Search

የመገናኛው ድንኳን ጥናት፤

ቅድስቱ ስፍራ

ተዛማጅ ስብከቶች

· የቅደስቱ ስፍራ መጋረጃና ምሰሶዎች፡፡ ‹‹ዘጸዓት 26፡31-37››

የቅደስቱ ስፍራ መጋረጃና ምሰሶዎች፡፡
‹‹ ዘጸዓት 26፡31-37 ››
‹‹መጋረጃውንም ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊም፣ ከቀይም ግምጃ ከተፈተለ ከጥሩ በፍታም አድርግ፡፡ ብልህ ሰራተኛ እንደሚሰራ ኪሩቤል በእርሱ ላይ ይሁኑ፡፡ በወርቅ በተለበጡት ከግራር እንጨትም በተሰሩት በአራቱ ምሰሶች ላይ ስቀለው፡፡ ኩላቦቻቸውም ከወርቅ አራቱም እግሮቻቸው ከብር የተሠሩ ይሁኑ፡፡ መጋረጃውንም ከመያዣዎቹ በታች ታንጠለጥለዋለሁ፡፡ በመጋረጃውም ውስጥ የምስክርን ታቦት አግባው፡፡ መጋረጃውም በቅድስቱና በቅድስተ ቅዱሳኑ መካከል መለያ ይሁን፡፡ በቅድስተ ቅዱሳኑም ውስጥ የስርየት መክደኛውን በምስክሩ ታቦት ላይ አድርግ፡፡ ገበታውንም በመጋረጃው ውጭ መቅረዙንም በገበታው ፊት ለፊት በማደርያውም በደቡብ ወገን አድርግ፡፡ ገበታውንም በሰሜን ወገን አድርገው፡፡ ለድንኳኑም ደጃፍ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊም፣ ከቀይም ግምጃ ከተፈተለ ከጥሩ በፍታም በጥልፍ አሰራር የተሰራ መጋረጃ አድርግለት፡፡ ለመጋረጃውም አምስት ምሰሶች ከግራር እንጨት አድርግ፡፡ በወርቅም ለብጣቸው፤ ኩላቦቻቸው ከወርቅ የተሰሩ ይሁኑ፤ አምስትም እግሮች አድርግላቸው፡፡››
 
 
ቅድስቱ ስፍራ፡፡ 
 
ቅድስቱ ስፍራ
በቅድስቱ ስፍራ ውስጥ ስላሉት ምሰሶዎችና ስለ መጋረጃዎቹ ቀለማቶች መንፈሳዊ ትርጉሞች ማሰላሰል እፈልጋለሁ፡፡ እዚህ ላይ እየተመለከትነው ያለው የመገናኛው ድንኳን 45 ጫማ ርዝመትና 15 ጫማ ስፋት ያለው ሲሆን ቅድስትና ቅድስተ ቅዱሳኑ ተብለው በሚጠሩ ሁለት ክፍሎች ተከፍሎዋል፡፡ በቅድስቱ ውስጥ መቅረዙ፣ የሕብስቱ ገበታና የዕጣኑ መሰውያ ያሉ ሲሆን በቅድስተ ቅዱሳኑ ውስጥ ደግሞ የምስክሩ ታቦትና የስርየት መክደኛው ይገኛሉ፡፡
 
ቅድስቱንና ቅድስተ ቅዱሳኑን የያዘው የመገናኛው ድንኳን በሁሉም ወገን ዙሪያውን 2.3 ጫማ ስፋትና 15 ጫማ ርዝመት ባላቸው የግራር እንጨት ሳንቃዎች የተከበበ ነው፡፡ በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ላይ በወርቅ የተለበጡ አምስት የግራር እንጨት ምሰሶዎች ይደረጋሉ፡፡ አንድ ሰው ከውጪው አደባባይ ወደ መገናኛው ድንኳን የሚገባበት የመግቢያው በር ራሱ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ግምጃና ከጥሩ በፍታ የተሰራ ነው፡፡
 
በመገናኛው ድንኳን አደባባይ ውስጥ እያንዳንዳቸው 7.5 ጫማ ርዝመት ያላቸው ስልሳ ምሰሶዎች ተተክለው ነበር፡፡ በስተ ምስራቅ ያለው የአደባባዩ መግቢያ በርም እንደዚሁ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ግምጃና ከጥሩ በፍታ የተሰራ ነበር፡፡ ማንኛውም ሰው ወደ መገናኛው ድንኳን አደባባይ መግባት የሚችለው በዚህ በውጪው አደባባይ በር ውስጥ በማለፍ ብቻ ነበር፡፡ በዚህ በመገናኛው ድንኳን አደባባይ ውስጥ የሚቃጠለው መስዋዕት የሚቀርብበት መሰውያና የመታጠቢያው ሰን ይገኛሉ፡፡
 
አንድ ሰው እነዚህን ሁሉቱን ካለፈ በኋላ 15 ጫማ ርዝመት ወዳለው የመገናኛው ድንኳን በር ይደርሳል፡፡ ይህ የመገናኛው ድንኳን በር የናስ ኩላቦች ያሉዋቸው አምስት ምሰሶች አሉት፡፡ የመገናኛው ድንኳን በር ልክ እንደ መገናኛው ድንኳን አደባባይ የመግቢያ በር ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ በተሰሩና በአምስቱ ምሰሶዎች ጫፍ ላይ በተሰሩ የወርቅ ኩላቦች ላይ የተንጠለጠሉ ነበሩ፡፡ ይህ መጋረጃ የመገናኛውን ድንኳን በስተ ውስጥና በስተ ውጪ የሚለይ መለያ ነበር፡፡
 
 
በመጀመሪያ ማጤን የሚገባን የመገናኛውን ድንኳን በር ምሰሶች ነው፡፡ 
 
የመገናኛው ድንኳን በር አምስቱ ምሰሶዎች 15 ጫማ ቁመት አላቸው፡፡ በእነዚህ ምሰሶዎች ላይ ከአራቱ የሰማያዊ፣ የሐምራዊ፣ የቀይና የጥሩ በፍታ ግምጃዎች የተጠለፈ መጋረጃ ተንጠልጥሎባቸዋል፡፡
 
በመጀመሪያ 15 ጫማ ቁመት ባላቸው የመገናኛው ድንኳን በር አምስት ምሰሶዎች ላይ እናተኩር፡፡ የዚህ ትርጉም ምንድነው? ይህ ማለት እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን ለመደምሰስና ልጆቹ ለማድረግ ራሱ ታላቁን መስዋዕት ከፍሎዋል ማለት ነው፡፡ እናንተና እኔ ከመጀመሪያውም እንዲህ ብቃት የሌለንና ደካሞች በመሆናችን በዚህ ዓለም ላይ እየኖርን ያለነው ብዙ መተላለፎችንን እየፈጸምን ነው፡፡ እናንተና እኔ በዚህ ዓለም ላይ በየቅጽበቱ ሐጢያት የምንሰራ እጅግ የለየልን ሐጢያተኞች ስለሆንን ብዙ እንከኖችና መተላለፎች አሉብን፡፡ እነዚህ የመገናኛው ድንኳን በር አምስቱ ምሰሶዎች እግዚአብሄር እኛን ከእነዚህ እንከኖችና ከዓለም ሐጢየት ለማዳን አንድያ ልጁን ኢየሱስ ክርስቶስን የሐጢያታችን ደመወዝ አድርጎ መስዋዕት በማድረግ በእርግጥም ከዓለም ሐጢያቶች አድኖናል፡፡
 
በሌላ አነጋገር ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋውን መስዋዕት አድርጎ በእግዚአብሄር ፊት ያቀረበውና የዓለምን ሐጢያቶች ደመወዝ ከበቂ በላይ የከፈለው ስለ እንከኖቻችንና በዚህ ዓለም ላይ ስለፈጸምናቸው ሐጢያቶች ነው፡፡ ይህንን በማድረግም አድኖናል፡፡ አንድ ሰው በደልን ቢያደርግና የጌታን የተቀደሱ ነገሮች በሚመለከት ሳያውቅ ሐጢያት ቢሰራ አንድ አውራ በግ ለበደል መስዋዕት አድርጎ ያቀርባል፡፡ በዚህ ላይም አምስተኛ እጅ ጨምሮ ለካህናት ይሰጣል፡፡ (ዘሌዋውያን 5፡15-16) ይህ ማለት ኢየሱስ ክርስቶስ እናንተንና እኔን ለማዳን ራሱን ሰጥቶ የሐጢያቶቻችንን ደመወዝ ከበቂ በላይ ከፍሎዋል ማለት ነው፡፡ ጌታችን ሐጢያቶቻችንን ለመደምሰስና ለእነዚህ ሐጢያቶቻችንም ራሱን የበደል መስዋዕት አድርጎ ለመስጠት ወደዚህ ምድር መጣ፡፡
 
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጠቀሱት የሚቃጠል መስዋዕት፣ የሐጢያት መስዋዕትና የደህንነት ቁርባን የተሰጡት ሐጢያት የሰሩ ሰዎች ባቀረቡዋቸው መስዋዕቶች ላይ እጆቻቸውን ጭነው ሐጢያቶቻቸውን ማስወገድ ይችሉ ዘንድ ነበር፡፡ ከእነዚህ መስዋዕቶች ውስጥ አንዱ የበደል መስዋዕት ሲሆን የዚህ መስዋዕት ዓላማ የአንድን ሰው እንከኖች መደምሰስ ነበር፡፡ ይህ የበደል መስዋዕት የሚቀርበው አንድ ሰው በቸልተኝነት ሌላውን በሚጎዳበት ጊዜ ለተጎጂው ካሳ በመስጠት ዝምድናቸውን ለማደስ ነው፡፡ የበደል መስዋዕቱ ቅጣቶችንና ጉዳቶችን ጨምሮ ከጠቅላላው የካሳ ክፍያ ላይ 20 እጅ የካሳ ጭማሪን ያካትታል፡፡ የበደል መስዋዕቱ መሰረታዊ መጠይቅ ይህ ነበር፡፡ ይህ መስዋዕት በሌላ ሰው ጉዳት የደረሰበትን ግለሰብ ለማስተሰረይ ዓላማ የተሰጠ መስዋዕት ነበር፡፡ (ዘሌዋውያን 5፡14-6፡7)
 
እናንተና እኔ ከሐጢያት ተራርቀናልን? የሕይወት ዘመናችንን በሙሉ የኖርነው ሐጢያት በመስራት አይደለምን? ይህንን የማድረጉን ነገር ማስወገድ አንችልም፡፡ ምክንያቱም እናንተና እኔ የአዳም ዘሮች ነንና፡፡ ምን ያህል ጉድለቶች እንዳሉብንና ብዙ ሐጢያቶችን በመስራት እንዴት ሕይወታችንን እንደምንኖር ራሳችን እናውቀዋለን፡፡ በእርስ በርሳችንና በእግዚአብሄር ላይ ምን ያህል ክፋቶችን ፈጽመናል? ብዙውን ጊዜ ኑሮዋችንን ስንኖር እነዚህን ክፋቶች የምንረሳቸው ሐጢያቶች መሆናቸውን ለመረዳት በጣም ዘገምተኞችና ብቁ ስላልሆንን ነው፡፡ ነገር ግን እናንተና እኔ በእርስ በርሳችንና በእግዚአብሄር ላይ በጣም ብዙ በደሎችን ስለፈጸምን በእግዚአብሄር ፊት ሐጢያተኞች መሆናችንን ከመገንዘብ ማምለጥ አንችልም፡፡
 
እነዚህን ሐጢያተኞች ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ለማዳን እግዚአብሄር ኢየሱስ ክርስቶስን የበደል መስዋዕታቸው አድርጎ ሊልክ ፈለገ፡፡ እግዚአብሄር በመስዋዕቱ ዋጋ አማካይነት ኢየሱስ ክርስቶስ የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ እንዲሸከም በማድረግ የደህንነትን ስጦታ ሰጥቶናል፡፡ እግዚአብሄር አብ ልጁን ወደዚህ ምድር ልኮ እንዲጠመቅና እንዲሰቀል በማድረግ ሁላችንንም ከሐጢያቶቻችን አድኖ የራሱ ሕዝቦች አድርጎን ሳለ ራሳችንን ከዚህ መስዋዕት ክቡርነት ጋር እንዴት ማነጻጸር እንችላለን? ጌታችን እኛን ሐጢያተኞችን ከሐጢያቶቻችን ለማዳን መስዋዕት በመሆን የሐጢያቶቻችንን ዋጋ በሙሉ ከፍሎ ከዓለም ሐጢያቶቻችን ሁሉ አዳነን፡፡ ይህ አስደናቂ ከሆነው የእግዚአብሄር ጸጋ ውጪ እንዴት ሌላ አንዳች ነገር ሊሆን ይችላል? የመገናኛው ድንኳን በር አምስቱ ምሰሶዎች 15 ጫማ ቁመት ያላቸው መሆናቸው እግዚአብሄር በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት ለእኛ ስላለው ፍቅር ይነግረናል፡፡
 
ጌታችን እንደ እኛ ዓይነቱን ከንቱ ፍጡራን ከሐጢያት ኩነኔ አርነት ለማውጣት በራሱ መስዋዕት አማካይነት አዳነን፡፡ ለዚህ እውነት አመስግነናል፡፡ ለሐጢያቶቻችን ቅጣት ይሆን ዘንድ ለሲዖል የታጨነውን ሰዎች ጌታችን ሥጋውን ሰጥቶ ከእነዚህ ሐጢያቶቻችን በከበረው ሰውነቱ ወሰደ፡፡ ከሐጢያቶቻችን አድኖን ሳለ እንዴት አናመሰግነውም? እናመሰግነዋለን! ኢየሱስ በዮሐንስ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችንን በከበረው ሰውነቱ ወሰደ፡፡ የሐጢያቶቻችንንም ዋጋ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ከፈለ፡፡ በዚህ ከሐጢያቶቻችንና ከኩነኔያችን ሁሉ አዳነን፡፡ ስለዚህ በዚህ ወንጌል ላይ ባለን እምነታችን እናመሰግነዋለን፡፡ በመገናኛው ድንኳን በር ላይ ያሉት የአምስቱ ምሰሶዎች ጥልቅ የደህንነት ትርጉም ይህ ነው፡፡
 
የመገናኛው ድንኳን በር አምስቱ ምሰሶዎች እያንዳንዳቸው 15 ጫማ ቁመት ነበራቸው፡፡ ‹‹5›› ቁጥር በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ‹‹የእግዚአብሄርን ጸጋ›› ያመለክታል፡፡ ስለዚህ አምስት ምሰሶዎች መኖራቸው እግዚአብሄር የሰጠንን የደህንነት ስጦታ ያመለክታሉ፡፡ እግዚአብሄር እኛን በመውደድና በደህንነት ፍቅሩ በመሸፈን የእርሱ ሕዝቦች እንሆን ዘንድ አንዳች የማይጎድለን አደረገን፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ወርቅ የሚያመለክተው በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ አማካይነት ባዳነን አምላክ የሚያምነውን እምነት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር መጽሐፍ ቅዱስ ወርቅን ሲጠቅስ እግዚአብሄር ራሱ ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን መውሰዱን፣ በመስቀል ላይ መሞቱን፣ ከሙታን መነሳቱንና በዚህም እኛን ፍጹም ጻድቃን ማድረጉን በሚናገረው እውነት ከሙሉ ልብ የሚያምነውን ‹‹እምነት›› መጥቀሱ ነው፡፡ የቅድስቱ ምሶሶዎች ሙሉ በሙሉ በወርቅ የተለበጡት ለዚህ ነው፡፡
 
የመገናኛው ድንኳን በር ምሰሶዎች ኩላቦች ከናስ የተሰሩ መሆናቸው ጌታ በይፋ ተኮንኖ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ አማካይነት በሐጢያታችን የተነሳ በእርግጥም ለሲዖል ከመታጨት ማምለጥ የማንችለውን እኛን እንዳዳነን ይገልጣል፡፡ እኛ በእንከኖች የተሞላን በመሆናችን ሞትን ማምለጥ የማንችል ከንቱ ፍጡራን ነበርን፡፡ ነገር ግን እኛን የራሱ ሕዝብ ለማድረግ ከእኛ እጅግ የሚልቀው ፍጹምና ቅዱስ አምላክ ራሱን መስዋዕት አድርጎ የእግዚአብሄር አብ ልጆች አደረገን፡፡ ወርቅ በዚህ እውነት የሚያምነውን እምነት የሚያመለክተው ለዚህ ነው፡፡ የመገናኛውን ድንኳን በር ቀለማቶች መረዳት የሚገባን በዚህ መንገድ ነው፡፡ ይህንን ልናሰላስለው፣ ልናወድሰውና ከሙሉ ልባችንም ልናምነው ይገባናል፡፡
 
 
የመገናኛው ድንኳን ምሰሶዎች የናስ ኩላቦች፡፡ 
 
በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ከናስ የተሰሩት የበሩ ምሰሶዎች ኩላቦች ብቻ ነበሩ፡፡ ይህ ማለት እናንተና እኔ በዚህ ምድር በእርስ በርሳችንና በእግዚአብሄር ላይ ብዙ ሐጢያቶችን ስለሰራን ለእነዚህ ሐጢያቶች ከመኮነን ማምለጥ አንችልም ማለት ነው፡፡ በእነዚህ የናስ ኩላቦች ውስጥ የተሰወረው እውነት ስለሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ እንዳንስብ ያደርገናል፡፡ ሐጢያተኞች የመግቢያውን በር አልፈው ወደ መገናኛው ድንኳን አደባባይ ሲገቡ መጀመሪያ የሚገጣጠሙት የሚቃጠሉ መስዋዕቶች ከሚቀርቡበት ከዚህ መሰውያ ጋር ነው፡፡
 
እዚህ ላይ ‹‹መሰውያ›› የሚለው ቃል ‹‹ማረግ›› የሚል ትርጉም አለው፡፡ የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ኢየሱስ ክርስቶስ መጠመቁንና በእኛ በሐጢያተኞች ሁሉ ፈንታም በመስቀል ላይ በይፋ መስዋዕት የመሆን እውነት ከማመላከት በቀር ሌላ የሚያመለክተው ነገር የለም፡፡ የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ በእጆች መጫን አማካይነት መስዋዕቶች ሐጢያቶችን ተቀብለው ለእነዚህ ሐጢያቶች የሞት ቅጣትን የሚቀበሉበት ስፍራ ነው፡፡ ካህናት የእነዚህን መስዋዕቶች ደም በሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ቀንዶች ላይ በመቀባት የቀረውን ደም ከበታቹ ባለው አሸዋማ መሬት ላይ ያፈሱትና ሥጋቸውን በመሰውያው ላይ በእሳት ያቃጥሉታል፡፡ መሰውያው ሐጢያቶችን የወሰዱ መስዋዕቶች የሚገደሉበት ስፍራ ነው፡፡
 
የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ የተቀመጠው በመገናኛው ድንኳን አደባባይ የመግቢያ በርና በራሱ በመገናኛው ድንኳን መካከል ነበር፡፡ ስለዚህ ወደ መገናኛው ድንኳን መግባት የሚፈልግ ሁሉ በመጀመሪያ በዚህ የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ በኩል ማለፍ አለበት፡፡ በሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ውስጥ ሳይታለፍ ወደ መገናኛው ድንኳን የሚገባበት መንገድ ፈጽሞ የለም፡፡ ይህም የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ በግልጽ የኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀትና መስቀል ጥላ ነው፡፡ የጌታችን ጥምቀትና መስቀሉ በእግዚአብሄር ፊት የሚቀርቡ ሐጢያተኞችን በደሎች ሁሉ የሚያስወገዱ ናቸው፡፡
 
ስለዚህ ማንም ሐጢያተኞች በመጀመሪያ ሐጢያቶቻቸውን ሳያቀርቡ፣ በሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ አጠገብ ሳይቆሙና ለመስዋዕት የቀረበው ቁርባን በእጆች መጫን አማካይነት እነዚህን ሐጢያቶች በመውሰድና በዚህ ስፍራ የመስዋዕት ደሙን በማፍሰስ እንዳዳናቸው ሳያስታውሱ በእግዚአብሄር ፊት መቼም መቅረብ አይችሉም፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ለመቅረብ መንገዱ ይህ እምነት ነው፡፡ ወደ ሐጢያት ስርየታችን የሚመራንና የሐጢያት ቅጣታችንን (ማለትም ለሐጢያት ወደ መሞት) ወደ መቀበል የሚመራንም ይኸው እምነት ነው፡፡
 
የእስራኤል ሕዝብ ሐጢያቶቻቸውን ለማስወገድ በመጀመሪያ እጆቻቸውን በራሱ ላይ በመጫን ሐጢያቶቻቸውን ወደ መስዋዕቱ መሻገርና ማረድ፣ ደሙንም ማፍሰስ፣ ከዚያም ይህንን ደም በመሰውያው ቀንዶች ላይ በመቀባት የቀረውን ደም በሙሉ ከመሰውያው በታች ማፍሰስ ነበረባቸው፡፡ ከሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ በታች ያለው ወለል መሬት ነው፡፡ እዚህ ላይ መሬት የሚያመለክተው የሰዎችን ልብ ነው፡፡ ስለዚህ ሐጢያተኞች የሐጢያት ስርየትን የሚቀበሉት መስዋዕቱ በደህንነት ሕግ መሰረት ሐጢያቶቻቸውን ወስዶ በምትካቸው መሞቱን ይነግረናል፡፡ የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ቀንዶች በመንፈሳዊ ሁኔታ በፍርድ መጽሐፍ ውስጥ የተጻፉትን ሐጢያቶቻችንን ይነግሩናል፡፡
 
በብሉይ ኪዳን ዘመን ይኖሩ የነበሩ ሐጢያተኞች የሐጢያት ስርየታቸውን የተቀበሉት እጆቻቸውን በመስዋዕቱ ቁርባን ራስ ላይ በመጫን ሐጢያቶቻቸውን ወደ እርሱ በማሻገሩ እውነታ በማመናቸው ነበር፡፡ ከዚያም ይህ መስዋዕት ደሙን ያፈስስና በመሰውያው ላይ ይቀርባል፡፡ ሐጢያተኞች ለሐጢያቶቻቸው ስርየትን እንዲያገኙ የሚያስችላቸው የእጆች መጫን የመስዋዕት ቁርባኑ ሞትና መቃጠል ባይኖር ኖሮ ወደ እግዚአብሄር የሚቀርቡበት መንገድ ፈጽሞ ይገደብና ቅዱስ በሆነው አምላክ ፊት መቅረብ ባልቻሉም ነበር፡፡ በአጭሩ በእግዚአብሄር ፊት እንዲቀርቡ ከሚያስችላቸው ከዚህ የመስዋዕት ቁርባን በስተቀር ሌላ እውነት የለም፡፡
 
በኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀት፣ በሞቱና በስርየት መስዋዕቱ እምነት ከሌለን የሐጢያቶቻችንን ስርየት የምንቀበልበትና በእግዚአብሄር ፊት የምንቀርብበት መንገድ አይኖርም፡፡ የእስራኤል ሕዝብ እጅግ ያማረ፣ ፍጹም፣ ጣፋጭና ነውር የሌለበት ጠቦት ወደ ካህናቶቻቸው ይዘው ቢቀርቡም እጆቻቸውን በራሱ ላይ ካልጫኑ፣ ጠቦቱም ሐጢያቶቻቸውን ካልተቀበለና ደሙን አፍስሶ ካልሞተ ይህ ምንም ዓይነት ውጤት አይኖረውም፡፡
 
ወደ እምነታችን ስንመጣ ኢየሱስ ክርስቶስ ከዮሐንስ የተቀበለው ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ክቡር ደሙ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንዳስወገደ የማናምን ከሆንን የሐጢያቶቻችንን ፍጹም ስርየት ተቀብለናል ማለት አንችልም፡፡ ኢየሱስ የተቀበለው ጥምቀትና የመስቀል ላይ ሞቱ በሐጢያተኞችና በእግዚአብሄር አብ መካከል በግልጽ ይቆማል፡፡ ስለዚህ እነርሱ ሐጢያተኞችን ከሐጢያቶቻቸው ለማዳን አስታራቂ ክፍሎች ይሆናሉ፡፡
 
የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ሁሉን ቻይ አምላክ ራሱ በሰማይ አዘጋጅቶ በኢየሱስ ክርስቶስ የፈጸመውን የደህንነት ዕቅድ የያዘ ሞዴል ነው፡፡ ሙሴ የመገናኛውን ድንኳን የሰራው እግዚአብሄር በሲና ተራራ ባሳየው የደህንነት ዘዴና ምሳሌ ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስንመለከት ይህ መመሪያ በተደጋጋሚ እንደተሰጠ እናያለን፡፡ ዘጸዓት 25፡40 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በተራራው ላይ ባሳየሁህ ምሳሌ መሰረት እንድትሰራው ተጠንቀቅ፡፡›› 
ሰዎች መስቀልን ሰርተው ኢየሱስ ክርስቶስን እዚያ ላይ ሰቅለውት ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን ከዚህ በሻገር ሌላ አንዳች ነገር ማድረግ አይችሉም፡፡ እጆቹን አስረውም ወደ ቀራንዮ ነድተውት ሊሆን ይችላል፡፡ በእግዚአብሄር ፊት እያደረጉ የነበሩትን ሳያውቁ ሰቀሉት፡፡ ሐጢያተኞች እስከዚህ ድረስ መሄድ ችለዋል፡፡ ምክንያቱም እነዚህ ነገሮች እግዚአብሄር አስቀድሞ ባቀደው መሰረት በቸርነቱ መፈጸም ነበረባቸውና፡፡ ነገር ግን በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅና የዓለምን ሐጢያቶች በመውሰድ በአንድ ጊዜ አስወግዶ ደሙን በመስቀል ላይ በማፍሰስ ሐጢያተኞችን ሁሉ በጥምቀቱና ባፈሰሰው ደሙ አማካይነት ለአንዴና ለመጨረሻ ያዳነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡
 
ስለዚህ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ከመሞቱ በፊት ከዮሐንስ የተቀበለው ጥምቀት ለደህንነታችን ፈጽሞ አስፈላጊ የሆነ እጅግ ወሳኝ ሁነት ነበር፡፡ እርሱ ሐጢያቶቻችንንና የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ መሸከሙ ከፍጥረት በፊት በእግዚአብሄር የተወሰነ ነበር፡፡ ኢየሱስ በዮሐንስ 3 ውስጥ ለኒቆዲሞስ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ይህ እንደሆነ ነግሮታል፡፡ ስለዚህ የኢየሱስ ጥምቀትና መስቀል አስቀድሞ በኢየሱስ ክርስቶስ የታቀደና የተወሰነ የእግዚአብሄር ዕጣ ፋንታ ነበር፡፡
 
ኢየሱስ ራሱ እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት አንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሄር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና፡፡›› (ዮሐንስ 3፡16) ጴጥሮስም ስለ ኢየሱስ ጥምቀት እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድነናል፡፡›› (1ኛ ጴጥሮስ 3፡21) በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ውስጥም እንዲህ ተጽፎዋል፡- ‹‹እርሱንም በእግዚአብሄር በተወሰነው አሳቡና በቀደመው ዕውቀቱ ተሰጥቶ በዓመጸኞች እጅ ሰቅላችሁ ገደላችሁት፡፡›› (የሐዋርያት ሥራ 2፡23)
 
እግዚአብሄር የተቀበለው ጥምቀቱና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ በሙሉ የተፈጸሙት ሁሉን በሚችለው አምላክ ዕቅድና አሳብ ነው፡፡ ስለዚህ ማንም ሰው ይህንን እውነት በልቡ ሳይቀበልና በዚህ እውነት ሳያምን ወደ እግዚአብሄር መንግሥት መግባት ስለማይችል እግዚአብሄር ከእኛ እምነትን እንደሚጠይቅና እኛም እምነት ሊኖረን እንደሚገባ መረዳት አለብን፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምን እምነት ሳይኖረው ማንም መዳን አይችልም፡፡ ኢየሱስ በራሱ ፈቃድ በዮሐንስ ለመጠመቅ ራሱን በሐጢያተኞች እጅ አሳልፎ ለመስጠትና በመስቀል ላይ ደሙን ለማፍሰስ ባይወስን ኖሮ ሐጢያተኞች ፈጽመው ሊሰቅሉት ባልቻሉም ነበር፡፡ ኢየሱስ በሌሎች ወደ ቀራንዮ እየተጎተተ ለመወሰድ አልተገደደም፡፡ ነገር ግን በጥምቀቱ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በራሱ ላይ የወሰደው፣ በመስቀል ላይ ደሙን ያፈሰሰው፣ በዚህም ሐጢያተኞችን ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ያዳነው ሙሉ በሙሉ በራሱ ፈቃድ ነበር፡፡
 
ኢሳይያስ 53፡7 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ተጨነቀ፤ ተሰቃየም፤ አፉንም አልከፈተም፡፡ ለመታረድ እንደሚነዳ ጠቦት በሸላቾቹም ፊት ዝም እንደሚል በግ እንዲሁ አፉን አልከፈተም፡፡›› ስለዚህ የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀትና የመስቀል ላይ ሞቱ ሙሉ በሙሉ በፈቃዱ ያደረጋቸው ነገሮች ናቸው፡፡ በእነዚህ አማካይነትም በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ደሙ የሚያምኑትን ለአንዴና ለመጨረሻ ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ አድኖዋቸዋል፡፡ የዕብራውያን መጽሐፍ ጸሐፊ ስለ እነዚህ የጌታ ሥራዎች ጽፎዋል፡- ‹‹አሁን ግን በዓለም ፍጻሜ ራሱን በመሰዋት ሐጢአትን ሊሽር አንድ ጊዜ ተገልጦዋል፡፡›› (ዕብራውያን 9፡26)
 
የኢየሱስ ክርስቶስን ጥምቀትና የመስቀል ላይ ሞቱን በሚያሳየን በሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ የሰማይን መንፈሳዊ የደህንነት ስጦታ በተጨባጭ መመስከር እንችላለን፡፡ በሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ላይ የሚሆነው የመስዋዕቱ ሞት በእያንዳንዱ ሰው ሐጢያቶች ምክንያት የተጠየቀውን የኢየሱስ ጥምቀትና ሞት የሚያመለክት ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ሐጢያተኞች የሐጢያቶቻቸውን ስርየት የሚያገኙት በእጆቻቸው መጫን ሐጢያቶቻቸውን በመውሰድ በምትካቸው በሚሞተው መስዋዕት አማካይነት ነው፡፡ በተመሳሳይ መንገድም በአዲስ ኪዳን የእግዚአብሄር ልጅ በጨካኞች እጅ በቀራንዮ ከመገደሉ በፊት በመጀመሪያ በዮሐንስ በመጠመቅ የዓለምን ሐጢያቶች ወሰደ፡፡ ኢየሱስ የተሰቀለው፣ ደሙን ያፈሰሰውና የሞተው በዚህ ምክንያት ነበር፡፡
 
ስለዚህ እግዚአብሄር ኢየሱስ እጆች እንዲጫኑበትና እስከ ሞት ድረስ እንዲሰቀል አቀደ፡፡ አስቀድሞም ወሰነ፡፡ ይህ ሁሉ የተደረገው የእርሱን ልጅ በገደሉት ነፍሰ ገዳዮችና በእርሱ መካከል ሰላምን ለመፍጠር ነበር፡፡ እግዚአብሄር በእጆች መጫንና በሞት የተደነገገውን የደህንነት ሕግ አቀደ፡፡ በዚህ ሕግ መሰረትም የእስራኤል ሕዝብ መስዋዕታቸውን ለእርሱ በማቅረብ የሐጢያቶቻቸውን ስርየት እንዲያገኙ ፈቀደላቸው፡፡
 
በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር ሐጢያተኞችን ለማዳን ሲል ብቻ የደህንነት መስዋዕት ሆነ፡፡ ይህ የእግዚአብሄር ደህንነት ምን ያህል ልኬት የሌለው፣ ጥልቅ፣ ጠቢብና ጻድቅ ነው! የእርሱ ጥበብና እውነት የሚያስገርም፣ ድንቅና በእኛ ሊደረስበት የማይችል ነው፡፡ እጆችን በመጫንና በሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ በተገለጠው ደምን የማፍሰስ ስርዓት የተደነገገውን የደህንነት ዕጣ ፋንታ ማን ሊያስበው ይደፍራል? ልክ እንደ ጳውሎስ ማድረግ የምንችለው ነገር ቢኖር መደነቅ ብቻ ነው፡፡ ‹‹የእግዚአብሄር ባለጠግነትና ጥበብ ዕውቀቱም እንዴት ጥልቅ ነው! ፍርዱም እንዴት የማይመረመር ነው! ለመንገዱም ፍለጋ የለውም፡፡›› (ሮሜ 11፡33) የውሃው፣ የደሙና የመንፈሱ ወንጌል እግዚአብሄር ሐጢያተኞችን ፈጽሞ ያዳነበት ብቸኛው የጽድቅ ወንጌል ነው፡፡
 
 
የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ቀንዶች፡፡ 
 
የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ዕቃዎች
በመገናኛው ድንኳን አደባባይ በተቀመጠው የሚቃጠል መስዋዕት መሰውያ በአራቱ ማዕዘኖች ላይ ከናስ የተሰሩ ቀንዶች ተደርገውበት ነበር፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እነዚህ ቀንዶች የሚያሳዩት የሐጢያትን ፍርድ ነው፡፡ (ኤርምያስ 17፡1፤ ዮሐንስ ራዕይ 20፡11-15) ይህም የመስቀሉ ወንጌል ኢየሱስ በተቀበለው ጥምቀት ላይ እንደተመሰረተ ያሳየናል፡፡ ስለዚህ ሐዋርያው ጳውሎስ እንዲህ አለ፡- ‹‹በወንጌል አላፍርምና፤ አስቀድሞ ለአይሁዳዊ ደግሞም ለግሪክ ሰው ለሚያምኑ ሁሉ የእግዚአብሄር ሐይል ለማዳን ነውና፡፡›› (ሮሜ 1፡16) በ1ኛ ቆሮንቶስ 1፡18 ላይም እንዲህ ተጽፎዋል፡- ‹‹የመስቀሉ ቃል ለሚጠፉት ሞኝነት ነውና፤ ለእኛ ለምንድን ግን የእግዚአብሄር ሐይል ነው፡፡››
 
እነዚያ የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ቀንዶች የእግዚአብሄር የጽድቅ ፍርድና ደህንነት በጥምቀቱ፣ በመስቀል ላይ ሞቱና በትንሳኤው ሙሉ በሙሉ እንደተፈጸሙ ይናገራሉ፡፡
 
 
በሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ቀለበቶች ውስጥ የሚገቡት ሁለቱ መሎጊያዎች፡፡ 
 
በምድረ በዳ በተገነባው የመገናኛው ድንኳን ውስጥ ያሉት ዕቃዎች በሙሉ ተንቀሳቃሽ ነበሩ፡፡ ይህም ከቦታ ቦታ ለሚንቀሳቀሰው የእስራኤል ሕዝብ ሕይወት ባህርይ ተስማሚ ዘዴ ነበር፡፡ በከንዓን ምድር እስኪሰፍሩ ድረስ በምድረ በዳ መቅበዝበዝ ነበረባቸው፡፡ በምድረ በዳ ውስጥ ሲጓዙ የእንግድነት ሕይወታቸወን በመቀጠላቸው የእስራኤል ሕዝብ ወደፊት እንዲጓዙ በእግዚአብሄር በታዘዙ ጊዜ ካህናቱ መሰውያውን መሸከም ይችሉ ዘንድ እግዚአብሄር ከሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ጋር የሚቆራኙ ሁለት መሎጊያዎች እንዲዘጋጁ አደረገ፡፡
 
ዘጸዓት 27፡6-7 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ለመሠዊያውም ከግራር እንጨት መሎጊያዎችን ሰርተህ በናስ ለብጣቸው፡፡ መሎጊያዎቹም በቀለበት ውስጥ ይግቡ፡፡ መሠዊያውንም ስትሸከሙ መሎጊያዎቹ በሁለቱ ወገኖች ይሁኑ፡፡›› በሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ በሁለቱ ወገኖች ሁለት መሎጊያዎች በአራቱ የመሰውያው የናስ ቀለበቶች ውስጥ ስለሚገቡ የእስራኤል ሕዝብ በሚጓዙበት ጊዜ ሌዋውያን በትከሻዎቻቸው መሸከምና መጓዝ ይችሉ ነበር፡፡ የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ የኢየሱስን ጥምቀትና መስቀል ያሳያል፡፡ ስለዚህ ሌዋውያን የሚቃጠለውን መስዋዕት መሰውያ በሁለቱ መሎጊያዎች አንስተው በምድረ በዳ እንደሚሸከሙት ሁሉ የእርሱ ጥምቀትና መስቀል ወንጌልም እንደዚሁ በአገልጋዮቹ አማካይነት በዚህ ዓለም ምድረ በዳ ሁሉ ተሰራጭቷል፡፡
 
ከመቀጠላችን በፊት ልንመረምረው የሚገባን ሌላው ጉዳይ እስራኤሎች የሚቃጠለውን መስዋዕት መሰውያ ለማንቀሳቀስ የሚያስችሉዋቸው ሁለቱ መሎጊያዎች የመሆናቸው እውነታ ነው፡፡ ልክ እንደዚሁ የውሃውና የመንፈሱም ወንጌል በሁለት ክፍሎች የተዋቀረ ነው፡፡ አንዱ ክርስቶስ ከዮሐንስ የተቀበለው ጥምቀት ሲሆን ሌላው ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ የተሸከመው ቅጣት ነው፡፡ እነዚህ ሁለቱ ሲቀናጁ የሐጢያት ስርየት ደህንነት ይፈጸማል፡፡ የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ሁለት መሎጊያዎች ነበሩት፡፡ በሌላ መንገድ ሲቀመጥ መያዣዎች ነበሩት፡፡ አንድ መሎጊያ በቂ አልነበረም፡፡ መሰውያው በሚንቀሳቀስበት ጊዜ በአንድ መሎጊያ ብቻ ሚዛኑን መጠበቅ አይቻልም፡፡
 
ልክ እንደዚሁ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል በሁለት ክፍሎች የተዋቀረ ነው፡፡ እነዚህም ኢየሱስ ክርስቶስ ከዮሐንስ የተቀበለው ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ ናቸው፡፡ በሌላ አነጋገር የኢየሱስ ጥምቀትና የመስቀል ላይ ሞቱ በጋራ የጽድቅ እውነትን የሚያዋቅሩ የጋራ ሚዛናዊ ፍሬ ነገሮች ናቸው፡፡ የኢየሱስ ጥምቀትና ደም የሐጢያተኞችን የሐጢያት ስርየት በጽድቅ ፈጽመዋል፡፡ ከእነዚህ ከሁለቱ (የኢየሱስ ጥምቀትና የመስቀል ላይ ሞቱ) አንዱ ችላ ቢባል ሌላውም እንደዚሁ ችላ ይባላል፡፡ ያለ ኢየሱስ ጥምቀትና ያለ ደሙ ደህንነት የለም፡፡
 
ትንሳኤውም ደግሞ አስፈላጊ መሆኑ እርግጥ ነው፡፡ ያለ ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሳኤ ሞቱ ምንም ዓይነት ውጤት የሌለው ከንቱ ይሆን ነበር፡፡ በክርስቶስ ሞት ብቻ የምናምን ከሆንን እንግዲያውስ እርሱ ራሱንም ጨምሮ ማንንም ማዳን ባልቻለም ነበር፡፡ ነገር ግን የተጠመቀው፣ በመስቀል ላይ እስከ ሞት ድረስ የደማውና ዳግመኛ ሕያው ለመሆን ሞትን ያሸነፈው ክርስቶስ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አምነው ወደ እግዚአብሄር ለቀረቡት እውነተኛ አዳኝ ሆኖላቸዋል፡፡ ዘላለማዊ የደህንነት ጌታና ጠባቂም ሆኖላቸዋል፡፡
 
ያለ ትንሳኤው የክርሰቶስን ሞት ብቻ ማሰራጨት ተቃርኖ መፍጠርና ማስመሰል ብቻ ነው፡፡ ያለ ክርስቶስ ትንሳኤ የእርሱ መስቀል ብቻውን በእግዚአብሄር ዘንድ ሽንፈት ነው፡፡ ኢየሱስንም ከቁም ነገር የማይቆጠር ወንጀለኛ ወደ ማድረግ ይመለሳል፡፡ ይህም ብቻ አይደለም፤ ከዚህም በላይ እግዚአብሄርን ውሸታም በማድረግ ውጤቱ በመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ላይ ማላገጥ ይሆናል፡፡ ክርስቶስ በዮሐንስ ተጠምቆ በመስቀል ላይ ሞተ፤ ዳግመኛም ከሙታን ተነሳ፤ በዚህም በእርሱ ለሚያምኑት እውነተኛ አዳኝ ሆነ፡፡
 
ዛሬ ብዙዎቹ ክርስቲያኖች እየተከተሉት ያለውና የኢየሱስን ጥምቀት ከመላው ወንጌል ውስጥ ያገለለው ወንጌል እግዚአብሄርን የካደ፣ ሰዎችን ያሳተና ነፍሳቸውንም ወደ ሲዖል የሚነዳ ወንጌል ነው፡፡ በዚህ ዓይነቱ ወንጌል ማመን የእግዚአብሄርን ዘላለማዊ የእውነት ቃል ችላ ማለትና መናቅ ነው፡፡ የክርስቶስን መስቀል ብቻ የሚያስተምሩ ሐሰተኛ አስተማሪዎች ክርስትናን ከብዙ የዓለም ሐይማኖቶች ወደ አንዱ እየቀየሩት ነው፡፡ እነርሱ እየተከተሉት ያለው ወንጌል ከእውነተኛው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ፈጽሞ የተለየ የሆነው ለዚህ ነው፡፡
 
በእግዚአብሄርና በሕያው ክርስቶስ የሚያምነው ብቸኛው ሐይማኖት ክርስትና ነው፡፡ ነገር ግን ክርስትና ከሌሎች የዓለም ሐይማኖቶች ሁሉ የሚበልጥ መስሎ ቢታይና ራሱንም ተጨባጭ እውነት አድርጎ ቢያውጅም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ማመን ትቶ በአንድ አምላክ የማመንን አመኔታ ብቻ የሚያብራራ ከሆነ የፍቅርና የእውነት እምነት ከመሆን ይልቅ የዕብሪት ሐይማኖት ሆኖ ብቻ ይቀራል፡፡
 
 
የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ የሚገኝበት ስፍራ፡፡ 
 
እዚህ ላይ የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ በመገናኛው ድንኳን አደባባይ ውስጥ የት ቦታ እንደተቀመጠ እንደገና እንመልከት፡፡ ከመገናኛው ድንኳን ዕቃዎች ሁሉ እጅግ ትልቁ የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ነበር፡፡ ካህናቶች ለስግደት ወደ ቅድስቱ ስፍራ መግባት በሚፈልጉበት ጊዜ በየተራ ከሚቀርቡባቸው የመገናኛው ድንኳን ዕቃዎች የመጀመሪያው ይህ የሚቃጠል መስዋዕት መሰውያ ነበር፡፡ የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ በእግዚአብሄር የማመን የመጀመሪያው ስፍራ ነው፡፡ ይህ መሰውያ ሰዎች እግዚአብሄርን ለመቅረብ የእርሱን ቀመር እንዲከተሉ ይጠይቃቸዋል፡፡ በሌላ አነጋገር የሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ሰዎች አላማኒዎች ከመሆን ይልቅ አማኞች በመሆን የሐጢያት ችግሮቻቸውን በሙሉ ማቃለል ያለባቸው የመሆኑን እውነት ይገልጣል፡፡ ኢየሱስ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀትና በመስቀሉ አለማመን ማንም በሕያው እግዚአብሄር ፊት እንዳይቀርብ ያግዳል፡፡
 
ከሐጢያቶቻችን የዳንነው በአለማመን ሳይሆን በእግዚአብሄር ልጅ ጥምቀትና ሞት በማመን ነው፡፡ ከሐጢያቶቻችን ድነን አዲስ ሕይወትን የተቀበልነው በእግዚአብሄር ልጅ ጥምቀትና ባፈሰሰው ደሙ በማመን ብቻ ነው፡፡ ይህ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል በጣም ጠቃሚ፣ መሰረታዊና እጅግ ፍጹም በመሆኑ በልባችን ውስጥ ደጋግመን ልናሰላስለው ይገባናል፡፡ ሁላችንም ለሲዖል የታጨን እንደነበርንም በልባችን ማመን አለብን፡፡ ከዚህ እምነት ጋር አብሮም ጌታ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰስ የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ መሸከሙንም ማመን አለብን፡፡
 
ከዚህ ከሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ጋር አብሮ የመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ምሰሶዎች ኩላቦችም ከናስ መሰራታቸው ከእንከኖቻችን የተነሳ ሁላችንም ወደ ሲዖል መጣል የሚገባን የነበርን የመሆናችንን እውነታ መቀበል እንደሚገባን ይነግረናል፡፡ ‹‹የሐጢአት ደመወዝ ሞት›› መሆኑን በሚያውጀው የእግዚአብሄር ፍርድ መሰረት በሐጢያቶቻችን ምክንያት ሁላችንም ለሲዖል የታጨን እንደሆንን ግልጽ ነው፡፡
 
ነገር ግን በእርግጥም ወደ ሲዖል መሄድ የሚገባንን እንደ እኛ ያሉትን ሰብዓዊ ፍጡራን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ፍርድ ለማዳን ጌታችን ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር በመምጣት፣ በመጠመቅ፣ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በገዛ ሥጋው በመውሰድ፣ የዓለምን ሐጢያቶች በመስቀል ላይ ተሸክሞ ደሙን በማፍሰስ ከተኮነነ በኋላ እናንተንና እኔን ፈጽሞ ከሐጢያቶቻችንና ከኩነኔ አዳነን፡፡ ከእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ጋር በመቀላቀል የእርሱ ሕዝብ መሆን የሚችሉት በዚህ እውነት የሚያምኑት ብቻ ናቸው፡፡ የመገናኛው ድንኳን መጋረጃና የመግቢያው በር ምሰሶዎች የእግዚአብሄር ሕዝብ ሊሆኑና ወደ እግዚአብሄር መንግሥት ሊገቡ የሚችሉት ይህ እምነት ያላቸው ብቻ እንደሆኑ ያሳዩናል፡፡
 
 
በመገናኛው ድንኳን በር መጋረጃ አራት ቀለማቶች ውስጥ በተገለጠው እውነት ማመን አለብን፡፡ 
 
የአደባባዩ ደጅ
ጌታ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ አገልግሎቶቹ አማካይነት ወደዚህ ምድር በመምጣት እንዳዳነን ታምናላችሁን? ሐምራዊው ማግ ኢየሱስ ራሱ አምላክ መሆኑን ያሳያል፡፡ ሰማያዊው ማግ ራሱ አምላክ የሆነው ኢየሱስ ሰው ሆኖ በዚህ ምድር ላይ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችንን እንደወሰደ ያሳያል፡፡ ቀዩ ማግ በዚህ ሁኔታ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ የወሰደው ኢየሱስ ክርስቶስ በመሰቀል ክቡር ሥጋውን መስዋዕት እንዳደረገ ያሳየናል፡፡ የተጠመቀውና የተሰቀለው ኢየሱስ ዳግመኛ ከሙታን ተነስቶ እናንተንና እኔን ፈጽሞ እንዳዳነን ማመን በጣም አስፈላጊ ነው፡፡
 
የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ሰራተኞች መሆን የሚችሉት በዚህ እውነት ከልባቸው የሚያምኑ ብቻ ናቸው፡፡ የመገናኛው ድንኳን መግቢያ በር ምሰሶዎች ሰራተኞችን ያመለክታሉ፡፡ የእግዚአብሄር ሕዝብ የሚሆኑት በዚህ መንገድ የሚያምኑና እግዚአብሄርም የራሱ ሰራተኞችና ምሰሶዎች አድርጎ ሊጠቀምባቸው የሚችልባቸውም እነዚህ ብቻ እንደሆኑ ያሳዩናል፡፡
 
ነጩ ጥሩ በፍታ የእግዚአብሄር ሕዝብ የሆኑት ጻድቃን በልባቸው ውስጥ ጨርሶ ሐጢያት የሌለባቸው ሰዎች እንደሆኑ ይነግረናል፡፡ ጻድቃን በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በማመን የሐጢያቶቻቸውን ስርየት የተቀበሉት ናቸው፡፡ ጌታችን ወደዚህ ምድር መጥቶ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀትና በመስቀሉ ደም አማካይነት ሐጢያተኞችን በሙሉ አዳነ፡፡ ጌታ የራሱን ክቡር ሕይወት በመስጠት ስላዳነን በውሃውና በደሙ በመጣው በእርሱ ማመን አለብን፡፡ (1ኛ ዮሐንስ 5፡6)
 
ሐምራዊው ማግ ኢየሱስ የነገሥታት ንጉሥ የመሆኑን እውነት ይጠቁማል፡፡ በሌላ አነጋገር ጌታ ክቡር ሕይወቱን በመስጠት ከንቱና በእንከኖች የተሞላነውን እኛን በማዳን የእግዚአብሄር ሕዝብ እንዳደረገን ማመን አለብን፡፡ ይህንን እውነት ብቻ በልባችን ብናምነው ፍጹም በሆነው ደህንነት ላይ ባለን እምነታችን ሁላችንም ሐጢያት አልባ ጻድቃን እንሆናለን፡፡ የዚህ ዓይነቱ እምነት ይኖረን ዘንድ የእምነት ስጦታ ስለሰጠን እግዚአብሄርን ማመስገን ይገባናል፡፡
 
በዚህ እውነት ማመናችን ራሱም ቢሆን የእግዚአብሄር ስጦታ ነው፡፡ ከሐጢያት መዳናችንም እንደዚሁ የእግዚአብሄር ስጦታ ነው፡፡ እግዚአብሄር ከእኛ እጅግ የላቀውን ክቡር ሕይወቱን በመስጠት ከሐጢያቶቻችን አላዳነንምን? ኢየሱስ በመጠመቁ፣ በመስቀል ላይ በመሞቱ፣ ከሙታን በመነሳቱና በዚህም የደህንነትን ስጦታ ለእኛ በመስጠቱ አሁን በዚህ ወንጌል የሚያምኑ ሁሉ ይህንን የደህንነት ስጦታ መቀበልና የራሱ የእግዚአብሄር ሕዝብ መሆን ይችላሉ፡፡ ደህንነትን በሚመለከት ፈጽሞ የእኛ ሥራ አያስፈልግም፡፡ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በመጣው በኢየሱስ ክርስቶስ ከማመን በስተቀር እኛ የምናደርገው ምንም ነገር የለም፡፡ ይህ ደህንነት እግዚአብሄር ለእኛ የሰጠን ስጦታ ነው፡፡
 
በኢየሱስ ማመን የሚጀምረው መጀመሪያ ‹‹በእርግጥ ለሲዖል የታጨን መሆን አለመሆናችንን›› በሚመለከት በማሰብ ነው፡፡ ለምን? ምክንያቱም በመጀመሪያ ሐጢያተኛ የሆነውን እውነተኛ ማንነታችንን ስናውቅና ስናምን ኢየሱስ ለሐጢያቶቻችን የበደል መስዋዕት እንደሆነልን እውነቱን ከማመን ማምለጥ አንችልም፡፡ ሐጢያት እየሰራንም ቢሆን መዳን እንችላለን፡፡ እኛ ማድረግ የምንችለው ሁሉ ተግባራዊ የሆነው ራሱን በእኛ ፋንታ መስዋዕት ባደረገው ጌታ በሰጠው የደህንነት ስጦታ ነው፡፡ የዳንነው እንዲያው በእርሱ በማመን ብቻ ነውን? የእግዚአብሄር ሕዝብ የሆንነውም በእምነት ነውን? በእርግጥ የዚህ ዓይነት እምነት አለን? ደህንነታችን የሥራዎቻችን ውጤት ሳይሆን የእግዚአብሄር ስጦታ መሆኑን መናገር እንችላለንን? በእግዚአብሄር በተሰጠው የደህንነት ስጦታ ከማመናችን በፊት ሁላችንም ለሲዖል የታጨን እንደነበርን በተጨባጭ አምነናልን? እነዚህን ጉዳዮች እንደገና ልንመረምራቸው ይገባናል፡፡
 
 

የመገናኛው ድንኳን ኢየሱስን በዝርዝር የሚገልጥ ስዕላዊ መግለጫ ነው፡፡ 

 
በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የተገለጠው እውነት የሐሰተኛ ነቢያቶችን አፍ ይዘጋል፡፡ የመገናኛውን ድንኳን ቃል ከፍተን በእነርሱ ፊት ስለ እርሱ ስንናገር ማታለያቸው በሙሉ ይገለጣል፡፡
 
የመገናኛው ደንኳን የመግቢያ በር ምሰሶዎች በሙሉ በወርቅ የተለበጡ ነበሩ፡፡ ይህም በመገናኛው ድንኳን ውስጥ በየትም ቦታ አንዳች የሰው ነገር እንደሌለበት ያሳያል፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ያለው እያንዳንዱ ነገር በወርቅ የተለበጠ ነበር፡፡ የመግቢያው በር ምሰሶዎችም በወርቅ የተለበጡ ነበሩ፡፡ ከምሰሶዎቹ በላይ ያለው መሸፈኛም እንደዚሁ በወርቅ የተለበጠ ነበር፡፡ የምሰሶዎቹ ኩላቦች ግን ከናስ የተሰሩ ነበሩ፡፡ ይህም በሐጢያቶቻችንና በእንከኖቻችን ምክንያት እናንተና እኔ ሁላችንም ለሲዖል የታጨን እንደነበርን ያሳያል፡፡ ይህ እውነት አይደለምን? በተጨባጭ ነገሩ እንዲህ አይደለምን? እናንተም በየቀኑ ከምትሰሩዋቸው አስጸያፊ ሐጢያቶቻችሁ የተነሳ ለሲዖል የታጫችሁ እንደነበራችሁ በእርግጥ ታምናላችሁን? እናንተ ለሲዖል የታጫችሁ መሆናችሁ እግዚአብሄር የፈረደው የጽድቅ ፍርድ ነው፡፡ ታዲያ ይህንን ፍርድ ትቀበላላችሁን? መቀበል አለባችሁ! ይህ ተራ ዕውቀት አይደለም፡፡ ነገር ግን በዚህ በማመን ልትቀበሉት ይገባችኋል፡፡
 
መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሰው በልቡ አምኖ ይጸድቃልና በአፉም መስክሮ ይድናልና፡፡›› (ሮሜ 10፡10) ለሲዖል የታጨን እንደነበርን በልባችን ስናውቅና ጌታ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጡት ሥራዎቹ የተፈጸመውን የደህንነት ስጦታ በመስጠት ያዳነን የመሆኑን እውነት ስናምን ያን ጊዜ ሁላችንም ወደ ቅድስቱ ስፍራ ገብተን መኖር እንችላለን፡፡ ጌታ ወደዚህ ምድር እንድመጣ፣ ከእኛም እጅግ የሚከብረው እርሱ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወስዶ ደሙን በማፍሰስ በመስቀል ላይ እንደሞተ፣ እንዲህ በማድረጉም ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንዳስወገደና ከኩነኔያችን ሁሉ እንዳዳነን እናምናለን፡፡ ጌታ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ አማካይነት እኛን በማዳን ጻድቃን አድርጎናል፡፡
 
ይህንን ከሙሉ ልባችን በተጨባጭ ማመን አለብን፡፡ የእግዚአብሄር ሕዝብና የእርሱ ሰራተኞች መሆን የሚችሉት በዚህ እውነት ከሙሉ ልባቸው የሚያምኑ ብቻ ናቸው፡፡ ይህንን እውነት የሰው ፈጠራ አስተሳሰቦች ብቻ አድርጎ መቀበል እውነተኛ እምነት አይደለም፡፡ ‹‹ኦ ለካስ የመገናኛው ድንኳን እንደዚህ ያለ ትርጉም ነበረው፡፡ ስለ ሰማያዊው፣ ሐምራዊውና ቀዩ ማግ በቤተክርስቲያኔ ውስጥ ብዙ ጊዜ ሰምቻለሁ፡፡ ለካስ ትርጉማቸው ልክ እንደዚህ ሊተረጎም ይችላል!›› እስካሁን ድረስ እውነቱን ያመናችሁት በአእምሮዋችሁ ብቻ ከሆነ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በልባችሁ ውስጥ በተገቢው መንገድ ልታምኑ የሚገባበት ጊዜ አሁን ነው፡፡
 
የመገናኛው ድንኳን በር ምሰሶዎች ኩላቦች ከናስ የተሰሩ ነበሩ፡፡ ነገር ግን የናስ ኩላቦች ጥቅም ላይ የዋሉት ለመገናኛው ድንኳን አምስቱ ምሰሶዎች ብቻ ነበር፡፡ በተቃራኒው ለቅድስቱ ስፍራ መጋረጃ የሆኑት ምሰሶዎች አራቱ ኩላቦች ሁሉም ከብር የተሰሩ ነበሩ፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ብር የሚያመለክተው የእግዚአብሄርን ስጦታና ጸጋ ሲሆን ወርቅ የሚያመለክተው ደግሞ ከሙሉ ልብ የሚያምነውን እምነት ነው፡፡ በሌላ በኩል ናስ የሚያመለክተው የሐጢያትን ፍርድ ነው፡፡ እኛ ሁላችን ስለ ሐጢያቶቻችን በእግዚአብሄር ፍርድ ስር ለመሆን የታጨን አልነበርንምን? እያንዳንዳችሁ በእግዚአብሄርና በሰዎች ፊት ለሐጢያቶቻችሁና ለእንከኖቻችሁ መኮነን ነበረባችሁ፡፡ ነገሩ እንደዚህ አይደለምን? እናንተ እንደዚህ ነበራችሁ ማለቴ አይደለም፡፡ በፈንታው አኔ ራሴ እንደዚህ እንደነበርሁ በእግዚአብሄር ፊት ማመኔ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ይህንን የምጠይቀው እናንተን ብቻ ሳይሆን እኔንም ጭምር ነው፡፡ እኔን በሚመለከት ስለ ሐጢያቶቼ በእርሱ ፍርድ ስር ለመሆን የታጨሁ እንደነበርሁ በእግዚአብሄር ፊት በሚገባ አውቃለሁ፡፡ በሕጉ መሰረትም በሐጢያቶቼ ምክንያት ለሲዖል የታጨሁ ነበርሁ፡፡ ይህንን በግልጽ እቀበላለሁ፡፡
 
ጌታ እንደ እኔ ላለው ፍጡር ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ ሰው ሆኖ በሥጋ መጣ፡፡ በጥምቀቱም ሐጢያቶቼን በሙሉ በሥጋው ወሰደ፡፡ በመስቀል ላይ በመሞትም የሐጢያቶቼን ኩነኔ በሙሉ ተሸከመ፡፡ ዳግመኛም ከሙታን በመነሳት ፍጹም የሆነ አዳኜ ሆነ፡፡ የማምነው ይህንን ነው፡፡ ይህንን በማመኔ እግዚአብሄር ከፍጥረት በፊት ያቀደው ደህንነቴ በሙሉ ተፈጽሞዋል፡፡ ይህንን ከሙሉ ልቤ በማመኔ ተፈጽሞዋል፡፡
 
የእናንተም ልብ ደግሞ እንደዚህ ነው፡፡ በዚህ እውነት በማመን እግዚአብሄር ከዚህ ዓለም ፍጥረት በፊት በኢየሱስ ክርስቶስ ያቀደው ደህንነታችሁ በልባችሁ ውስጥ ይፈጸማል፡፡ በዚህ ዕቅድ ከሙሉ ልባችሁ ስታምኑ እግዚአብሄር እናንተን የራሱ ሕዝብ ለማድረግ ያቀደው እቅድ ይፈጸማል፡፡ እውነተኛው ደህንነት ወደ ልባችሁ ጥልቅ የሚገባው ከልባችሁ በማመን ነው፡፡ ደህንነት በሥጋ አስተሳሰቦቻችን አይደረስበትም፡፡ ደህንነት በነገረ መለኮት ትምህርቶችም አይገኝም፡፡ ደህንነት የሚመጣው በዚህ እውነት በማመን ብቻ ነው፡፡
 
 

ይህ ደህንነት ከፍጥረት በፊት በኢየሱስ ክርስቶስ የታቀደ ነበር፡፡ 

 
ደህንነት በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ደሙ አማካይነት በኢየሱስ ክርስቶስ የተሰጠን ስጦታ ነው፡፡ ይህ ደህንነት ከ2,000 ዓመታት በፊት በዚህ ምድር ላይ በተጨባጭ ተፈጽሞዋል፡፡ ከዚህ ደህንነት ስጦታ የተገለለ ማንም የለም፡፡ ምክንያቱም የእያንዳንዱን ሰው ሐጢያቶች ለመደምሰስ የእግዚአብሄርን የደህንነት ዕቅድ ፈጽሞዋልና፡፡ ስለዚህ በዚህ ደህንነት ከሙሉ ልባቸው ያመኑ ሁሉ የእግዚአብሄር ልጆች ሆነዋል፡፡ ሐጢያቶቻቸው በሙሉ ተደምስሰው እንደ በረዶ ነጭ ሆነዋል፡፡ ሁሉም የሐጢያቶቻቸውን ስርየት በነጻ ተቀብለዋል፡፡
 
ነገር ግን የሐጢያት ስርየትን ያልተቀበሉ ብዙ ሰዎች በዚህ ዓለም ላይ አሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች እነማናቸው? እነዚህ ሰዎች እውነቱን እያወቁትም ቢሆን የማያምኑት ናቸው፡፡ ለሐጢያት የታጩ እንደነበሩ ከልባቸው የማያምኑና የውሃውን፣ የደሙንና የመንፈሱን ወንጌል ያልተረዱ ሰዎች ከእግዚአብሄር ጋር ዕድል የላቸውም፡፡
 
የእግዚአብሄር ደህንነት የሚሰጠው ሐጢያተኛ ተፈጥሮዋቸውን ለሚያውቁና በሐጢያቶቻቸው ምክንያት ለኩነኔ የታጩና ወደ ሲዖል የሚጣሉ መሆናቸውን ለሚገነዘቡ ብቻ ነው፡፡ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ የተሰራው መጋረጃ ያለባቸው የበሩ አምስት ምሰሶዎች የሚተከሉት የት ላይ ነበር? በናሱ ኩላቦች ላይ ነበር፡፡ እናንተና እኔ በሐጢያቶቻችን ምክንያት ለሲዖል የታጨን ነበርን፡፡ እምነታችን በዚህ ግንዛቤ ላይ ሊተከል የሚችለው ይህንን እውነት ስንቀበል ብቻ ነው፡፡ ‹‹እግዚአብሄር ዓለሙን ሁሉ እንዲሁ ወዶአልና፡፡›› ጌታ ለእኔና ለእናንተ ሲል ወደዚህ ምድር መጥቶ በአጥማቂው ዮሐንስ ተጠመቀ፡፡ በመስቀል ላይ ደሙን አፍስሶ ተሰዋ፡፡ በዚህም ከሐጢያቶቻችን አዳነን፡፡
 
ስለዚህ እናንተና እኔ ከሙሉ ልባችን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በተጨባጭ ማመን አለብን፡፡ ቢያንስ ልባችን አንድ ጊዜ ‹‹በእርግጥም ለሲዖል የታጨሁ ነበርሁ፡፡ ነገር ግን ጌታ በውሃውና በመንፈሱ አማካይነት አዳነኝ›› ብሎ መረዳት አለበት፡፡ ስለዚህ ለመዳን ከልባችን ማመን አለብን፡፡ ሮሜ 10፡10 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሰው በልቡ አምኖ ይጸድቃልና በአፉም መስክሮ ይድናልና፡፡››
 
በደህንነታችን ከሙሉ ልባችን በተጨባጭ ማመንና ይህንን በአፋችን መመስከር ይገባናል፡፡ ‹‹ጌታ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ አማካይነት አዳነኝ፡፡ እኔ ወደ ሲዖል ተጥዬ የምኮነን ነበርሁ፡፡ ጌታ ግን በእኔ ፋንታ ሆኖ ሐጢያቶቼን አስወገደ፡፡ ሐጢያቶቼን ወሰደ፡፡ በእኔ ፋንታም ኩነኔዎችን ሁሉ ተሸከመ፡፡ በዚህም ሙሉ በሙሉ አዳነኝ፡፡ ፍጹም የእግዚአብሄር ልጅም አደረገኝ፡፡›› በዚህ መንገድ ከሙሉ ልባችን ማመንና በአፋችንም መመስከር አለብን፡፡ ታምናላችሁን?
 
በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ እውነት ብታምኑም ጌታ በዚህ መንገድ እንዳዳነን ብታምኑም ለሲዖል ታጭታችሁ የነበረ የመሆኑን እውነት አሁንም አልተቀበላችሁምን? መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሁሉ ሐጢአትን ሰርተዋልና፤ የእግዚአብሄርም ክብር ጎድሎአቸዋልና፡፡›› (ሮሜ 3፡23) እውነተኛው እምነት ሁሉም ሐጢያት ስለሰሩ ሁሉም ወደ ሲዖል መሄድ የነበረባቸው ቢሆኑም ጌታ ወደዚህ ምድር መጥቶ በመጠመቅ፣ በመስቀል ላይ በመሞት፣ ዳግመኛም ከሙታን በመነሳትና እኛን ፈጽሞ ጻድቃን እንዳደረገን የሚያምን እምነት ነው፡፡
 
ይህ ደህንነት ምንኛ አስገራሚ ነው? እንዲያው በአጭሩ ድንቅ አይደለምን? የመገናኛው ድንኳን በዘፈቀደ የተሰራ አልነበረም፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ቃል መሰረት በተብራራ ዝርዝር የተሰራ ነበር፡፡ እግዚአብሄር በመገናኛው ድንኳን አማካይነት ክቡር ሕይወቱን በመስጠት እንደሚያድነን አስቀድሞ በዝርዝር ነገረን፡፡ በመገናኛው ድንኳን አማካይነት ኢየሱስ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ሞቱ የከበረ ደህንነት እንደሰጠን ነገረን፡፡ እኛ ማድረግ የሚገባን ከሙሉ ልባችን በዚህ ማመን ነው፡፡ ለእናንተ ሲል ደህንነትን ማን ሊሰጣችሁ ይችላል? ልክ እንደ እናንተ የሰው ሥጋ ለብሶ በመጣው በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን መዳን ትችላላችሁ፡፡
 
አንድ ሰው ሐጢያቶቻችሁን ወስዶ በእናንተ ምትክ በይፋ ቢኮነን አመስጋኝ ለመሆን ከበቂ በላይ የሆነ ምክንያት ይኖራችኋል፡፡ ነገር ግን እኛ ይልቅ ሚሊዮን ጊዜ እጅግ ክቡርና እጅግ ባለጠጋ የሆነው ጌታ ኢየሱስ ስለ እኛ ሲል ክቡር የሆነ መስዋዕትነት ከፈለ፡፡ ይህ ምንኛ የሚያረካ ነው? ከፍ ያለው ጌታ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ የሰጠን ደህንነት ምንኛ በዋጋ የማይተመን ነው? ይህንን በልባችን ማመን ያልቻልነው እንዴት ነው?
 
ሐጢያተኝነታቸውን የተቀበሉ በዚህ እውነት ማመን ያለባቸው ለዚህ ነው፡፡ በዚህ እውነት ለማመን ብቁ የሆኑት ወደ ሲዖል ከመወርወር ማምለጥ የማይችሉ መሆናቸውን የተቀበሉ ናቸው፡፡ በእግዚአብሄር ክቡር ደህንነት ለማመን ብቁ የሆኑትና ይህንንም ደህንነት በእምነት የሚቀበሉት በእርግጥ ሐጢያተኞችና በእርግጠኝነትም ለሲዖል የታጩ መሆናቸውን የሚገነዘቡ ብቻ ናቸው፡፡ እውነቱን በልባቸው የሚያምኑትም የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ሰራተኞች መሆን ይችላሉ፡፡
 
እኛ በዚህ ዓለም ላይ ባላቸው ተራ ችሎታዎች እንኳን ዝነኛ ከሆኑት ጋር ራሳችንን ስናነጻጽር የምንኮራበት አንዳች ነገር የሌለን ምስኪን ፍጡራን ነን፡፡ ነገሩ እንደዚህ ሆኖ ሳለ ቅዱስ፣ ፍጹምና ሁሉን ቻይ በሆነው አምላክ ፊት እንዴት ለመኩራራት እንደፍራለን? በእርሱ ፊት ማድረግ የምንችለው በርኩሰቶቻችንን ምክንያት ከመሞት ማምለጥ የማንችለውን እኛን ጌታ እንዳዳነን መቀበል ብቻ ነው፡፡
 
መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይነግረናል፡- ‹‹የሐጢአት ደመወዝ ሞት ነውና፤ የእግዚአብሄር የጸጋ ስጦታ ግን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን የዘላለም ሕይወት ነው፡፡›› (ሮሜ 6፡23) በሐጢያቶቻችን ምክንያት የሞትን ደመወዝ መክፈል የነበረብን መሆኑ እርግጥ ነው፡፡ ነገር ግን ለሲዖል ታጨነውን እኛን ጌታ ስላዳነን አሁን በዚህ እምነት ሰማይ መግባት እንችላለን፡፡ ይህንን እምነት ካስወገድነው ሁላችንም ለመቶኛ ጊዜ ለሲዖል እንታጫለን፡፡ ነገሩ ይህ አይደለምን? በእርግጥም ነው፡፡ ሁላችንም ወደ ሲዖል መወርወር ይገባን ነበር፡፡
 
ነገር ግን ከፍ ያለው ጌታ ሊለካ በማይችለው ፍቅሩ ወደዚህ ምድር መጥቶ ስለተጠመቀ፣ ደሙን ስላፈሰሰና በመስቀል ላይ ስለተኮነነ አሁን በእርግጠኝነት መድረሻችን ከሆነው ሲዖል አምልጠናል፡፡ ጌታ ስለ እኛ ሲል ክቡር ሕይወቱን አሳልፎ በመስጠቱ የሐጢያት ስርየትን ተቀብለናል፡፡ ነገሩ ይህ ሆኖ ሳለ ጌታ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖን የደህንነትን ስጦታ እንደሰጠን እንዴት ማመን አንችልም? ጻድቃን ለመሆን እንዴት እምቢተኞች እንሆናለን? የመገናኛው ድንኳን የመጋረጃ በር ምሰሶዎች በወርቅ እንደተለበጡ ሁሉ እኛም እንደዚሁ ልባችንን ሙሉ በሙሉ በእምነት መለበጥ ይገባናል፡፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ከሙሉ ልባችን ካላመንን በእግዚአብሄር ፊት መቅረብ አንችልም፡፡
 
በእርግጥ ለሐጢያት የታጨን ሐጢያተኞች የሆንነው በእምነት ነው፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ጻድቃን የምንሆነውም በእምነት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ሐጢያተኞች የሐጢያቶቻቸውን ስርየት የሚያገኙት በእምነት ጌታ በውሃውና በደሙ አማካይነት እንዳዳነን በማመን ነው፡፡ ‹‹ለሰዎችም አንድ ጊዜ መሞት ከእርሱም በኋላ ፍርድ እንደተመደበባቸው›› (ዕብራውያን 9፡27) የሚለው የጌታችን ቃል የሚፈጸመው እንዲህ ነው፡፡
 
በዚህ ዓለም ላይ አንድ ጊዜ ስንወለድ ቀድሞውኑም ለሐጢያቶቻችን ተኮንነናል፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት የደህንነትን ስጦታ ሰጥቶናል፡፡ ስለዚህ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ከሙሉ ልባችን በማመን የእግዚአብሄር ልጆች መሆን ችለናል፡፡ እግዚአብሄር የማይወሰነውን የደህንነት ፍቅር ለሚያምኑ ሁሉ ሰጥቶዋል፡፡ ነገር ግን በዚህ ወንጌል የማያምኑትን በአለማመን ሐጢያቶቻቸው ይፈርድባቸዋል፤ ይኮንናቸውማል፡፡ (ዮሐንስ 3፡16-18)
 
 
በእነዚህ በሁለቱ የደህንነት እውነታዎች ማመን አለብን፡፡
 
እኛ ስለ ሐጢያቶቻችን ለመኮነንና ለመሞት የታጨን ሐጢያተኞች ነበርን፡፡ እግዚአብሄር ባቀደውና ለእኛ በሰጠን የሰማያዊ፣ የሐምራዊ፣ የቀይ ማግና የጥሩ በፍታ ደህንነት በማመን የሐጢያቶቻችንን ስርየት ተቀብለናል፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ከልባችን ‹‹በእርግጥ ለሲዖል የታጨሁ ነበርሁ›› ብለን መናዘዝ አለብን፡፡ ‹‹ነገር ግን በውሃና በደም ወንጌል አድኖኛል›› ብለንም መመስከር ይገባናል፡፡ በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ ወንጌል ማለትም በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ እውነት ማመን አለብን፡፡ የዳንነው በዚህ እውነት ከሙሉ ልባችን በማመን ነው፡፡ የዳንነው በወንጌል በማመን ነው፡፡
 
እኛ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ድነናል፡፡ ሰዎች የራሱ የእግዚአብሄር ሕዝብ መሆን የሚችሉት ጌታ ለሲዖል የታጩትን ሰብዓዊ ፍጡራን በሙሉ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ አማካይነት እንዳዳናቸው ሲያምኑ ብቻ ነው፡፡ ታምናላችሁን? እውነኛው እምነት በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ የሚያምን እምነት ብቻ ነው፡፡
 
በመገናኛው ድንኳን በር መጋረጃ የተገለጠው መንፈሳዊ ትርጉም ይህ ነው፡፡ ታምናላችሁን? ሰዎች እውነቱን ከልባቸው ሲያምኑ ያን ጊዜ ስለ እውነተኛው እምነት በትክክል መናገር ይችላሉ፡፡ እውነተኛ እምነት ከልብ ሳያምኑ እውነቱን በአፍ መናገር ብቻ አይደለም፡፡ ነገር ግን እውነቱን ከሙሉ ልብ በማመን እምነትን በአንደበት መመስከር ነው፡፡ ሁላችሁም ለዘላለም ባዳናችሁ የሰማያዊው፣ የሐምራዊው፣ የቀዩ ማግና የጥሩው በፍታ ደህንነት ማመን አለባችሁ፡፡
 
ምንም ያህል ጠንክረን ብናገለግለውም እግዚአብሄርን በበቂ ሁኔታ አላመሰገንነውም፡፡ ታዲያ እንዴት ስለ ደህንነታችን ልንረሳ እንችላለን? እግዚአብሄር ለሲዖል ከመታጨት ማምለጥ የማንችለውን እናንተንና እኔን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንዳዳነን እንዴት ልንረሳ እንችላለን? በዚህ ወንጌል ካልሆነ በስተቀር ሌላ የመዳን መንገድ እንደሌለ እንዴት ችላ ማለት እንችላለን? እኛ ሁልጊዜም አመስጋኞች ነን፡፡ እኛ ሁልጊዜም እንደሰታለን፡፡ እኛ እርሱን ሁልጊዜም እናወድሰዋለን፡፡
 
ይህንን እውነት የማያውቁ እግዚአብሄር ሰብዓዊ ፍጡራንን የፈጠረው አሻንጉሊቶች አድርጎ ብቻ ስለሆነ ይጫወትባቸዋል ይላሉ፡፡ እግዚአብሄርን በመቃወምም ‹‹እግዚአብሄር የተሰላቸ መሆን አለበት፡፡ እኛን የእርሱ አሻንጉሊቶች አድርጎ በመፍጠር እየተጫወተብን ነው፡፡ ሐጢያት እንደምንሰራ ያውቃል፡፡ ነገር ግን ሐጢያቶችን ስንሰራ ይመለከተናል፡፡ አሁን ደግሞ ሐጢያተኞችን እንዳዳነ ይናገራል፡፡ በእኛ እየተጫወተ አይደለምን? እኛን ፈጠረን፤ ከዚያም እርሱ በሚወደው በማንኛውም መንገድ ከእኛ ጋር ይጫወታል፡፡ ታዲያ እግዚአብሄር የእርሱ አሻንጉሊቶች አላደረገንምን?›› ይላሉ፡፡ በርካታ ቁጥር ያላቸው ሰዎች እንደዚህ ማሰብ ይወዳሉ፡፡ በእውነት የሚወዳቸው ከሆነ ምስኪን ሐጢያተኞች አድርጎ ከሚፈጥራቸው ይልቅ ፍጹማን የሆኑ ፍጡራን አድርጎ ሊፈጥራቸው እንደሚገባ በመናገር በእግዚአብሄር ላይ ቂም ይይዛሉ፡፡ የእግዚአብሄርን ልብ ሳያውቁ የቀሩና የክስ ጣቶቻቸውን በእርሱ ላይ የሚቀስሩ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡
 
 
እኛ በእግዚአብሄር የተፈጠርን ፍጥረታቶች፡፡ 
 
ሰብዓዊ ፍጡራንም ልክ እንደ ተክሎችና እንደ እንስሶች በእግዚአብሄር የተፈጠሩ ፍጥረታቶች ናቸው፡፡ እግዚአብሄር እኛን ከመፍጠሩ በፊትም ቢሆን በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ የራሱ ሕዝብ ሊያደርገንና የክብሩ ተካፋዮች እንድንሆን ሊፈቅድልን ወስኖዋል፡፡ እግዚአብሄር የፈጠረን ለዚህ ዓላማ ነው፡፡ ሰዎች የተፈጠሩበት ዓላማ ከሌሎች ፍጥረታቶች የተለየ ነው፡፡ ታዲያ እግዚአብሄር ሰዎችን የፈጠረበት ይህ ዓላማ ምንድነው? የእግዚአብሄርን ክብር ለማወደስ ብቻ ከተፈጠሩት ተክሎችና እንስሶች በተቃራኒ ሰዎች የተፈጠሩት በመንግሥቱ ውስጥ በክብርና በግርማ ሞገስ ሁሉ ለዘላለም እንዲኖሩ ነበር፡፡ እግዚአብሄር ሰብዓዊ ፍጡራንን የፈጠረበት ዓላማ ሐጢያተኛውን ማንነታቸውን እንዲያውቁ፣ የፍጥረት ጌታ የሆነውን አዳኛቸውን አውቀው እንዲያምኑበትና ምሉዓን ሆነው ወደፊት ወደ እግዚአብሄር መንግሥት እንዲገቡ ለማስቻል ነው፡፡
 
እግዚአብሄር አሻንጉሊቶች ወይም ሮቦቶች አድርጎ አልፈጠረንም፡፡ ነገር ግን የፈጠረን ፈጣሪን በማወቅ፣ በአዳኙ በማመንና በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል አማካይነትም ዳግመኛ በመወለድ የእርሱ ልጆች እንሆን ዘንድ ነው፡፡ ስለዚህ ይህንን የተፈጠርንበትን ዓላማ በመከተል ክብርን እንቀበላለን፤ ደስም እንሰኛለን፡፡ በዚህ ምድር ላይ ሌሎች ነፍሳቶችን በወንጌል ለማገልገል ራሳችንን መስዋዕት ብናደርግም በእግዚአብሄር መንግሥት ውስጥ እንገለገላለን፡፡ እግዚአብሄር ለሰው ዘር የነበረው መሰረታዊ ዓላማ ምን ነበር ብላችሁ ታስባላችሁ? ሰብዓዊ ፍጡራን በእግዚአብሄር ክብርና ግርማ ለዘላለም እንዲደሰቱ ማስቻል ነበር፡፡ እግዚአብሄር ሰብዓዊ ፍጡራንን የፈጠረበት ዓላማ እነርሱን የራሱ ሕዝብ ለማድረግና የራሱ ግርማና ክብር ተካፋይ እንዲሆኑ ለመፍቀድ ነበር፡፡
 
ለምን ተወለድን? የሕይወት ዓላማስ ምንድነው? ከየት መጣን? የምንሄደውስ ወዴት ነው? እንደ እነዚህ ዓይነት የፍልስፍና ጥያቄዎች እስከ አሁን አልተመለሱም፡፡ ስለዚህ ሰዎች አሁንም ችግሩን ለማቃለል በመሞከር እየተሰቃዩ ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎች የራሳቸውን ዕጣ ፈንታ ሳያውቁ ወደ አስማተኞችና ጠንቋዎች ይሄዳሉ፡፡ እነዚህ ሁሉ ሰብዓዊ ፍጡር እኛን የፈጠረንን አምላክ ባለማወቁና እኛን የፈጠረንን አምላክ ባለማመኑ የመጡ የውድቀት ውጤቶች ናቸው፡፡
 
ነገር ግን እግዚአብሄር የራሱ ልጆች ሊያደርገን ከሌሎች ፍጥረቶች ሁሉ የተለየን አድርጎ ፈጠረን፡፡ ደህንነታችንንም ከፍጥረት በፊት በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ አቅዶ በውሃውና በመንፈሱ አዳነን፡፡ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው የደህንነት ሕግ እኛን በማዳን በእርግጥም ለእኛ ያለውን ዓላማውን ፈጽሞዋል፡፡
 
ስለዚህ እግዚአብሄር በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል የዘላለም ሕይወትን ሊሰጠን ባቀደው በዚህ ዓላማ ማመንና ይህንንም ዓላማ ማወቅ አለብን፡፡ ይህንን ካላወቅን የሕይወት ዓላማ ለዘላለም እንቆቅልሽ ሆኖ ይቀራል፡፡ በዚህ ዓለም ላይ ለምን ተወለድን? መኖር ያለብን ለምንድነው? መብላት ያለብን ለምንድነው? ሕይወታችንን በዕድል ፈንታ መኖር ያለብን ለምንድነው? የሕይወትንና የሞትን፣ የዕርጅናንና የበሽታን ችግር ማቃለል የምንችለው እንዴት ነው? ስለ ሐጢያቶቻችን ሲዖል መውረድ ያለብን ለምንድነው? ሕይወት ለምን እንደዚህ በስቃይ የተሞላች ሆነች? እነዚህ ጥያቄዎች በሙሉ በኢየሱስ ክርስቶስ ባዳነን በውሃውና በደሙ ወንጌል አማካይነት ከእግዚአብሄር ዘንድ መልሶች አሉዋቸው፡፡
 
እግዚአብሄር በዚህ ምድር ላይ እንድንወለድ ፈቀደልን፡፡ ለሲዖል የታጨነውን እናንተንና እኔን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ያድነንና እኛም የዘላለምን ሕይወት እናገኝ ዘንድ አድካሚና አስቸጋሪ በሆነው ሕይወታችን ውስጥ መንግሥተ ሰማይን ተስፋ እንድናደርግ አደረገን፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ስናምን የሕይወት ምስጢር በሙሉ ይፈታል፡፡
 
 
እግዚአብሄር ለእናንተና ለእኔ ታላቅና ድንቅ ዕቅድ አለው፡፡ 
 
እግዚአብሄር ባቀደው መሰረት ልጁን ኢየሱስ ክርስቶስን ወደዚህ ምድር ላከው፡፡ እንዲጠመቅ በማድረግም ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ወደ እርሱ ክቡር ሥጋ አሻገረው፡፡ ስለ እኛም እንዲኮነንና እንዲሞት በማድረግ ለሐጢያቶቻችን፣ ለኩነኔያችንና ለእርግማኖቻችን ሁሉ የዘላለም ጥፋትን መጋፈጥ የነበረብንን እኛን አዳነን፡፡ አሁን በዚህ እውነት ማመን አለብን፡፡ ልንሸሸው ከማንችለው የጥፋት ዕጣ ፈንታ ወደ እግዚአብሄር ልጅ መንግሥት ስላፈለሰንና በዘላለም ሕይወት እንድንደሰት ስላስቻለን እግዚአብሄርን ማመስገን ይገባናል፡፡ በሌላ አነጋገር ከእግዚአብሄር ዘንድ የመጣው የደህንነት እውነት በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተሰራውና በመገናኛው ድንኳን በሮች ላይ በተንጠለጠለው መጋረጃ በተገለጠው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ነው፡፡
 
የመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ምሰሶዎች የናስ ኩላቦች መሰረታዊ የሆነውን የሐጢያት ማንነታችንን በማሳየት በውሃውና በኢየሱስ ደም ወንጌል እንድናምን ያስችሉናል፡፡ የመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ምሰሶዎችና ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ የተሰራው መጋረጃ ለሐጢያት ታጭተን የነበርነውን ሁሉ በከበረው የኢየሱስ ክርስቶስ መስዋዕትነት አማካይነት ከኩነኔ ያዳነንን የእግዚአብሄር ምህረት ይገልጣሉ፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እንደዚህ በማመን ከሐጢያቶቼ ሁሉ ድኛለሁ፡፡ እናንተም እንደዚሁ ታምናላችሁን?
 
በመገናኛው ድንኳን ውስጥ በተገለጠው እውነት ታምናላችሁን? እናንተና እኔ ዕድለኞች ነን፡፡ ይህ በእርግጥም ትልቅ በረከት ነው፡፡ ምክንያቱም በቀጥታ ወደ ሲዖል እየሮጡ ያሉ ብዙ ሰዎች ቢኖሩም እኛ እውነቱን አግኝተን አሁን በኢየሱስ ክርስቶስ ሕያው ነን፡፡ እኛ በእርግጥም በዚህ በተወለድንበት ዓለም ላይ ከንቱዎችና የማንረባ ነበርን፡፡ ሐጢያት ከመስራትና ለሲዖል ከመታጨት ማምለጥ የማንችል፣ የፍርሃት ኑሮን የምንኖርና ወደ ሲዖል የምንወረወር ሰዎች ነበርን፡፡ ነገር ግን እንደዚያም ቢሆን ጌታ ወደዚህ ምድር መጥቶ ተጠመቀ፤ በመስቀል ላይ ሞተ፤ ከሙታንም ተነሳ፡፡ በዚህም ለዘላለም ከሐጢያቶቻችን አዳነን፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ ከሲዖል ጋር የሚያገናኘን ምንም ነገር የሌለ ከመሆኑም በላይ የሚረቡ፣ ጠቃሚና የጽድቅ ሥራዎች ለመስራት ችሎታ ያለን በመሆናችን እውነታ ከመደነቅ በቀር ሌላ ማድረግ የምንችለው ነገር የለም፡፡ ወደ ቅድስቱ ስፍራ መግባት የሚችሉት ለአንዴና ለመጨረሻ የሐጢያቶቻቸውን ስርየት ያገኙት ናቸው፡፡ ጌታችን ያለፉትን ሐጢያቶቻችንን እንዲያው በዘፈቀደ አልደመሰሳቸውም፡፡ ነገር ግን በጥምቀቱ የዕድሜ ዘመናችንን ሐጢያቶች በሙሉ ወሰደ፤ በመስቀል ላይ በመሞትም ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ለዘላለም ደመሰሳቸው፡፡ ስለዚህ የካህናት እምነት የሚኖራቸው ለአንዴና ለመጨረሻ የተፈጸመውን ደህንነት የሚያምኑ ብቻ ናቸው፡፡ ወደ ቅድስቱ ስፍራ መግባት የሚችሉትም እነዚህ ሰዎች ብቻ ናቸው፡፡
 
በግልጽ አነጋገር በመገናኛው ድንኳን ስርዓት መሰረት ሊቀ ካህኑ ብቻ እንጂ ተራ ካህናቶች ወደ ቅድስተ ቅዱሳን መግባት አይችሉም፡፡ ዘላለማዊው ሊቀ ካህንም ኢየሱስ ክርስቶስ እንጂ ሌላ ማንም አይደለም፡፡ ወደ እግዚአብሄር ቤት ከኢየሱስ ክርስቶስም ጋር ወደ ቅድስተ ቅዱሳን ውስጥ መግባት የሚችሉት ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ሁኔታ እንዳዳነን የሚያምኑ ብቻ ነው፡፡
 
‹‹የእነዚህም ስርየት ባለበት ዘንድ ከዚህ ወዲህ ስለ ሐጢአት ማቅረብ የለም፡፡ እንግዲህ ወንድሞች ሆይ በመረቀልን በአዲስና በሕያው መንገድ ወደ ቅድስት በኢየሱስ ደም በመጋረጃው ማለት በሥጋው በኩል እንድንገባ ድፍረት ስላለን በእግዚአብሄርም ቤት ላይ የሆነ ታላቅ ካህን ስላለን ከክፉ ሕሊና ለመንጻት ልባችንን ተረጭተን ሰውነታችንንም በጥሩ ውሃ ታጥበን በተረዳንበት በቅን ልብ እንቅረብ፡፡›› (ዕብራውያን 10፡18-22) ራሳቸውን ለሲዖል እንደታጩ ክፉዎች የሚቆጥሩና በንጹህ ውሃና (የኢየሱስ ጥምቀት) በኢየሱስ ደም በመታጠብ ነጽተው የሐጢያቶቻቸውን ሁሉ ስርየት የተቀበሉ ከእርሱ ጋር ለዘላለም ለመኖር ወደ እግዚአብሄር መንግሥት መግባት ይችላል፡፡
 
ሐጢያቶቻችን የነጹት በየቀኑ ለሐጢያቶቻችን ንስሐ ስለምንገባ ሳይሆን ጌታ ወደዚህ ምድር መጥቶ በመጠመቅ የዓለም ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ወስዶ በመስቀል ላይ በመኮነን ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ለዘላለም በመደምሰሱ ነው፡፡ ‹‹እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና፡፡›› ኢየሱስ ተጠመቀ፡፡ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ወሰደ፡፡ የዓለምንም ሐጢያቶች በመስቀል ላይ ተሸክሞ ሞተ፡፡ ዳግመኛም ከሙታን ተነሳ፡፡ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለዘላለም እኛን አዳነን፡፡ ወደ ቅድስቱ ስፍራ መግባት የሚችሉት ይህንን እውነት ከሙሉ ልባቸው የሚያምኑ ብቻ ናቸው፡፡ እኛ ጌታ ለዘላለም እንዳዳነን የዕድሜ ዘመናችንን የመላውን አጽናፈ ዓለማት ሐጢያቶች በሙሉ በመውሰድ እንዳስወገደ በማመን የሐጢያቶቻችንን ስርየት ለአንዴና ለመጨረሻ አግኝተናል፡፡
 
ጌታ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን ለአንዴና ለመጨረሻ እንደወሰደ ታምናላችሁን? የዓለምን ሐጢያቶች መሸከሙን፣ በመስቀል ላይ መሞቱን፣ ከሙታንም ዳግመኛ መነሳቱንና በዚህም ለዘላለም ፍጹም አዳኛችን እንደሆነ ታምናላችሁን? ጌታችን በ33 ዓመታት ዕድሜው የዚህን ዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ለዘላለም ደምስሶዋቸዋል፡፡ አንዲት ነቁጥ እንኳን ሳይተው ሁሉንም አጥፍቶዋቸዋል፡፡ እኔ ይህንን ከሙሉ ልቤ አምነዋለሁ፡፡ እርሱ በተጠመቀ ጊዜ የዓለምን ሐጢያቶች ለአንዴና ለመጨረሻ እንደወሰደ፣ ደሙን በመስቀል ላይ በማፍሰስም የሐጢያቶቼን ኩነኔ በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ እንደተሸከመና ከሙታን ተነስቶ ለዘላለም ሕያው በመሆን ፍጹም አዳኜ መሆኑን አምናለሁ፡፡ ከሐጢያቶቼ ሁሉ የዳንሁት በዚህ እምነት ነው፡፡
 
በዚህ በማመን ሁላችንም መንግሥተ ሰማይ መግባት እንችላለን፡፡ በዚህ ምድር ላይ ስንኖርም ይህንን እምነት በየቀኑ ማሰላሰል ይገባናል፡፡ ለምን? ምክንያቱም ጌታ ገና ወደፊት የምንሰራቸውን ሐጢያቶችም አስወግዶዋልና፡፡ ነገር ግን ሐጢያት በምንሰራበት ጊዜ ሁሉ መናዘዝ አለብን፡፡ ጌታ እነዚያንም ሐጢያቶች ማስወገዱን ከሙሉ ልባችን ማመን አለብን፡፡ ጌታን ዳግመኛ በማመን የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ እንዳስወገደ መረዳት አለብን፡፡ ለምን? የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ደጋግመን ካላሰላሰልነው ልባችን ይረክሳል፡፡ ጌታ ገና ያልሰራናቸውን ሐጢያቶች እንኳን ስለወሰደ ድካሞቻችን በሚገለጡበት ጊዜ ሁሉ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ አገልግሎቶቹ ባለን እምነት ልናመሰግነው ይገባናል፡፡
 
ጌታ ወደዚህ ምድር መጥቶ ሐጢያቶቻችንን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንደወሰደ ሁላችንም ማመን አለብን፡፡ ሐጢያቶቻችን በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ወደ ኢየሱስ ተሻግረዋል፡፡ ምክንያቱም እርሱ በጥምቀቱ አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ተቀብሎዋልና፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ በመሞቱ የዘላለምን ሕይወት ስለሰጠን በዚህ እውነት በጽናትና በድፍረት ማመን አለብን፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱ ባለን ጽኑ እምነት የእግዚአብሄርን መንግሥት መውረስ እንደምንችል ተናግሮዋል፡፡ ኢየሱስ እንዲህ አለ፡- ‹‹ከመጥምቁም ከዮሐንስ ዘመን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ መንግሥተ ሰማያት ትገፋለች፤ ግፈኞችም ይናጠቋታል፡፡›› (ማቴዎስ 11፡12) ከአካላችን፣ ከአስተሳሰባችን፣ ከአእምሮዋችንና ከሥጋችን የሐጢያት እንከኖች ሁሉ የዳንነው በዚህ እምነት ነው፡፡ ጌታችን በጥምቀቱ እነዚህን ሐጢያቶች በሙሉ እንደወሰደና የሐጢያቶችን ኩነኔም በሙሉ እንደተሸከመ በማመን የእግዚአብሄርን መንግሥት ለመውረስ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ መዳን አለብን፡፡
 
ምንም ያህል ብቁዓን ባትሆኑም ይህ እምነት ብቻ ካላችሁ እናንተ የእምነት ሰዎች ናችሁ፡፡ ብቁዓን ባትሆኑም ጌታ ፈጽሞ አድኖዋችኋል፡፡ ስለዚህ በዚህ ማመን አለባችሁ፡፡ ጌታችን ለዘላለም እንደሚኖር የእኛም ደህንነት ለዘላለም ፍጹም ነው፡፡ እኛ ማድረግ የሚኖርብን ኢየሱስ ክርስቶስ በሰጠን ደህንነታችን ማመን ነወ፡፡ ያ ትክክል ነው! በእርሱ ከልባችን በማመን ድነናል፡፡
 
ጌታ ፍጹም የሆነ አዳኛችን በመሆኑ የሐጢያቶቻችንን ችግሮች በሙሉ አቃሎዋል፡፡ ጌታችን እንደተጠመቀ፣ በመስቀል ላይ ደሙን እንዳፈሰሰ፣ ዳግመኛ ከሙታን እንደተነሳና በዚህም የዘላለም ደህንነት እንደሰጠን ታምናላችሁን? ይህ ደህንነት ምንኛ ድንቅ ነው? እኛ በምግባሮቻችን ብቁዓን ባንሆንም በዚህ እውነት በማመን አሁንም ወደ እግዚአብሄር መንግሥት መግባትና በእግዚአብሄር ክብራማ ሞገስና ግርማ በሙሉ መደሰት የምንችለው በእምነት ነው፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ በእነዚህ ነገሮች ለመደሰት ተፈቅዶላቸዋል፡፡ ይህ እምነት ከሌለው ግን ማንም ሰው ወደ እግዚአብሄር መንግሥት ለመግባት እግሮቹን እንኳን ማንሳት አይችልም፡፡
 
በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ አማካይነት ያዳነን እውነት ከፍጥረት በፊት በኢየሱስ ክርስቶስ ውስጥ በእግዚአብሄር የታቀደ ነበር፡፡ እግዚአብሄር እኛን ለማዳን ከወሰነ በኋላ ወደዚህ ዓለም መጥቶ ተጠመቀ፡፡ ሐጢያቶቻችንንም ለአንዴና ለመጨረሻ ወሰደ፡፡ የዓለምንም ሐጢያቶች በመስቀል ላይ ተሸከመ፡፡ ለአንዴና ለመጨረሻም ተኮነነ፡፡ አንድ ጊዜ ሞተ፡፡ ዳግመኛም አንድ ጊዜ ከሙታን ተነሳ፡፡ በዚህም የዘላለም ደህንነት ሰጠኝ፡፡ ይህ ከሰማያዊው፣ ከሐምራዊው፣ ከቀዩ ማግና ከጥሩው በፍታ አገልግሎቶቹ የተሰራ ደህንነታቸውን ነው፡፡ እኛም በዚህ ደህንነት ማመን አለብን፡፡ በእምነት ፈጽመን የእግዚአብሄር ሕዝብ የሆንነው ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡ በእምነት የእግዚአብሄር ሰራተኞች የምንሆነው ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡ ፍጹም ወደሆነው የእግዚአብሄር መንግሥት ገብተንም ለዘላለም እንኖራለን፡፡
 
ፍጹም የሆነው አምላክ ፈጽሞ አድኖናል፡፡ ነገር ግን እኛ አሁንም በየቀኑ ብቁዓን እደለንም፡፡ ምክንያቱም ሥጋችን ብቁ አይደለምና፡፡ ነገር ግን ይህ እንዴት ሆነ? ጌታ ሙሉ በሙሉ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችንን በእርግጠኝነት ወስዶዋል ወይስ አልወሰደም? በእርግጥም ወስዶዋል! ጌታችን በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን ስለወሰደ ሐጢያቶቻችን በሙሉ በእርግጥም ከጥምቀቱ ጋር ወደ እርሱ መሻገራቸውን እናውቃለን፡፡ ሐጢያቶቻችሁ በእርግጥም ወደ ኢየሱስ እንደተሻገሩ ታውቃላችሁን? ኢየሱስ እንዲህ በማድረጉ የእኛን ሐጢያቶችና የዓለምን ሐጢያቶች ተሸክሞ ተሰቀለ፡፡ በዚህም የእግዚአብሄርን የደህንነት ዕቅድ በሚገባ ፈጸመ፡፡ እኛ ብቁዓን ባንሆንም በማመን ወደ እግዚአብሄር መንግሥት መግባት እንችላለን፡፡
 
የሐጢያት ስርየትን ከተቀበልን በኋላ በጎ እምነት መያዝና በቤተክርስቲያን ውስጥ ጥሩ ነገር ማድረግ በቂ አይደለም፡፡ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ብርቱው የሚነግስበት ስፍራ አይደለችም፡፡ ነገር ግን ደካማው በእምነት የሚነግስበት ስፍራ ነች፡፡ ለምን? ምክንያቱም በእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ውስጥ ሆነን ጌታን በእምነት መከተል የምንችለው ደካሞች መሆናችንን ስናውቅ ነው፡፡ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን የእንክብካቤና ቁስሎች የሚፈወሱበት ስፍራ ነች፡፡ ሰማይ ሕጻን ልጅ ‹‹በእፉኝት ቤት ላይ እጁን የሚጭንበትና›› (ኢሳይያስ 11፡8) የማይነደፍበት ስፍራ እንደሆነ ሁሉ በዚህ ምድር ላይ ያለው ገነትም የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን አስገራሚው ምስጢር ይህ ነው፡፡
 
ወደ እግዚአብሄር መንግሥት የምንገባው በእምነት ነው፡፡ የእግዚአብሄርን መንግሥት የሚናጠቀው ጽኑ የሆነ ሐይለኛ እምነት ነው፡፡ በዚህ እውነት ከልባችሁ ታምናላችሁን? እኔ ደግሞ አምናለሁ፡፡ እግዚአብሄርን የማመሰግነው ለዚህ ነው፡፡
 
ይህንን ወንጌል የማገለግለው እግዚአብሄርን ስለማመሰግን ነው፡፡ ለእኔ ለዚህ እውነት እኖራለሁ፡፡ ይህንንም ወንጌል አገለግላለሁ፡፡ ምክንያቱም የሰማያዊውን፣ የሐምራዊውንና የቀዩን ማግ እውነት የማያውቁ አሁንም ብዙ ሰዎች አሉና፡፡ አሁን ግን ሌሎች ይህንን ወንጌል ያገለግላሉ ወይም አያገለግሉም የሚለውን ጥያቄ ገለል እናድርግና የሚያስፈልገው ነገር እናንተ ራሳችሁ በመጀመሪያ በዚህ ወንጌል ማመናችሁ ነው፡፡
 
ሁላችሁም ኢየሱስ ለአንዴና ለመጨረሻ ከሐጢያቶቻችሁ ያዳናችሁ በመሆኑ እውነት ታምኑ ዘንድ ተስፋ አደርጋለሁ፤ እጸልያለሁም፡፡