችን ደህንነትን ለማግኘት በመሞከር እናበቃለን፡፡ የዚህ ዓይነቱ እምነት ሙሉ አይደለም፡፡ የተሳሳተ ነው፡፡
 
ወደ ዕብራውያን 10፡26-31 እንሂድ፡- ‹‹የእውነትን እውቀት ከተቀበልን በኋላ ወደን ሐጢአት ብናደርግ ከእንግዲህ ወዲህ ስለ ሐጢአት መስዋዕት አይቀርልንም፡፡ የሚያስፈራ ግን የፍርድ መጠበቅ ተቃዋሚዎችንም ሊበላ ያለው የእሳት ብርታት አለ፡፡ የሙሴን ሕግ የናቀ ሰው ሁለት ወይም ሦስት ቢመሰክሩበት ያለ ርህራሄ ይሞታል፡፡ የእግዚአብሄርን ልጅ የረገጠ፣ ያንንም የተቀደሰበትን የኪዳኑን ደም እንደ ርኩስ ነገር የቆጠረ፣ የጸጋውንም መንፈስ ያክፋፋ እንዴት ይልቅ የሚብስ ቅጣት የሚገባው ይመስላችኋል? በቀል የእኔ ነው፤ እኔ ብድራትን እመልሳለሁ ያለውን እናውቃለንና፡፡ ደግሞም፡- ጌታ በሕዝቡ ይፈርዳል፡፡ በሕያው እግዚአብሄር እጅ መውደቅ የሚያስፈራ ነው፡፡››
 
ምንባቡ የእውነትን ዕውቀት ከተቀበልን በኋላ ወደን ሐጢያት ብንሰራ ለሐጢያቶች መስዋዕት የሚሆን ነገር እንደማይቀርልን ነገር ግን አስፈሪ ፍርድ እንደሚጠብቀን ይነግረናል፡፡ እዚህ ላይ የእውነትን ዕውቀት ከተቀበሉ በኋላ ወደው ሐጢያት የሚሰሩ የተባሉት ቢያውቁትም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የማያምኑት ናቸው፡፡ እግዚአብሄር በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ ያዳነን የመሆኑን፣ በወርቅ፣ በብርና በናስ ያዳነን የመሆኑን፣ የመገናኛውንም ድንኳን ጣሪያ በሰማያዊ፣ በሐምራዊ፣ በቀይ ማግና በጥሩ በፍታ፣ በፍየል ጠጉር፣ በቀይ አውራ በግ ቁርበትና የአቆስጣ ቁርበት ሽፋኖች የሰራው የመሆኑን እውነት ማመን አለብን፡፡ ሁላችንም እነዚህን ነገሮች በግልጽ ማወቅና የእምነታችንን መሰረት በጽናት መመስረት አለብን፡፡
 
ጌታችን ሙሉ በሙሉ እንደሚያድነን ቃል ገብቷል፡፡ ጊዜው ሲደርስ ሐጢያቶቻችንን በራሱ ላይ ለመውሰድ ተጠመቀ፤ በመስቀል ላይ ሞተ፤ እንደገናም ከሙታን ተነሳ፡፡ በዚህ ሁኔታም በእርግጥ ሙሉ በሙሉ አዳነን፡፡ ስለዚህ የደህንነታችንን መሰረት ሙሉ በሙሉ በመሰረተው በዚህ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን ፈጽሞ ድነናል፡፡
 
ይህንን እውነት አውቀው ሊያምኑበት እምቢተኞች የሆኑ የመጨረሻው ፍርዳቸው ጊዜ ሲመጣ በእርግጥም የእግዚአብሄርን አስፈሪ ፍርድ ይጋፈጣሉ፡፡ ሰውነታቸው አይሞትም፤ ነገር ግን ለዘላለም ይሰቃያል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እነርሱን የሚጠብቃቸው የእሳት ቁጣ ብቻ እንደሚሆን ይነግረናል፡፡ የሲዖል ስቃያቸውም ብርቱ ስለሚሆን በእሳት የታጀበ እንደሆነ ተብራርቷል፡፡ (ማርቆስ 9፡49) ተቃዋሚዎችን የሚበላ የፍርድ መጠበቅና የእሳት ብርታት እንዳለ ይነግረናል፡፡
 
ሕጉን ከመጠበቅ መጉደል እንደዚህ ወዳለው አስፈሪ ፍርድ የሚመራ ከሆነ የእግዚአብሄር ልጅ በሰጣቸው ደህንነት የማያምኑት የሚገጥማቸው ፍርድ ምን ያህል የከፋ ይሆን? ሁላችንም አዳኛችን በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ፣ የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር በመጣው፣ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ በራሱ ላይ በወሰደው፣ እነዚህን የዓለም ሐጢያቶች በመስቀል ላይ በወሰደው፣ በስቅለቱም የሐጢያቶችን ኩነኔ ሁሉ በተሸከመው፣ ዳግመኛ ከሙታን በተነሳውና አሁንም ሕያው በሆነው ጌታ ማመን ያለብን ለዚህ ነው፡፡
 
 
ስለዚህ የእምነታችን መሰረት በጽናት መመስረት አለበት፡፡ 
 
እግዚአብሄር የመገናኛው ድንኳን እንዲሰራ ያዘዘው ለምንድነው? የመገናኛውን ድንኳን ለመሰራት ጥቅም ላይ የዋሉትን ቁሰቁሶች እያንዳንዳቸውን ስንመለከት ሁሉም ኢየሱስ ክርስቶስ የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር የመምጣቱን፣ ከአጥማቂው ዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱም ሐጢያቶቻችንን በራሱ ላይ የመውሰዱን፣ የመሞቱን፣ ዳግመኛም ከሙታን የመነሳቱን፣ ወደ ሰማይ የማረጉን፣ በእግዚአብሄር ዙፋን ቀኝ የመቀመጡንና አሁን ዘላለማዊ አምላካችን የመሆኑን እውነት እንደሚገልጡ ማየት እንችላለን፡፡ የመግቢያው በር ቋሚዎቹ፣ የናስ ኩላቦቹ፣ የመገናኛው ድንኳን ዕቃዎች በሙሉ የወንጌሉን እውነት ያሳዩናል፡፡ በሌላ አነጋገር ብሉይ ኪዳን በሙሉ ስለ ኢየሱስ ጥምቀት፣ ስለ መስዋዕቱ፣ ስለ ማንነቱና ስለ ደህንነት ሥራዎቹ ይነግረናል፡፡
 
ከብሉይ ኪዳን እስከ አዲስ ኪዳን ድረስ ኢየሱስ ስለ ውሃውና ስለ መንፈሱ ወንጌል ስለነገረን -- ማለትም የሰማያዊ፣ የሐምራዊ፣ የቀይ ማግና የጥሩ በፍታ ወንጌል -- በዚህ እውነት የሚያምኑ አጋጣሚ በሚያገኙበት ጊዜ ሁሉ ሁልጊዜም የሰማያዊውን፣ የሐምራዊውን፣ የቀዩን ማግና የጥሩውን በፍታ እውነት ይናገራሉ፡፡ ይህ እውነት ብዙ ጊዜ ስለተሰበከና ስለተደመጠ ምን ያህል የከበረ እንደሆነ ልንረሳ እንችላለን፡፡ ነገር ግን ይህ እውነት ምን ያህል አስፈላጊ ነው? የከበረ ወርቅና ብር ከብዛቱ የተነሳ እንደ ድንጋዮች ይቆጠር በነበረበት በንጉሥ ሰሎሞን የአገዛዝ ዘመን እየኖርን ይመስለናል፡፡ እኛ ይህንን እውነት በየቀኑ በእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ውስጥ ስለምንሰማ አንዳንድ ጊዜ ይህንን ደህንነት ችላ ልንለው እንችላለን፡፡ ነገር ግን ይህንን ማስታወስ ይኖርባችኋል፡፡ ይህ እውነት ከእግዚአብሄር ውጪ በማንኛውም ስፍራ ሊደመጥ አይችልም፡፡ ያለዚህ ደህነት ማንም ሊድንም ሆነ የእምነትን መሰረት በጽናት ሊመሰርት አይችልም፡፡
 
እኔና እናንተ የዳንበት እምነት ጌታችን ሙሉ በሙሉ ያዳነንና የእምነት መሰረታችንንም በአራቱ የሰማያዊ፣ የሐምራዊ፣ የቀይ ማግና የጥሩ በፍታ ፈትሎች በጽኑ የመሰረተው በሆነው እውነት የሚያምን ነው፡፡ ሁላችንም በልባችን ይህንን ማመን እንደሚገባን ደግሜ ማበከር እወዳለሁ፡፡ እግዚአብሄር ተስፋ ሰጥቶናል፡፡ በተስፋው መሰረት የሴቲቱ ዘር ሆኖ ወደዚህ ምድር በመምጣት (ዘፍጥረት 3፡15) በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ በራሱ ላይ ወሰደ፡፡ የሐጢያቻችንን ኩነኔ በሙሉም በመስቀል ላይ ተሸከመ፤ ዳግመኛ ከሙታን ተነሳ፤ በዚህም ፈጽሞ አዳነን፡፡ ይህ በቀላሉ የሚብራራና የሚስተዋል ቀላል እውነት ስለሆነ በየቀኑ ይህንን ወንጌል በመላው ዓለም መስበክ እንችላለን፡፡ በእርግጥ ይህንን እውነት የማያውቁ በጣም ብዙ ምስኪን ሰዎች አሁንም አሉ፡፡ ነገር ግን ይህንን እውነት ከማያውቁ ከእነዚህ ምስኪኖች ይልቅ ይበልጥ ምስኪኖች የሆኑት በእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ውስጥ እየኖሩ የማያምኑት ናቸው፡፡
 
እናንተ በእርግጥም የሐጢያቶቻችሁን ስርየት ተቀበላችሁ ብትሆኑም አስተሳሰቦቻችሁ አሁንም ክፉ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ቢያንስ ልባችሁ ገር ሆንዋል፡፡ ግብዞች ግን እንደዚህ አይደሉም፡፡ በውጪያዊ ገጽታቸው ራሳቸውን ገሮች አድርገው ለማቅረብ ቢሞክሩም በውስጣቸው በጣም ክፉዎች ስለሆኑ በየቀኑ እግዚአብሄርንና ብዙ ሰዎችን ያታልላሉ፡፡ እናንተና እኔ የእምነት መሰረትን በጽናት መመስረት አለብን፡፡ ጌታችን በሰጠን በዚህ ደህንነት ላይ ጸንተን በመመስረት በዚህ እያመንን በእግዚአብሄር ፊት መቆም አለብን፡፡
 
 
እንደ መገናኛው ድንኳን ቁሳቁሶች ጸንቶ የቆመ እምነት፡፡ 
 
እግዚአብሄር እነዚህን መባዎች እንድናመጣና የመገናኛውን ድንኳን እንድንሰራ ነግሮናል፡፡ እናንተና እኔ ሁላችንም ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ምድር መጥቶ በመንፈሳዊ ሁኔታ እንዳዳነን በማመን የእምነት ሰዎች መሆን አለብን፡፡ ለመገናኛው ድንኳን ጥቅም ላይ እንደዋሉት የግንባታ ቁሶች ብርቱ እምነት ይዘን በእግዚአብሄር ፊት በጽናት መቆም አለብን፡፡ ታምናላችሁን? በእርግጥ የዚህ ዓይነት እምነት አላችሁን? የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል አሁንም በእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን መሰበክ አለበት፡፡ ይህ የእውነተኛው እምነት መሰረት ስለሆነ በሚገባ ላተኩርበት አልቻልሁም፡፡
 
ብዙዎች የዚህ ዓለም የሐይማኖት ድርጅቶችና ቤተክርስቲያኖች ኢየሱስ በጥምቀቱ ሐጢያቶችን ሁሉ በራሱ ላይ የተቀበለ የመሆኑን እውነት ስለማያውቁ በፈንታው በመስቀሉ ደም ብቻ ያምናሉ፡፡ በእነዚህ ሁኔታዎች ውስጥ እንኳን ቢሆን ጌታችን አሁንም እውነቱን እንድናገኝ ፈቅዶልናል፡፡ ኢየሱስ በመስቀል ላይ የተቸነከረውና የተበሳው በአጥማቂው ዮሐንስ በዮርዳኖስ ስለተጠመቀ ነበር፡፡ በመስቀል ላይ የተሰቀለውና የተቸነከረው ወደ እርሱ የተሻገሩትን የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ስለተቀበለ ነው፡፡
 
ስለዚህ በመስቀሉ ደም በማመናቸው ብቻ የሐጢያት ይቅርታን አግኝተናል የሚሉት ሰዎች እምነት ምንም ያህል ራሳቸውን ቀድሰው የሰጡ ቢሆኑም ውሎ አድሮ የሚፈረካከስ የተሳሳተ እምነት ነው፡፡ ሕዝቡ በኢየሱስ እንዲያምን ድምጻቸውን ከፍ አድርገው ቢሰብኩም በመስቀሉ ደም ብቻ የሚያምነው እምነታቸው የሚያቀርበው የንስሐ ጸሎቶችን ብቻ ስለሆነ የሐጢያት ችግራቸውን ማቃለል አይችልም፡፡ ዝናቡ ሲዘንብ፣ ንፋሱ ሲነፍስና ጎርፉ ሲጎርፍ በቀላሉ በሚወድቅ የተሳሳተ መሰረት ላይ የተገነባ ነው፡፡
 
እኔ ራሴ በኢየሱስ ማመን ከጀመርሁበት ጊዜ ጀምሮ ከ10 ዓመታት ለሚበልጥ ጊዜ የኢየሱስን ጥምቀት በዝርዝር ሰምቼ አላውቅም ነበር፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ በእውነት ቃሉ ተገናኘኝ፡፡ ከውሃና ከመንፈስም መወለድ ቻልሁ፡፡ አሁን በመላው ዓለም እውነትን የሚሹ ነገር ግን ገና ያላገኙት ብዙ ሰዎች እንዳሉ አውቃለሁ፡፡ የውሃውንና የመንፈሱን ወንገል እንዲያምኑና ይህንንም በልባቸው በማመን የሐጢያቶቻቸውን ስርየት እንዲቀበሉ ከሁሉም ጋር መነጋገር እፈልጋለሁ፡፡
 
እናንተም ዳግመኛ ከመወለዳችሁ በፊት የሐይማኖትን ሕይወት ትኖሩ ነበር፡፡ በዚያን ወቅት ምናልባት የሰማያዊውን፣ የሐምራዊውን፣ የቀዩን ማግና የጥሩውን በፍታ ምንነት አልሰማችሁ ይሆናል፡፡ ያም ብቻ አይደለም፡፡ ምናልባትም ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችን ወደ እርሱ እንደተላለፉ ልትሰሙ ይቅርና ስለ ውሃውና ስለ መንፈሱ ወንጌልም ሰምታችሁ አታውቁም ይሆናል፡፡
 
ለክርስቲያኖች የሰማያዊውን፣ የሐምራዊውን፣ የቀዩን ማገና የጥሩውን በፍታ እውነት ማወቅና በዚያም ማመን በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ሁላችንም በእምነታችን ጸንተንና ጠንክረን መቆም የምንችለው የእምነት መሰረቱ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ ላይ ሲመሰረት ብቻ ነው፡፡ ሙሉ በሙሉ የምትድኑት፣ የእምነት መሰረታችሁንም በጽናት የምትመሰርቱትና እምነታችሁንም በዚህ መሰረት ላይ የምታንጹት እንደዚህ ስታምኑ ብቻ ነው፡፡
 
 
በእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ውስጥ ያሉትም የእምነት መሰረታቸውን በጽናት መመስረት አለባቸው፡፡ 
 
ማቴዎስ 24፡40 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በዚያን ጊዜ ሁለት ሰዎች በእርሻ ይሆናሉ፤ አንዱ ይወሰዳል አንዱም ይቀራል፡፡›› ሁላችንም ተመሳሳይ በሆነ እምነት እናምናለን፤ አብረንም በእግዚአብሄር ቤተክርሰቲያን ውስጥ ተመሳሳይ ወንጌል እናገለግላለን እያልን ሳለን እንዳንዶቻችን ወደኋላ ብንቀር ከዚህ የከፋ ምን ነገር ሊኖር ይችላል?
 
የእግዚአብሄር ቃል ግልጽና ክቡር ስለሆነ እምነት በማንም ሰው ላይ በግዴታ ሊጫን አይችልም፡፡ የእግዚአብሄር ቃል በዚህ ሁኔታ በየዋህነት ተሰብኮላችሁ ስትሰሙ በጥሩ አእምሮ ልታምኑት ይገባል፡፡ በእርግጥም የእግዚአብሄርን ቃል እየሰማችሁ እንደሆነ በማመን አእምሮዋችሁን እዚያ ላይ ማነጣጠር ይገባችኋል፡፡ የእስራኤል ሕዝብ ሙሴ የነገራቸውን ቃል በሰሙ ጊዜ የእርሱ ቃል ሳይሆን የእግዚአብሄር ቃል እንደሆነ አስተዋሉ፡፡ ልክ እንደዚሁ የእግዚአብሄር ቃል ምን እየተናገረ እንደሆነ ሲነገራችሁ በእርግጥ በዚህ የእግዚአብሄር ቃል መሰረት እያመናችሁ እንደሆነና እንዳልሆነ ለማወቅ መመርመር ያስፈልጋችኋል፡፡ ቃሉን ረጋ ባለ አእምሮ ማጤንና ከዚያም በትክክል በነገራችሁ ነገር ማመን ያስፈልጋችኋል፡፡
 
መጽሐፍ ቅዱስ የቤሪያ ሰዎች በእግዚአብሄር ቃል ላይ ስለነበራቸው ክፍት አእምሮ አመስግኖዋቸዋል፡፡ የቤሪያ ምዕመናን ‹‹በተሰሎንቄ ከሚኖሩት ይልቅ ልበ ሰፊዎች ነበሩና ነገሩ እንደዚህ ይሆንን? ብለው ዕለት ዕለት መጻህፍትን እየመረመሩ ቃሉን በሙሉ ፈቃድ ተቀበሉ፡፡›› (የሐዋርያት ሥራ 17፡11) በአጭሩ በተማሩት መሰረት አመዛዝነው በቃሉ አመኑ፡፡
 
እውነተኛ እምነት የሚመጣው ቃሉን ከሚመረምር ሚዛናዊና ልበ ሰፊ አእምሮ ነው፡፡ ያለ ፈቃዳችሁ እንድታምኑ መገደድ ስሜት የሚሰጥ ነገር ነውን? አንዱ ሌላውን እንዲያምን ቢያስገድደው እንኳን ነገሩ ፈጽሞ ከንቱ ይሆናል፡፡ የተገደደው ሰው እንዲያምን በተነገረው ነገር የግድ አያምንም፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ሁሉም ነገር የሚጎዳኘው ሰው በገዛ ፈቃዱ በማመኑ ላይ ነው፡፡ አንድ ሰው ተመሳሳይ የሆነ ታሪክ በተደጋጋሚ ተነግሮት የማያምን ከሆነ ይህ ሰው መጨረሻው ሲዖል ይሆናል፡፡
 
ስለዚህ በዚህ ዓለም ላይ የሚኖር እያንዳንዱ ሐጢያተኛ ሊያሳዝነን ይገባል፡፡ ነገር ግን ከአንዱ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ጣርያ ስር ሆነን አንዳንዶቻችን በተጻፈው የእግዚአብሄር ቃል የማናምን ከሆንን ያን ጊዜ ይበልጥ የምናሳዝነው እኛ ነን፡፡ ምንም እንኳን በአንዲት የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ውስጥ በሥጋ አብረውን ቢኖሩም መጨረሻቸው ሲዖል የሚሆን ሰዎች እንዴት አያሳዝኑም?
 
ኢየሱስ አስራ ሁለት ደቀ መዛሙርት ነበሩት፡፡ ከእነርሱ መካከል ኢየሱስ መሲህና አዳኝ መሆኑን ያላመነው ይሁዳ ብቻ ነበር፡፡ ስለዚህ ይሁዳ ሁልጊዜም ኢየሱስን መምህር ብሎ ይጠራው ነበር፡፡ ጴጥሮስም እንደዚሁ አንዳንድ ጊዜ ኢየሱስን መምህር ብሎ ይጠራው ነበር፡፡ ነገር ግን ውሎ አድሮ አመነ፡፡ ‹‹ጌታ ሆይ አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሄር ልጅ ነህ፡፡ አንተ ሐጢያቶቼን ለማስወገድ የመጣህ የእግዚአብሄር ልጅ አዳኝ ነህ፤ አንተ የደህንነት አምላክ ነህ›› ብሎ መሰከረ፡፡
 
በሌላ አነጋገር የጴጥሮስ እምነት ከይሁዳ እምነት የተለየ ነበር፡፡ ይሁዳ ኢየሱስን አሳልፎ በመስጠት ከሸጠው በኋላ ራሱን ሰቅሎ ገደለ፡፡ ይሁዳ ከሌሎቹ አስራ አንድ ደቀ መዛሙርት ጋር አብሮ የነበረ ቢሆንም በመጨረሻ ኢየሱስ ክርስቶስ በትክክል ማን እንደነበረ መለየት ተሳነው፡፡ መጨረሻውም ሲዖል ሆነ፡፡ በተቃራኒው ጴጥሮስ ብዙ ድካሞች ያሉበት ግልፍተኛ ሰው ቢሆንም ኢየሱስ ክርስቶስን በማወቁና አዳኝ አድርጎ በማመኑ ዳነ፡፡
 
ልክ እንደዚሁ ደህንነት እውነትን አውቆ በልብ የማመንና ያለማመን ጉዳይ ነው፡፡ አንድ ሰው እውነትን ሳያውቅ ሊያምንበት አይችልም፡፡ ነገር ግን ሰዎች እያወቁት እውነትን ባያምኑ የከፋ ቅጣት ይጠብቃቸዋል፡፡ (ሉቃስ 12፡48) እግዚአብሄር የእምነት መሰረታችን ጽኑና ትክክለኛ መሆን እንዳለበት የሚነግረን ለዚህ ነው፡፡
 
 
እምነታችን እንዴት ነው?
 
አሁን የእምነታችን መሰረት ጠንክሮዋልን? ጽኑ ነውን? ጌታ ፈጽሞ እንዳዳናችሁ ታምናላችሁን? ጌታችን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አማካይነት በእርግጠኝነት አድኖናል፡፡ ይህ የእኛ የእምነት ድርጅት ብቻ የሚያስተምረው የተለየ ነገር አይደለም፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር በብሉይ ኪዳን ውስጥ ተስፋ የሰጠውና ኢየሱስ በተጨባጭ በአዲስ ኪዳን ውስጥ የፈጸመው ነገር ነው፡፡ ክርስቶስ በእርግጥም ያዳነን በዚህ መንገድ ነው፡፡
 
ኢየሱስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱ (ሰማያዊ ማግ) የዓለምን ሐጢያቶች የወሰደ፣ እነዚህን ሐጢያቶች በመስቀል ላይ ተሸክሞ የተሰቀለ፣ (ቀይ ማግ) ዳግመኛ ከሙታን የተነሳና በዚሁም ያዳነን የነገሥታት ንጉሥ (ሐምራዊ ማግ) ነው፡፡ ይህንን እንደሚያደርግ በብሉይ ኪዳን ውስጥ ቃል ገብቷል፡፡ ይህንን ተስፋ በአዲስ ኪዳን በተጨባጭ በመፈጸምም አድኖናል፡፤ ታምናላችሁን? ጠንካራ የእምነት መሰረት መመስረት ማለት ይህ ነው፡፡
 
በመላው ዓለም ላይ በመቶ ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ክርስቲያኖች አሉ፡፡ ነገር ግን አብዛኞቹ የእምነት መሰረታቸው ፈራሽ ነው፡፡ አሁን ያሉትን የክርስቲያን መጽሐፎች በመመርመር ብቻ ሰዎች ትክክለኛ እምነት እንዳላቸውና እንደሌላቸው ማወቅ እንችላለን፡፡ የእነዚህ መጽሐፎች ጸሐፊዎች የክርስቲያን ማህበረሰቦች መሪዎች ይመስላሉ፡፡ መጽሐፎቻቸውን በማንበብ ትክክለኛ እውነት እንዳላቸው ማወቅ እንችላለን፡፡ ከእነዚህ መሪዎች አንዱ የሚያውቀውን እውነት እንኳን ችላ የሚል ወይም የማያምንበት ከሆነ ይህንን መሪ የሚከተል እያንዳንዱ ሰው ለሲዖል የታጨ ይሆናል፡፡ አሳዛኙ እውነታ እውነትን የሚያውቅ አለመኖሩ ነው፡፡ ከሚሊዮን አንድ ቢገኝ ነው፡፡ እውነትን የምናውቅ ጥቂቶቻችን ወንጌልን በመላው ዓለም በታማኝነት ማሰራጨት የሚኖርብን ለዚህ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር በእኛ አማካይነት እየሰራ ነው፡፡ እናንተና እኔ ወንጌልን ከመስበክ በቀር መከልከል አንችልም፡፡ ይህንን የውሃና የመንፈስ ወንጌል በመላው ዓለም አለመስበክ በእግዚአብሄር ፊት ትልቅ ሐጢያት ከመስራት ጋር የተመሳሰለ ነው፡ እንዲያውም ይህንን ሥራ በእምነት የማንከተልና ከልባችን የማናገለግል ከሆንን በእርግጥም በእግዚአብሄር ፊት ትልቅ ሐጢያት እየሰራን ነው፡፡ ይህ ሰዎችን ወደ ሲዖል የመስደድ ሐጢያት ነው፡፡ ልናቆመው እንደምንችል ብናውቅም ሰዎች ባለማወቃቸው መጨረሻቸው ሲዖል መሆኑ ይቅር የማይባል ሐጢያት ነው፡፡ ምክንያቱም እውነቱን የምናውቅ ሰዎች አፎቻችንን ለጉመናልና፡፡
 
ለእኛ የተሰጠንን ተግባር የማንፈጽም ከሆነን እነዚህ ሰዎች በእኛ ላይ ያጉረመርማሉ፡፡ ምክንያቱም ይህ የእኛ የግዴታ ተግባር ነው፡፡ ‹‹ጉበኛው ግን ሰይፍ ሲመጣ ቢያይ፣ መለከቱንም ባይነፋ፣ ሕዝቡንም ባያስጠነቅቅ፣ ሰይፍም መጥቶ አንድ ሰው ከእነርሱ ቢወስድ እርሱ በሐጢአቱ ተወስዶዋል፤ ደሙን ግን ከጉበኛው እጅ እፈልጋለሁ፡፡›› (ሕዝቅኤል 33፡66) በመጀመሪያ ያወቅንና ያመንን እኛ ይህንን የጉበኛ ተግባር መፈጸም አለብን፡፡
 
ይህንን ወንጌል ስለሰጠንና ይህንን እውነት እንድናውቅ ስላስቻለን ጌታን አመሰግናለሁ፡፡ በዚህ ዓለም ላይ ይህንን እውነት የምናውቅና በዚህ ወንጌል የምናምን ጥቂት ምርጦች እኛ መሆናችንን በማወቄም ጌታን ይበልጥ አመሰግነዋለሁ፡፡ እኛ በመላው ዓለም የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ለብዙ መጋቢዎችና ምዕመናኖች ሰብከናል፡፡ ነገር ግን ከዚህ በፊት በእርግጥ ይህንን ወንጌል ያወቀና ያመነ ሰው እንዳልነበር በየቀኑ አረጋግጠናል፡፡ በእኛ አማካይነት የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል እውነት ሰባኪዎች በመላው ዓለም ብቅ እያሉ ነው፡፡ እነርሱም እንደ እኛ ጠንካራ የእምነት መሰረት አላቸው፡፡ ይህንንም ጠንካራ እምነት እያሰራጩ ነው፡፡
 
ወንጌልን የሚያሰራጩ እንደዚህ ያሉ ብዙ ሰዎች ቢኖሩ ምናልባትም በወንጌል ስብከታችን ትንሽ እፎይ በማለት እናርፍ ነበር፡፡ ነገር ግን አሳዛኙ ነገር ይህንን እውነት የሚያውቁና የሚያምኑበት ብዙ ሰዎች በዚህ ዓለም ላይ አለመኖራቸው ነው፡፡ ብዙዎች በዚህ ዓለም ታሪክ ውስጥ የተሐድሶን ክንውኖች ከመጠን በላይ አጋነዋቸዋል፡፡ በጥልቀት ስንመረምረው ግን የተሐድሶ ሰዎች በተሐድሶ ዘመን የመጀመሪያውን የመጽሐፍ ቅዱስ እምነት መሰረት ቁልፍ አዛብተው በማስቀመጣቸው ሌላው ነገር ሁሉ እንደዚሁ መዛባቱን እንረዳለን፡፡ ከእነዚህ በኋላ የተከሰቱ ስህተቶች ቢታረሙም የመጀመሪያው ቁልፍ አሁንም ስለተዛባ እንደዚያው ተበላሽቶ ቀርቷል፡፡ ስለዚህ የክርስትና ታሪክ እንደገና መጻፍ አለበት፡፡
 
ሁላችሁም ጽኑ በሆነው የእምነት መሰረታችሁ ላይ እንደምትቆሙ ተስፋ አደርጋለሁ፤ እጸልያለሁም፡፡ በዚህ የእምነት መሰረት ላይ በመቆምም ሕይወታችሁን እውነተኛውን ወንጌል ለማገልገል ታውሉታላችሁ፡፡ ለወንጌል ስትኖሩ ልባችሁ በደስታ ይሞላል፡፡ አንድ ሰው ለወንጌል ሲኖር ልቡ ወደ መንፈሳዊነት ይለወጣል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ልባችሁን ሲሞላውና በውስጣችሁም ሲሰራ ልባችሁ በደስታ ይጥለቀለቃል፡፡
 
ነገር ግን የሐጢያት ስርየትን ተቀብላችሁና የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል አውቃችሁ ለወንጌል የማትኖሩና የሥጋችሁን ምኞት ብቻ የምትከተሉ ከሆናችሁ መጨረሻችሁ ትርጉም የሌለው ባዶ ሕይወት መኖር ይሆናል፡፡
 
ይህንን ክቡር ወንጌል ስለሰጠንና ደህንነታችንንም በነጻ ስለለገሰን እግዚአብሄርን አመሰግነዋለሁ፡፡ ሁላችሁም እምነታችሁን እንደገና እንድትመረምሩና በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ አማካይነተት ፍጹም የሆነውን የደህንነት ስጦታ እንደምትቀበሉ ተስፋ አደርጋለሁ፤ እጸልያለሁም፡፡