Search

ስብከቶች፤

ርዕስ 11፡ የመገናኛው ድንኳን

[11-16] በምስክሩ ታቦት ውስጥ የተደበቁት መንፈሳዊ ምስጢሮች ‹‹ ዘጸዓት 25፡10-22 ››

በምስክሩ ታቦት ውስጥ የተደበቁት መንፈሳዊ ምስጢሮች
‹‹ ዘጸዓት 25፡10-22 ››
‹‹ከግራር እንጨትም ታቦቱን ይሥሩ፤ ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፣ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል፣ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል ይሁን፡፡ በውስጥና በውጭም በጥሩ ወርቅ ለብጠው፡፡ በእርሱም ላይ በዙሪያው የወርቅ አክሊል አድርግለት፡፡ አራት የወርቅ ቀለበቶችም አድርግለት፤ እነርሱንም በአራቱ እግሮቹ ላይ አኑር፤ በአንድ ወገን ሁለት ቀለበቶች በሌላው ወገን ሁለት ቀለበቶች ይሁኑ፡፡ መሎጊያዎቹንም ከግራር እንጨት ሥራ፤ በወርቅም ለብጣቸው፡፡ ለታቦቱ መሸከሚያ ከታቦቱ ጎን ባሉት ቀለበቶች መሎጊያዎቹን አግባ፡፡ መሎጊያዎቹም በታቦቱ ቀለበቶች ውስጥ ይኑሩ፤ ከቶም አይውጡ፡፡ በታቦቱም ውስጥ እኔ የምሰጥህን ምስክር ታስቀምጠዋለህ፡፡ ከጥሩ ወርቅም ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል የሆነ የስርየት መክደኛ ሥራ፡፡ ሁለት ኪሩቤል ከተቀጠቀጠ ወርቅ ሥራ፤ በስርየት መክደኛውም ላይ በሁለት ወገን ታደርጋቸዋለህ፡፡ ከስርየት መክደኛውም ጋር አንዱን ኪሩብ በአንድ ወገን ሁለተኛውንም ኪሩብ በሌላው ወገን አድርገህ በአንድ ላይ ትሠራዋለህ፡፡ ኪሩቤልም ክንፎቻቸውን ወደ ላይ ይዘረጋሉ፤ የስርየት መክደኛውንም በክንፎቻቸው ይሸፍናሉ፤ ፊታቸውም እርስ በርሳቸው ይተያያል፤ የኪሩቤልም ፊቶቻቸው ወደ ስርየት መክደኛው ይመለከታሉ፡፡ የስርየት መክደኛውንም በታቦቱ ላይ ታደርገዋለህ፤ እኔም የምሰጥህን ምስክር በታቦቱ ውስጥ ታኖረዋለህ፡፡ በዚያ ከአንተ ጋር እገናኛለሁ፤ የእስራኤልንም ልጆች ታዝዝ ዘንድ የምሰጥህን ነገር ሁሉ በምስክሩ ታቦት ላይ ባለው በሁለት ኪሩቤል መካከል በስርየት መክደኛው ላይ ሆኜ አነጋግርሃለሁ፡፡››
 
የኪዳኑ ታቦት
 
የዛሬው ርዕሰ ጉዳይ የምስክሩ ታቦት ነው፡፡ የምስክሩ ታቦት ርዝመቱ 3.7 ጫማ፣ ወርዱ 2.2 ጫማና ቁመቱ 2.2 ጫማ ሆኖ ከግራር እንጨት የተሰራና በንጹህ ወርቅ የተለበጠ ነበር፡፡ በዚህ ታቦት ውስጥ አስርቱ ትዕዛዛት የተቀረጹባቸው ሁለት የድንጋይ ጽላቶችና መናውን የያዘ የወርቅ ማሰሮ በኋላ ደግሞ ያበበችው የአሮን በትር ነበሩበት፡፡ እነዚህ በምስክሩ ታቦት ውስጥ የተቀመጡት ሦስት ቁሳቁሶች ምን ይነግሩናል? በእነዚህ ቁሳቁሶች አማካይነት ሦስቱን የኢየሱስ ክርስቶስ አገልግሎቶች በሚገባ አብራራለሁ፡፡ አሁን በምስክሩ ታቦት ውስጥ ባሉት በእነዚህ ሦስት ቁሳቁሶች የተገለጠውን መንፈሳዊ እውነት እንመርምር፡፡
 
 
ሕጉ የተቀረጸባቸው ሁለቱ የድንጋይ ጽላቶች፡፡ 
 
የኪዳኑ ታቦት ይዞታዎች
 
ሕጉ የተቀረጸባቸውና በምስክሩ ታቦት ውስጥ የተቀመጡት ሁለቱ ጽላቶች እግዚአብሄር ሕጎቹን የሰጠን ሕግ አውጪ መሆኑን ይነግሩናል፡፡ ሮሜ 8፡1-2 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እንግዲህ በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉት አሁን ኩነኔ የለባቸውም፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ ያለው የሕይወት መንፈስ ሕግ ከሐጢአትና ከሞት ሕግ አርነት አውጥቶኛልና፡፡›› እግዚአብሄር በልቦቻችን ውስጥ ሁለት ሐጎች ማለትም የሕይወት ሕግና የኩነኔ ሕግ እንዳስቀመጠ ከዚህ ምንባብ ማየት እንችላለን፡፡
 
ጌታ በእነዚህ በሁለቱ ሕጎች በሰብዓዊ ፍጡራን ሁሉ ላይ ኩነኔንና ደህንነትን አምጥቷል፡፡ በመጀመሪያ በሕጉ አማካይነት ለሲዖል የታጨን ሐጢያተኞች እንደሆንን መረዳት እንችላለን፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር ሐጢያተኛ ተፈጥሮዋቸውንና የጥፋት ዕጣ ፈንታቸውን ለሚያውቁት የደህንነት ሕጉን ‹‹በክርስቶስ ኢየሱስ ያለውን የሕይወት መንፈስ ሕግ›› ሰጥቶዋቸዋል፡፡ እግዚአብሄር እነዚህን ሁለት ሕጎች ለእነርሱ በመስጠት ለሁሉም እውነተኛ አዳኝ ሆኖላቸዋል፡፡
 
 
በወርቃማው ማሰሮ ውስጥ ያለው መና፡፡ 
 
በታቦቱ ውስጥ የሚገኘው ወርቃማው ማሰሮም መና ነበረው፡፡ የእስራኤል ሕዝብ በምድረ በዳ 40 ዓመታቶችን ባሳለፉበት ጊዜ እግዚአብሄር ከሰማያት ምግብን ሰጥቶዋቸው ነበር፡፡ እስራኤሎችም ይህንን መና በተለያዩ መንገዶች በማብሰል እየተመገቡት ኖረዋል፡፡ መናው እንደ ድንብላል ዘር የመሰለ ሲሆን ጣዕሙም ልክ እንደ ማር እንጀራ ነበር፡፡ እግዚአብሄር ለእስራኤል ሕዝብ የሰጠው ይህ መና ወደ ከንዓን ምድር እስከሚገቡ ድረስ ሕይወታቸውን አቆይቶላቸዋል፡፡ ስለዚህ መናው በማሰሮ ውስጥ የተቀመጠው ይህንን ምግብ ለማስታወስ ነበር፡፡
 
እኛ የዘመኑ ምዕመናን የእግዚአብሄር መንፈሳዊ ልጆች ሰማይ እስከሚገቡ ድረስ በዚህ ዓለም ላይ ሳሉ ሊመገቡ የሚገባቸውን የሕይወት እንጀራ መብላት እንደሚገባን ይህ ይነግረናል፡፡ ነገር ግን ከእግዚአብሄር ቃል ይልቅ የዓለምን እንጀራ ማለትም የዓለምን ትምህርቶች የምንሻባቸው ወቅቶች አሉ፡፡ አሁንም የእግዚአብሄር ልጆች ወደ መንፈሳዊቷ ከንዓን ከመድረሳቸው በፊት በትክክልና በተጨባጭ ሊኖሩበት የሚገባቸው ከሰማይ የሚመጣው የእውነተኛው ሕይወት መንፈሳዊ እንጀራ የእግዚአብሄር ቀል ነው፡፡
 
ሁልጊዜም እውነተኛ ሕይወትን የሚሰጠውን እንጀራ የሚያገኝ ሰው ፈጽሞ አይታክትም፡፡ ይህ መንፈሳዊ እንጀራ አብዝቶ በኖረን መጠን ለነፍሳችን አብዝቶ እውነተኛ ሕይወት ይሆናል፡፡ ነገር ግን ከእግዚአብሄር ቃል ይልቅ የዓለም ትምህርቶች የሆነው እንጀራ የምንመገብ ከሆንን ነፍሳችን ትሞታለች፡፡
 
እግዚአብሄር እስራኤሎችን ከሰማያት የወረደውን መና በማሰሮ ውስጥ ሰብስበው እንዲያስቀምጡት አዘዛቸው፡፡ በዘጸዓት 16፡33 ላይ እንደታየው እግዚአብሄር እንዲህ አለ፡- ‹‹አንድ ማድጋ ጎሞር ሙሉ መና አግባበት፤ ለልጅ ልጃችሁም ይጠበቅ ዘንድ በእግዚአብሄር ፊት አኑረው፡፡›› ከሰማያት የወረደው መና ለሰዎች ነፍስ እውነተኛ ሕይወትን የሚሰጥ እንጀራ ነበር፡፡ ‹‹ሰውም ከእግዚአብሄር አፍ በሚወጣ ነገር ሁሉ እንጂ ሰው በእንጀራ ብቻ በሕይወት እንዳይኖር ያስታውቅህ ዘንድ አስጨነቀህ፤ አስራበህም፡፡ አንተም ያላወቅኸውን አባቶችህም ያላወቁትን መና አበላህ፡፡›› (ዘዳግም 8፡3)
 
 

ታዲያ ለእኛ እውነተኛው የሕይወት እንጀራ ማነው? 

 
ኢየሱስ ክርስቶስ ሐጢያቶቻችንን በሥጋው ለመሸከም የተቀበለው ጥምቀት፣ ስቅለቱና ያፈሰሰው ደሙ እውነተኛ ሕይወት የሚሰጥ እንጀራችን ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋውንና ደሙን በመስጠት የዘላለም ሕይወት እንጀራ ሆኖዋል፡፡ ዮሐንስ 6፡48-58 እንዲህ ይነግረናል፡- ‹‹የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ፤ አባቶቻችሁ በምድረ በዳ መና በሉ ሞቱም፤ ሰው ከእርሱ በልቶ እንዳይሞት ከሰማይ አሁን የወረደ እንጀራ ይህ ነው፡፡ ከሰማይ የወረደ ሕያው እንጀራ እኔ ነኝ፡፤ ሰው ከዚህ እንጀራ ቢበላ ለዘላለም ይኖራል፡፡ እኔም ስለ ዓለም ሕይወት የምሰጠው እንጀራ ሥጋዬ ነው፡፡ እንግዲህ አይሁድ፡- ይህ ሰው ሥጋውን ልንበላ ይሰጠን ዘንድ እንዴት ይችላል? ብለው እርስ በርሳቸው ተከራከሩ፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ እንዲህ አላቸው፡- እውነት እውነት እላችኋለሁ፤ የሰውን ልጅ ሥጋ ካልበላችሁ ደሙንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ ሕይወት የላችሁም፡፡ ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘላለም ሕይወት አለው፡፡ እኔም በመጨረሻው ቀን አስነሳዋለሁ፡፡ ሥጋዬ እውነተኛ መብል ደሜም እውነተኛ መጠጥ ነውና፡፡ ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ በእኔ ይኖራል፤ እኔም በእርሱ እኖራለሁ፡፡ ሕያው አብ እንደላከኝ እኔም ከአብ የተነሣ ሕያው እንደምሆን እንዲሁ የሚበላኝ ደግሞ ከእኔ የተነሣ ሕያው ይሆናል፡፡ ከሰማይ የወረደ እንጀራ ይህ ነው፤ አባቶቻችሁ መና በልተው እንደሞቱ አይደለም፤ ይህን እንጀራ የሚበላ ለዘላለም ይኖራል፡፡››
 
ጌታችን እንዲህ አለ፡- ‹‹የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ፤ አባቶቻችሁ በምድረ በዳ መና በሉ ሞቱም፡፡ ሰው ከዚህ እንጀራ ቢበላ ለዘላለም ይኖራል፡፡›› ‹‹ከሰማይ የወረደው እንጀራ›› ምን ነበር? የኢየሱስ ሥጋና ደም ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የኢየሱስ ሥጋ ኢየሱስ ክርስቶስ በዮርዳኖስ ወንዝ በዮሐንስ በመጠመቅ የዓለምን ሐጢያት እንደወሰደ ይነግረናል፡፡ የኢየሱስ ደም ደግሞ ኢየሱስ በመጠመቁ የዓለምን ሐጢያት እንደወሰደና በመስቀል ላይ በመሰቀልም የሐጢያትን ኩነኔ እንደተሸከመ ይነግረናል፡፡
 
በምስክሩ ታቦት ውስጥ ባለው ማሰሮ ውስጥ ያለው መና እስራኤሎች በምድረ በዳ በነበሩ ጊዜ የሕይወት እንጀራ ነበር፡፡ በአዲስ ኪዳን ዘመን መንፈሳዊ ትርጉሙ የኢየሱስ ክርስቶስን ስጋ የሚያመለክት መሆኑ ነው፡፡ ይህ እውነት ኢየሱስ ክርስቶስ የሐጢያተኞችን ሐጢያቶች በሙሉ የወሰደበትን ጥምቀትና በመስቀል ላይ የፈሰሰውን ደሙን ያሳየናል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የዚህን ዓለም ሐጢያቶች በሙሉ በጥምቀቱ አማካይነት በሥጋው ላይ ወስዶ ደሙን በማፍሰስ በመስቀል ላይ ስለሞተ ጥምቀቱና ያፈሰሰው ደሙ ምዕመናኖች ዳግመኛ እንዲወለዱ የሚያስችላቸው ዘላለማዊ የአዲስ ሕይወት ምንጭ ሆንዋል፡፡
 
ኢየሱስ በጥምቀቱ አማካይነት የሐጢያተኞችን ሐጢያቶች ለመውሰድ አሳልፎ የሰጠው ሥጋና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ ሐጢያተኞች በሙሉ የሐጢያት ስርየትን እንዲያገኙ ያስቻላቸው የሕይወት እንጀራ ነው፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ ‹‹የሰውን ልጅ ሥጋ ካልበላችሁ ደሙንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ ሕይወት የላችሁም›› (ዮሐንስ 6፡53) ያለበትን ምክንያት መረዳት አለብን፡፡
 
 
የሚበልጠው ማነው? 
 
ዮሐንስ 6ን ስንመለከት በወቅቱ የነበሩት አብዛኞቹ አይሁዶች ሙሴ ከኢየሱስ ይበልጣል ብለው ያስቡ እንደነበር መመልከት አንቸችላለን፡፡ ኢየሱስ ወደዚህ ምድር በመጣ ጊዜ ‹‹አንተ ከአባታችን ሙሴ ትበልጣለህን?›› ብለው ጠየቁት፡፡ በእርግጥ እነርሱ ሙሴ ከሁሉም ይበልጣል ብለው ያስቡ ነበር፡፡ አይሁዶች ኢየሱስ መሲህ መሆኑን መረዳት ስለተሳናቸው አስቀያሚ ነገር አድርገው ተመለከቱት፡፡ ስለዚህ ‹‹አንተ ከሙሴ ትበልጣለህን?›› ብለው በመጠየቅ ተገዳደሩት፡፡ የእስራኤል ሕዝብ በያህዌህ አምላክ አምነዋል፡፡ 30 ዓመት ዕድሜ ያለው አንድ ወጣት ‹‹አባቶቻችሁ መና በልተው ሞቱ፤ እኔ የምሰጠውን እንጀራ የሚበሉ አይሞቱም›› እያለ መጣ፡፡ እነርሱ የሁለቱን ማለትም የሙሴንና የኢየሱስን ሥልጣን ማወዳደር የያዙት ለዚህ ነው፡፡
 
ኢየሱስ በኋላ ‹‹አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ›› ብሎ እንደተናገረ ሁሉ በመላው የሰው ታሪክ ውስጥ ይኖር ከነበረ ከማንኛውም ሰብዓዊ ፍጡር ሁሉ እርሱ ይበልጣል፡፡ ምክንያቱም እርሱ ራሱ ፈጣሪ ነውና፡፤ ተራ ፍጡራኖች የራሳቸው የሆነው ፈጣሪ ነው በማለት ሊገዳደሩት እንዴት ደፈሩ? ይህም ሆኖ አንዳንድ ሰዎች አሁንም ድረስ ኢየሱስ በሰው ታሪክ ውስጥ ከተፈጠሩ ታላላቅ ጠቢባን አንዱና ታላቅ አስተማሪ ብቻ ነው ይላሉ፡፡ ይህ እንዴት ያለ ስድብ ነው! ኢየሱስ አምላክ፣ የነገሥታት ንጉሥና የአጽናፈ ዓለም ሁሉ ፈጣሪ ነው፡፡ እርሱ ሁሉን የሚችልና ሁሉን የሚያውቅ አምላክ ነው፡፡ ነገር ግን እናንተንና እኔን ከሐጢያቶቻችንና ከዘላለም ሞት ሊያድነንና እውነተኛ አዳኛችን ሊሆን ራሱን አዋርዶና የሰው ሥጋ ለብሶ መጣ፡፡
 
ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲህ አለ፡- ‹‹ሁሉም ከእግዚአብሄር የተማሩ ይሆናሉ ተብሎ በነቢያት እንደተጻፈ ከአብ የሰማና የተማረ ሁሉ ወደ እኔ ይመጣል፤ ከእግዚአብሄር ከመጣው በስተቀር አብን ያየ የለም፤ እርሱ አብን አይቷል፡፡›› ኢየሱስ በግልጽ እየተናገረ ያለው እርሱ አይሁዶች ሲጠብቁት የነበረው መሲህ መሆኑን ነው፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ እየተናገረ የነበረውን መረዳት ተሳናቸው፡፡ ሊያምኑትም ሊቀበሉትም አልቻሉም፡፡ ውጤቱም ከበድ ያለ አለመግባባት ሆነ፡፡ ‹‹ሥጋህን እንበላ ዘንድ እንዴት ልትሰጠን ይቻልሃል? በእርግጥ ሥጋህን ብንበላና ደምህን ብንጠጣ የዘላለም ሕይወት እንደምናገኝ እየተናገርህ ነውን? እኛ አንዳች ዓይነት ሰው በላዎቸ እንመስልሃለንን?›› በማለት ግራ ተጋቡ፡፡
 
ነገር ግን የኢየሱስን ሥጋ የሚበሉና ደሙን የሚጠጡ ለዘላለም ይኖራሉ፡፡ የኢየሱስ ሥጋ የሕይወት እንጀራ ነው፡፡ በዚህ ማሰሮ ውስጥ የተቀመጠው መና ማለትም የሕይወት እንጀራ እውነተኛ ምንነቱ የኢየሱስ ክርሰቶስ ሥጋና ደም ነው፡፡ ኢየሱስ ወደዚህ ምድር መጥቶ ሥጋውንና ደሙን በመስጠት የሕይወትን እንጀራ እንድንበላና የዘላለምን ሕይወት እንድናገኝ አስችሎናል፡፡
 
ታዲያ ሰው ሁሉ የኢየሱስን ሥጋ የሚበላውና ደሙን የሚጠጣው እንዴት ነው? የኢየሱስን ሥጋ ለመብላትና ደሙን ለመጠጣት ብቸኛው መንገድ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ማመን ነው፡፡ የኢየሱስን ሥጋ በእምነት መብላትና ደሙን መጠጣት አለብን፡፡ ጌታችን ለእናንተና ለእኔ የሐጢያት ስርየትን ሊሰጠንና በመንግሥተ ሰማይ ውስጥ ለዘላለም እንድንኖር ሊያስችለን በጥምቀቱና ደሙን በማፍሰስ ለአንዴና ለመጨረሻ ሐጢያቶቻችንን ደመሰሰ፡፡ በዚህም ለነፍሳችን ምግብ ሆነልን፡፡ አሁን በእግዚአብሄር የውሃና የመንፈስ ቃል በማመን ይህንን መንፈሳዊ ምግብ መመገብና የዘላለምን ሕይወት ማግኘት አለብን፡፡
 
የኢየሱስን ሥጋ እንዴት መብላትና ደሙንም እንዴት መጠጣት እንደምንችል በዝርዝር ልመስክር፡፡ እናንተና እኔ በሚገባ እንደምናውቀው ኢየሱስ ክርሰቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በ30 ዓመቱ በዮሐንስ በመጠመቅ የሰውን ዘር ሐጢያቶች ወሰደ፡፡ ከዚያም በመስቀል ላይ እስከ ሞት ድረስ ደሙን በማፍሰስ የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ በሙሉ ወሰደ፡፡ የእርሱን ሥጋ መብላትና ደሙን መጠጣት የምንችለው በዚህ ዋና እውነት በማመን ነው፡፡ የሰው ዘር ሐጢያቶች በተቀበለው ጥምቀቱ አማካይነት ወደ ኢየሱስ ሥጋ በተሻገሩ ጊዜ የሐጢያት መንጻት ተፈጽሞዋል፡፡ ደሙን መጠጣት ማለት ኢየሱስ በተጠመቀና በመስቀል ላይ ደሙን ባፈሰሰ ጊዜ ይህ ያፈሰሰው ደም የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ ተሸክሞዋል ማለት ነው፡፡
 
ስለዚህ በልቦቻቸው በኢየሱስ ደም የሚያምኑ ጥማቸው ተቆርጦዋል፡፡ ምክንያቱም የሐጢያቶቻቸው ኩነኔ በሙሉ ኢየሱስ በመስቀል ላይ በተሸከመው ቅጣት ሙሉ በሙሉ አብቅቷልና፡፡ ይህንን እውነት መገንዘብ አለብን፡፡ በእርሱም ልናምንበት ይገባል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በዮሐንስ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችንን ስለወሰደ በዚህ እውነት በማመን ለአንዴና ለመጨረሻ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ነጽተናል፡፡
 
እግዚአብሄር በእምነት የኢየሱስን ሥጋ እንድንበላና ደሙን እንድንጠጣ ነግሮናል፡፡ ኢየሱስ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት አማካይነት የማንንም ሐጢያቶች ሳይተው ሐጢያቶችን ሁሉ ስለወሰደ፣ ሥጋውንም ለመስቀል ቅጣት ስለሰጠና ክቡር ደሙን ስላፈሰሰ አሁን እነዚያ የሚያምኑ ሰዎች ልቦቻቸው ነጽተዋል፡፡ በእምነትም ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ሁሉ ስለታጠቡና የሐጢያትን ኩነኔ ስለተሸከሙ ከጥማት ነጻ ናቸው፡፡ ኢየሱስ እንዲህ ያለው ለዚህ ነው፡፡ ‹‹ስጋዬ እውነተኛ መብል ደሜም እውነተኛ መጠጥ ነውና፡፡›› (ዮሐንስ 6፡55)
 
ይህ ኢየሱስ በእርግጥም አዳኝ፣ ሐጢያቶቻችንን ያስወገደና የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ የተሸከመ የእግዚአብሄር ልጅ መሆኑ በሚገባ የተረጋገጠ ነው፡፡ የሐጢያት ደመወዝ ሞት መሆኑን ከሚያውጀው ሕግ እኛን ነጻ ለማውጣት፣ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እኛን ለማጠብና ከቅጣቶቻችን ሁሉ እኛን ለማዳን አዳኙና የእግዚአብሄር ልጅ በመስቀል ላይ የራሱን ሥጋ አሳልፎ ሰጠ፡፡ ደሙን አፈሰሰ፡፡ በዚህም በእርሱ የሚያምኑትን ሰዎች ልቦች አንጽቶ ጥማቸውን አረካላቸው፡፡ የኢየሱስ ሥጋና ደም ውጤት ይህ ነው፡፡
 
ኢየሱስ የሰውን ዘር ሐጢያቶችና ኩነኔ ያስወገደ አዳኝ ነው፡፡ ኢየሱስ በተቀበለው ጥምቀቱ አማካይነት የሰውን ዘር ሐጢያቶች የወሰደ፣ የእነዚህን ሐጢያቶች ኩነኔ ለመሸከምም የተሰቀለና ደሙን ያፈሰሰ አዳኝ ነው፡፡ በመስቀል ላይ በመሰቀል የተሸከመው የሐጢያት ቅጣት የገዛ ሐጢያቶቻችን ቅጣት መሆን የቻለው ኢየሱስ ከእኛ የተሻገሩትን የዓለም ሐጢያቶች ስለተቀበለ ነበር፡፡
 
እኛ የሐጢያት ስርየትን መቀበል የምንችለው በውሃውና በመንፈሱ እውነት በማመን ነው፡፡ ሁላችሁም የኢየሱስን ጥምቀትና ያፈሰሰውን ደሙን የሐጢያታችሁ ስርየት አድርጋችሁ መቀበል አለባችሁ፡፡ በመንፈሳዊ መልኩ የኢየሱስን ሥጋ መብላትና ደሙን መጠጣት የምንችለው፤ በዚህም የዘላለም ሕይወትን የምናገኝ ሰዎች መሆን የምንችለው የእግዚአብሄር ልጅ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን እንደወሰደና የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ በሙሉ በመስቀል ላይ እንደተሸከመ በማመን ነው፡፡ በኢየሱስ ጥምቀትና ባፈሰሰው ደሙ በማመን አሁን ሥጋውን መብላትና ደሙን መጠጣት እንችላለን፡፡ የኢየሱስን ጥምቀትና ለሐጢያት ስርየታችን ምግብ ይሆን ዘንድ በመስቀል ላይ ያፈሰሰውን ደሙን በመመገብ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ነጻ እንሆናለን፡፡ የሐጢያቶቻችንን ስርየት መቀበል የቻልነው፣ የእግዚአብሄር ልጆች የሆንነውና በእግዚአብሄር መንግሥት ውስጥ ለዘላለም የምንኖረው በዚህ እምነት አማካይነት ነው፡፡
 
 
ያበበችው የአሮን በትር፡፡ 
 
በምስክሩ ታቦት ውስጥ ከተቀመጡት ቁሳቁሶች መካከል ያበበችው የአሮን በትር ኢየሱስ ክርስቶስ የመንግሥተ ሰማይ ዘላለማዊ ሊቀ ካህን መሆኑን ታመለክታለች፡፡ የዘላለም ሕይወት የሚገኘውም በእርሱ እንደሆነ ትነግረናለች፡፡ ይህንን ማስተዋል እንችል ዘንድ ወደ ዘሁልቁ 16፡1-2 እንሂድ፡- ‹‹የሌዊም ልጅ የቀዓት ልጅ የይስዓር ልጅ ቆሬ ከሮቤልም ልጆች የኤልያብ ልጆች ዳታንና አቢሮን የፋሌትም ልጅ ኦን በሙሴ ላይ ተነሡ፡፡ ከእስራኤልም ልጆች ሁለት መቶ አምሳ ሰዎች ከእነርሱ ጋር ወሰዱ፡፡ ከጉባኤው የተመረጡ፣ ዝናቸውም የተሰማ የማህበሩ አለቆች ነበሩ፡፡››
እዚህ ላይ ያለው ምንባብ ከሌዋውያን መካከል 250 ዝነኛ የማህበሩ መሪዎች ተሰባስበው በሙሴ ላይ እንደተነሱ ይነግረናል፡፡ እነርሱ እንዲህ አሉ፡- ‹‹ሙሴና አሮን እኛን ከግብጽ ምድር በማውጣት ምን አደረጋችሁልን? ምን ሰራችሁልን? በመጨረሻ በአሸዋማው በረሃ እንድንሞት ወደ ምድረ በዳ ያወጣችሁን አይደላችሁምን? እንዴት ራሳችሁን የእግዚአብሄር ባሮች አድርጋችሁ ትጠራላችሁ? እግዚአብሄር የሚሰራው በእናንተ በኩል በቻ ነውን?›› በሌላ አነጋገር በሙሴና በአሮን አመራር ላይ ዓመጽ ተነሳ፡፡
 
በዚያን ጊዜ እግዚአብሄር ቆሬን፣ ዳታንን፣ ኦንንና ሌሎቹን የማህበሩን የዓመጽ መሪዎች እንዲህ አላቸው፡- ‹‹አንድ በትርም ለአባቶቻቸው ቤት አለቃ ይሆናልና፡፡ በሌዊ በትር ላይ የአሮንን ስም ጻፍ፡፡ እኔ ከእናንተ ጋር በምገናኝበት በመገናኛው ድንኳን ውስጥ በምስክሩ ፊት አኑራቸው፡፡ ሌሊቱን እዚያ ተዋቸው፡፡ በቀጣዩም ቀን ተመልከታቸው፡፡›› ከዚያም እግዚአብሄር እንዲህ አለ፡- ‹‹የመረጥሁት ሰው በትር ታቆጠቁጣለች፤ በእናንተም ዘንድ የሚያጉረመርሙባችሁን የእስራኤልን ልጆች ማጉረምረም አጠፋለሁ፡፡›› (ዘሁልቁ 17፡5) በቁጥር 8 ላይ ይህንን እንመለከታለን፡- ‹‹እነሆም ከሌዊ ቤት የሆነች የአሮን በትር አቆጠቆጠች፤ ለመለመችም፤ አበባም አወጣች፤ የበሰለ ለውዝም አፈራች፡፡››
 
ከዚያም በቁጥር 10 ላይ ይህንን እንመለከታለን፡- ‹‹እግዚአብሄርም ሙሴን፡- የአሮንን በትር ወደ ምስክሩ ፊት መልስ፡፡ ማጉረምረማቸው ከእኔ ዘንድ እንዲጠፋ እነርሱም እንዳይሞቱ ለሚያምጹብኝ ልጆች ምልክት ሆና ትጠበቅ አለው፡፡›› ያበበችው የአሮን በትር በምስክሩ ታቦት ውስጥ የተቀመጠችውና የተጠበቀችው በዚህ መንገድ ነው፡፡
 
ይህም የሌዊ ዘር የሆነው አሮን የእስራኤል ሕዝብ ሊቀ ካህን ሆኖ መቀባቱን ያሳያል፡፡ ሙሴ የእግዚአብሄር ነቢይ ሲሆን አሮንና ዘሮቹ ደግሞ የእስራኤል ሕዝብ ሊቀ ካህናት ነበሩ፡፡ የምድራዊውን ሊቀ ክህነት ተግባራቶች ለአሮን በአደራ የሰጠው ራሱ እግዚአብሄር ነበር፡፡ እግዚአብሄር የእስራኤል ሕዝብ ሐጢያት በሚሰሩበት ጊዜ መስዋዕታቸውን ለእግዚአብሄር የሚያቀርቡበትን የመስዋዕት ስርዓት ለሙሴ አሳየው፡፡ እነዚህ መስዋዕቶች በመስዋዕት ስርዓቱ መጠይቆች መሰረት የቀረቡ መሆናቸውን እንዲቆጣጠር አሮንን ሾመው፡፡
 
እግዚአብሄር የክህነቱን ሐላፊነቶች በሙሉ ለአሮን በአደራ ቢሰጠውም የእርሱን ክህነት የሚቃወሙ ሰዎች ነበሩ፡፡ እግዚአብሄር የአሮን ክህነት ከእግዚአብሄር የተሰጠ መሆኑን ለማሳየት የአሮን በትር እንድታብብ ያደረገው ለዚህ ነው፡፡ ከዚያም የእስራኤል ሕዝብ ይህን ትምህርት እንዲያስታውሱ ይህችን በትር በምስክሩ ታቦት ውስጥ እንዲጠብቁዋት አደረገ፡፡ የሕጉ ሁለቱ የድንጋይ ጽላቶች፣ መና ያለበት ማሰሮና ያበበችው የአሮን በትር ሁሉም በምስክሩ ታቦት ውስጥ እንዲቀመጡ የተደረጉት በዚህ ሁኔታ ነበር፡፡ እነዚህ ሦስቱ ቁሳቁሶች ምን ዓይነት መንፈሳዊ መልዕክት አላቸው? የአዳኛችንን የኢየሱስ ክርስቶስን አገልግሎቶች ያመለክታሉ፡፡
 
 

ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ለመደምሰስ ምን ዓይነት አገልግሎቶችን ፈጸመ? 

 
በመጀመሪያ የነቢይን አገልግሎት ፈጸመ፡፡ እርሱ አልፋና ዖሜጋ ነው፡፡ እርሱ መጀመሪያውንና መጨረሻውን ያውቃል፡፡ ስለ ፊተኛውና ስለ ኋለኛውም አስተምሮናል፡፡ ጌታችን ሐጢያተኞች ሆነን ብንቀር በሰው ዘር ላይ፣ በእኔና በእናንተ ላይ የሚደርስብንን አውቋል፡፡
 
ሁለተኛ ኢየሱስ የመንግሥተ ሰማይ ዘላለማዊ ሊቀ ካህን ሆንዋል፡፡ ወደዚህ ምድር የመጣው ራሱ አዳኛችን በመሆን ከሐጢያት ሊያድነን የመንግሥተ ሰማይ ሊቀ ካህናችን በመሆንም ሙሉ በሙሉ ሊያድነን ስለፈለገ ነው፡፡
 
ሦስተኛ ኢየሱስ ክርስቶስ ንጉሣችን ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹በልብሱና በጭኑም ላይ የነገሥታት ንጉሥና የጌቶች ጌታ የሚል ስም ተጽፎአል፡፡›› (ዮሐንስ ራዕይ 19፡16) እርሱ የመላው አጸናፈ ዓለም ዋና ፈጣሪ ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ዓለም ላይ ያለውን እያንዳንዱን ነገር ለመግዛት ሥልጣን አለው፡፡
 
እውነተኛው ንጉሣችን፣ ከሐጢያት የምንድንበትን እውነት ያስተማረን ነቢይና ዘላለማዊው የሰማይ ሊቀ ካህን አሁን እውነተኛ አዳኛችን እንደሆነ ሁላችንም መገንዘብ አለብን፡፡
 
ጌታችን እናንተንና እኔን ከሐጢያት አድኖን የእግዚአብሄር ሕዝብ፣ የራሱ ልጆችና ሠራተኞች አድርጎናል፡፡ በጎ ሥራዎችን እንድንሰራም አስችሎናል፡፡ በዚህ ምድር ላይም እንኳን አዲስ ሕይወት እንኖር ዘንድ ነፍሳችን ዳግመኛ እንድትወለድ አድርጓል፡፡ ጊዜው ሲመጣ ሥጋችንን አስነስቶ ለዘላለም በሰማይ ከእርሱ ጋር ለመኖር እንድንችል አዲስ ሕይወትን ሰጥቶናል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ለእናንተና ለእኔ ማነው? እርሱ እውነተኛው አዳኛችን ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ነቢያችን፣ የዘላለም ሊቀ ካህናችንና ንጉሣችን ነው፡፡
 
በእግዚአብሄር ፈቃድ ላይ ማመጽ ባንፈልግም እኛ በጣም ብቁዓን ያይደለንና ደካሞች ስለሆንን ሁልጊዜም ሐጢያትን እንሰራለን፡፡ እንደዚህ ሆነን በመኖር የምንቀጥል ከሆነ እንደዚህ ሆነን እንሞትና በእግዚአብሄር ፊት እንቀርባለን፡፡ ልንሄድበት የሚገባን ተገቢው ስፍራ የት ነው? ሰማይ ነው ወይስ ሲዖል? ‹‹የሐጢአት ደመወዝ ሞት ነው›› በሚለው የሕጉ አዋጅ መሰረት ሁላችንም ቢፈረድብን ሁላችንም አንጠፋምን? እንደ እኛ ዓይነቶቹን ሰዎች ከሐጢያትና ከጥፋት አድኖ አዳኛችን የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ እርሱ ራሱ ወደዚህ ምድር መጥቶ ወደደን፡፡ ከሐጢያት ያዳነን አዳኝም ሆነ፡፡ በዚህም የመንጋው ታላቅ እረኛ ሆነ፡፡
 
ዮሐንስ 3፡16 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሄር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና፡፡›› እግዚአብሄር እናንተንና እኔን አብዝቶ ስለወደደን እርሱ ራሱ ለእኛ ሲል ወደዚህ ምድር መጥቶ የዓለምን ሐጢያቶች ለመውሰድ ተጠመቀ፤ ተሰቀለ፤ በመስቀል ላይም ሞተ፡፡ ዳግመኛም ከሙታን ተነሳ፡፡ በዚህም በተጨባጭ አዳኛችን ሆነ፡፡ ስለዚህ አዳኛችን የሆነውን ኢየሱስ ክርስቶስን በልባችን በማመን ከሐጢያት የነጻን የእግዚአብሄር ልጆች እንድንሆንና የዘላለምን ሕይወት እንድናገኝ የደህንነት ስጦታ የተሰጠን ሰዎች ሆነናል፡፡
 
በእግዚአብሄር ፊት ፈጽሞ እርግጠኞች ሆነን ልናምንበት የሚገባን አንድ ነገር አለ፡፡ ይህም እግዚአብሄር ስለወደደን ሐጢያቶቻችንን ለመደምሰስ የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር በመምጣት መጠመቁ፣ በመስቀል ላይ መሞቱ፣ ከሙታን መነሳቱና በዚህም እውነተኛ አዳኛችን መሆኑ ነው፡፡ የዘላለም ሕይወት ሊጨመርልን የሚችለው በልባችን ውስጥ ባለን እምነት የኢየሱስን ሥጋ በመብላትና ደሙን በመጠጣት ነው፡፡ ከዚህ እውነት የበለጠ ግልጽ የሆነ አንዳች ነገር ስለሌለ ይህን ተቀ ብለን ከማመን በስተቀር ሌላ ልናደርገው የምንችለው ነገር የለም፡፡
 
በእምነት የኢየሱስን ሥጋ መብላትና ደሙን መጠጣት አለብን፡፡ ማንም ሰው እንዳለ በኢየሱስ የተፈጸመውን የውሃና የመንፈስ ወንጌል የሚያውቅና የሚያምን ይህ አንድ እምነት ሊኖረው ይገባል፡፡ እኛ ከማመን በቀር ሌላ ልናደርገው የምንችለው ምን ነገር አለ? እግዚአብሄርን ከመቃወም በስተቀር ሌላ አንዳች የምናደርገው ነገር ሊኖር አይችልም፡፡ እኛ በእግዚአብሄር ላይ ለማመጽና ሐጢያት ለመስራት ፈጣኖች ነን፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር አሁንም እናንተንና እኔን ለአንዴና ለመጨረሻ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖናል፡፡ ምክንያቱም ሁላችንንም ይወደናልና፡፡
 
 
እግዚአብሄር በብሉይ ኪዳን ዘመን ስለ ማዳኑ የተናገረው እንዴት ነው?
 
ታዲያ ጌታ ያዳነን በየትኛው ዘዴ አማካይነት ነው? እርሱ በብሉይ ኪዳን ውስጥ በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በርና ሊቀ ካህኑ በለበሳቸው መጎናጸፊያዎች ላይ በተገለጡት ቀለማቶች አማካይነት ስለዚህ ማዳን ተናግሮዋል፡፡ በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ላይ የተገለጡት የሰማያዊ፣ የሐምራዊ፣ የቀይ ማግና ጥሩ በፍታ ቀለማቶች የእርሱን ፍጹም ደህንነት የሚያሳዩን መገለጦች ናቸው፡፡ በሊቀ ካህኑ መጎናጸፊያዎች ላይም የወርቅ ማግ ተጨምሮበታል፡፡
 
ሰማያዊው ማግ ኢየሱስ ክርስቶስ አዳኛችን ሆኖ ወደዚህ ምድር በመምጣት በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን እንደወሰደ ይነግረናል፡፡ ሐምራዊው ማግ ኢየሱስ ክርስቶስ አጽናፈ ዓለማትን የፈጠረ የነገሥታት ንጉሥና እግዚአብሄር መሆኑን ይነግረናል፡፡ ቀዩ ማግ ኢየሱስ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን ስለወሰደ የዓለምን ሐጢያቶች ተሸክሞ ደሙን በማፍሰስና በመሞት በመስቀል ላይ ስለ እነዚህ ሐጢያቶች መኮነኑንና በዚህም ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ኩነኔ ያዳነንን ደህንነት እንደሰጠን ይነግረናል፡፡
 
ጥሩው በፍታ ጌታችን ወደዚህ ምድር በመምጣት መጠመቁን፣ በመስቀል ላይ መሞቱን፣ ዳግመኛ ከሙታን መነሳቱንና በዚህም በእውነት የምናምነውን የእኛን ሐጢያቶች በመደምሰስ መንፈሶቻችንን እንደ በረዶ ነጭ አድርጎ በማንጻት እንዳዳነን የሚነግረንን የተብራራ የብሉይና የአዲስ ኪዳናት ቃል ያሳየናል፡፡ የወርቁ ማግ ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ ያደረገውን እምነት ያመለክታል፡፡ የወርቁ ማግ የሚያበራው ለዚህ ነው፡፡ እናንተና እኔ የምንኮራበት አንዳች ነገር የለንም፡፡ ነገር ግን ራሱ እግዚአብሄርና የእግዚአብሄር ልጅ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ በሰራልን ነገር በሙሉ ልባችን በማመን እንኮራለን፡፡ በእርግጥ በእግዚአብሄር ፍቅር ልንሸፈን፣ የእርሱን በረከቶች ልንቀበልና በእርሱም ልንመሰገን የምንችለው እርሱ ባደረጋቸው የጽድቅ ድርጊቶች በማመን ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር በመገናኛው ድንኳን አማካይነት እየነገረን ያለው ይህንን ነው፡፡
 
እግዚአብሄር በመገናኛው ድንኳን ውስጥ በተቀመጠው የምስክር ታቦት አማካይነት እየነገረን ያለውን ነገር መረዳት አለብን፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅም የሰውን ዘርና የእኛን ሐጢያቶች በሙሉ ወሰደ፡፡ በመስቀል ላይ በመሞትም የሐጢያት ኩነኔያችንን ተሸከመ፡፡ ዳግመኛም ሕያው ይሆን ዘንድ ከሙታን ተነሳ፡፡ እግዚአብሄር በምስክሩ ታቦት አማካይነት ኢየሱስ ክርስቶስን እውነተኛ አዳኛችንና አምላካችን አድርገን ከልባችን ማመን እንደሚገባን ግልጽ እያደረገ ነው፡፡ ሐጢያቶቻቸውን በወሰደበት በኢየሱስ ጥምቀት፣ ለሐጢያቶቻቸው ኩነኔ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ የኢየሱስ ክርስቶስን ሞት የራሳቸው ሞትና የእርሱ ትንሳኤ የራሳቸው ትንሳኤ እንደሆነ የሚያምኑ እግዚአብሄር ያዳናቸው ሰዎች ናቸው፡፡
 
ታዲያ ይህ የመገናኛው ድንኳን የሚያመለክተው ማንን ነው? የሚያመለክተው ኢየሱስ ክርስቶስን ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ እናንተንና እኔን ከሐጢያቶቻችን ያዳነበትን የደህንነት ዘዴ ይነግረናል፡፡ በአዲስ ኪዳን በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ሞቱ ሐጢያቶቻችንን የደመሰሰ፣ ሁሉንም ያስወገደ፣ ለሐጢያቶቻችን ሁሉ የተኮነና ለአንዴና ለመጨረሻ ከሐጢያታችን ሁሉ ያዳነን ኢየሱስ ክርስቶስ ነበር፡፡
 
በብሉይ ኪዳን እጆቻቸውን በራሱ ላይ በመጫን፣ ሐጢያቶቻቸውን በመሸከምና ደሙን አፍስሶ በመሞት ሐጢያተኞችን ያዳነው የመስዋዕቱ ቁርባን ነበር፡፡ ብሉይ ኪዳን በእጆች መጫን አማካይነት የእነዚህን ሐጢያተኞች ሐጢያቶች በመውሰድ በምትካቸው የስርየት ሞት የሚሞተውን የመስዋዕት ቁርባን ሞት ይዘረዝራል፡፡ በብሉይ ኪዳን ውስጥ የተገለጠው መስዋዕታዊ የስርየት ስርዓት ከአዲስ ኪዳን ጋር ሲቆራኝ በጥምቀትና በደም የመጣውን የውሃና የመንፈስ ወንጌል ፈጻሚ ኢየሱስ ክርስቶስን ያመለክታል፡፡
 
ታዲያ ይህንን የደህንነት ሕግ ያዘጋጀውና የመሰረተው ማነው? የመሰረተው እግዚአብሄር አዳኛችን ነው፡፡ ሐጢያተኞችን ከሐጢያት የሚያድነውን የደህንነት ሕግ የመሰረተው እግዚአብሄር ነው፡፡ ይህንን ሕግም ለእኛ ሰጥቶናል፡፡ በምስክሩ ታቦት ውስጥ የሕጉ ሁለት ጽላቶች፣ የመናው ማሰሮና ያበበችው የአሮን በትር ነበሩ፡፡ እነዚህ ነገሮች ሁሉ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ባህርያቶችና አገልግሎቶች ይናገራሉ፡፡
 
ያበበችው የአሮን በትር በመንፈሳዊ መልኩ የመንግሥተ ሰማይ ሊቀ ካህንና ታላቁ እረኛ በሆነው በኢየሱስ ክርሰቶስ ስናምን እግዚአብሄር እንደሚያድነን ይነግረናል፡፡ የመናው ማሰሮም እንደዚሁ የሕይወት እንጀራችን ስለሆነው የኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋና ደም ይነግረናል፡፡ የሕጉ ሁለት ጽላቶችም እግዚአብሄር ሕግ አውጪ መሆኑን ይነግሩናል፡፡ በእግዚአብሄር የጸኑት ሕጎች የሐጢያትና የሞት ሕግና የሐጢያት ስርየትና የደህንነት ሕግ ናቸው፡፡ ኢየሱስ አምላካችን በመሆኑ የሕይወትን ሕግና የኩነኔን ሕግ አዘጋጅቶልናል፡፡
 
ልክ እንደዚሁ የምስክሩ ታቦትና በውስጡ ያሉት ነገሮች በሙሉ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ይነግሩናል፡፡ እኛ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ነጽተን ደህንነታችንን መቀበል የምንችለው ኢየሱስ ክርስቶስ አዳኛችን መሆኑን በማመን ነው፡፡ እኛ ምንም ያህል ብቁዓን ባንሆንና ደካሞችም ብንሆን ኢየሱስ ክርስቶስ የመሰረታቸውን ሁለቱን ሕጎች ከተቀበልንና ከተከተልን አንድ ጊዜ ሐጢያተኞች ልንሆን እንችላለን፡፡ ከዚያም ዳግመኛ የሐጢያቶቻችንን ስርየት በመቀበል ጻድቃን እንሆንና የራሱ የእግዚአብሄር ሕዝብ እንሆናለን፡፡ ታምናላችሁን?
 
በዚህ ዘመን በመላው ዓለም የሚገኙ አብዛኞቹ ክርስቲያኖች በኢየሱስ የሚያምኑት በከንቱ ነው፡፡ ምክንያቱም በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የተገለጠውን እውነት አያውቁምና፡፡ እነርሱ ኢየሱስ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ብቻ በማመን የሐጢያት ስርየትን መቀበል እንደሚችሉ ያምናሉ፡፡ በሌላ አነጋገር ኢየሱስ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ብቻ እንዳዳናቸው ያምናሉ፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ ለደህንነታችን ብቻ በመስቀል ላይ ሞቷልን? ለቤዛነታችን ያደረገው ነገር ሁሉ ይህ ብቻ ነውን? በተቃራኒው በዮሐንስ በመጠመቅ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ አልወሰደምን? (ማቴዎስ 3፡13-15፤ 1ኛ ጴጥሮስ 3፡21፤ 1ኛ ዮሐንስ 5፡6)
 
ሆኖም የዘመኑ ክርስቲያኖች ኢየሱስ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ብቻ ስለሚያምኑ የሐጢያት ስርየትን የሚቀበሉት በከፊል ነው፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ ክርስቶስ አዳኛቸው መሆኑን በማመን ከአዳም ሐጢያታቸው ቢገላገሉም በየቀኑ የሚሰሩዋቸውን ሐጢያቶቻቸውን በራሳቸው ጥረት ለማስወገድ በመሞከር በየቀኑ የንስሐ ጸሎቶችን ያቀርባሉ፡፡ ይህ ደህንነት ምንኛ እርስ በርሱ የሚቃረን ነው? ነገሩ በእምነት ከፊል ሒጢያቶቻውን ብቻ ማስወገድና የቀረውን ደግሞ በራሳቸው ጥረቶች ለማስወገድ መሞከር ይመስላል፡፡
 
ነገሩ እንደዚህ ከሆነ እኔ የኢየሱስን ጥምቀትና ደም በማቆራኘት በተደጋጋሚ መስበኬን የማልቀጥለው ለምንድነው? በዚህ ዓለም ላይ የሚኖሩ ብዙ ክርስቲያኖች በጥንት ዘመን በነበረችው ቤተክርስቲያን ውስጥ ከነበሩት ክርስቲያኖች ተነጥለው እስካሁን ድረስ ጎደሎ ደህንነትን አምነዋል፡፡ ሰዎች ክርስትናን እንደ ዓለማዊ ሐይማኖት ብቻ አድርገው የሚያምኑት ለዚህ አይደለምን?
 
በቅርቡ በአሜሪካ የምትኖር ቫለሪያ ጆንስ የምትባል ሴት የዚህን የመገናኛውን ድንኳን ተከታታይ መጽሐፎች የመጀመሪያውን ቅጽ ካነበበች በኋላ የሐጢያት ስርየትን ተቀበለች፡፡ ይህንን መጽሐፍ ከማንበብዋ በፊት ቀደም ብላ ሌሎች ብዙ ዕትሞቻችንን አንብባ ነበር፡፡ መጽሐፎቻን ከሚናገሩት ጋር ብትስማማም ራስዋን ሙሉ በሙሉ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምን አድርጋ ማቅረብ አልቻለችም፡፡ አሁንም ድረስ ‹‹ይህ ትክክል ይመስላል፤ ታዲያ ለምን ብዙ አይሰብኩትም?›› በሚል ግራ መጋባት ውስጥ አንዳንድ ጥርጣሬዎች እንደነበሩዋት ነገረችኝ፡፡ ነገር ግን የመገናኛውን ድንኳን ተከታታይ መጽሐፎች የመጀመሪያውን ቅጽ ማንበብዋን ስትጨርስ የውሃው ወንጌል ትክክል እንደሆነና በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የተገለጠ ትክክለኛ እውነት እንደሆነ በማመን ግልጽ ወደሆነ የእምነት ደህንነት እንደመጣች መሰከረች፡፡
 
ከቤኒን የሆነና ይህንኑ መጽሐፍ ያነበበ ሌላ አንባቢ እንዲህ ሲል ጻፈልን፡- ‹‹መጽሐፋችሁን በማንበብ የሐጢያት ስርየትን ከተቀበልሁ በኋላ አሁን ቤተክርስቲያኔን ትቼ እንደወጣሁ ስታውቁ በአያሌው ትገረሙ ይሆናል፡፡ የምሄድበትን ቤተክርስቲያን ለምን ለቀቅሁ? ምክንያቱም እነርሱ መጽሐፍ ቅዱስ የማያስተምረውን እያደገ የሚሄድ የቅድስና ትምህርት ስለሚሰብኩ ነው፡፡ ይህ እያደገ የሚሄድ የቅድስና ትምህርት ሙሉ በሙሉ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሰረተ አይደለም፡፡ ሥጋዬ ፈጽሞ ሊቀደስ የማይችል ሆኖ ሳለ መቀደስ እንዳለብኝና እንደምችል ማስተማራቸውን ሲቀጥሉ እንዲህ ያለውን ስብከት ተጎልቶ መስማቱ ከምሸከመው በላይ ሆነብኝ፡፡
 
ከዚህ ቤተክርስቲያን የለቀቅሁትና ራሴን ከእነርሱ የለየሁት ለዚህ ነው፡፡ የእናንተን መጽሐፍ በማንበብ የሐጢያቶቼን ስርየት ስለተቀበልሁ የምከታተለውን ቤተክርስቲያን ከመልቀቅና ከአሁን ጀምሮም ራሴን ከእነርሱ ከመለየት በስተቀር ምርጫ አልነበረኝም፡፡ በዚህ ሁሉ ውስጥ ያለፍን እኛ አሁን የእምነት ሰዎች ሆነን ራሳችንን ከእግዚአብሄር ቤተክርሲያን ጋር እንዳቆራኘን የዚህ ዓለም ሰዎች በሙሉም ቃሉ ‹‹እውነትንም ታውቃላችሁ፤ እውነትም አርነት ያወጣችኋል›› እንደሚል እውነትን ብቻ ቢያውቁ ሊለወጡ ይችላሉ፡፡
 
በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ያለው የምስክሩ ታቦት ኢየሱስ ክርስቶስንም ደግሞ ይገልጣል፡፡ ይህ የምስክሩ ታቦት የተቀመጠው እጅግ ጥልቅ በሆነው የመገናኛው ድንኳን ክፍል ውስጥ ነበር፡፡ አንድ ሰው ይህንን ማየት የሚችለው የመገናኛውን ድንኳን መጋረጃ ከፍቶ ወደ ውስጥ በመግባት ነው፡፡ ከዚያም የቅድስተ ቅዱሳኑን መጋረጃ ይከፍትና ወደ ውስጥ ይዘልቃል፡፡ በሌላ አነጋገር የመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር የሚገኘው በስተ ምሥራቅ ሲሆን ታቦቱ የተቀመጠው ደግሞ በመገናኛው ድንኳን በስተ ምዕራብ ጫፍ ላይ ነበር፡፡
 
 
መሎጊያዎቹ ከታቦቱ አይወጡም፡፡ 
 
ዘጸዓት 25፡14-15 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ለታቦቱ መሸከሚያ በታቦቱ ጎን ባሉት ቀለበቶች መሎጊያዎችን አግባ፡፡ መሎጊያዎቹም በታቦቱ ቀለበቶች ውስጥ ይኑሩ፤ ከቶም አይውጡ፡፡›› እነዚህ ጥቅሶች ምን ማለት ናቸው? እግዚአብሄር በእነዚህ ጥቅሶች ራሳችንን ለእርሱ ቀድሰን በመስጠት የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ማገልገል እንደሚኖርብን እየነገሩን ነው፡፡ ወንጌል ሊሰራጭ የሚችለው ራሳችንን ለሥራው አሳልፈን በመስጠት ጌታን ማገልገል፣ ጌታችን ከእኛ በፊት የተጓዘበትን የመስቀሉን መንገድ መከተል ነው፡፡ እርሱ ለደቀ መዛሙርቶቹ ‹‹እኔን መከተል የሚወድ ቢኖር ራሱን ይካድ፤ መስቀሉንም ተሸክሞ ይከተለኝ›› (ማርቆስ ማርቆስ 8፡34) ያለው ለዚህ ነው፡፡
 
እውነተኛውን ወንጌል በመላው ዓለም ለማሰራጨት ትልቅ መስዋዕትነት፣ ጥረትና መከራ ጠይቋል፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ ምን ያህል ለውሃውና ለመንፈሱ ወንጌል መከራን እንደተቀበለ በማየት ይህንን መረዳት እንችላለን፡፡ ‹‹የክርስቶስ አገልጋዮች ናቸውን? እንደ እብድ ሰው እላለሁ እኔ እበልጣለሁ፡፡ በድካም፣ አብዝቼ በመገረፍ፣ አብዝቼ በመታሰር፣ አትርፌ በመሞት ብዙ ጊዜ ሆንሁ፡፡ አይሁድ እንኳ አንድ ሲጎድል አርባ ግርፋት አምስት ጊዜ ገረፉኝ፤ ሦስት ጊዜ በብትር ተመታሁ፤ አንድ ጊዜ በድንጋይ ተወገርሁ፡፡ መርከቤ ሦስት ጊዜ ተሰበረ፤ ሌሊትና ቀን በባህር ውስጥ ኖርሁ፡፡ ብዙ ጊዜ በመንገድ ሄደሁ፡፡ በወንዝ ፍርሃት፣ በወንበዴዎች ፍርሃት፣ በወገኔ በኩል ፍርሃት፣ በአሕዛብ በኩል ፍርሃት፣ በከተማ ፍርሃት፣ በምድረ በዳ ፍርሃት፣ በባህር ፍርሃት፣ በውሸተኞች ወንድሞች በኩል ፍርሃት ነበረብኝ፡፡ በድካምና በጥረት፣ ብዙ ጊዜም እንቅልፍ በማጣት፣ በራብና በጥም፣ ብዙ ጊዜም በመጦም፣ በብርድና በራቁትነት ነበርሁ፡፡ የቀረውንም ነገር ሳልቆጥር ዕለት ዕለት የሚከብድብኝ የአብያተ ክርስቲያናት ሁሉ አሳብ ነው፡፡›› (2ኛ ቆሮንቶስ 12፡23-28)
 
ነገር ግን እነዚያ ከኩነኔ ሁሉ ሊያድናቸው ራሱን አሳልፎ የሰጠውን ጌታ ከመውደድ ይልቅ ራሳቸውን የሚወዱ ራሳቸውን ለእግዚአብሄር መንግሥት መስዋዕት ሊያደርጉ አይችሉም፡፡ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ለማገልገል ቀላል የሚባል መንገድ የለም፡፡ ገበሬ ወዙን ሳያንጠፋጥፍ እንዴት ጥሩ ምርት ሊያገኝ ይችላል?
 
ልክ እንደዚሁ እኛም የምስክሩን ታቦት ለመሸከም መስዋዕቶችን መክፈል ይገባናል፡፡ በአንድ ወቅት ንጉሥ ዳዊት ታቦቱን በሰዎቹ አማካይነት በመሎጊያዎቹ በማሸከም ፋንታ በበሬዎች በሚሳብ አዲስ ሰረገላ ላይ ጭኖ ለማምጣት ሞከረ፡፡ በመንገዳቸው ላይ በሬዎቹ ስለተደናቀፉ ዖዛ የተባለ ሰው እጆቹን ወደ ታቦቱ ልኮ ታቦቱን ደገፈው፡፡ ያን ጊዜ የጌታ ቁጣ በዖዛ ላይ ነደደ፡፡ እግዚአብሄርም ስለ ስህተቱ በዚያ ቀሰፈው፡፡ ዖዛም እዚያው በእግዚአብሄር ታቦት ፊት ሞተ፡፡ (2ኛ ሳሙኤል 6፡1-7) ስለዚህ በዚህ ተደናግጦና በዚያች ቀንም ጌታን ፈርቶ ታቦቱን ወደ ጌት ሰው ወደ አቢዳራ ቤት ላከው፡፡ ከሦስት ወር በኋላ ታቦቱን ወደ ራሱ ቅጥር ያመጣው በራሱ ሰዎች ትከሻ ላይ አሸክሞ ነበር፡፡ ይህ ታሪክ እንደሚያሳየው የምስክሩን ታቦት እግዚአብሄር እንደነገረን በወዛችን፣ በደማችን፣ በመስዋዕታችንና ለወንጌሉ ባለን የማያመነታ መሰጠት በትክክል መሸከም አለብን፡፡
 
የሐጢያት ስርየትን በታላቅ ምስጋና የተቀበሉ ሰዎች ራሱን ለእኛ ለቀደሰው ጌታ ራሳቸውን ቀድሰው ለመስጠት እጅግ ደስተኞች ናቸው፡፡ እኛ ደጋግመን ጌታ አዳኛችንንና አምላካችንን እናመሰግናለን፡፡ በዚህ ምድር ላይ ወንጌልን እንድናገለግል ስለፈቀደልን እናመሰግነዋለን፡፡
 
ጌታ ይህንን የእውነት ወንጌል እንድናገለግል፣ እንድንከተለውና እርሱ የሚደሰትበትን ሕይወት እንድንኖር እኛን በመረጠበት በዚህ ሕልም መሰል እውነታ ሁላችንም ተደንቀን ከመጠን በላይ ተደስተናል፡፡ የደህንነትን እውነት እንድናውቅ መፍቀዱ ብቻ በደስታ ሊያጥለቀልቀን በቂ ነው፡፡ ነገር ግን ጌታ ወንጌልንም እንድናገለግል ፈቀደልን፡፡ እንዲህ ያሉ በረከቶች ተሰጥተውን ሳሉ እንዴት ላናመሰግነው እንችላለን? እግዚአብሄርን እጅግ እናመሰግነዋለን፡፡ ለዚህ ዓለምን በወንጌል የመድረስ ቅዱስ ተግባር ጊዜን፣ ጥረትን ወይም ሐብትን ሳንሰስት እውነተኛውን ወንጌል ለማሰራጨት ራሳችንን መስዋዕት እናደርግ ዘንድ የወደድነው ለዚህ ነው፡፡
የሐጢያት ስርየትን መቀበላችን በራሱ ከመጠን በላይ አመስጋኞች የሚያደርገን አንዳች ነገር ነው፡፡ እግዚአብሄር ግን እዚያ ላይ አላቆመም፡፡ ነገር ግን የእውነት ወንጌል የሆነውን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል እንድንገናኝና እንድናሰራጭ አስቻለን፡፡ ይህ ለእኛ ታላቅ በረከት እንጂ ሌላ ምንድነው?
 
ይህንን የውሃና የመንፈስ ወንጌል ለማገልገል የሚደፍር ሌላ ማነው? ማንም ሰው ይህንን ወንጌል ማገልገል አይችልም፡፡ ፖለቲከኞች፣ ከንቲባዎች፣ ፕሬዚዳንቶች፣ ነገሥታቶች ይህንን ወንጌል ማገልገል ይችላሉ? የእነዚህ ሰዎች ማህበራዊ ቦታ ምንም ያህል ትልቅ ቢሆንም የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል የማያውቁና የማያምኑበት ከሆነ እውነተኛውን ወንጌል ፈጽሞ ማገልገል አይችሉም፡፡ ሆኖም እግዚአብሄር እንዲህ ያለውን የማይገባ ዕድል ሰጥቶን ይህንን ወንጌል በተጨባጭ እንድናገለግል አስችሎናል፡፡ ይህ እንዴት ያለ ታላቅ በረከት ነው?
 
እኛን ስላዳነን ጸጋው ጌታን አመሰግነዋለሁ፡፡ ምክንያቱም ወዶናልና፡፡ ወንድሞችና እህቶች እኛ ኢየሱስ ክርስቶስ አምላካችንና አዳኛችን እንደሆነ እናምናለን፡፡ እኛ በመንፈሳዊው እምነታችን አማካይነት የኢየሱስን ሥጋ የበላንና ደሙን የጠጣን የእግዚአብሄር ሕዝብ ነን፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ኢየሱስ የሕያዋን አምላክ እንጂ የሙታን አምላክ እንዳልሆነ ይናገራል፡፡ (ሉቃስ 20፡38) እዚህ ላይ ሕያዋኖቹ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የዘላለምን ሕይወት የተቀበሉት ናቸው፡፡ በዚህ የእውነት ወንጌል የማያምን ማንኛውም ሰው መንፈሳዊ ሙት ነው፡፡ በዚህ የእውነት ወንጌል የሚያምን ማንኛውም ሰው በመንፈሳዊ ሁኔታው ሕያው ነው፡፡ እግዚአብሄር በእርግጥም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ለሚያምኑ አምላክ ነው፡፡
 
ወንድሞችና እህቶች ኢየሱስ ራሱ በሥጋውና በደሙ አማካይነት የሐጢያት ስርየትን ሰጥቶናል፡፡ በዚህ እውነት ካላመናችሁ ከኢየሱስ ጋር ዕድል ፈንታ እንደሌላችሁ መረዳት አለባችሁ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ሰማያዊ በረከቶች፣ የዘላለም ሕይወትና ለሐጢያቶቻችሁም ስርየትን ሰጥቶዋችኋል፡፡ ዘላለማዊ በረከቶችን የለገሳችሁ፣ የመራችሁና የጠበቃችሁ እረኛ ማነው? የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ፈጻሚ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ኢየሱስ ይህ አምላክ ነው፡፡ ሁላችሁም ይህንን ኢየሱስን አምላካችሁ አድርጋችሁ እንድታምኑበት ተስፋ አደርጋለሁ፤ እጸልይማለሁ፡፡
 
እኔ በዚህ እውነት ማመንና አሁኑኑ እግዚአብሄርን ማገልገል ብቻ ሳይሆን ወደፊትም ሁልጊዜ ይህንን በማድረግ እቀጥላለሁ፡፡ ነገር ግን እናንተስ? በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ታምናላችሁን? በእምነታችሁ በእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ውስጥና በክርስቶስ ፍቅር መኖር እንደሚገባችሁ ታምናላችሁን? ሁላችንም ጌታን እስከምንገናኘው ድረሰ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እያመንን ሕይወታችን እንኑር፡፡