Search

የመገናኛው ድንኳን ጥናት፤

ቅድስቱ ስፍራ

ተዛማጅ ስብከቶች

· ለእያንዳንዱ የመገናኛው ድንኳን ሳንቃ ሁለት የብር እግሮች ሁለት ማጋጠሚያዎች፡፡ ‹‹ዘጸዓት 26፡15-37››

ለእያንዳንዱ የመገናኛው ድንኳን ሳንቃ ሁለት የብር እግሮች ሁለት ማጋጠሚያዎች፡፡
‹‹ ዘጸዓት 26፡15-37 ››
‹‹ለማደርያውም የሚቆሙትን ሳንቆች ከግራር እንጨት አድርግ፡፡ የሳንቃው ሁሉ ርዝመቱ አሥር ክንድ ወርዱም አንድ ተኩል ይሁን፡፡ ለእያንዳንዱም ሳንቃ አንዱን በአንዱ ላይ የሚያያይዙ ሁለት ማጋጠሚያዎች ይሁኑለት፤ ለማደርያው ሳንቆች ሁሉ እንዲሁ አድርግ፡፡ ለማደርያውም በደቡብ ወገን ሀያ ሳንቆችን አድርግ፡፡ ከሀያውም ሳንቆች በታች አርባ የብር እግሮችን አድርግ፤ ከእያንዳንዱ ሳንቃ በታች ለሁለት ማጋጠሚያዎች ሁለት እግሮች ይሁኑ፡፡ ለማደርያውም ለሁለተኛው ወገን በሰሜን በኩል ሀያ ሳንቆች፤ ለእነርሱም አርባ የብር እግሮች ይሁኑ፤ ከእያንዳንዱም ሳንቃ በታች ሁለት እግሮች ይሁኑ፡፡ ለማደርያውም በምዕራቡ ወገን በስተኋላ ስድስት ሳንቆችን አድርግ፡፡ ለማደርያውም ለሁለቱ ማዕዘን በስተኋላ ሁለት ሳንቆችን አድርግ፡፡ ከታችም እስከ ላይ እስከ አንደኛው ቀለበት ድረስ አንዱ ሳንቃ ድርብ ይሁን፤ እንዲሁም ለሁለቱ ይሁን፤ እነርሱም ለሁለቱ ማዕዘን ይሆናሉ፡፡ ስምንት ሳንቆችና አሥራ ስድስት የብር እግሮቻቸው ይሁኑ፤ ከእያንዳንዱም ሳንቃ በታች ሁለት እግሮች ይሆናሉ፡፡ ከግራርም እንጨት በማደርያው በአንድ ወገን ላሉት ሳንቆች አምስት መወርወሪያዎች፤ በማደርያውም በሁለተኛው ወገን ላሉት ሳንቆች አምስት መወርወርያዎች፤ በማደርያውም በስተኋላ በምዕራብ ወገን ላሉት ሳንቆች አምስት መወርወሪያዎች አድርግ፡፡ መካከለኛው መወርወሪያ በሳንቆች መካከል ከዳር እስከ ዳር ይለፍ፡፡ ሳንቆቹንም በወርቅ ለብጣቸው፡፡ ቀለበቶቻቸውንም የመወርወሪያ ቤት እንዲሆኑላቸው ከወርቅ ሥራቸው፤ መወርወሪያዎቹንም በወርቅ ለብጣቸው፡፡ ማደርያውንም በተራራ እንዳሳየሁህ ምሳሌ አቁም፡፡ መጋረጃውንም ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊም፣ ከቀይም ግምጃ፣ ከተፈተለ ከጥሩ በፍታም አድርግ፤ ብልህ ሠራተኛ እንደሚሠራ ኪሩቤል በእርሱ ላይ ይሁኑ፡፡ በወርቅ በተለበጡት ከግራር እንጨትም በተሠሩት በአራቱ ምሰሶች ላይ ስቀለው፤ ኩላቦቻቸውም ከወርቅ አራቱም እግሮቻቸው ከብር የተሠሩ ይሁኑ፡፡ መጋረጃውንም ከመያዣዎቹ በታች ታንጠለጥለዋለህ፤ በመጋረጃውም ውስጥ የምስክርን ታቦት አግባው፤ መጋረጃውም በቅድስቱና በቅድስተ ቅዱሳኑ መካከል መለያ ይሁናችሁ፡፡ በቅድስተ ቅዱሳኑም ውስጥ የስርየት መክደኛውን በምስክሩ ታቦት ላይ አድርግ፡፡ ገበታውንም በመጋረጃው ውጭ መቅረዙንም በገበታው ፊት ለፊት በማደርያው በደቡብ ወገን አድርግ፤ ገበታውንም በሰሜን ወገን አድርገው፡፡ ለድንኳኑም ደጃፍ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊም፣ ከቀይም ግምጃ፣ ከተፈተለ ከጥሩ በፍታም በጥልፍ አሠራር የተሠራ መጋረጃ አድርግለት፡፡ ለመጋረጃውም አምስት ምሰሶች ከግራር እንጨት አድርግ፤ በወርቅም ለብጣቸው፤ ኩላቦቻቸውም ከወርቅ የተሠሩ ይሁኑ፤ አምስትም እግሮች አድርግላቸው፡፡››
 
ሳንቃዎቹ
 
የመገናኛው ድንኳን ራሱ የተሰራው በ48 ሳንቆች ነበር፡፡ በደቡብና በሰሜን ወገን ለእያንዳንዳቸው ሃያ ሳንቆች፣ ለምዕራብ ወገን ስድስት ሳንቆች፣ ለበስተኋላ ማዕዘኖች ደግሞ ሁለት ሳንቆች ነበሩ፡፡ እያንዳንዱ ሳንቃ 15 ጫማ ርዝመትና 2.2 ጫማ ወርድ ነበረው፡፡ እያንዳንዱ ሳንቃ ቀጥ ብሎ እንዲቆም እርስ በርሳቸው በትክክል የተቆራኙ ሁለት የብር እግሮች ሁለት መጋጠሚያዎች ነበሩ፡፡ ይህም እንደገና የእግዚአብሄር ደህንነት ሊሰጥ የሚችለው በክርስቶስ በማመን በጸጋ ብቻ መሆኑን ያሳያል፡፡
 
 

በክርስቶስ በማመን በጸጋ የሚሰጥ ደህንነት፡፡ 

 
አብዛኞቹ ክርስቲያኖች የታወቀውን የኤፌሶን 2፡8-9 ምንባብ ያውቁታል፡- ‹‹ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም፡፡ ማንም እንዳይመካ ከሥራ አይደለም፡፡›› ነገር ግን ይህ ጸጋ በትክክል ምን እንደሆነና ለመዳን ምን ዓይነት እምነት ሊኖራቸው እንደሚገባ የማያውቁ መሆናቸው ያሳዝናል፡፡ ሆኖም እርስ በርሳቸው በትክክል የተቆራኙት የሁለቱ የብር እግሮችና ማጋጠሚያዎች ምስጢር የእግዚአብሄርን የደህንነት ምስጢር በግልጽ ያሳየናል፡፡ 
 
ከሳንቆቹ በታች ያሉትን ‹‹ሁለት ማጋጠሚያዎችና ሁለት የብር እግሮች›› እውነት ለመረዳት በመጀመሪያ የወንጌልን መሰረታዊ እውነት ማወቅ ያስፈልገናል፡፡ የመገናኛው ድንኳን በሮች በሙሉ የተሰሩት ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ ነበር፡፡ እነዚህ አራቱ ቀለማቶች እኛ ከሐጢያቶቻችንና ከጥፋት እንድንድን የኢየሱስ ጥምቀትና ደም አስፈላጊ እንደነበሩ ያሳዩናል፡፡ ከማንኛውም ጥርጥሬ ነጻ ሆነን በኢየሱስ የደህንነት እውነት እንድናምንም ያስችለናል፡፡ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ ተገልጦ ስላዳነን እውነት ግልጽ የሆነ ዕውቀት ሊኖረንና በእርሱም ልናምንበት ይገባናል፡፡ 
 
ኢየሱስ እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹እውነትንም ታውቃላችሁ እውነትም አርነት ያወጣችኋል፡፡›› (ዮሐንስ 8፡32) ስለዚህ በመገናኛው ድንኳን የመጋረጃ በርና በቅድስተ ቅዱሳኑ መጋረጃ የተገለጠውንና በአራቱ ቀለማቶች ውስጥ የተደበቀውን መንፈሳዊ እውነት በማወቅ ሁላችንም የሐጢያቶቻችንን ፍጹም የሆነ ስርየት መቀበል አለብን፡፡ የመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ቁሰ ቁሶች ሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግና ጥሩ በፍታ ናቸው፡፡ 
 
በሌላ አነጋገር ኢየሱስ ክርስቶስ አዳኛችንና ለሚያምኑትም ንጉሥ ነው፡፡ እርሱ በዮሐንስ በመጠመቅና ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ በራሱ ሥጋ በመውሰድ፣ የዓለምን ሐጢያቶች በመሸከምና በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰስ ከዓለም ሐጢያቶች በሙሉ በአንድ ጊዜ አድኖናል፡፡ ንጉሥ የሆነው ኢየሱስ ከሐጢያቶቻችን በተጨባጭ ሊያድነን የቻለው ስለተጠመቀና ስለተሰቀለ ነው፡፡ ስለዚህ ሰማያዊውና ቀዩ ማጎች እኛ ከሐጢያቶቻችን እንድን ዘንድ ልንተወው የማንችለውን ግልጽና ተጨባጭ እውነት ይነግሩናል፡፡ ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን ለመውሰድ በዮሐንስ ተጠመቀ፡፡ የዓለምን ሐጢያቶች በመሸከምና በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰስ ለአንዴና ለመጨረሻ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖን የደህንነት ሥራዎቹን አጠናቀቀ፡፡ 
እዚህ ላይ እነዚህ አራቱ የሰማያዊው ማግ፣ (የኢየሱስ ጥምቀት) የቀዩ ማግ፣ (የፈሰሰው የኢየሱስደም) ሐምራዊው ማግ (እርሱ ንጉሣችን መሆኑ) እና ጥሩው በፍታ (እርሱ የተብራራው ቃል አምላክ መሆኑና እኛን ጻድቃን ማድረጉ) ነጥቦች በሙሉ ለደህንነታችን ጥቅም ላይ የዋሉ ቁሳ ቁሶች ናቸው፡፡ ይህ ሆኖ ሳለ እነዚህ በአንዱ ብቻ በማመን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ለመዳን የምንሞክር ከሆነ የዚህ ዓይነቱ ደህንነት ምሉዕ እንደማይሆን መረዳት አለብን፡፡ ለምን? ምክንያቱም ከመገናኛው ድንኳን ከእያንዳንዱ ሳንቃ በታች ሳንቃውን ለመደገፍ ከብር እግሮቹ ጋር የሚጋጠሙ ሁለት ማጋጠሚያዎች አሉና፡፡ 
 
በመጽሐፍ ቅዱስ ውሰጥ ብር የሚያመለክተው የእግዚአብሄርን ስጦታ የሆነውን የአምላክ ጸጋ ነው፡፡ በሮሜ 5፡1-2 ላይ እንዲህ ተጽፎዋል፡- ‹‹እንግዲህ በእምነት ከጸደቅን በእግዚአብሄር ዘንድ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሰላምን እንያዝ፡፡ በእርሱም ደግሞ ወደቆምንበት ወደዚህ ጸጋ መግባትን አግኝተናል፡፡ በእግዚአብሄር ክብርም ተስፋ እንመካለን፡፡›› ደህንነታችንን ማግኘት የምንችለው እምነታችን ከእግዚአብሄር ጸጋ ጋር በትክክል ሲጣጣም ብቻ ነው፡፡ በእያንዳንዱ የመገናኛው ድንኳን ሳንቃ በታች ሁለት ማጋጠሚያዎች እንደነበሩና እነዚህ ማጋጠሚያዎችም ሳንቃውን ለመደገፍ በብሩ እግሮች ላይ እንደሚጋጠሙ ሁሉ እግዚአብሄርም ደህንነታችን የሚጠናቀቀው እኛም በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደሙ ስናምን ብቻ እንደሆነ እየነገረን ነው፡፡ 
 
ሁላችንም እያንዳንዱ ሳንቃ ለምን ሁለት ማጋጠሚያዎች እንደነበሩት በማመዛዘንና በተጨባጭ ፍሬ ነገር ማመን አለብን፡፡ 
 
እነዚህ የሳንቃው ሁለት እግሮችና ሁለት ማጋጠሚያዎች በአዲስ ኪዳን ዘመን ኢየሱስ መጥቶ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ፣ በመሰቀል፣ ደሙን በማፍሰስና በመስቀል ላይ በመሞት ደህንነታችንን በሚገባ እንደሚፈጽም ለሚናገረው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ጥላ ነበሩ፡፡ 
 
በሌላ አነጋገር የሐጢያት ስርየት ጸጋ የተሰጠው ኢየሱስ በዮሐንስ በመጠመቁና ሐጢያቶቻቸውንም ለመደምሰስ በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰሱ በፈጸመው የጽድቅ ደህንነታቸው በተጨባጭ ለሚያምኑ ልቦች ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ እኛ ከሐጢያቶቻችን እንድን ዘንድ በእነዚህ በሁለቱ የኢየሱስ ሥራዎች የሚያምን እምነት ያስፈልገናል፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ የመገናኛው ድንኳን እያንዳንዱ ነገር ከሐጢያቶቻችን ያዳነንን የኢየሱስን ስዕላዊ መግለጫ በዝርዝር ያቀርባል፡፡ ጌታ እስራኤሎች ለእያንዳንዱ የማደርያው ሳንቃ ሁለት ማጋጠሚያዎችንና ሁለት የብር እግሮችን እንዲጠቀሙ ያደረገው ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ 
 
እኛ እግዚአብሄር በሰጠን የጥምቀትና የፈሰሰ ደም ሥራዎች አማካይነት ሙሉ በሙሉ ከሐጢያቶቻችን ሁሉና ከሐጢያት ኩነኔ ሁሉ ድነናል፡፡ ነጻም ወጥተናል፡፡ በሌላ አነጋገር የእግዚአብሄር ልጆች የመሆንን መብት ያገኘነው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ነው፡፡ እንደ ንጹህ ወርቅ የሆነው እምነታችን የተገነባው ይህንን የእግዚአብሄር ስጦታ በመቀበል ነው፡፡
 
 

ኢየሱስን እያመናችሁ እንኳን አሁንም ድረስ በትክክል ማን እንደሆናችሁ አታውቁምን?

 
ራሳችሁን ጥሩ ሰው አድርጋችሁ ትመለከታላችሁን? በራሳችሁ በማናቸውም ሁኔታዎችና በማናቸውም መልኮች ፈጸሞ ዓመጽን ሊታገስ የማይችል የጽድቅ ባህርይ እንዳላችሁ ታስባላችሁን? በየቀኑ የእግዚአብሄርን ትዕዛዛቶች በልባችሁ ስለምትጠብቁና በሕይወታችሁም ልትታዘዙዋቸውና ልትተገብሩዋቸው የምትሞክሩ በመሆናችሁ ቢያንስ በእግዚአብሄር ፊት ጻድቃን እንደሆነ ታስባላችሁን? እኛ የምናደርገው ነገር በሙሉ ጻድቃን ለመሆን ማስመሰል ነው፡፡ ነገር ግን በድብቅ ምንዝርናንና ዝሙትን እንፈጽማለን፡፡
 
በዚህ ዘመን በኬብል ወይም ሳተላይት የሚተላለፉ በመቶዎች የሚቆጠሩ የቴሌቪዥን ጣቢያዎችን ማየት ይቻላል፡፡ እነዚህ ጣቢያዎች በቀን ለ24 ሰዓታት ስለሚተላለፉ የራሳቸውን ልዩ መርሃ ግብሮች ይዘው ያለ ማቋረጥ ይተላለፋሉ፡፡ ከእነዚህ ጣቢያዎች መካከል በንግዱ ዘርፍ እጅግ የተዋጣላቸው ልዩ ጣቢያዎች ከሁሉም በላይ ለጎልማሶች የሚተላለፉ ጣቢያዎች ናቸው፡፡ ጣቢያዎችን በመቀያየር ብቻ ሁሉንም ዓይነት ልቅ የሆኑ የወሲብ ድርጊቶች የሚታዩባቸውና ለጎልማሶች የተዘጋጁ ብዙ የዚህ ዓይነት ጣቢያዎች አሉ፡፡ ልቅ የወሲብ ድርጊቶችን የያዙ ድረ ገጾችን በሚመለከትስ? አሁን ልቅ የወሲብ ድርጊቶችን ጎርፍ የያዙ ስፓም ሜሎች ዓለምን እያጥለቀለቁ ነው፡፡ የእነዚህን አሳፋሪ ድረ ገጾች ክፋት ሁሉም ሰው ይጠላዋል፡፡ ነገር ግን ወደ ‹‹አቅርቦትና ፍላጎት ሕግ›› ስናስብ የእነርሱ ስኬት ማለት እጅግ ብዙ ሰዎች በድብቅ እነዚህን ድረ ገጾች በመጎብኘት መደሰታቸው ነው፡፡
 
ይህ ክስተት እኛ ሰብዓዊ ፍጡራን በመሰረቱ የተበላሸንና የምናሳፍር መሆናችንን ያሳየናል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ዝሙትን፣ ምንዝርናንና ልቅነትን በመጠቆም የሰውን ዘር በሐጢያት የተሞሉ ልቦች ይጠቁማል፡፡ እግዚአብሄር እነዚህ ነገሮች ከሰዎች ልብ ወጥተው እንደሚያረክሱዋቸውና በግልጽ ሐጢያቶች እንደሆኑም ተናግሮዋል፡፡ ታዲያ ሁላችንም በሐጢያት የተሞላን አይደለንምን? እግዚአብሄር ለእኛ ውስብስብ የሆኑብን ጉዳዮች በሐጢያት የተሞሉ እንደሆኑ በተደጋጋሚ ነግሮናል፡፡
 
ነገር ግን ይህንን በእርግጠኝነት እናምነዋለን? እንዴት ነው? ዓኖቻችንን በመጨፈንና ጆሮዎቻችንን በመድፈን ለእኛ ውስብስብ ከሆኑት ሐጢያት ባህሪያቶች ማምለጥ እንችላለንን? በአእምሮዋችን እሳቤዎችና አስተሳሰቦች ሁሉንም ዓይነት ሐጢያቶች ከመስራት በስተቀር ማድረግ የምንችለው ነገር የለም፡፡ እንደዚህ ካሉት ሐጢያቶች መራቅ እንዳለብን ምንም ያህል ጠንከረን ብንሞክር ሁሉም ከንቱ ነው፡፡ ሥጋችን እንደዚህ ያለ በመሆኑ ሥጋዊ ሐጢያት የማይሰሩ ፍጹም ቅዱሳን መሆን ጨርሶ አለመቻል ብቻ አይደለም፡፡ ነገር ግን ከሐጢያት ጋር በተጨባጭ ፍቅር ስለያዘን ከእርሱ የመራቅ ፍላጎትም የለንም፡፡ የሰው ዘር ሥጋና ልብ ሁልጊዜም ቅዱስ ከሆኑት ነገሮች በጣም የራቁ ናቸው፡፡ ከዚህም በላይ እነርሱ ወደ ሐጢያት መቅረብ የሚፈልጉ ከመሆናቸውም በላይ ታላላቅ ሐጢያቶችንም እንኳን መስራት እንደሚሹ የታወቀ እውነታ ነው፡፡
 
በምስራቁ ዓለም ብዙዎች ከውልደታቸው ጀምረው የኮንፊሺየስን ትምህርቶች ተምረዋል፡፡ ከዚህ የተነሳ እነዚህን ትምህርቶች ለመተግበር አብዝተው ይሞክራሉ፡፡ በሌላ በኩል በምዕራቡ ዓለም ካቶለካዊነት ወይም ሕግ አጥባቂ የክርስቲያን ቤተክርስቲያኖች የሐይማኖት ክልሉን ስለተቆጣጠሩት ብዙ ምዕራባውያን አጥብቀው እስከሞከሩ ድረስ ይበልጥ ቅዱሳን እየሆኑ እንደሚሄዱ በማሰብ የእግዚአብሄርን ሕግ ለመጠበቅ ጠንክረው ሞክረዋል፡፡ ነገር ግን ሐይማኖታዊ ዳራዎቻቸው ምንም ሊሆኑ ቢችሉም ራሳቸውን በእግዚአብሄር ፊት ሲያቀርቡና እውነተኛ ማንነታቸው ሲጋለጥ ሁሉም የሐጢያት ማከማቻዎችና የክፉ አድራጊ ዘሮች ናቸው፡፡
 
ሰብዓዊ ፍጡራን ዓመጸኞች በእንከኖች የተሞሉና ከአፈርና ከቆሻሻ የተሰሩ የሐጢያት ማከማቻዎች ናቸው፡፡ በጎ ምግባሮቻቸው ለመታወቅ የተደረጉ ሳይሆኑ ከእውነተኛ ልባቸው የፈለጉና ለሰሩዋቸው በጎ ምግባሮች አንዳች ምስጋና መቀበል የማይመቻቸው በጎ ሰዎች የሚመስሉ እንኳን መሰረታዊ ነገራቸው በእግዚአብሄር ፊት ሲታይ የሐጢያት ማከማቻዎችና የክፉ አድራጊ ዘሮች ከመሆናቸው እውነታ ማምለጥ አይችሉም፡፡ የሰውን ዘር ጽድቅ ማቀንቀን በእግዚአብሄር ፊት ትልቅ ሐጢያት ስለሆነ ሰዎች ቅጣታቸውን ተረድተው የእግዚአብሄር ፍቅር የሆነውን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል እስካልተቀበሉ ድረስ ከሐጢያት ኩነኔ ማምለጥ አይችልም፡፡ የሰው ዘር ጥረቶች በእግዚአብሄር ፊት ወደ ምንም ዓይነት ቸርነት አይለወጡም፡፡ የአቧራ ያክል እንኳን ዋጋ የላቸውም፡፡ የሰው ዘር ፈቃድ በእርሱ ፊት የረከሰ ነው፡፡
 
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሰብዓዊ ፍጡራን ብዙውን ጊዜ በእንጨት ተመስለዋል፡፡ የግራር እንጨት በራሱ እግዚአብሄር በመጀመሪያ ወርቅ ካልለበጠው በስተቀር የእግዚአብሄር ቤተ መቅደስ የመግቢያ በር ምሰሶ ሆኖም ሊቆም አይችልም፡፡ ሰዎች እግዚአብሄር ከሰጠው የደህንነት ጸጋ ውጪ የፍርድ እሳት ከሚጠብቀው አቧራ በቀር አንዳች ነገር ሊሆኑ አይችሉም፡፡
 
ነገር ግን ሐጢያተኞች ሆነን ሳለን እንኳን እግዚአብሄር መሲሁ ኢየሱስ ክርስቶስን እንዲጠመቅና እስከ ሞት ድረስ እንዲደማ በማድረግ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ አስወገደ፡፡ ይህ ደህንነት መሲሁ ከመምጣቱ ከሺህ ዓመታቶች በፊት በንጉሥ ዳዊት ዝርዝር ተተንብዮአል፡፡ ‹‹ምሥራቅ ከምዕራብ እንደሚርቅ እንዲሁ እግዚአብሄር ለሚፈሩት ይራራል፡፡ ፍጥረታችንን እርሱ ያውቃልና፡፡ አቤቱ እኛ አፈር እንደሆንን አሰስብ፡፡›› (መዝሙረ ዳዊት 103፡12-14)
 
የእግዚአብሄርን ጽድቅ ከማወቃችን በፊት የሕይወት መለኪያችን የሰው ዘር ጽድቅ ነበር፡፡ የእግዚአብሄርን የደህንነት ስጦታ ሳላውቅና በቃሉ ሳላምን በፊት እኔም እንደዚያ ነበርሁ፡፡ በእርግጥ የራሴ የሆነ ጽድቅ አልነበረኝም፡፡ ነገር ግን ራሴን ጨዋ እንደሆንሁ አድርጌ አስብ ነበር፡፡ ስለዚህ ከልጅነቴ ጀምሮ ብዙ ጊዜ የፍትህ መጓደልን በመቃወም ከማልችላቸው ሰዎች ጋር እንኳን እጣላ ነበር፡፡ የኔ መፈክር ‹‹የጽድቅ ሕይወት መኖር›› የሚል ነበር፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ማንነቴን ማየት ስለተሳነኝ በራሴ ጽድቅ የተሞላሁ ነበርሁ፡፡ ስለዚህ ከሌሎቹ ይልቅ ስለ ራሴ ጥሩ አስብና በጽድቅ ለመኖርም እጥር ነበር፡፡
 
ነገር ግን እንደ እኔ ዓይነት ሰው በእግዚአብሄር ጽድቅ ፊት ከተራ የሐጢያት ማከማቻ የዘለለ አልነበረም፡፡ እኔ እግዚአብሄር እንዲጠበቁ ካዘዛቸው አስርት ትዕዛዛት ወይም ከ613 ሕጎች አንዱን እንኳን መጠበቅ ያልቻልሁ ሰው ነበርሁ፡፡ እነዚህን ሕጎች የመጠበቅ ፈቃድ ያለኝ የመሆኑ እውነት በራሱ እኔ ከሐጢያት በስተቀር አንዳች ነገር ፈጽሞ ማድረግ የማልችል መሆኔን በሚነግረኝ የእግዚአብሄር ቃልና በራሱ በእግዚአብሄር ላይ ያመጸ የዓመጽ ድርጊት ነበር፡፡ የሰው ዘር ጽድቅ ሁሉ በእግዚአብሄር ፊት ዓመጽ ብቻ ነው፡፡ 
 
በልቅነትና በብልሹነት ጎርፍ ውስጥ እግዚአብሄርንና የእርሱን ሕግ የጣሰው ይህ ትውልድ የጥፋተኝነት ስሜትም የለውም፡፡ ነገር ግን ሰብዓዊ ፍጡራን በየቀኑ ሐጢያት ከመስራት በቀር የምናደርገው ነገር ስለሌለ ያለ ምንም ማመንታት ወደ ሲዖል ለመሄድ የተኮነንን መሆናችንን መረዳት ይኖርብናል፡፡
 
 
እኛ ዓመጸኞችና በሐጢያት የተሞላን ነበርን፤ አሁን ግን ጌታ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ከሐጢያቶቻችን በማዳን የራሱ ሕዝብ አድርጎናል፡
 
እኛ ሁላችን ዓመጸኞች ነበርን፡፡ ነገር ግን በደህንነት ስጦታ አማካይነት እኛን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖናል፡፡ ርዝመቱ 15 ጫማ ወርዱ 2.2 ጫማ የሆነው የቅድስተ ቅዱሳኑ እያንዳንዱ ሳንቃ በወርቅ ከተለበጠ የግራር እንጨት ተሰርቶ የቅድስተ ቅዱሳኑ ግድግዳዎች ሆኖ ቆሞዋል፡፡ ከእያንዳንዱ ሳንቃ በታች ሳንቃውን ለመደግፍ ሲባል ሁለት የብር እግሮች ይኖራሉ፡ እዚህ ላይ የብሩ እግሮች እግዚአብሄር እናንተንና እኔን ሙሉ በሙሉ በራሱ እንዳዳነን ይገልጣል፡፡
 
እግዚአብሄር እኛን ከሐጢያት ያዳነበት እውነት ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ መጥቶ ሐጢያቶቻችንን ለመውሰድ መጠመቁን፣ በመስቀል ላይ በመሞትም፣ የሐጢያቶቻችን ኩነኔ መሸከሙንና በዚህም ከዓለም ሐጢያቶችና ኩነኔ ሁሉ ማዳኑን የሚገልጠው ፍቅሩ ነው፡፡ እርሱ በሰጠን የደህንነት ስጦታ በማመን ዳግመኛ ተወልደናል፡፡ ጌታ የሰጠን ይህ የደህንነት ስጦታ ልክ እንደ ወርቅ የማይበሰብስ ስለሆነ ለዘላለም የማይለወጥ ነው፡፡
 
ጌታ የሰጠን ደህንነት ከኢየሱስ ጥምቀትና ደም የተገኘ ነው፡፡ ይህም ሙሉ በሙሉና በግልጽ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ደምስሶታል፡፡ እናንተና እኔ በአእምሮዋችን፣ በአስተሳሰቦቻችንና በተጨባጭ በምናደርጋቸው ምግባሮች ከምንሰራቸው ሐጢያቶች ሁሉ ሙሉ በሙሉ ነጻ መውጣት የቻልነው ጌታ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ስላዳነን ነው፡፡ እግዚአብሄር በልባችን ውስጥ በሰጠን የደህንነት ስጦታ በማመን የእርሱ ክቡር ቅዱሳን ሆነናል፡፡ እግዚአብሄር የመገናኛውን ድንኳን እያንዳንዱን ሳንቃ በሚደገፉት በሁለቱ እግሮች አማካይነት የውሃውንና የመንፈሱን ደህንነት እየነገረን ነው፡፡ እግዚአብሄር እኛ የእርሱ ልጆች የሆንነው 100 በመቶ በእርሱ ጸጋና ስጦታ እንደሆነ እየነገረን ነው፡፡
በኢየሱስ ጥምቀትና ደም ላይ ያለንን እምነት ብናስወግድ በውስጣችን የሚቀር አንዳች ነገር አይኖርም፡፡ ሁላችንም ለሐጢያት ለመኮነን የታጨን ነበርን፡፡ እኛ የሐጢያት ደመወዝ ሞት መሆኑን በሚያውጀው የእግዚአብሄር ሕግ መሰረት እርግጠኛ በሆነው ሞታችን ፊት ለመንቀጥቀጥ የታጨን ተራ ሟቾች የነበርንና የሚጠብቀንን የጽድቅ እሳት ፍርድ በማወቅ ስናለቅስ የነበርን ሰዎች ነበርን፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ላይ ያለንን እምነት ካስወገድን ከንቱዎች የምንሆነው ለዚህ ነው፡፡
 
አሁን እየኖርን ያለነው በሐጢያት በተሞላ ዘመን ውስጥ ስለሆነ ዕድላችን የእሳት ፍርድን መጠባበቅ ብቻ እንደነበር ፈጽሞ መርሳት የለብንም፡፡ እኛ እንዲህ ያለን ሟቾች ነበርን፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር የውሃውንና የመንፈሱን ደህንነት ስለሰጠን ጸጋውን በሙላት ለገሰን፡፡ መሲሁ ወደዚህ ምድር መጥቶ በዮሐንስ በመጠመቅ ደሙን አፍስሶ በመስቀል ላይ ሞተ፡፡ ዳግመኛም ከሙታን ተነሳ፡፡ በዚህም ከሐጢያቶቻችን ሁሉ፣ ከዓመጻችን ሁሉና ከኩነኔያችን ሁሉ አዳነን፡፡ አሁን እኛ በዚህ የውሃና የደም ፍጹም ወንጌል በማመን ከሐጢያቶቻችን ስለዳንን በእምነታችን እግዚአብሄርን ማመስገን እንችላለን፡፡
 
በሥጋችን ብቁዓን ባንሆንም ሰራተኞቻችን፣ አገልጋዮቻችንና እኔ ይህንን የውሃና የመንፈስ ወንጌል በመላው ዓለም እየሰበክን ነው፡፡ ይህ ዘመን የተበላሸ ዘመን ቢሆንም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ስለምናምን ከማናቸውም ሐጢያት ነጻ ሆነን ጌታን በንጽህና ማገልገል ችለናል፡፡ ይህንን አእምሮ የያዝነው ከእኛ ጉልበት የተነሳ ሳይሆን ጌታ እኛን በደህንነት ጸጋው በማልበስ ቅድስናን ስለሰጠን ነው፡፡
 
ይህንን የደህንነት ሐይል የለበስነው ጌታ ከሐጢያትና ከኩነኔ ፈጽሞ ስላዳነን ነው፡፡ ጌታን በንጽህና ማገልገል የቻልነውም ሙሉ በሙሉ ከዚህ የተነሳ ነው፡፡ ጌታ በውሃና በመንፈስ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ስላዳነን ደካሞች ብንሆንም ከእንግዲህ ወዲህ በሐጢያቶቻችን፣ በድካሞቻችንና በኩነኔ ሳንታሰር እርሱን ልናገለግለው እንደምንችል አምናለሁ፡፡
 
 
እኔ የሆንሁትን የሆንሁት ሙሉ በሙሉ በእግዚአብሄር ጸጋ ነው፡፡
 
በጌታ ጸጋ ባይሆን ኖሮ እነዚህን ነገሮች ማድረግ አዳጋች መሆኑ እውነት ነው፡፡ በእግዚአብሄር ጸጋ ባይሆን ኖሮ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በመላው ዓለም ማሰራጨትና ይህንን ወንጌል በንጽህና ማገልገል ፈጽሞ የሚቻል ነገር አልነበረም፡፡ እናንተና እኔ ወንጌልን እየደገፍንና እያገለገልን ሕይወታችንን መኖር የቻልነው 100 በመቶ እግዚአብሄር በሰጠን የደህንነት ጸጋ ነው፡፡
 
እኛ በእምነት የእግዚአብሄር መቅደስ አምዶችና (ዮሐንስ ራዕይ 3፡12) የመንግሥቱ ሕዝቦች ሆነናል፡፡ ጌታ እንደ ወርቅ የሆነውን እምነት ስለሰጠን አሁን በእግዚአብሄር ቤት ውስጥ እንኖራለን፡፡ ዓለም በሐጢያት እየተጥለቀለቀና እየሰጠመ ባለበት በዚህ ዘመን፤ አብዛኛው ሕዝብ እግዚአብሄርን እየረሳ ወይም እየሰደበ ባለበት በዚህ ዘመን እኛ በንጹህ ውሃ ታጥበን ነጽተናል፡፡ ጥሩ ውሃ መጠጣትና ጌታን በንጽህና ማገልገልም ችለናል፡፡ እኔ ለዚህ በረከት ምንኛ አመስጋኝ እንደሆንሁ ቃላቶች መግለጥ አይችሉም፡፡
 
እምነታችን በእርግጥም እንዲህ ነው፡፡ እንዴት ጻድቃን ልንሆን ቻልን? በውስጣችን በጎነት የሌለ ሆኖ ሳለ ራሳችንን እንዴት ጻድቃን ብለን መጥራት ቻልን? እንደ እናንተና እንደ እኔ ያሉ ሐጢያተኛ ፍጡራን እንዴት ሐጢያት አልባ ሆኑ? በሥጋችሁ ጽድቅ ሐጢያት አልባና ጻደቅ መሆን ይቻላችኋልን? የስጋችሁ አስተሳሰቦች፣ የገዛ ራሳችሁ ጥረቶችና ምግባሮቻችሁ ከእነዚህ ማናቸውም እናንተን ሐጢያት አልባ ወደ መሆን ሊቀይሩዋችሁና ጻድቃን ሊያደርጉዋችሁ ይችላሉን? ጻድቃን መሆን የቻላችሁት በሰማያዊው በሐምራዊው በቀዩ ማግና በጠሩው በፍታ በተገለጠው የእግዚአብሄር ደህንነት በማመናችሁ አይደለምን? በመሲሁ በተፈጸመውና በእግዚአብሄር ቃል ውስጥ በተገለጠው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል አማካይነት በተገኘው ደህንነታችሁ ሳታምኑ ጻድቃን መሆን ትችላላችሁን? በፍጹም እንደዚያ መሆን አትችሉም ነበር! በቀዩ ማግ በማመን ብቻ ፈጽሞ ጻድቃን መሆን አንችልም፡፡
 
አዳኛችንና መሲሃችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእኛ ፋንታ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ለመደምሰስ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት አማካይነት በሕይወት ዘመናችን የሰራናቸውን ሐጢያቶች በሙሉ ጨምሮ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ስለተሸከመ በእምነት ጻድቃን ሆነናል፡፡ የብሉይ ኪዳኑ መስዋዕት ሐጢያተኞች ወይም ሊቀ ካህኑ በራሱ ላይ እጆቻቸውን ሲጭኑበት ሐጢያትን እንደሚሸከም ሁሉ በአዲስ ኪዳን ዘመንም ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ በመጠመቅ ወደ እርሱ የተሻገሩለትን የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ተቀብሎዋል፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በተጨባጭ ወስዶዋል፡፡ (ማቴዎስ 3፡15) ዮሐንስም ‹‹የዓለምን ሐጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሄር በግ›› (ዮሐንስ 1፡29) ብሎ መስክሮለታል፡፡
 
ኢየሱስ ከተጠመቀ በኋላ የሕይወቱን ቀጣይ ሦስት ዓመታቶች ለእኛ ደህንነት በመኖር ወደ መስቀል ሄዶ በሸላቾቹ ፊት ዝም እንደሚል በግ ሥጋውን ለእግዚአብሄር በመስጠት ሐጢያቶቻችንንና ኩነኔን ሁሉ አስወግዶ አዲስ ሕይወትን ሰጠን፡፡
 
ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን በዝምታ አሳልፎ የሰጠውና በሮማውያን ወታደሮች በተሰቀለ ጊዜ እጆቹና እግሮቹ የተቸነከሩት በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በመውሰዱ ነው፡፡ ኢየሱስ በመስቀሉ ላይ ተሰቅሎ በሰውነቱ ውስጥ የነበረውን ደሙን ሁሉ አፈሰሰ፡፡ ‹‹ተፈጸመ!›› (ዮሐንስ 19፡30) በማለት በደህንነታችን ላይ የመጨረሻውን ምዕራፍ አኖረ፡፡
 
በዚህ መንገድ ከሞተ በኋላ በሦስት ቀናት ውስጥ ዳግመኛ ከሙታን ተነስቶ የዘላለምን ሕይወት በመስጠት አዳኛችን ሆነ፡፡ ኢየሱስ ከአጥማቂው ዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት የዓለምን ሐጢያቶች በመሸከሙ፣ በመሰቀሉ፣ በትንሳኤውና በዕርገቱ ፍጹም የሆነ አዳኛችን ሆነ፡፡ ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹የእነዚሀም ስርየት ባለበት ዘንድ ከዚህ ወደዚህ ሰለ ሐጢአት ማቅረብ የለም፡፡›› (ዕብራውያን 10፡18)
 
 

በመስቀሉ ደምና እያደገ በሚሄድ ቅድስና ማመን ፈጽሞ ሙሉ በሙሉ ከሐጢያቶቻችሁ አላዳናችሁም፡፡ 

 
ክርስቲያኖች ኢየሱስ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ብቻ በማመን ፈጽመው ከሐጢያቶቻቸው ሊድኑ እንደማይችሉ ማወቅ አለባቸው፡፡ ሰዎች በዓይኖቻቸውና በድርጊቶቻቸው በየቀኑ ሐጢያት ስለሚሰሩ በመስቀል ላይ በፈሰሰው ደም በማመን ብቻ ሐጢያቶቻቸውን መደምሰስ አይችሉም፡፡ በዚህ ዘመን በሰዎች ሕይወት ውስጥ ከሚፈጽሙት እጅግ ድብቅ ሐጢያቶች አንዱ ስድ የጾታ ግንኙነት ነው፡፡ ልቅና አሳፋሪ የጾታ ግንኙነት ባህል ዓለምን እንዳጥለቀለቀው ሁሉ ይህ ሐጢያት በሥጋችን ውስጥ ተተክሎዋል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንዳናመነዝር ያዝዛል፡፡ ነገር ግን ዛሬ የምናየው ተጨባጭ ነገር ብዙ ሰዎች ከከበቡዋቸው ሁኔታዎች የተነሳ ባይፈልጉትም ይህንን ሐጢያት የሚሰሩ መሆናቸው ነው፡፡ 
 
ሴትን በፍትወት ዓይን የሚያይ ማንኛውም ሰው በልቡ ከእርስዋ ጋር እንዳመነዘረ እግዚአብሄር ይናገራል፡፡ (ማቴዎስ 5፡28) ነገር ግን ዓይኖቻችን በየቀኑ የሚያየው ሁሉ አሳፋሪ ነው፡፡ ስለዚህ ሰዎች በየደቂቃውና በየሰከንዱ እነዚህን ልቅ ሐጢያቶች ይፈጽማሉ፡፡ ነገሩ ይህ ሆኖ ሳለ የንስሐ ጸሎቶችን በማቅረብ እንዴት ሊቀደሱና ወደ እግዚአብሄር መንግሥት ሊገቡ ይችላሉ? እንዴት ጻድቃን ሊሆኑስ ይችላሉ? ለረጅም ጊዜ ራሳቸውን በመግታትና ባረጁ ጊዜ በመጠኑም ቢሆን በመቀደስ ልባቸው ጻድቅ ይሆናልን? ጠባያቸው ይበልጥ ልዝብ ይሆናልን? ይበልጥ ታጋሾች ይሆናሉን? በእርግጥም አይሆኑም! የሚሆነው የዚህ ተቃራኒ ነው!
ገናና ከሆኑት የክርስትና ትምህርቶች መካከል ‹‹እያደገ የሚሄድ ቅድስና ትምህርት›› ይገኝበታል፡፡ ይህ ትምህርት ክርስቲያኖች በመስቀል ላይ የሆነውን የኢየሱስ ሞት ለረጅም ጊዜ ካመኑበት፣ በየቀኑ የንስሐ ጸሎቶችን ከጸለዩና ጌታን በየቀኑ የሚያገለግሉ ከሆኑ ቀስ በቀስ ቅዱስና ራሳቸውን የሚገዙ ይሆናሉ ብሎ ያስተምራል፡፡ ኢየሱስን ማመን ከጀመርንበት ጊዜ አንስቶ ብዙ ዘመን እያለፈ በሄደ ቁጥር ከሐጢያት ጋር ምንም ግንኙነት የሌለውና ምግባሮቹም የተቀደሱ ዓይነት ሰው እንሆናለን ይላል፡፡ ወደ ሞት በምንቀርብበት ወቅት ሙሉ በሙሉ የተቀደስን ስለሆንን ፈጽሞ ሐጢያት አልባ እንሆናለን፡፡
 
ይህ ትምህርት በየጊዜው የንስሐ ጸሎቶችን ስለምንጸልይ ልብሶቻችን እንደሚታጠቡ ሁሉ በየቀኑ ከሐጢያቶቻችን እንታጠባለን፤ ስለዚህ በመጨረሻ ስንሞት ፈጽሞ ጻድቅ እንደሆነ ሰው ሆነን በእግዚአብሄር ፊት እንቀርባለን ብሎ ያስተምራል፡፡ ይህ ግን በሰው ሰራሽ አስተሳሰብ የረቀቀ መላ ምታዊ ግምት ብቻ ነው፡፡
 
ሮሜ 5፡19 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በአንዱ ሰው አለመታዘዝ ብዙዎች ሐጢአተኞች እንደሆኑ እንዲሁ ደግሞ በአንዱ መታዘዝ ብዙዎች ጻድቃን ይሆናሉ፡፡›› ምንባቡ ሁላችንም በአንዱ ሰው መታዘዝ ሐጢያት አልባ እንደሆንን ይነግረናል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በግሉ ወደዚህ ምድር በመጣ ጊዜ እናንተና እኔ ማድረግ ያልቻልነውን አደረገ፡፡ ኢየሱስ እናንተና እኔ ራሳችንን ከሐጢያት ነጻ ማውጣት እንደማንችል በሚገባ በማወቁ በእኛ ፋንታ ሐጢያቶቻችንን አስወገደ፡፡ ይህ ደግሞ እናንተም ሆናችሁ እኔ መቼም ልናደርገው የማንችለው ነገር ነው፡፡ እርሱ ወደዚህ ምድር በመምጣት፣ በመጠመቅ፣ በመሰቀልና ዳግመኛም ከሙታን በመነሳት እናንተንና እኔን አዳነን፡፡ ለአንዴና ለዘላለምም ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አነጻን፡፡
 
ኢየሱስ ክርስቶስ በሐጢያቶቻቸው ስርየት ለሕዝቡ ደህንነትን መስጠት የቻለው የእግዚአብሄርን ፈቃድ በመታዘዙ ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ መሲህ ሆኖ የእግዚአብሄርን ፈቃድ በመታዘዝ በጥምቀቱ፣ በመስቀሉና በትንሳኤው የደህንነትን ጸጋ ሰጠን፡፡ ኢየሱስ እንዲህ የደህንነትን ስጦታ ለእኛ በመስጠት የሐጢያት ስርየትን ፈጽሞ አጠናቀቀ፡፡ አሁን እኛ በእምነት ይህንን የደህንነት ጸጋ ለብሰናል፡፡ ምክንያቱም በራሳችን ውጥኖች ፈጽሞ ሊከናወን የማይችለውን ከሐጢያት መዳናችንን ጌታ ፈጽሞታልና፡፡
 
ሆኖም አብዛኞቹ ክርስቲያኖች ኢየሱስ በተቀበለው ጥምቀት በማመን ፋንታ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ብቻ በማመን በራሳቸው ምግባሮች ለመቀደስ ይሞክራሉ፡፡ በሌላ አነጋገር ኢየሱስ በዮሐንስ በተጠመቀ ጊዜ የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ የወሰደ ቢሆንም ሰዎች አሁንም በዚህ እውነት አያምኑም፡፡ ማቴዎስ ምዕራፍ 3 ኢየሱስ የአገልግሎት ሕይወቱን ሲጀምር ያደረገው የመጀመሪያው ነገር ከዮሐንስ ጥምቀትን መቀበል እንደነበር ይነግረናል፡፡ ይህ በአራቱም የወንጌል ጸሐፊዎች የተመሰከረለት እውነት ነው፡፡
 
ኢየሱስ የሰው ዘር ወኪልና ከሴቶች ከተወለዱት ሁሉ እጅግ በሚበልጠው በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችንን ወሰደ፡፡ ነገር ግን ይህንን እውነት ችላ የሚሉና የማያምኑበት በጣም ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች በጥምቀቱ ሳያምኑ በኢየሱስ ያምናሉ፡፡ እነርሱ በመስቀል ላይ ያፈሰሰውን ክቡር ደም ብቻ በግለት ያመሰግናሉ፡፡ ኢየሱስ በመስቀል ላይ በመሞቱ አዝነው ስሜቶቻቸውን በማነሳሳት በምስጋናቸው ውስጥ ሁሉንም ዓይነት ጫጫታ በማስገባት ‹‹♫በደሙ ውስጥ ግሩም ሐይል አለ፡፡ ♪በበጉ ክቡር ደም ውስጥ ሐይል ድንቅን የሚያደርግ ሐይል አለ♫!›› እያሉ ይጮሃሉ፡፡ በሌላ አነጋገር በራሳቸው ስሜቶች ጥንካሬና ጉልበት ግለው ወደ እግዚአብሄር ሊቀርቡ ይሞክራሉ፡፡ ነገር ግን ይህንን አብዝተው ባደረጉ ቁጥር ቅዱሳን የሆኑ በማስመሰል ይበልጥ ግብዞች ይሆናሉ፡፡ ነገር ግን በልባቸው ውስጥ በድብቅ ሐጢያቶችን እያከማቹ ነው፡፡
 
 

የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ሳናውቅ ኢየሱስን አዳኛችን አድርገን ማመን የምንችለው እንዴት ነው?

 
ሰዎች ስለ መገናኛው ድንኳን ሲናገሩ ስንሰማ ብዙውን ጊዜ በእርግጥ እያወሩ ያሉት ስለምን እንደሆነ ቅንጣት ያህል ፍንጭ እንደሌላቸው እናያለን፡፡ በመገናኛው ድንኳን ስለ ማመን ስንመጣ እንዴት አመቺና ተስማሚ በሚመስለን በማናቸውም መንገድ ማመን እንችላለን? ጌታ የፈጸመው የሐጢያት ደህንነት በጣም ግልጽ ስለሆነ እግዚአብሄር ደህንነታችን ምን ያህል በግልጽና በተጨባጭ እንደተፈጸመ እንረዳ ዘንድ አስችሎናል፡፡
 
እርሱ በመገናኛው ድንኳን አማካይነት ጌታ በሰማያዊውና በቀዩ ማጎች በውሃና በደም እንዳዳነን እንገነዘብ ዘንድ አድርጎናል፡፡ ጌታ ሐጢያቶቻችንን ለመደምሰስ ‹‹በውሃ ብቻ ሳይሆን በውሃና በደም›› (1ኛ ዮሐንስ 5፡6) እንደመጣ ተገንዝበናል፡፡ እኛ የምናምንባቸው ውሃው፣ ደሙና መንፈሱ አንድ ናቸው፡፡ እግዚአብሄር ያዳነን ሰው ሆኖ በመምጣት፣ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ፣ በመሞትና ዳግመኛም ከሙታን በመነሳት ነው፡፡
 
በመገናኛው ድንኳን አማካይነት ይህንን የተብራራውን የደህንነት ስዕላዊ መግለጫ መረዳትና ማመን ችለናል፡፡ የእያንዳንዱን ሳንቃ ሁለት ማጋጠሚያዎችና ሁለት የብር እግሮች በማጥናት ኢየሱስ እኛን ከሐጢያቶቻችን ያዳነበትን ዘዴ ወደ መረዳቱ ደርሰናል፡፡ በዚህም በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጡት የኢየሱስ አገልግሎቶች በእርግጠኝነት ማመን እንዳለብን እውነቱን አግኝተናል፡
 
ይህ ደህንነት ምንጩ መጽሐፍ ቅዱስ እንጂ ሌላ ነገር አይደለም፡፡ እኛ ከእነዚህ ከሁለቱ የጥምቀትና የመስቀል ፍሬ ነገሮች የተሰራው የደህንነት ስጦታ ያስፈልገናል፡፡ በዚህ እውነት የሚያምኑ ከእግዚአብሄር የተወለዱ መሆን ይችላሉ፡፡ እግዚአብሄር በውሃውና በመንፈሱ እኛን ከሐጢያቶቻችን በማዳኑ ፈጽሞ ደህንነታችንን አጠናቆታል፡፡
 
በሌላ አነጋገር ከእያንዳንዱ ሳንቃ በታች ሁለት ማጋጠሚያዎች ተሰርተው በሁለት የብር እግሮች ላይ ተጋጥመው ነበር፡፡ ይህ እውነት ለእኛና ለሐጢያት ስርየታችን በጣም አስፈላጊና እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡ ይበልጥ ደግሞ እግዚአብሄር ለእኛ በፈጸመው ደህንነታችን ማመን አለብን፡፡ ምክንያቱም በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ እውነት የማናምን ከሆንን ፈጽሞ ልንድን አንችልም፡፡
 
የቅዱሱ ማደርያ እያንዳንዱ ሳንቃ ቀጥ ብሎ ለመቆም ሁለት የብር እግሮች እንዳስፈለጉት ሁሉ በኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ማመን ስንመጣም ሁለት የጸጋው እውነቶች ፈጽመው ያስፈልጋሉ፡፡ እነርሱ ምንድናቸው? ኢየሱስ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን መውሰዱና የሐጢያቶቻችንን ኩነኔና እርግማኖች ሁሉ ተሸክሞ ወደ መስቀል በመውሰድ መሰቀሉ ናቸው፡፡ ጻድቅ የሆነ ሰው እንደዚያ ሊሆን የቻለው በእነዚህ ሁለት ፍጹም የደህንነት ጸጋዎች በማመኑ ብቻ ነው፡፡ የደህንነት ስጦታው በሆኑት በሁለቱ ፍሬ ነገሮች ማለትም በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ያለን እምነት በእግዚአብሄር ቤት ውስጥ በጽናት እንድንቆም አድርጎናል፡፡
 
ልክ እንደዚሁ እኛም የእርሱ እንከን የለሽ ሕዝብ የሆንነው በሁለቱ የደህንነት ፍሬ ነገሮች በሚያምነው ትክክለኛ እምነታችን ነው፡፡ እኛ በኢየሱስ የተሰጠውን የውሃና የደም ወንጌል በማመን ለዘላለም የማይለወጠውን እንደ ወርቅ ያለ እምነት ተቀብለናል፡፡ በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጠው የውሃና የመንፈስ ወንጌል በማመን ፍጹም የሆነውን የሐጢያት ስርየት ደህንነት የተቀበልን ቅዱሳን ሆነናል፡፡
 
 
የሥነ መለኮት ዕውቀት እስካሁን ድረስና የውሃና የመንፈስ ወንጌል ዘመን፡፡ 
 
በ313 ዓ.ም የሚላን ሕግ ከወጣበት ጊዜ አንስቶ የዘመኑን ክርስትና ጨምሮ ክርስትና የጥንቱን የቤተክርስቲያን ዘመን አግልሎ የኢየሱስን ጥምቀት በማስወገድ የመስቀሉን ወንጌል ሲያሰራጭ ነበር፡፡ ከጥንቷ ቤተከርስቲያን ዘመን ጀምሮ ክርስትና አዲሱ የሮም ሐይማኖት ሆኖ በሕግ እስከተደነገገበት 313 ዓ.ም ድረስ ክርስትና የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ሲሰብክ ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ ግን የሮም ካቶሊክ ቤተክርስቲያን የሐይማኖቱን ትዕይንት ተቆጣጠረች፡፡ ከዚያም ከ14ኛው ምዕተ ዓመት መጀመሪያ ጀምሮ ሁሉም ነገር በሰው ሰራሽ አስተሳሰቦች ላይ የሚያነጣጥርና የሰብዓዊነትን መታደስ የሚሻ ባህል ብቅ ማለት ጀመረ፡፡ በመጀመሪያ በአንዳንድ የበለጠጉ የሰሜን ጣልያን ጠቅላይ ግዛቶች ተስፋፋ፡፡ ይህ ሕዳሴ ነበር፡፡
 
በ16ኛው ምዕተ ዓመት በጣሊያን የጀመረው የዚህ ባህል ዱካ በምዕራቡ ዓለም መስፋፋት በመጀመሩ በሰብዓዊነት ላይ ያነጣጠረ ሰው ሰራሽ ፍልስፍናን ያጠኑ ምሁራን ነገረ መለኮትን ማጥናት ጀመሩ፡፡ በራሳቸው ጭንቅላት መጽሐፍ ቅዱስን በመተርጎም የክርስትና ትምህርቶችን ማነጽ ጀመሩ፡፡ ነገር ግን እውነትን ባለማወቃቸው መጽሐፍ ቅዱስን በትክክልና በሙላት መረዳት አልቻሉም፡፡ ስለዚህ በጭንቅላታቸው መረዳት ያልቻሉትን ነገር ዓለማዊ ዕውቀታቸውንና አስተሳሰቦቻቸውን በማስገባት አሸነፉት፡፡ በዚህም የራሳቸውን የክርስትና ትምህርቶች አፈለቁ፡፡
 
ከዚህ የተነሳ በክርስትና ታሪክ ውስጥ በርካታ ትምህርቶችና የነገረ መለኮት ዕውቀቶች ብቅ አሉ፡፡ ሉተራውያንነት፣ ካልቪናዊነት፣ አርሜናዊነት፣ አዲስ ነገረ መለኮት፣ ወግ አጥባቂነት፣ ቀና አስተሳሰባዊነት፣ ነቃሽ ነገረ መለኮት፣ ነጻ አውጪ ነገረ መለኮት፣ እንስት ላይ ያተኮረ ነገረ መለኮት፣ በጥቁሮች ላይ ያተኮረ ነገረ መለኮትና ወ.ዘ.ተረፈ ከዚህ ውስጥ ይገኙበታል፡፡
 
የክርስትና ታሪክ በጣም ረጅም ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን በተጨባጭ ያን ያህል ረጅም አይደለም፡፡ ከጥንቷ የክርስቲያን ቤተክርስቲያን ዘመን አንስቶ ለ300 ዓመታት ሰዎች ስለ መጽሐፍ ቅዱስ መማር ችለው ነበር፡፡ ነገር ግን ይህ ፈጥኖ የክርስትና የጨለማ ዘመን በሆነው በመካከለኛው ዘመን ተተካ፡፡ በዚህ ዘመን ለተራ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ በመታረድ ሞት የሚያሰቀጣ ወንጀል ነበር፡፡ የቃለ እግዚአብሄር ዕውቀት ነፋስ በ1700 መንፈስ ጀመረ፡፡ ከዚያም ክርስትና የቃለ እግዚአብሄር ዕውቀቶቹ ብሩህና ሕያው ሆነው ሲያድጉ በ1800ዎቹና በ1900ዎቹ ያበበ መሰለ፡፡ አሁን ግን ብዙ ሰዎች በራሳቸው ልምምዶች ላይ ተመስርተው በእግዚአብሄር በማመን ረቂቅ በሆኑ ትምህርቶች ተጠልፈው ወድቀዋል፡፡ የተለያዩ የቃለ እግዚአብሄር ዕውቀት ቢኖራቸውም የክርስትና ምንጭ ቅርንጫፎች በሙሉ አንድ የጋራ እምነት መሰረት አላቸው፡፡ እርሱም በኢየሱስ ደም ብቻ ማመን ነው፡፡
 
ይህ ግን እውነት ነውን? በዚህ መንገድ ስታምኑ ሐጢያቶቻችሁ በእርግጥ ይወገዳሉን? እናንተ በየቀኑ ሐጢያትን ትሰራላችሁ፡፡ እናንተ በየቀኑ በልቦቻችሁ፣ በአስተሳሰቦቻችሁ፣ በድርጊቶቻችሁና በድካሞቻችሁ ሐጢያት ትሰራላችሁ፡፡ ኢየሱስ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ በማመን ብቻ ከእነዚህ ሐጢያቶች ነጻ መሆን ትችላላችሁን? ኢየሱስ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ በመሞቱ ሐጢያቶቻችንን መሸከሙ መጽሐፍ ቅዱሳዊ እውነት ነው፡፡ ነገር ግን በመስቀሉ ደም ብቻ በማመን ሐጢያቶቻቸው እንደተወገዱላቸው የሚያምኑና በየቀኑ የንስሐ ጸሎቶቻቸውን የሚጸልዩ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ እነዚህን የንስሐ ጸሎቶች በማቅረብ የልባችሁና የሕሊናችሁ ሐጢያቶች ነጽተዋልን? ይህ የማይቻል ነው፡፡
 
እናንተ ክርስቲያኖች ከሆናችሁ ኢየሱስ ክርሰቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በዮሐንስ በመጠመቅ የዓለም ሐጢያቶቻችንን የወሰደ የመሆኑን ይህንን የደህንነት እውነት ማወቅና ማመን አለባችሁ፡፡ ይህ ሆኖ ሳለ አሁንም ይህንን እውነት ላለማወቅና በእርሱም ላለማመን ስትሉ ችላ ትሉታላችሁን? እንደዚያ ከሆነ በኢየሱስ ላይ የማላገጥን፣ ስሙን የማዋረድንና የመናቅን ሐጢያት እየሰራችሁ ነው፡፡ ኢየሱስ በእርግጥም አዳኛችሁ ስለመሆኑ አምናለሁ ማለት አትችሉም፡፡ የኢየሱስን ጥምቀት በኢየሱስ ክርስቶስ ከተፈጸመው ከዚህ ደህንነት በማስወገድ እናንተ በፈለጋችሁት በማንኛውም መንገድ በእርሱ በማመን ፈጽሞ የደህንነትን ጸጋ መልበስ አትችሉም፡፡
 
ነገር ግን ብዙ ሰዎች ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን የደመሰሰ የመሆኑን እውነት እንዳለ አያምኑትም፡፡ በፈንታው ግን የራሳቸውን አስተሳሰቦች በመከተል ማመን በሚፈልጉዋቸው በማናቸውመ የተዛቡ እውነቶች ያምናሉ፡፡ በዚህ ዘመን ሐጢያቶቻቸው በመስቀሉ ደም ብቻ በማመን ሊደመሰሱ እንደሚችሉ በማመን ልቦቻቸው በተሳሳተው የእምነት ትምህርት ይበልጥ ደንድነዋል፡፡
 
ነገር ግን በእግዚአብሄር የታቀደው የደህንነት ምላሽ እንደሚከተለው ነው፡፡ በኢየሱስ ጥምቀት፣ በመስቀል ላይ ሞቱና በትንሳኤው በማመን ዘላለማዊ የሐጢያት ስርየትን ማግኘት እንችላለን፡፡ ነገር ግን የእርሱን ጥምቀት ከዚህ የደህንነት እውነት በመነጠል የሚያምኑና ቀጣዩ ቀመር የማይለወጥ ሕግ መሆኑን በተሳሳተ መንገድ የተረዱና በተሳሳተ መንገድ የሚያምኑ ብዙ ቁጥር ያላቸው ሰዎች አሉ፡፡ ‹‹ኢየሱስ (መስቀሉና ትንሳኤው) + የንስሐ ጸሎቶች + መልካም ምግባሮች = እያደገ በሚሄድ ቅድስና አማካይነት የተሰጠ ደህንነት፡፡›› በዚህ መንገድ የሚያምኑ በአንደበታቸው የሐጢያት ስርየታቸውን እንደተቀበሉ ይናገራሉ፡፡ ነገር ግን እውነቱ ልቦቻቸው በተጨባጭ አሁንም ድረስ መፍትሄ ባጡ የሐጢያት ክምሮች የተሞሉ መሆናቸው ነው፡፡
 
አሁንም ድረስ በልቦቻችሁ ውስጥ ሐጢያት አለን? አሁንም በኢየሱስ እያመናችሁ እንኳን በልቦቻችሁ ውስጥ ሐጢያት ካለባችሁ እምነታችሁ ከባድ ችግር አለበት ማለት ነው፡፡ ሕሊናዎቻችሁ ያልነጹትና ሐጢያት ያለባችሁ በኢየሱስ የምታምኑት ከሐይማኖት ጉዳይ ጋር ብቻ አያይዛችሁ ስለሆነ ነው፡፡ ነገር ግን አሁንም ድረስ በልቦቻችሁ ውስጥ ሐጢያት እንዳለ መረዳት የመቻላችሁ እውነት በራሱ በጣም አስደሳች ነው፡፡ ለምን? ምክንያቱም ሐጢያት እንዳለባቸው በእውነት የሚረዱ ለዚህ ሐጢያት ለሲዖል የታጩ ከመሆን ውጪ ማምለጥ እንደማይችሉ ይገነዘባሉ፡፡ ይህንን ሲያደርጉም በመጨረሻ በመንፈስ ድሆች ስለሚሆኑ የእውነተኛውን ደህንነት ቃል መስማት ይችላሉ፡፡
 
ከእግዚአብሄር ዘንድ የሐጢያት ስርየትን መቀበል የምትፈልጉ ከሆነ ልቦቻችሁ ዝግጁ መሆን አለባቸው፡፡ ልቦቻቸው በእግዚአብሄር ፊት ዝግጁ የሆኑላቸው ሰዎች ‹‹አቤቱ የሐጢያት ስርየትን መቀበል እፈልጋለሁ፡፡ ለረጅም ጊዜ በኢየሱስ አምኜአለሁ፡፡ ነገር ግን አሁንም ድረስ ሐጢያት አለብን፡፡ የሐጢያት ደመወዝ ሞት ስለሆነ ወደ ሲዖል ከመጣል አላመልጥም›› በማለት ያምናሉ፡፡ በእግዚአብሄር ፊትም ሙሉ በሙሉ ሐጢያተኞች መሆናቸውን ይገነዘባሉ፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል የሚረዱና የእግዚአብሄር ቃል በእርግጥም እንደሚናገረው በትክክል የሚፈጸም መሆኑን የሚያምኑ ሰዎች ልባቸው ዝግጁ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር እነዚህን ነፍሳቶች ያለ ማመንታት ይቀበላቸዋል፡፡ እነዚህ ሰዎች የእርሱን ቃል ይሰማሉ፡፡ ቃሉን በራሳቸው ዓይኖች አይተው ያረጋግጣሉ፡፡ እንዲህ በማድረግም ‹‹አሃ በተሳሳተ መንገድ ሳምን ቆይቻለሁ፡፡ በርካታ ሰዎች አሁንም በተሳሳተ መንገድ እያመኑ ነው›› ወደሚል ግንዛቤ ይመጣሉ፡፡ ሌሎች ምንም ቢናገሩም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የሐጢያት ስርየታቸውን ይቀበላሉ፡፡
 
 

ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ የዳኑ ሰዎች በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን እምነታቸውን መደገፍ አለባቸው፡፡

 
ነገር ግን ይህ ዓለም ዳግመኛ የተወለዱትን ሰዎች ልቦች ማናወጥና ማርከስ በሚችሉ ስፍር ቁጥር የሌላቸው ክፉ ትምህርቶች የተሞላ ነው፡፡ ጌታ ኢየሱስ እንዲህ ሲል አስጠንቅቆናል፡- ‹‹ተጠንቀቁ ከፈሪሳውያንና ከሔሮድስ እርሾ ተጠንቀቁ፡፡›› (ማርቆስ 8፡15) ነገር ግን አንድ ጊዜ ብቻ ተደምጠው የሰዎችን ልብ ያረከሱት እንደዚህ ያሉ እርሾ ያለባቸው ትምህርቶች ምን ያህል እንደሆኑ መቁጠር እንኳን አንችልም፡፡ ይህ ዓለም እንዴት በልቅ ወሲብ እየተንገዳገደ እንዳለ መገንዘብ አለብን፡፡
 
እኛ የምናምን በምን ዓይነት ዘመን ላይ እየኖረን እንዳለን በትክክል ማወቅና እምታችንን መከላከል አለብን፡፡ ነገር ግን እንደዚህ ባለው ሐጢያተኛ ዓለም ውስጥ ብንኖርም በልቦቻችን ውስጥ ጌታ እኛን ከሐጢያት ያዳነበት ሊጠቃ የማይችል እውነት አለ፡፡ ለማይለወጠው ደህንነታችን የሚመሰክረው የምስክርነት ቃል የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ነው፡፡ በእውነት ላይ በዓለም የማይናወጥና የማይጎተት እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡
 
ከዚህ ዓለም የሚመነጭ ማንኛውም ነገር እውነት አይደለም፡፡ እግዚአብሄር ጻድቃን ዓለምን እንደሚያሸንፉ ነግሮናል፡፡ ጻድቃን ዲያብሎስን ድል የሚነሱትና ዓለምን የሚያሸንፉት በማይለወጠው የደህንነት እውነት ባላቸው እምነት ነው፡፡ ብቁዓን ባንሆንም ልቦቻችን፣ አስተሳሰቦቻችንና አካሎቻችን አሁንም ደረስ በእግዚአብሄር ቤት ውስጥ ናቸው፡፡ በእምነትም በደህንነት ወንጌል ላይ በጽናት ተተክለዋል፡፡ ጌታ እኛን ባዳነበት በውሃውና በደሙ ወንጌል ላይ በጽናት እንቆማለን፡፡
 
ከዚህ የተነሳ እግዚአብሄርን አብዝተን እናመሰግነዋለን፡፡ ሐጢያት በዚህ ዓለም ላይ ምንም ያህል ቢበዛም ቢያንስ እኛ ጻድቃኖች ነቁጥ የሌለባቸው ሕሊናዎችና በልባችን ውስጥ እንደ ወርቅ የሚያበራ እምነት አለን፡፡ ጌታ እስከሚመጣበት ቀን ድረስ በመንግሥቱ ውስጥም ሆነን እንኳን ሁላችንም ይህንን እውነት እናወድሳለን፡፡ ያዳነንን ጌታና ይህንን እምነት የሰጠንን አምላክ ለዘላለም እናመሰግነዋለን፡፡
ይህ በእግዚአብሄር ፊት ያለን እውነተኛ እምነት በዓለት ላይ የተገነባ ስለሆነ በማናቸውም ሁኔታዎች አይናወጥም፡፡ ስለዚህ በጌታ ፊት እስከምንቆምበት ቀን ድረስ በዚህ ምድር ላይ ስንኖር ምንም ነገር ቢገጥመን ልቦቻችንን በእምነት እንከላከላለን፡፡ በዚህ ዓለም ላይ ያለው እያንዳንዱ ነገር ቢወድም እንኳን፣ ይህ ዓለም በሐጢያት እየሰጠመ ቢሆንም እንኳን፣ ይህ ዓለም ከጥንቶቹ ሰዶምና ገሞራ የከፋ ቢሆንም ይህንን ዓለም አንከተልም፡፡ ነገር ግን በንጽህና በእግዚአብሄር እናምናለን፡፡ የእርሱን ጽድቅ እንከተላለን፡፡ እነዚህን ሁለት የደህንነት ጸጋዎች፣ (የኢየሱስን ጥምቀትና የመስቀል ላይ ሞቱን) እውነተኛ የእግዚአብሄር ጸጋዎች የሚያሰራጩትን ሥራዎች በመስራት እንቀጥላለን፡፡
 
 
በእውነተኛው ወንጌል በማመን የሚያስመስሉ፡፡ 
 
አንዳንድ ሰዎች በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በተጨባጭ ሳያምኑ አሁንም ድረስ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ እንደሚያምኑ ያስመስላሉ፡፡ ነገር ግን እነዚህ ሰዎች ከልባቸው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ባለማመናቸው በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት እንዳለ ማየት እንችላለን፡፡ እነርሱ ከጎረቤቱ የለመነው የብረት ምሳር ውሃ ውስጥ ወድቆ የጠፋበትን ሰው ይመስላሉ፡፡ (2ኛ ነገሥት 6፡5)
 
በተመሳሳይ መንገድ እንደ አስፈላጊነቱ አንዳንድ ሰዎች ለጊዜውም ቢሆን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ይጠቀሙበታል፡፡ ይህ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል እውነት መሆኑን ሳያምኑ በሚሰብኩበት ወይም ሕብረት በሚያደርጉበት ጊዜ ከእውነተኛ እምነት መናገር አይችሉም፡፡ በዚህ እውነት የማያምኑ ሰዎች መሃከል ላይ የእምነት ሕይወታቸውን በአሳዛኝ ሁኔታ በማውገዝ ያበቃሉ፡፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል እውነት ግን አይለወጥም፡፡ በዚህ የውሃና የመንፈስ ወንጌል ማመን ያለባቸው ለዚህ ነው፡፡
 
ነገር ግን አንዳንድ ሰዎች ‹‹ክህነቱ ሲለወጥ ሕጉ ደግሞ ሊለወጥ የግድ ነውና›› የሚለውን ከዕብራውያን 7፡12 በመጥቀስ ‹‹ሕጉም ተለውጦዋል፤ ስለዚህ ኢየሱስ የፈጸመው ደህንነት በብሉይ ኪዳን ባለው ተመሳሳይ ዘዴ መሰረት በትክክል አልተፈጸመም፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ መጥቶ በመስቀል ላይ በመሞት ብቻ አድኖን ዘዴውን አሻሽሎታል›› ይላሉ፡፡ ሌሎች ደግሞ ‹‹እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን ወደ ልጁ ያሻገረው ኢየሱስ በመስቀል ላይ በሞተ ጊዜ ይመስላል›› ይላሉ፡፡
 
ነገር ግን እነዚህ አባባሎች በሙሉ የተሳሳቱና መሰረት የሌላቸው ናቸው፡፡ ‹‹ታዲያ ይህ ማለት እግዚአብሄር ሐጢያት የሌለበትን ክርስቶስን በመስቀል የዓለምን ሐጢያቶች ወደ እርሱ ያሻገረው ያን ጊዜ ብቻ ነውን?›› ብለን በመጠየቅ አባባሎቻቸውን በቀላሉ መቃወም እንችላለን፡፡ በእግዚአብሄር ቃል ስናምን እንዳለ ልናምነው ይገባናል፡፡ የገዛ ራሳችንን አስተሳሰቦች የሙጥኝ ብለን መያዝ የለብንም፡፡ የራሳችን መከራከሪያዎች ቢኖሩንም እንኳን መጽሐፍ ቅዱስ እነዚህ መከራከሪያዎች የተሳሳቱ መሆናቸውን ከነገረን የራሳችንን ጽድቆች ሰብረን በእግዚአብሄር ቃል ማመን አለብን፡፡
 
ጊዜ ባለፈ ቁጥር ጌታ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እኛን የማዳኑ እውነታ ይበልጥ ተወዳጅና ክቡር ነው፡፡ በራሳችን አስተሳሰቦች ባመንን ጊዜ የእምነት ሕይወታችን አደጋ ላይ የወደቀባቸው ወቅቶች ነበሩ፡፡ ከቤተክርስቲያን ተለያይተን ልንቀር የነበርንበት ወቅትም አለ፡፡ ነገር ግን የመገናኛው ድንኳን ሁለቱ ማጋጠሚያዎች ከሁለቱ የብር እግሮች ጋር ተጋጥመው እያንዳንዱን ሳንቃ እንደደገፉት ሁሉ በጥምቀቱና ደሙን በማፍሰሱ ሐጢያቶቻችንን በወሰደው የኢየሱስ እውነት ላይ ያለንን እምነት አጽንቶ ደግፎናል፡፡ ጌታችን በዮሐንስ በመጠመቅና በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰስ ኩነኔያችንን በመሸከም ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አዳነን፡፡ ስለዚህ እምነታችን ለዘላለም አይናወጥም፡፡
 
ምሳሌ 25፡4 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ከብር ዝግተን አስወግድ፤ ፈጽሞም ይጠራል፡፡›› ይህ ምንባብ እንደሚናገረው በሥጋ አስተሳሰቦቻችን ውስጥ ብዙ የረከሱ፣ ክፉና የተበላሹ ነገሮች ብቅ ቢሉም ኢየሱስ በጥምቀቱና በደሙ ከእነዚህ የረከሱ ነገሮችና ከሰው ዘር ሐጢያቶች አንጽቶን የእግዚአብሄር የጽድቅ ሰራተኞች አድርጎናል፡፡ ጌታ ከዓለም ሐጢያቶች አንጽቶናል፡፡ ኢየሱስ በዮሐንስ ተጠምቆ ለአንዴና ለመጨረሻ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በመቀበል፣ በመሰቀልና ደሙንም በማፍሰስ የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ በሙሉ በመውሰድ ከዓለም ሐጢያቶች አንጽቶ አድኖናል፡፡
ስለዚህ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ የዘላለም ደህንነታቸው ተረጋግጦላቸዋል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ድርጊቶቻችን ያሳስቡን ይሆናል፡፡ ነገር ግን የብር እግሮቹ ሁለቱን ማጋጠሚያዎች በመያዝ እያንዳንዱን ሳንቃ እንደደገፉ ሁሉ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌልም እምነታችንን አጽንቶ ይይዛል፡፡
 
 
ደግፎ የያዘን ዘላለማዊው የደህንነት ጸጋ፡፡ 
 
አሁን ትኩረታችንን የመገናኛውን ድንኳን ሳንቃዎች አብረው ወደያዙት መወርወሪዎች ላይ እናድርግ፡፡ ዘጸዓት 26፡26-27 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ከግራርም እንጨት በማደርያው በአንድ ወገን ላሉት ሳንቆች አምስት መወርወሪያዎች፤ በማደርያውም በሁለተኛው ወገን ላሉት ሳንቆች አምስት መወርወርያዎች፤ በማደርያውም በስተኋላ በምዕራብ ወገን ላሉት ሳንቆች አምስት መወርወሪያዎች አድርግ፡፡›› የመገናኛው ድንኳን ሙሉ ቅርጽ አራት ማዕዘን ነበር፡፡ በመገናኛው ድንኳን በር ላይና ለቅድስተ ቅዱሳኑ መጋረጃ ምሰሶዎች ተደርገዋል፡፡ የቀረው ከሳንቃዎች የተሰራ ነበር፡፡ እነዚህ ሳንቃዎች በአምስት መወርወሪያዎች ታጥረዋል፡፡
 
በእያንዳንዱ ሳንቃ ላይ እነዚህን መወርወሪያዎች የሚይዙ አምሰት የወርቅ ቀለበቶች አሉ፡፡ መወርወሪያዎቹ ራሳቸውም ከግራር እንጨት ተሰርተው በወርቅ ተለብጠው ነበር፡፡ አምስቱ መወርወሪያዎች በሰሜን፣ በደቡብና በምዕራብ በሦስቱም የመገናኛው ድንኳን ወገን ባሉት ሳንቃዎች ተቀምጠው ነበር፡፡ ሳንቃዎቹ በወርቅ ቀለበቶቹ ውስጥ በሚያልፉት በእነዚህ መወርወሪያዎች የተያያዙ ስለነበሩ አብረው ተጣብቀዋል፡፡ ሳንቃዎቹ ከታች በብር እግሮች ስለተደገፉና በየጎናቸውም በአምስት መወርወሪያዎች በአንድ ላይ ስለተያያዙ ጽኑና ጥብቅ ሆነው ቆመው ነበር፡፡
 
48ቱ ሳንቃዎች በአምስት መወርወሪያዎች ዙሪያውን እንደታጠሩና እርስ በርሳቸው እንደተደገፉ ሁሉ የእግዚአብሄር ሕዝብም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ከእግዚአብሄር ጋር ተቆራኝተዋል፡፡ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን የውሃወንና የመንፈሱን የደህንነት ስጦታ የተቀበሉ አብረው የሚሰባሰቡባትና የእምነት ሕይወታቸውን የሚኖሩባት ስፍራ ናት፡፡ ኢየሱስ ለጴጥሮስ ቤተክርስቲያኑን በዓለት ላይ እንደሚመሰረት ነግሮታል፡፡ (ማቴዎስ 16፡18-19) ስለዚህ የሐጢያት ስርየትን በተቀበሉት በእነዚያ መሰባሰብ የእግዚአብሄር መንግሥት የሚመሰረትበት ስፍራ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ነች፡፡ እግዚአብሄር በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በገለጡት የኢየሱስ ሥራዎች ሙሉ በሙሉ ከዓለም ሐጢያቶች እንዳዳነን እያሳየን ነው፡፡
 
ዘጸዓት 26፡28 እንዲህ ይላል፡- ‹‹መካከለኛውም መወርወሪያ በሳንቆች መካከል ከዳር እስከ ዳር ይለፍ፡፡›› ይህ መካከለኛው መወርወሪያ በአንድ በኩል ያሉትን ሳንቃዎች በሙሉ በአንድ ጊዜ አጥብቆ ለመያዝ ረጅም ሆኖ ተሰርቶ ነበር፡፡ በሳንቃዎች መካከል ከዳር እስከ ዳር የሚያልፈው የዚህ የመካከለኛው መወርወሪያ ትርጉም ምንድነው? ትርጉሙ ጻድቃን እርስ በርሳቸው ሕብረት መፍጠራቸውና እምነታቸው እርስ በርስ የሚተላለፍ መሆኑ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር በጌታ በተሰጠው የውሃና የመንፈስ ወንጌል አማካይነት የተፈጸመውን ደህንነት በማመን በእምነት እርስ በርሳቸው ሊገናኙ ይችላሉ፡፡ ጻድቃን በእምነታቸው ዓይን ለዓይን ይተያያሉ፡፡ አብረውን ካሉት ቅዱሳን ወይም አገልጋዮች ጋር ተገናኝተን ከእነርሱ ጋር ሕብረት በምናደርግበት ጊዜ ሁሉ ይህ ዓይነቱ የልቦች መገናኘት ስሜት በተጨባጭ የሚሰማን ለዚህ ነው፡፡
 
 
‹‹አንድ እምነት፣ አንዲት ጥምቀት፣ አንድ ጌታ፡፡›› 
 
ወደ ኤፌሶን 4፡3-7 እንመለስ፡- ‹‹በሰላም ማሰርያ የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ትጉ፡፡ በመጠራታችሁ በአንድ ተስፋ እንደተጠራችሁ አንድ አካልና አንድ መንፈስ አለ፡፡ አንድ ጌታ፣ አንድ እምነት፣ አንዲት ጥምቀት ከሁሉ በላይ የሚሆን፣ በሁሉም የሚሰራ፣ በሁሉም የሚኖር አንድ አምላክ የሁሉም አባት አለ፡፡ ነገር ግን እንደ ክርስቶስ ጸጋ መጠን ለእያንዳንዳችን ጸጋ ተሰጠን፡፡›› ሐዋርያው ጳውሎስ የመንፈስን አንድነት በሰላም ማሰሪያ ለመጠበቅ እንድንተጋ ነግሮናል፡፡ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀሉ የተገኘውን የደህንነት ስጦታ ስንቀበል ሰላም ወደ ልቦቻችን ይመጣል፡፡ የሐጢያት ስርየትን ወደ ልቦቻችንን ስንቀበል ያን ጊዜ በክርስቶስ አንድ ቤተሰብ እንሆናለን፡፡ በአጭሩ አንድ አካል እንሆናለን፡፡
 
‹‹አንድ ጌታ፡፡›› እኛን ያዳነን ኢየሱስ ክርስቶስ አንድ ነው፡፡ ‹‹አንድ እምነት፡፡›› የምታምኑት ምንድነው? የምታምኑት በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጠው የኢየሱስ ውሃ፣ ደምና መንፈስ ነው፡፡ ‹‹አንዲት ጥምቀት፡፡›› ሐዋርያው ጳውሎስ በኢየሱስ ጥምቀት ላይ እንደገና ትኩረት አድርጓል፡፡ ለእኛ በእርሱ ጥምቀት ማመን ማለት በክርስቶስ ውስጥ መጠመቅና ክርስቶስን መልበስ ነው፡፡ (ገላትያ 3፡27) ‹‹አንድ አምላክ፡፡›› እግዚአብሄር አንድ ነው፡፡ ይህ አምላክ የራሱን ልጅ በመላክ አዳነን፡፡
 
እነዚህ ሁሉ ነገሮች በውሃው፣ በደሙና በመንፈሱ ላይ ያለውን አንድ እምነት ይጠቁማሉ፡፡ (1ኛ ዮሐንስ 5፡8) ልቦቻችን ከእርስ በርሳችን ጋር የሚገናኙት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ላይ እምነት ሲኖረን ነው፡፡ የሐጢያት ስርየትን የተቀበሉ እርስ በርሳቸው ዓይን ለዓይን መተያየት ይችላሉ፡፡ እርስ በርስ ፈጽሞ መስተዋዋል የማይችሉባቸው ጥቂት ወቅቶች ይኖሩ ይሆናል፡፡ ነገር ግን መካከለኛው መወርወሪያ ከዳር እስከ ዳር በሳንቃዎቹ መካከል እንዳለፈ ሁሉ ከልባቸው የሐጢያት ስርየትን በትክክል ተቀብለው ከሆነ ሁሉም እርስ በርሳቸው ሊስማሙ ይችላሉ፡፡ ‹‹ይህም ወንድም ደግሞ ከሐጢያት ድኖዋል፡፡ ነገር ግን ሥጋው ደካማ ነው፡፡ በልቡ ውስጥም ብዙ የሥጋ ቅሪቶች አሉ፡፡ እንደ ሌሎቹ ሁሉ እርሱም የክፉ አድራጊዎች ዘር ነው፡፡ ነገር ግን ጌታ አሁንም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ሐጢያቱን አስወግዶለታል፡፡›› እርስ በርስ ወደ መረዳዳትና ጌታን ወደ ማመስገን ይመጣሉ፡፡
 
ሰዎች ምንም ያህል ብቁዓን ባይሆኑም የሐጢያት ስርየትን ተቀብለው በቤተክርስቲያን ውስጥ ከቆዩ አስተሳሰቦቻቸው ይበራሉ፡፡ እርስ በርሳቸውም መስማማት ይችላሉ፡፡ ጻድቃን ዓይን ለዓይን መተያየት ይችላሉ፡፡ ይህንን እንዲቻል የሚያደርገው ምንድነው? እርስ በርሳቸው የሚተያዩት ከሌላ ሁኔታ የተነሳ ሳይሆን ከእምነት የተነሳ ነው፡፡ ታዲያ ከሌሎች ጋር እንዳንስማማ የሚያደርገንን ጉድለት የሚያብራራው ምንድነው? እኛ ልቦቻችንን በክርስቶስ ላልሆኑት ሰዎች መክፈት አንችልም፡፡ ምክንያቱም እነርሱ በልቦቻቸው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እውነት አያምኑም፡፡ በዚህ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የማያምኑ ከእኛ ጋር ፈጽሞ ሊስማሙ አይችሉም፡፡
 
ወንድሞችና እህቶች የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን በትክክል ምንድነች? እርስዋ በክርስቶስ ኢየሱስ ተቀድሰው ቅዱሳን ተብለው የሚጠሩ ስብስብ ነች፡፡ (1ኛ ቆሮንቶስ 1፡2) እርስዋ ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻቸውን ያስወገደላቸው፣ እነዚህን ሐጢያቶችና ኩነኔያቸውን ሁሉ በመስቀል ላይ ተሸክሞ ያዳናቸው፣ ዳግመኛም ከሙታን ተነስቶ የራሳቸው አዳኝ የሆነላቸው በመሆኑ እውነት የሚያምኑ ጉባኤ ናት፡፡ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን አንድ የሆኑ ሰዎች ስብስብ እንጂ ሌላ አይደለችም፡፡
 
በእርሱ ቤተክርስቲያን ውስጥ በምንገኝበት ጊዜ እርስ በርስ ዓይን ለዓይን መተያየት የምንችለው ይህ እምነት በእኔና በእናንተ ልቦች ውስጥ ስላለ ነው፡፡ እግዚአብሄር ሲያየን የሚመለከተው የውስጥ ልባችንን እንጂ ውጫዊ ገጽታችንን ስላልሆነ እኛም የሐጢያት ስርየትን የተቀበልን ውጫዊ ገጽታዎችን አንመለከትም፡፡ ነገር ግን የእያንዳንዳችንን የእምነት ማዕከል በመመልከት ሕብረት አለን፡፡ ‹‹ይህ ግለሰብ በእርግጥ እውነቱን በልቡ ያምናልን?›› የምንሻው ይህንን ነው፡፡ በማንነቱ ውስጥ ያለው ልዩነት ምንም ይሁን ‹‹በአንድ ጌታ፣ በአንድ እምነት፣ በአንዲት ጥምቀት፣ በአንድ አምላክና የሁሉ አባት›› በሆነው እስካመነ ድረስ ይህ ያን ያህልም ከቁም ነገር አይቆጠርም፡፡
 
እኛ ስለምናምን የመገናኛው ድንኳን ምሰሶዎችና ሳንቆች ሆነናል፡፡ ስለምናምን የእግዚአብሄር ቤተሰብ ሆነናል፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ታምናላችሁን? ንጹህ ወርቅ (እምነት) በእግዚአብሄር ቤት ውስጥ እንደሚያበራ ሁሉ የደህንነትን ብርሃን በመላው ዓለም የምናሰራጨው ስለምናምን ነው፡፡ በቅርቡ የሐጢያት ስርየትን ለተቀበሉት ብቻ ልቦቻችንን ማጋራት እንችላለን፡፡ ምክንያቱም መንፈስ ቅዱስ በእነርሱም ልቦች ውስጥ ያድራልና፡፡ የሐጢያት ስርየትን ከተቀበልን በኋላ ሁላችንም እርስ በርሳችን መስማማት እንችላለን፡፡ በውጫዊ ገጽታዎች ላይ በመመስረት በሰዎች ላይ አድልዎ የሚያደርጉ ሐጢያተኞች እርስ በርሳቸው የሚሞከሻሹት እንደ አመለካከት፣ ሐብት ወይም ዝና ባሉ ጥራዝ ነጠቅ ገጽታዎች ላይ በመመረኮዝ ነው፡፡ እኛ ጻድቃኖች ግን ይህንን በልቦቻችን ውስጥ አናደርግም፡፡ በጻድቃን ዘንድ አድልዎ የለም፡፡
 
ሰዎች የሐጢያት ስርየትን ለመጀመሪያ ጊዜ ሲቀበሉ ብዙውን ጊዜ ‹‹በእርግጥ የሐጢያት ስርየትን ተቀብላችኋልን? አሁንም ድረስ ሐጢየት አለባችሁ ወይስ ሐጢያቶቻችሁ በሙሉ ብን ብለው ጠፍተዋል? በነገራችን ላይ ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ብዙ ጥያቄዎች ያሉዋችሁ መሆን አለባችሁ፡፡ አይደለምን? በእምነት ሕይወታችሁ እየተጓዛችሁ ሳለ በጊዜው ጠይቁዋቸው፡፡ ድካሞቻችሁም እንዲሁ ይገለጣሉ፡፡ ምናልባትም በጉዞዋችሁ ላይ አንዳንድ ስህተቶች ትሰራላችሁ፡፡ ነገር ግን መሪዎችና በቤተክርስቲያን ውስጥ ከእናንተ ቀድመው እየሄዱ ስለሚረዱዋችሁ ሁሉም ነገር መልክ ይይዛል›› በማለት ይጠይቁዋቸዋል፡፡
 
ወንድሞችና እህቶች እኛ ጻድቃን የሆንን ቤተክርስቲያን ታስፈልገናለች፡፡ የመገናኛው ድንኳን ማለትም የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ማለት ነው፡፡ በውሃውና በደሙ የማያምኑ ወደ እግዚአብሄር ቤተክርስቲያን መጥተው በዚያ ሊኖሩ አይችሉም፡፡ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው የውሃና የመንፈስ ወንጌል የማያምኑ ወደ እግዚአብሄር ቤተክርስቲያን መግባትና በዚያ መኖር አይችሉም፡፡ በቤተክርስቲያን ውስጥ ሊኖሩና የእግዚአብሄርን ክብር ሊያዩ የሚችሉት በእውነት የሚያምኑ ብቻ ናቸው፡፡ ሰዎች የእግዚአብሄር ልጆች መሆን የሚችሉት በደም ብቻ ወይም በሥጋቸው ብቃት አይደለም፡፡ አንዳንድ መጋቢዎች ምንም ያህል የሥልጣን ጥመኞች ቢሆኑም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የማያምኑ ከሆኑ የእግዚአብሄር ልጆች አይደሉም፡፡
 
 

በውሃና በደም የመጣው ኢየሱስ ፈጽሞ አድኖናል፡፡ 

 
ጌታ ወደዚህ ምድር መጥቶ ያደረገው ነገር በውልደቱ፣ በጥምቀቱ፣ ባፈሰሰው ደሙና በትንሳኤው ሊጠቃለል ይችላል፡፡ እነዚህ ሁሉ የሐጢያት ስርየት አገልግሎቶች ናቸው፡፡ ኢየሱስ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ አገልግሎቶቹ ተልዕኮውን ፈጽሞዋል፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የተገለጡት ሰማያዊ፣ ሐምራዊና ቀይ ማጎች ከሐጢያት ለመዳን የሚያገለግሉ ነበሩ፡፡ የእግዚአብሄር ደህንነት በጣም የተብራራ በመሆኑ በራሳችን መንገድ በእርሱ ማመን አይኖርብንም፡፡ እንዳለ በእርሱ ደህንነት ማመን ይገባናል፡፡
 
እምነታችን ከሁለቱ የእርሱ የደህንነት እውነቶች ጋር በትክክል መስማማት ይኖርበታል፡፡ እነዚህ እውነቶች የእርሱ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ ናቸው፡፡ ሁለቱ ማጋጠሚያዎች በሁለቱ የብር ቀዳዳዎች ውስጥ በትክክል የገጠሙት ለዚህ ነው፡፡ ኢየሱስ የሰጠንን እውነት ከዓለም ዕውቀት እንደ አንዱ አድርገን በመቁጠር በዚያ መንገድ ብቻ ልናምንበት አይገባንም፡፡ እናንተና እኔ በሁለቱ የብር እግሮች በተገለጡት የኢየሱስ የደህንነት ሥራዎች በማመን በእግዚአብሄር ፊት ከሐጢያት ድነናል፡፡
 
የመገናኛው ድንኳን የኢየሱስን የተብራራ የደህንነት ዘዴ ይነግረናል፡፡ ይህ ደህንነትም አስቀድሞ በተጨባጭ ለእኛ ተፈጽሞልናል፡፡ እግዚአብሄር በሰጣችሁ በሁለቱ የደህንነት ስጦታዎች እመኑ፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ጥቅም ላይ የዋለው ወርቅ እምነትን ያመለክታል፡፡ በተጻፈው እውነት እንዳለ ብታምኑ ያን ጊዜ ደህንነትና የእግዚአብሄር ክብር የእናንተ ይሆናሉ፡፡ ካላመናችሁ ግን የእናንተ ሊሆኑ አይችሉም፡፡ የእግዚአብሄርን ክብር ለብሳችሁና በእርሱ ተጠብቃችሁ በእምነት በመገናኛው ድንኳን ውስጥ መኖር ትፈልጋላችሁ ወይስ አለማመናችሁን በመቀጠል ለዘላለም የተረገማችሁ መሆን ትፈልጋላችሁ? በመስቀል ላይ በፈሰሰው ደም ብቻ የምታምኑ ከሆነ ልትድኑ አትችሉም፡፡ የመስቀሉ ደምና ጥምቀት አንድ መሆናቸውን ማመን አለባችሁ፡፡ የእግዚአብሄር ስጦታ ከእነዚህ ከሁለቱ የተሰራ ነው፡፡
 
የእግዚአብሄር መንፈስ በልቦቻችን ውስጥ የሚያድረው በእነዚህ በሁለቱ ፍሬ ነገሮች (የኢየሱስ ጥምቀትና የፈሰሰው ደሙ) ስናምን ብቻ ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ በእነዚህ በሁለቱ በማያምኑ ልቦች ውስጥ ሊያደር አይችልም፡፡ እምነታችሁን በልቦቻችሁ ሳታምኑ በአንደበታችሁ ብቻ የምትናገሩት ከሆነ፤ ዕውቀታችሁም እንዲያው የአእምሮ ልምምድ ብቻ ከሆነ ፍጹም መዳን አትችሉም፡፡ ለመዳን አስቀድማችሁ የደህንነታችሁን ድንበሮች የሚለይ ግልጽ የሆነ መለያ መስመር ማስመር አለባችሁ፡፡ ‹‹እስካሁን ድረስ አልዳንሁም ነበር፡፡ ያመንሁበት ደህንነት እውነተኛ ደህንነት አልነበረም፡፡ ነገር ግን በውሃውና በደሙ በመጣው ኢየሱስ በማመን አሁን ድኛለሁ፡፡›› ሰዎች ጻድቃን መሆን የሚችሉት በመጀመሪያ ቢያንስ አንድ ጊዜ ሐጢያተኞች ሲሆኑ ብቻ ነው፡፡ ያልዳኑ በመሆናቸው ለሐጢያቶቻቸው ይኮነኑ ዘንድ የታጩ እንደነበሩና በዚያም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ፈጽመው እንደዳኑ መቀበል አለባቸው፡፡
 
የኢየሱስን ጥምቀትና ደም በሚያመለክቱት በሰማያዊውና በቀዩ ማግ አማካይነት ፍጹም የሆነውን ደህንነታችንን መቀበል አለብን፡፡ ጌታ በራሳችን አስተሳሰቦች ላይ ተመስርተን ከማመን ሊከላከለን ይህንን ደህንነት በመገናኛው ድንኳን አማካይነት በዝርዝር ገለጠልን፡፡ ይህ ደህንነት በጣም ክቡርና ፍጹም ስለሆነ እያንዳንዱ ሰው ሊያምንበት ይገባዋል፡፡ የደህንነቱ አንድ ክፍል በሆነው የመስቀል ላይ ደም ብቻ አትመኑ፡፡ ነገር ግን በአጠቃላይ በኢየሱስ ጥምቀትና ደም እመኑ! በመካከላችን ገና ያልዳነ ሰው ካለ አሁንም እንኳን በዚህ እውነት በማመን ይድን ዘንድ ልባዊ ተስፋዬ ነው፡፡
 
አሁንም ድረስ በኢየሱስ ደም ብቻ የሚያምን ሰው አለን? አሁንም ድረስ በዚህ ግማሽ ወንጌል የሚያምኑ ብዙ ክርስቲያኖች አሉ፡፡ የእኔ ተስፋ ግን እንዲህ ያለ የተሳሳተ እምነት ዳግመኛ ልቦቻችንን የማይወር መሆኑ ነው፡፡ ምንም ነገር ቢከሰት እኔ ያልዳኑት ቡድን አባል ልሆን አልችልም፡፡ እኛ በእነዚህ በሁለቱ ነገሮች (ሰማያዊና ቀይ ማግ) ማለትም በኢየሱስ ጥምቀትና ደም በማመን ፈጽመን ድነናል፡፡ ጌታ እኔን ስላዳነባቸው ስለ እነዚህ ሁለት የደህንነት ስጦታዎች እግዚአብሄርን አመስግነዋለሁ፡፡ እግዚአብሄር ደህንነቴን በሚገባ ስለፈጸመው ከእርግማኖችና ከፍርድ ቀድሞውኑም ድኛለሁ፡፡
 
በሰማያዊውና በቀዩ ማግ የተገኘው ደህንነታችን ቃላቶች ከሚገልጡት በላይ ክቡር መሆኑ እውነት ነው፡፡ ደህንነታችሁ ፍጹም የሆነው በመስቀሉ ደም ብቻ እንዳልሆነ በኢየሱስ ጥምቀትም ብቻ እንዳልሆነ ነገር ግን በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ደሙ በሁለቱም እንደሆነ ማስታወስና ማመን ይገባችኋል፡፡ የእግዚአብሄር ልጆች የምትሆኑት በእነዚህ በሁለቱ በማመን ነው፡፡ በመገናኛው ድንኳን ሳንቃዎች፣ በሁለቱ ማጋጠሚያዎችና በሁለቱ የብር እግሮች ውስጥ በተደበቀው ምስጢር በውሃውና በመንፈሱ የወንጌል ቃል በማመን የዘላለም ሕይወትን አግኝተናል፡፡
ከዓለም ሐጢያቶች ያዳነንን ጌታችንን አመሰግነዋለሁ፡፡ ሐሌሉያ!