Search

የመገናኛው ድንኳን ጥናት፤

የምስክሩ ታቦት

ተዛማጅ ስብከቶች

· በስርየት መክደኛው ላይ የሚቀርብ የሐጢያት ስርየት ቁርባን፡፡ ‹‹ ዘጸዓት 25፡10-22 ››

በስርየት መክደኛው ላይ የሚቀርብ የሐጢያት ስርየት ቁርባን፡፡
‹‹ ዘጸዓት 25፡10-22 ››
‹‹ከግራር እንጨትም ታቦቱን ይሥሩ፤ ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፣ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል፣ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል ይሁን፡፡ በውስጥና በውጭም በጥሩ ወርቅ ለብጠው፡፡ በእርሱም ላይ በዙሪያው የወርቅ አክሊል አድርግለት፡፡ አራት የወርቅ ቀለበቶችም አድርግለት፤ እነርሱንም በአራቱ እግሮቹ ላይ አኑር፤ በአንድ ወገን ሁለት ቀለበቶች በሌላው ወገን ሁለት ቀለበቶች ይሁኑ፡፡ መሎጊያዎቹንም ከግራር እንጨት ሥራ፤ በወርቅም ለብጣቸው፡፡ ለታቦቱ መሸከሚያ ከታቦቱ ጎን ባሉት ቀለበቶች መሎጊያዎቹን አግባ፡፡ መሎጊያዎቹም በታቦቱ ቀለበቶች ውስጥ ይኑሩ፤ ከቶም አይውጡ፡፡ በታቦቱም ውስጥ እኔ የምሰጥህን ምስክር ታስቀምጠዋለህ፡፡ ከጥሩ ወርቅም ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል የሆነ የስርየት መክደኛ ሥራ፡፡ ሁለት ኪሩቤል ከተቀጠቀጠ ወርቅ ሥራ፤ በስርየት መክደኛውም ላይ በሁለት ወገን ታደርጋቸዋለህ፡፡ ከስርየት መክደኛውም ጋር አንዱን ኪሩብ በአንድ ወገን ሁለተኛውንም ኪሩብ በሌላው ወገን አድርገህ በአንድ ላይ ትሠራዋለህ፡፡ ኪሩቤልም ክንፎቻቸውን ወደ ላይ ይዘረጋሉ፤ የስርየት መክደኛውንም በክንፎቻቸው ይሸፍናሉ፤ ፊታቸውም እርስ በርሳቸው ይተያያል፤ የኪሩቤልም ፊቶቻቸው ወደ ስርየት መክደኛው ይመለከታሉ፡፡ የስርየት መክደኛውንም በታቦቱ ላይ ታደርገዋለህ፤ እኔም የምሰጥህን ምስክር በታቦቱ ውስጥ ታኖረዋለህ፡፡ በዚያ ከአንተ ጋር እገናኛለሁ፤ የእስራኤልንም ልጆች ታዝዝ ዘንድ የምሰጥህን ነገር ሁሉ በምስክሩ ታቦት ላይ ባለው በሁለት ኪሩቤል መካከል በስርየት መክደኛው ላይ ሆኜ አነጋግርሃለሁ፡፡››
 
 

የስርየት መክደኛው፡፡ 

የስርየት መክደኛው፡፡
አንድ ክንድ ከእጅ ጣት እስከ ክርን ደረስ የተዘረጋ ርዝመት ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አንድ ክንድ በዛሬው መለኪያ 45 ሳንቲ ሜትር (1.5 ጨማ) ይገመታል፡፡ የስርየት መክደኛው ርዝመት ሁለት ክንድ ተኩል ነበር፡፡ ስለዚህ በሜትሪክ ስርዓት ሲለካ ይህ ርዝመት 3.7 ጫማ አካባቢ ነው፡፡ ወርዱም አንድ ተኩል ክንድ ሲሆን በግምት 2.2 ጫማ ነው፡፡ ይህ የስርየት መክደኛውን ጠቅላላ መጠን ይነግረናል፡፡
 
የምስክሩ ታቦት በመጀመሪያ ከግራር እንጨት ተሰርቶ በውስጥና በውጭ በወርቅ ተለብጦዋል፡፡ ነገር ግን በታቦቱ ላይ የተቀመጠው የስርየት መክደኛ የተሰራው ከንጹህ ወርቅ ነበር፡፡ በሁለቱም ጫፎቹ ክንፎቻቸውን ከበላዩ የዘረጉና የታቦቱን መክደኛ ማለትም የስርየት መክደኛውን የሸፈኑ ኪሩቤሎች ነበሩ፡፡ ኪሩቤሎቹ ወደ ስርየት መክደኛው ይመለከታሉ፡፡ የስርየት መክደኛው እግዚአብሄር በእምነት ወደ እርሱ በቀረቡት ላይ ጸጋውን የሚለግስበት ስፍራ ነው፡፡
 
በታቦቱ በእያንዳንዱ ማዕዘን ላይ አራት ቀለበቶች ተደርገዋል፡፡ ለእያንዳንዱ ወገን ሁለት የወርቅ ቀለበቶች ተደርገዋል፡፡ ታቦቱ ለሸክም እንዲመች በቀለበቶቹ ውስጥ መሎጊያዎች ገብተዋል፡፡ እነዚህ መሎጊያዎች ከግራር እንጨት ተሰርተው በወርቅ የተለበጡ ነበሩ፡፡ በአንዱ ወገን ባሉት ሁለት ቀለበቶች ውስጥ መሎጊያዎችን በማስገባት እግዚአብሄር ሁለት ሰዎች አንስተው ሊሸከሙት እንደሚችሉ አረጋግጠዋል፡፡ ጌታችን እንዲህ ብሎዋል፡- ‹‹በስርየት መክደኛው ላይ ሆኜ አነጋግርሃለሁ፡፡››
 
እግዚአብሄር በታቦቱ ውስጥ መሎጊያዎችን በማኖር የምስክሩን ታቦት ከስርየት መክደኛው ጋር አብረው እንዲሸከሙት እስራኤሎችን አዘዛቸው፡፡ ይህ ማለት እግዚአብሄር ወንጌል በመላው ዓለም እንድናሰራጭ ይፈልግብናል ማለት ነው፡፡ ለዕጣኑ መሰውያውም ይኸው ነገር እውነት ነው፡፡ ማለትም በሁለቱም ወገን ቀለበቶች ተደርገውለት ነበር፡፡ በእነዚህ ቀለበቶች ውስጥ መሎጊያዎች ይገቡና ሁለት ሰዎች መሰውያውን ይሸከሙታል፡፡ ይህም ደግሞ ችግሮች በሚገጥሙን ጊዜ ሁሉ እግዚአብሄርን መለመን ይገባናል ማለት ነው፡፡ በምንሄድበት ስፍራ ሁሉ ወንጌል በመላው ዓለም እንዲሰራጭም መጸለይ አለብን፡፡
 
በምስክሩ ታቦት ውስጥ ሦስት ቁሳ ቁሶች የተቀመጡ ሲሆን እነርሱም መናውን የያዘው የወርቅ ማሰሮ፣ ያበበችው የአሮን በትርና የኪዳኑ የድንጋይ ጽላቶች ናቸው፡፡ እነዚህ ምን ማለት ናቸው? በመጀመሪያ መናውን የያዘው የወርቅ ማሰሮ ኢየሱስ ክርስቶስ ለምዕመናን አዲስ ሕይወት እንደሚሰጥ ያመለክታል፡፡ እርሱ በአንድ ወቅት እንዲህ ሲል ተናግሮ ነበር፡- ‹‹የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ፤ ወደ እኔ የሚመጣ ከቶ አይራብም፤ በእኔ የሚያምንም ሁልጊዜ ከቶ አይጠማም፡፡›› (ዮሐንስ 6፡35)
 
ያበበችው የአሮን በትር ኢየሱስ ክርስቶስ የትንሳኤ ጌታና የዘላለም ሕይወት የሰጠን መሆኑን ትነግረናለች፡፡ የኪዳኑ የድንጋይ ጽላቶች እኛ በሕጉ ፊት ለሞት የተኮነንን መሆናችንን ይነግሩናል፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሄር ምህረት በጣም ትልቅ ስለሆነ ሕጉ የረገመውን የሐጢያቶቻንን ኩነኔ ሁሉ ሸፍኖዋል፡፡ የስርየት መክደኛው የሕጉ እርግማን አፈንግጦ እንዳይወጣ የታቦቱ ሽፋን ሆኖ ማገልገሉ በሚገባ ይገጥማል፡፡ እግዚአብሄር ፍጹም በሆነው የልጁ የኢየሱስ መስዋዕት የምህረት መክደኛውን አጠናቆታል፡፡ ስለዚህ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምን እያንዳንዱ ምዕመን የስርየት መክደኛ ወደሆነው ወደ ወደ እግዚአብሄር ዙፋን ፊት በድፍረት መቅረብ ይችላል፡፡
 
 
በስርየት መክደኛው ላይ የተረጨው ክቡር ደም! 
 
በመጀመሪያ በስርየት መክደኛው ውስጥ የተደበቀው ምስጢር ምን እንደሆነ ማወቅ አለብን፡፡ ሊቀ ካህኑ በዓመት አንድ ጊዜ የመስዋዕቱን ደም ይዞ ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ ይገባል፡፡ ከዚያም ይህንን የመስዋዕቱን ደም በትክክል ሰባት ጊዜ ያህል ይረጨዋል፡፡ እግዚአብሄር በዚህ ጊዜ እስራኤሎችን በዚህ የስርየት መክደኛው ላይ ይገናኛቸዋል፡፡ እግዚአብሄር ሊቀ ካህኑ ያለውን ዓይነት እምነት ማለትም በመስዋዕታዊው ስርዓት ውስጥ የተገለጠው የሐጢያት ስርየቱ እምነት ያለውን ማንኛውንም ሰው ይገናኘዋል፡፡
 
በስርየት መክደኛው ላይ የሚረጨው የመስዋዕቱ ደም እግዚአብሄር በሐጢያት ላይ ያለውን ቅን ፍርድና ለሰው ዘር የሚሰጠውን ምህረት ያሳያል፡፡ በሰባተኛው ወር በአስረኛው ቀን ላይ የሚውለው የስርየት ቀን ሊቀ ካህኑ አሮን የእስራኤልን ሕዝብ ዓመታዊ ሐጢያቶች በሙሉ ለማሻገር እጆቹን በመስዋዕቱ ቁርባን ላይ ይረጫል፡፡ ከዚያም ያርደውና ደሙን ይወስዳል፡፡ ከዚያም ይህንን ደም ወደ መጋረጃው ውስጥ በማስገባት በስርየት መክደኛው ላይ ይረጨዋል፡፡ (ዘሌዋውያን 16፡11-16)
 
በዚህ ሁኔታ በተረጨው ደም አማካይነት እግዚአብሄር እስራኤሎችን ተገናኝቶ የሐጢያት ይቅርታን በረከት ሰጥቶዋቸዋል፡፡ እግዚአብሄር የመስዋዕቱን ስርዓት ያቋቋመው በእስራኤሎች ላይ ካለው ጸጋ የተነሳ ነበር፡፡ እግዚአብሄር በመስዋዕት እንስሳውና በደሙ ላይ በሚከናወነው እጆችን መጫን አማካይነት ሐጢያቶቻቸውን በጽድቅ ደምስሶ በጸጋው ምህረቱን ማለትም የሐጢያታቸውን ስርየት ሰጣቸው፡፡
 
ታዲያ ይህንን ጸጋ መቀበል የምንችለው እንዴት ነው? እግዚአብሄር ለአንዴና ለመጨረሻ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ የደመሰሰው በምን ቃል ነው? እግዚአብሄር ለእኛ የለገሰውን ስጦታ መቀበል እንችል ዘንድ በመስዋዕቱ ስርዓት የተገለጠውን እውነት የሚያውቅና የሚያምን እምነት ሊኖረን እንደሚገባ እንድናውቅ አስችሎናል፡፡ እግዚአብሄር ጽድቁ በእነዚህ ሁለት ጉዳዮች እንዲፈጸም አስችሎዋል፡፡ እነርሱም እጆችን በመስዋዕቱ ላይ መጫንና የመስዋዕቱ ደም ናቸው፡፡ ይህ የብሉይ ኪዳን መስዋዕት የሚያመለክተው ኢየሱስ የተቀበለውን ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰውን ደሙን እንጂ ሌላ ነገርን አይደለም፡፡
 
የእግዚአብሄር ልጅ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለምን ሐጢያቶች ለመውሰድ በዮሐንስ ተጠመቀ፤ የእነዚህን ሐጢያቶች ዋጋ ለመክፈልም በመስቀል ላይ መስዋዕት ሆኖ ስለ እኛ ሞተ፡፡ እኛን ሕያው ለማድረግም ዳግመኛ ከሙታን ተነሳ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የተቀበለው ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ የሐጢያት ይቅርታን የሚሰጡን ነበሩ፡፡ እነዚህ እግዚአብሄርን ለመገናኘት እንዲህ ያለ እምነት ያላቸው ሰዎች እውነተኛ በረከቶች የሚገኝበትን ጸጋ እንዲቀበሉ ያስችሉዋቸዋል፡፡ ይህ እውነት የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ጥላ ነው፡፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ሐጢያተኞች የሐጢያት ስርየትን ከእግዚአብሄር ያገኙ ዘንድ የሚያስችላቸውን የእውነተኛ እምነት መሰረት የጣለ እውነት ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐጢያቶቻችን የመስዋዕት ቁርባን ሆንዋል፡፡ ቅዱስ አባት ወደሆነው እግዚአብሄር እንድንቀርብ የሚፈቅድልን የእውነት ድልድይ ሆንዋል፡፡
 
እንደገናም ለመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ጥቅም ላይ በዋሉት በአራቱ ማጎች ቀለማት ማለትም ሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግና ጥሩ በፍታ ውስጥ ለዚህ እውነት አሳማኝ የሆነ ማስረጃ ማግኘት እንችላለን፡፡ በሌላ አነጋገር በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ላይ ያሉት አራቱ ማጎች ስለ እውነተኛው ወንጌል ፍንጮችን ይሰጡናል፡፡
 
የመጀመሪያው ፍንጭ በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ላይ የተገለጠው የሰማያዊው ማግ ምስጢር ነው፡፡ ይህም ምስጢር ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ መጠመቁ ማለትም የዓለምን ሐጢያቶች መውሰዱ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ጌታችን ዮሐንስ ያስረከበውን ሐጢያቶቻችንን ተቀበለ፡፡ ‹‹አሁንስ ፍቀድልኝ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና›› (ማቴዎስ 3፡15) በማለት ዮሐንስን እንዲያጠምቀው የለመነው ለዚህ ነው፡፡
 
ሁለተኛው ፍንጭ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የተገለጠው ሐምራዊው ማግ ነው፡፡ ‹‹ሐምራዊ›› ቀለም የንጉሥ ቀለም ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ዘር ከሐጢያት ለማዳን የእነርሱ አዳኝ ሆኖ ወደዚህ ምድር የመጣ የነገሥታት ንጉሥ ነው፡፡ እርሱ ሐጢያቶቻንን ለመደምሰስ የሰማይን ክብር ትቶ ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በባህርይው ራሱ አምላክ ነው፡፡ ነገር ግን እኛን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ለማዳን በመታዘዝም ተሰቀለ፡፡ በሌላ አነጋገር ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ለመደምሰስ እግዚአብሄር በሰማይ ያለውን የክብር ዙፋን ትቶ ሐጢያተኞችን ለማዳን በዚህ ምድር ላይ ከድንግል ማርያም ሥጋ ተወለደ፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር ራሱ ከ700 ዓመታት በፊት ለነቢዩ ኢሳይያስ በሰጠው ተስፋ መሰረት ከድንግል ማርያም ሥጋ መወለድ፣ መጠመቅና ደሙንም በመስቀል ላይ ማፍሰስ ነበረበት፡፡
 
ሦስተኛው ፍንጭ ቀዩ ማግ ነው፡፡ ይህም የኢየሱስን ደም ያመለክታል፡፡ ይህ እውነት ኢየሱስ ደሙን በመስቀል ላይ በማፍሰስ የእግዚአብሄርን የደህንነት ተልዕኮ እንዳጠናቀቀ ይገልጣል፡፡ በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ ከወንጀለኞች ሁሉ እጅግ ክፉ ለሆነው ሰው የተዘጋጀ ቅጣት ነበር፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ አማካይነት በተሸከመው የሐጢያቶች ቅጣት የሰው ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ውሳኔ አግኝተዋል፡፡ እርሱ በመስቀል ላይ በመሰቀልና ደሙን በማፍሰስ የዓለምን ሐጢያቶች ኩነኔ በሙሉ በመሸከም ከሐጢያት አድኖናል፡፡ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን ከዮሐንስ በመቀበልና አብንም እስከ ሞት ድረስ በመታዘዝ እግዚአብሄር ሐጢያተኞችን ሁሉ ከሐጢያቶቻቸው አድኖዋቸዋል፡፡
 
ኢየሱስ በስቅለት ቅጣቱ የገዛ ራሳችንን ቅጣት በይፋ በመሸከም የሐጢያትን ኩነኔ በሙሉ አስወግዶ ምዕመናንን የእግዚአብሄር ልጆች እንዳደረጋቸው ተረድታችኋልን? እግዚአብሄር እነዚህን ነገሮች ሁሉ ያደረገው በዚህ እውነት አምነን የዘላለም ሕይወትን እንድናገኝ ነው፡፡ ኢየሱስ በመጠመቁና በመስቀል ላይ በመሞቱ ከሐጢያት አድኖናል፡፡ የመጨረሻ እስትንፋሱን ሲሰጥ ‹‹ተፈጸመ!›› (ዮሐንስ 19፡30) ብሎ የጮኸው ለዚህ ነው፡፡ ኢየሱስ በእግዚአብሄር አብ ፈቃድ መሰረት የሐጢያታችንን ደህንነት ማጠናቀቁን በታላቅ ደስታና እፎይታ አወጀ፡፡
 
በመጨረሻም ጥሩው በፍታ ኢየሱስ የእግዚአብሄር ቃል እንደሆነ ያመለክታል፡፡ እርሱ በተብራራውና ጻድቅ በሆነው ቃሉ አማካይነት የእግዚአብሄርን ቃል ገልጦዋል፡፡ በመላው አዲስ ኪዳን ውስጥ ወደዚህ ዓለም መጥቶ በጥምቀቱና በስቅለቱ የሰውን ዘር ሁሉ እንደሚያድን አስቀድሞ ተናግሮዋል፡፡ ከዚያም በአዲስ ኪዳን ውስጥ ተስፋዎቹን ሁሉ በሚገባ ፈጸመ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ የሚለው ለዚህ ነው፡- ‹‹በመጀመሪያው ቃል ነበረ፤ ቃልም በእግዚአብሄር ዘንድ ነበረ፡፡ ቃልም እግዚአብሄር ነበረ፡፡…ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ፡፡ አንድ ልጅም ከአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የሆነውን ክብሩን አየን፡፡›› (ዮሐንስ 1፡1,14)
 
ይህ እውነት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንደ በረዶ ነጭ እንዲሆኑ አስችሎናል፡፡ ኢየሱስ የተቀበለው ጥምቀትና ያፈሰሰው ደሙ በመስዋዕት ስርዓቱ ላይ የሚጫኑትን እጆችና የስርየቱን ፍርድ የሚያመለክቱ ናቸው፡፡ ኢየሱስ መስቀል ላይ ደሙን ያፈሰሰው የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በሥጋው ስለተሸከመ ነበር፡፡ ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በእኛ ፋንታ ለመሸከም ተጠመቀ፤ ወደ መስቀል ሄደ፤ እዚያም ደሙን አፈሰሰ፡፡ ሐጢያቶቻችንን ያስወገደው ስርየት እንግዲህ ይህ እውነት ነው፡፡
 
ጌታችን ሰው ሆኖ ወደዚህ ምድር በመምጣት የተቀበለው ጥምቀትና በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ ውስጥ የተገለጠ እውነት ናቸው፡፡ ኢየሱስ ከ2,000 ዓመታት በፊት በዚህ ምድር ላይ ተወለደ፤ በጥምቀቱም የዓለምን ሐጢያቶች ወሰደ፤ በመስቀል ላይ ሞተ፤ በሦስት ቀናት ውስጥም ዳግመኛ ከሙታን ተነሳ፡፡ ከዚያ በኋላም ለ40 ቀናት መሰከረ፡፡ ከዚያም በእግዚአብሄር ዙፋን ቀኝ አረገ፡፡ ይህ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ ውስጥ የተገለጠ እውነት ነው፡፡ እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን በመደምሰስ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ባዳነን በዚህ እውነት እንድናምን እየነገረን ነው፡፡
 
በዚህ እውነት ስናምን እግዚአብሄር እንዲህ ይለናል፡፡ ‹‹አሁን የእኔ ልጆች ሆናችኋል፤ እናንተ ሕዝቤ ናችሁ፡፡ ከሐጢያቶቻችሁ፣ ከኩነኔና ከእርግማኖች ሁሉ አድኛችኋለሁ፡፡ ወሰን በሌለው ፍቅሬ አድኛችኋለሁ፡፡ እናንተ በእኔ ዘንድ በጣም ተወዳጅ ስለሆናችሁ ያለ አንዳች ቅድመ ሁኔታ አድኛችኋለሁ፡፡ ስለምወዳችሁ በራሴ ፈቃድ አድኛችኋለሁ፡፡ እኔ የወደድኋችሁ ብቻ ሳይሆን በዚህ መንገድ ለእናንተ ያለኝን ፍቅር አሳይቻለሁ፡፡ የመስዋዕቴን ደም ተመልከቱ፡፡ እኔ ለእናንተ ስላለኝ ፍቅር ማስረጃው ይህ ነው፡፡ ይህንን ማስረጃ አሳይቻችኋለሁ፡፡››
 
በመንፈስ ድሆች ሆነን ወደ ጌታ በቀረብን ጊዜ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ እንዳዳነን አሳየን፡፡ ጌታ ወደዚህ ምድር መጥቶ ተጠመቀ፤ ተናቀ፤ በመስቀል ላይም ሞተ፡፡ ዳግመኛም ከሙታን ተነስቶ ወደ ሰማይ አረገ፡፡ እግዚአብሄር በእርሱ የደህንነት ፍቅር የሚያምነውን ሁሉ ይገናኘዋል፡፡
 
እግዚአብሄር ጸጋውን ለሚያምኑ ለግሶዋል፡፡ የእርሱ ደህንነት ተራ ፍጥረቶችን ወደ እግዚአብሄር ልጅነት ለውጦዋቸዋል፡፡ እግዚአብሄር እንዲህ እያለን ነው፡- ‹‹አሁን እናንተ ልጆቼ ናችሁ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆቼ ናችሁ፡፡ እናንተ ከእንግዲህ ወዲህ የሰይጣን ልጆች አይደላችሁም፡፡ የራሴ ልጆች ናችሁ፡፡ እናንተ ከእንግዲህ ወዲህ ፍጡራን ሳትሆኑ የራሴ ሕዝብ ናችሁ፡፡ በልጄ በኢየሱስ አማካይነት ሐጢያቶቻችሁን ሁሉ አስተሰርያለሁ፡፡ አሁን የራሴ ሕዝብ አድርጌያችኋለሁ፡፡ እናንተም በእምነት ሕዝቤ ሆናችኋል፡፡››
 
እግዚአብሄር በመገናኛው ድንኳን ውሰጥ ያለውን የምስክሩን ታቦት መክደኛ የስርየት መክደኛ ብሎ ጠርቶታል፡፡ ወደ እርሱ የሚመለከቱ ሁለት ኪሩቤሎችም አስቀምጦዋል፡፡ እግዚአብሄር የእስራኤልን ሕዝብ ከስርየት መክደኛው በላይ እንደሚገናኛቸው የተናገረው ለምንድነው? ለዚህ ምክንያቱ እግዚአብሄር ሐጢያቶቻቸው በሙሉ በእጆች መጫን የተሻገረበትን የመስዋዕት እንስሳ ደም በመቀበል የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች ስላስቀረ ነው፡፡
 
በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር እንዲህ ያለው እጆቻቸውን በራሱ ላይ ጭነው ሐጢቶቻቸውን ለመሰዋዕት ባቀረቡት እንስሳ ላይ በማሻገርና ይህ ለመስዋዕት የቀረበው እንስሳ በእነርሱ ፋንታ የእነዚህን ሐጢያቶች ዋጋ በመክፈል የሐጢያቶቻቸውን ስርየት በስጦታ መልክ ለእስራኤል ሕዝብ ለመስጠትና የሕዝቡን ሐጢያቶች በሙሉ ለመደምሰስ ስለፈለገ ነው፡፡ እግዚአብሄር ለስርየት ከሚቀርበው መስዋዕት ውጪ ሐጢያተኞችን መገናኘት ስለማይችል ሐጢያቶቻቸውን የደመሰሰውና የተገናኛቸው በዚህ የመስዋዕት ቁርባን አማካይነት ነው፡፡
 
ሰው ሁሉ ወደዚህ ዓለም በሐጢያት የተወለደው የአዳም ዘር ሆኖ ነው፡፡ ስለዚህ ሰው ሁሉ ሐጢያት አለበት፡፡ ማንም ያለ መስዋዕት እግዚአብሄርን መገናኘት አይችልም፡፡ እግዚአብሄር የእስራኤሎችን ሐጢያቶች ያስተሰረየውን መስዋዕት እንደሚቀበልና ከስርየት መክደኛው በላይ እንደሚገናኛቸው የተናገረው ለዚህ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር የእስራኤል ሕዝብ ሰባተኛውን ወር አስረኛውን ቀን የስርየት ቀን አድርገው እንዲለዩት አደረገ፡፡ ሊቀ ካህኑም የዓመቱን የእስራኤሎች ሐጢያቶች ወደ መስዋዕቱ እንስሳ ላይ እንዲያሻግርና ይህንን የመስዋዕቱን ደም ለእርሱ እንዲያቀርብለት አደረገ፡፡ በዚያው ቀን የእስራኤል ሕዝብ ሐጢያቶች ለአንድ ዓመት ያህል ይወገዳሉ፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት በዚህ ቀን ሊቀ ካህኑ በእነርሱ ፋንታ መስዋዕት ስላቀረበ ነው፡፡
 
 
ሐጢያተኞች ከሐጢያቶቻቸው የሚድኑበት የብሉይ ኪዳን የመስዋዕት ስርዓት፡፡
 
ዘሌዋውያን 1፡4 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እጁንም በሚቃጠለው መስዋዕት ራስ ላይ ይጭናል፡፡ ያስተሰርይለትም ዘንድ የሰመረ ይሆንለታል፡፡›› እጆቹን በመስዋዕቱ ራስ ላይ በመጫን የሐጢያተኛው ሐጢያቶች በሙሉ በተጨባጭ ወደሚለቀቀው ፍየል ይተላለፋሉ፡፡ እግዚአብሄር ከልብ በቃሉ ከሚያምን እምነት የቀረቡ ቁርባኖችን በደስታ ይቀበላል፡፡ ይህ እግዚአብሄር ሕዝቡ ለሆኑት እስራኤሎች ላቋቋመው የመስዋዕት ስርዓት መሰረታዊውና የመጀመሪያው እርምጃ ይህ ነው፡፡
 
ከዚያም ግለሰቡ መስዋዕቱን ያርድና ደሙን ያፈስሰዋል፡፡ ይህንንም ደም ለካህናቱ ያቀርባል፡፡ ከዚያም ካህናቱ ይህንን ደም መስዋዕት በሚቀርብበት መሰውያ ቀንዶች ላይ ይቀባሉ፡፡ ሥጋውንም በመሰውያው ላይ አስቀምጠው ያቃጥሉታል፡፡ በዚህም ይህንን ለሐጢያተኛው ሐጢያቶች የመስዋዕት ቁርባን አድርጎ ለእግዚአብሄር ያቀርበዋል፡፡ ይህ እግዚአብሄር በተጨባጭ የእያንዳንዱን ሐጢያተኛ ሐጢያቶች ለማስቀረት ያቋቋመው የደህንነት ሕግ ነበር፡
 
ነገር ግን የስርየት ቀን በሆነው በሰባተኛው ወር አስረኛ ቀን እግዚአብሄር ሕዝቡ ዓመቱን ሙሉ የሰሩዋቸውን ሐጢያቶች ማስቀረት ይችሉ ዘንድ መስዋዕት እንዲያቀርቡ ፈቅዶላቸዋል፡፡ በዚያች ቀን የመላው እስራኤሎች ወኪል የሆነው ሊቀ ካህኑ ሁለት ፍየሎችን ማዘጋጀት ነበረበት፡፡ ‹‹አሮንም በሁለቱ ፍየሎች ላይ ዕጣ ይጥልባቸዋል፡፡ አንዱን ዕጣ ለእግዚአብሄር ሌለውንም ዕጣ ለሚለቀቀቅ፡፡ አሮንም የእግዚአብሄር ዕጣ የሆነበትን ፍየል ያቀርባል፡፡ ስለ ሐጢያትም መስዋዕት ያደርገዋል፡፡›› (ዘሌዋውያን 16፡8-9) እስራኤሎች ዓመቱን በሙሉ የሰሩዋቸው ሐጢያቶች ሁሉ ወደ መስዋዕቱ ይሻገሩ ዘንድ በመጀመሪያው ፍየል ራስ ላይ እጆቹን ይጭናል፡፡ ከዚያም ያርደውና ደሙን ወስዶ ወደ ቅድስተ ቅዱሳን በመግባት በምሥራቅ ወገን ባለው የስርየት መክደኛ ላይ ደሙን በጣቱ ይረጫል፡፡ በስርየት መክደኛው ፊትም ደሙን ሰባት ጊዜ ይረጨዋል፡፡ እግዚአብሄርም ይህንን የመስዋዕቱን ቁርባን ደም በመቀበል ሐጢያቶቻቸውን በማስወገድ የራሱ ሕዝብ አድርጎ ይቀበላቸዋል፡፡
 
ከዚህ በኋላ ሊቀ ካህኑ ከመገናኛው ድንኳን ይወጣና ሌላውን ፍየል በእስራኤል ሕዝብ ፊት ያቀርበዋል፡፡ የሕዝቡን ሐጢያቶች በተጨባጭ ለማሻገርም እጆቹን እንደገና ለመስዋዕት በቀረበው ፍየል ራስ ላይ ይጭናል፡፡ ከዚያም ‹‹ሕዝቤ ባለፈው አንድ ዓመት የፈጸሙትን ሐጢያቶች በሙሉ በዚህ መስዋዕት ላይ አሻግራለሁ፡፡›› በማለት ያውጃል፡፡ ከዚህ በኋላ መስዋዕቱን በቁ በሆነ ሰው እጅ ወደ ምድረ በዳ ይሰድደዋል፡፡
 
ይህ ፍየል ይሞት ዘንድ እልም ወዳለ ምድረ በዳ ይሰደዳል፡፡ (ዘሌዋውያን 16፡20-22) ይህም የእስራኤል ሕዝብ ሐጢያቶች በስርየት ቀን በቀረቡት የሐጢያት መስዋዕቶች ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ሙሉ በሙሉ መወገዳቸውን ይነግረናል፡፡
 
እነዚህ የሚለቀቁ ፍየሎች የሚያመለክቱት ኢየሱስን ነው፡፡ ይህ የሐጢያት መስዋዕት ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ በመጠመቅና በዚህ ዓለም ላይ የሚኖረውን የእያንዳንዱን ሰው ሐጢያቶች ለመደምሰስ በመስቀል ላይ በመሰቀል የፈጸመውን የደህንነት እውነት ይገልጣል፡፡ እግዚአብሄር የእስራኤል ሕዝብ በሊቀ ካህኑ አማካይነት ተገቢ የሆነውን መስዋዕት በሚያቀርብበት ጊዜ ከስርየት መክደኛው በላይ እንደሚገናኛቸው ቃል ገብቷል፡፡ የእስራኤል ሕዝብ ሊቀ ካህኑንና የስርየት መክደኛውን ክቡር ነገር አድርገው ይመለከቱዋቸዋል፡፡ ምክንያቱም በየዓመቱ በእነርሱ ምትክ የሐጢያት መስዋዕት የሚያቀርበው ሊቀ ካህኑ ሲሆን የስርየት መክደኛው ደግሞ ሐጢያቶች ይቅር የሚባሉበት ቦታ ነበርና፡፡
 
ልክ እንደዚሁ ኢየሱስ በጥምቀቱና ባፈሰሰው ደሙ አማካይነት ለሐጢያቶቻችን አንድን መስዋዕት ለዘላለም አቅርቦ ከእግዚአብሄር ጋር አስታርቆናል፡፡ ለጌታ ኢየሱስ በቂ ምስጋና መስጠት ያልቻልነው ለዚህ ነው፡፡ በጥምቀቱና በስቅለቱም ማመን ያለብን ለዚህ ነው፡፡
 
 
የስርየት መክደኛው በምስክሩ ታቦት ውስጥ ያሉትን የአስርቱን ትዕዛዛት ሁለቱን የድንጋይ ጽላቶች አትሞዋል፡፡ 
 
እግዚአብሄር በሲና ተራራ ላይ አስርቱ ትዕዛዛት የተጻፉባቸውን ሁለቱን የድንጋይ ጽላቶች በምስክሩ ታቦት ውስጥ አስቀምጦ ታቦቱን በስርየት መክደኛው እንዲከድነው ሙሴን አዘዘው፡፡ እግዚአብሄር እንዲህ ያደረገው የምህረት ፍቅሩን ለእስራኤል ሕዝብ ለመለገስ በመፈለጉ ነው፡፡ ምክንያቱም እነርሱ ሕጉን መጠበቅ አልቻሉምና፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር የሐጢያት ደመወዝ ሞት መሆኑን ያወጀው ጻድቅ በሆነው ሕጉ ላይ በየቀኑ ሐጢያት ከሚሰራው የእስራኤል ሕዝብ ጋር መስማማት ባለመቻሉ ነበር፡፡ ይህም ደግሞ ለእስራኤል ሕዝብ የሐጢያት ስርየትን ለመስጠት ነው፡፡
 
በሌላ አነጋገር የእስራኤል ሕዝብ በምግባሮቻቸው የእርሱን ሕግ ለመጠበቅ በእግዚአብሄር ፊት በጣም ደካሞች ነበሩ፡፡ በመስዋዕቱ ቁርባን አማካይነት እነርሱን ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ማንጻት ያስፈልግ ነበር፡፡ ይህም እግዚአብሄር የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች ለመደምሰስ እጆቻቸውን በእርሱ ላይ በመጫንና በምትካቸው በማረድ ሐጢያቶቻቸውን ወደ መስዋዕቱ ያሻግሩ ዘንድ እንደጠየቃቸው ያሳያል፡፡ እግዚአብሄር ለእስራኤል ሕዝብ ቅን ቁጣውን ከሚገልጠው ሕግ ጋር አብሮ የደህንነት ፍቅሩን የሚያሳየውን ሕጉን ሰጣቸው፡፡ ስለዚህ እኛም በሁለቱ ወሳኝ የእግዚአብሄር የደህንነት እውነቶች ማለትም መሲሁ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ ማመን ያስፈልገናል፡፡
 
በብሉይ ኪዳን ውስጥ ለሐጢያት ቁርባን የሚቀርበው መስዋዕት በአዲስ ኪዳን የመሲሁን ሥጋ ያመለክታል፡፡ በቅዱሳት መጽሐፍት ውስጥ የተሰጡን መስዋዕቶች ሐጢያቶቻችንን በሙሉ የሚደመስሱና የእግዚአብሄርን የምህረት ፍቅር የሚገልጡ ነበሩ፡፡ ዛሬም እንደ ቀድሞው ሐጢያቶቻችን እንዲወገዱ የስርየት መስዋዕት ፈጽሞ ያስፈልገናል፡፡ ከረጅም ዘመን ጀምሮ የሰውን ዘር ሐጢያቶች ለመደምሰስ የእግዚአብሄር ፍትህና የምህረት ፍቅሩ መኖር አለባቸው፡፡
 
ሐጢያት ስንሰራ የእግዚአብሄር ፍትህ ሊጠይቀን ስለሚገባ ሐጢያቶቻችንን ወደ ሐጢያት መስዋዕቱ በማሻገር ማስወገድ ይገባናል፡፡ በኮርያ አንድ አባባል አለ፡- ‹‹ሐጢያተኞችን ሳይሆን ሐጢያትን ጥላ፡፡›› እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን ይጠላል፡፡ ነፍሶቻችንን ግን አይጠላም፡፡ እግዚአብሄር የነፍሶቻችንን ሐጢያት ይደመስስ ዘንድ እጆቻችንን በመስዋዕቱ ላይ መጫን፣ ደሙን ማፍሰስና ለእርሱ ማቅረብ አስፈልጎናል፡፡ በብሉይ ኪዳን እግዚአብሄር የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች አስተሰርዮዋል ማለት ያቀረቡትን መስዋዕት ተቀብሎ ሐጢያቶቻቸውን አስወግዶዋል ማለት ነው፡፡
 
ለእስራኤል ሕዝብ ብቸኛው ሕግ አውጪ እግዚአብሄር ነበር፡፡ ራሱን በእስራኤል ሕዝብ ፊት የገለጠው ያህዌህ በራሱ የሚኖር አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሄር ብቸኛው ሕግ አውጪ መሆኑን እንደምንረዳ ሁሉ እርሱ የሁላችንም አምላክ መሆኑንም መገንዘብና ሐጢያቶቻችንን ለመደምሰስ ያቋቋመውን የመስዋዕት ስርዓትም መቀበል ይገባናል፡፡ እግዚአብሄር ባቋቋመው የመስዋዕት ስርዓት አማካይነት ምን ያህል እንደወደደንና እንዴት በጽድቅ ከሐጢያት እንዳዳነን መረዳት መቻል አለብን፡፡ በእግዚአብሄር ሕግ አማካይነትም ምን ያህል ትዕዛዛቶችን መጠበቅ እንደማንችል መገንዘብ ችለናል፡፡ በመሰረታዊ እምነቶቻችን በእግዚአብሄር ፊት ሁሉንም ዓይነት ሐጢያቶችና መተላለፎች እየሰራን ያለን ጣዖት አምላኪዎች ነበርን፡፡ ስለዚህ በማንኛውም ጊዜ በሐጢያቶቻችን የተነሳ ለሲዖል የታጨን እንደሆንን ከማመን በስተቀር የምናደርገው ነገር ሊኖር አይችልም፡፡ እግዚአብሄር ራሱ አዳኛችን ሆኖ መምጣት የነበረበት ለዚህ ነው፡፡
 
ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋውን ለዓለም ሐጢያቶች መስዋዕት አድርጎ ለዘላለም ሰጥቶዋል፡፡ እርሱ ራሱን የሰጠው በብሉይ ኪዳን ዘመን ይቀርብ የነበረው መስዋዕት በሚቀርብበት በተለይም ስለ ስርየት ቀን በሚናገረው ምንባብ ላይ በቀረበው ማለትም በመስዋዕቱ ራስ ላይ እጆች ተጭነው ደሙ በሚፈስበት ተመሳሳይ መንገድ ነበር፡፡ በምስክሩ ታቦት ውስጥ ያሉት ሁለቱ የድንጋይ ጽላቶችና የስርየት መክደኛው የእስራኤል ሕዝብ የሐጢያቶቻቸውን ስርየት ይቀበሉ ዘንድ በጣም አስፈላጊ ነበሩ፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሄር ቅን በሆነው የአምላክ ሕግና በሕይወት ተሰፋው ያመኑት አዲስ ሕይወትን እንዲቀበሉ አስችሎዋቸዋልና፡፡ ዛሬ የእግዚአብሄርን ፍትህ የሚያሳየው ሕግና ከሐጢያት የሚያድነው ዘላለማዊው ደህንነት የእስራኤል ሕዝብ ብቻ ሳይሆን ሁላችንም እግዚአብሄርን እንድንገናኝና የዘላለምን ሕይወት እንድንቀበል አስችሎናል፡፡
 
በዚህ ዘመን የምንኖር እናንተና እኔ አምላካችን ማን እንደሆነ፣ ምን እየነገረን እንደሆነና የሐጢያቶቻችንን ስርየት በምን በኩል እንድንቀበል እንዳደረገን ማወቅና ማመን አለብን፡፡ በብሉይ ኪዳኑ የመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር በተገለጠው የሰማያዊ፣ የሐምራዊ፣ የቀይ ማግና የጥሩ በፍታ እውነት አማካይነት እግዚአብሄር እናንተንና እኔን ጠርቶን ተቀብሎናል፡፡ በዚህ የሚያምን እምነትንም ሰጥቶናል፡፡
 
 
ሰማያዊው ማግ ኢየሱስ የተቀበለውን ጥምቀት በትክክል ያመለክታል፡፡ 
 
ወደ ማቴዎስ 3፡13-17 እንመለስ፡- ‹‹ያን ጊዜም ኢየሱስ በዮሐንስ ሊጠመቅ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ መጣ፡፡ ዮሐንስ ግን፡- እኔ በአንተ ልጠመቅ ያስፈልገኛል፤ አንተም ወደ እኔ ትመጣለህን? ብሎ ይከለክለው ነበር፡፡ ኢየሡስም መልሶ፡- አሁንስ ፍቀድልኝ፤ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና አለው፡፡ ያን ጊዜ ፈቀደለት፡፡ ኢየሱስም ከተጠመቀ በኋላ ወዲያው ከውሃ ወጣ፡፡ እነሆም ሰማያት ተከፈቱ፤ የእግዚአብሄርም መንፈስ እንደ ርግብ ሲወርድ በእርሱም ላይ ሲመጣ አየ፡፡ እነሆም ድምጽ ከሰማያት መጥቶ፡- በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው አለ፡፡›› 
እግዚአብሄር በብሉይ ኪዳን በተሰጠው የመስዋዕት ቁርባኖች ስርዓት አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወደ አንድያ ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሚያሻግር በተጨባጭ አሳይቷል፡፡ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ሁሉ ይፈጽም ዘንድም አጥማቂው ዮሐንስ ኢየሱስን ማጥመቁ እውነት ነው፡፡ ኢየሱስ በዮሐንስ በተጠመቀ ጊዜ በእርግጠም የዓለም ሐጢያቶች ወደ እርሱ ስለተሻገሩ በዚህ የሚያምኑ ከልበቦቻቸው ሐጢያቶች በሙሉ ተገላግለዋል፡፡
 
ኢየሱስ የተቀበለው ይህ ጥምቀት ብዙውን ጊዜ ሰዎች ክርስቲያኖች ለመሆን ሲሉ በቅዳሴ መልክ ከሚቀበሉት የውሃ ጥምቀት ፈጽሞ የተለየ ትርጉም አለው፡፡ በሌላ አነጋገር የዚህ ዘመን ሰዎች የሚቀበሉት የውሃ ጥምቀት ወደ ክርስትና ሐይማኖት መለወጣቸውን የሚያሳይ ውጫዊ ምልክት ብቻ ነው፡፡ ኢየሱስ የሰው ዘር ወኪል በሆነው በአጥማቂው ዮሐንስ እጆች መጫን በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠመቀ፡፡ ኢየሱስ የተቀበለው ጥምቀት የእግዚአብሄርን ዘላለማዊ ደህንነት ተስፋና እግዚአብሄር በዘሌዋውያን ውስጥ ባቋቋመው የመስዋዕት ስርዓት የሰጠውን የሐጢያት ስርየት የፈጸመ ጥምቀት ነው፡፡ ኢየሱስ በግሉ በመጠመቅና የእነዚህን ሐጢያቶች ዋጋ ለመክፈል በመስቀል ላይ እስከ ሞት ድረስ ደሙን ማፍሰሱ እግዚአብሄር ለሰው ዘር ያለውን ፍቅሩንና ፍጹም የሆነውን የሐጢያት ስርየት የሚያሳይ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር አብ ልጁ በዮሐንስ እንዲጠመቅ ያደረገው እኛን ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ ለማዳን ነበር፡፡ ‹‹አሁንስ ፍቀድልኝ፤ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና፡፡›› (ማቴዎስ 3፡15) እዚህ ላይ ‹‹እንዲህ›› ማለት ኢየሱስ በጥምቀቱ በዓለም ላይ ያሉትን የሰው ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ይወስዳል ማለት ነው፡፡ ዮሐንስ ኢየሱስ ክርስቶስን ስላጠመቀው ሐጢያቶቻችን ወደ እርሱ ተሻግረዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በእኛ ፋንታ ደሙን ያፈሰሰውና የሞተው በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን ስለወሰደ ነው፡፡ ኢየሱስ የተቀበለው ጥምቀት የእግዚአብሄር የመስዋዕት ፍቅርና የሐጢያት ስርየት ነው፡፡ ኢየሱስ በተጨባጭ ወደ እርሱ የተሻገሩትን ሐጢያቶች ከተቀበለ በኋላ በውሃው ውስጥ ጠለመ፡፡ ያ ጥልመት ሞቱን የሚያመለክት ነበር፡፡ ከውሃው ውስጥ መውጣቱ ደግሞ አስቀድሞ መነሳቱን የሚመሰክር ነበር፡፡
 
 
ኢየሱስ ፈጣሪያችንና አዳኛችን ነው፡፡ 
 
ወደ እኛ የመጣው ኢየሱስ ክርስቶስ አጽናፈ ዓለማትንና በውስጡ ያሉትን ነገሮች ሁሉ የፈጠረ ራሱ አምላክ እንደሆነ እውነት ነው፡፡ ዘፍጥረት 1፡1 እንዲህ አለ፡- ‹‹በመጀመሪያ እግዚአብሄር ሰማያትንና ምድርን ፈጠረ፡፡›› ዘፍጥረት 1፡3 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ብርሃን ይሁን አለ፤ ብርሃንም ሆነ፡፡›› ዮሐንስ 1፡3 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሁሉ በእርሱ ሆነ፤ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለ እርሱ አልሆነም፡፡›› ኢየሱስ ክርስቶስ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በጋራ መላውን አጽናፈ ዓለማት ፈጥሮዋል፡፡
 
ፊልጵስዩስ 2፡5-8 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በክርስቶስ ኢየሱስ የነበረ ይህ አሳብ በእናንተ ዘንድ ደግሞ ይሁን፤ እርሱ በእግዚአብሄር መልክ ሲኖር ሳለ ከእግዚአብሄር ጋር መተካከልን መቀማት እንደሚገባ ነገር አልቆጠረውም፡፡ ነገር ግን የባርያን መልክ ይዞ በሰውም ምሳሌ ሆኖ ራሱን ባዶ አደረገ፡፡ በምስሉም እንደ ሰው ተገኝቶ ራሱን አዋረደ፤ ለሞትም ይኸውም የመስቀል ሞት እንኳ የታዘዘ ሆነ፡፡›› እርሱ ይህንን ዓለም ያበጀ እውነተኛ ፈጣሪ ነው፡፡ እኛን የሰው ዘር የሆንነውንም ፈጥሮናል፡፡ ይህ ጌታ እኛን ከሐጢያት ለማዳን ሰው ሆኖ መጣ፡፡ በዮሐንስ በመጠመቅም የዓለምን ሐጢያቶች ወሰደ፡፡ ከዚህ ጥምቀት የተነሳም ደሙን አፈሰሰ፡፡ በዚህም ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አዳነን፡፡
 
መሲሁ እስራኤሎች የመገናኛውን ድንኳን የመግቢያ በሮች በሙሉ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ እንዲሰሩ አደረገ፡፡ ለመገናኛውም ድንኳን በሮች ሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግና ጥሩ በፍታ እንዲጠቀሙ ማድረጉ የሰውን ዘር በሙሉ ከሐጢያቶቻቸው ለማዳን ኢየሱስ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች ለመውሰድና ዋጋውንም ደሙን በመስቀል ላይ በማፍሰስ ለመክፈል ያለውን ዕቅድ ይገልጣል፡፡
 
በብሉይ ኪዳን ሐጢያተኞች መስዋዕታቸውን ወደ መገናኛው ድንኳን አምጥተው በሚቃጠለው መስዋዕት ፊት እጆቻቸውን በራሱ ላይ በመጫን ሐጢያቶቸቸውን ወደ እርሱ ያሻግራሉ፡፡ ከዚያም ያርዱትና ደሙን ያፈስሱታል፡፡ ይህንንም ደም ለካህናቶች ያቀርባሉ፡፡ ከዚያም ካህናቱ ደሙን በሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያ ቀንዶች ላይ በመቀባትና የቀረውን ደም መሬት ላይ በማፍሰስ ይህንን መስዋዕት ለእግዚአብሄር ያቀርባሉ፡፡
 
በስርየት ቀን ሊቀ ካህኑ እጆቹን በራሱ ላይ የጫነበትን መስዋዕት ደም ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ ይዞ ይገባና በስርየት መክደኛው ላይ ይረጨዋል፡፡ እግዚአብሄርም የዚህን መስዋዕት ደም በሕዝቡ ላይ በይፋ የተወሰነ የፍርድ ውሳኔ አድርጎ ይቀበለዋል፡፡ ለመስዋዕት የሚቀርበው እንስሳ የሚገደለው ለምንድነው? ምክንያቱም ሊቀ ካህኑ እጆቹን በራሱ ላይ በመጫን የእሰራኤላውያንን ሐጢያቶች በሙሉ እንዲወስድ ስላደረገው ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ደሙ የዚህ የእጆች መጫን ውጤት ነበር፡፡ ከዚህ የተነሳ እግዚአብሄር የመስዋዕቱን እንስሳ ደም ተቀብሎ በመሰውያው ላይ የሚቃጠለውን የሥጋውን መልካም መዓዛ በማሽተት የእስራኤልን ሕዝብ ሐጢያቶች በሙሉ አስወግዶዋል፡፡
 
በአዲስ ኪዳንም ዘመን ኢየሱስ ይህንኑ ለማድረግ መጣ፡፡ ጌታችን ሐጢያቶቻችንን ለመውሰድና የሐጢያት ኩነኔን ለመሸከም በድንግል ማርያም ሥጋ በኩል ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ በዮሐንስ በመጠመቅና በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰስ ደህንነትን ፈጸመ፡፡ ሰማያዊው፣ ሐምራዊውና ቀዩ ማግም ራሱ አምላክ የሆነው ኢየሱስ የመጠመቁንና የመሰቀሉን እውነት የሚገልጥ ተጨባጭ ወንጌል ነው፡፡
 
ኢየሱስ የተሰቀለው፣ ደሙን ሁሉ ያፈሰሰው፣ የሞተው፣ በሦስት ቀናት ውስጥም ዳግመኛ የተነሳውና ለምናምነው ለእኛ አዳኛችን በመሆን በእግዚአብሄር ዙፋን ቀኝ የተቀመጠው በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን ስለወሰደ ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በእግዚአብሄር አብ ፊት ለአንዴና ለዘላለም ሐጢያቶቻቸውን በሙሉ በመውሰድ እግዚአብሄርን አባ አባት ብለው በመጥራት እርሱን እንደ አዳኛቸው አድርገው በተጨባጭ እንዲያምኑ አስችሎዋቸዋል፡፡ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ ውስጥ የተደበቁት የእውነት ምስጢሮች እነዚህ ናቸው፡፡
 
መሲሁ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ የሐጢያቶቻችንን መንጻት ፈጸመ፡፡ በምትካችንም የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ ተሸከመ፡፡ አሁን እርሱ የዓለም አዳኝ ሆንዋል፡፡ ስለዚህ በብሉይ ኪዳን ያለው የመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር የተሰራው ጥሩ በሆነ በፍታ ላይ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊና ከቀይ ማግ እንደሆነ ማመን አለብን፡፡ በአዲስ ኪዳን መሲሁ አዳኛችን በተጨባጭ ወደዚህ ምድር መጥቶ በጥምቀቱ የዓለምን ሐጢያቶች እንደወሰደና የእነዚህን ሐጢያቶች ኩነኔ በሙሉ በመስቀል ላይ እንደተሸከመም ማመን አለብን፡፡ በዚህም የሐጢያቶቻችንን ስርየት መቀበል አለብን፡፡
 
 
ክርስቲያኖች እንደመሆናችሁ ለቃሉ ምን ያህል ትኩረት እየሰጣችሁ ነው?
 
ዘጸዓት 25፡22 እንዲህ ይላል፡- ‹‹በዚያም ከአንተ ጋር እገናኛለሁ፤ የእስራኤልንም ልጆች ታዝዝ ዘንድ የምሰጥህን ነገር ሁሉ በምስክሩ ታቦት ላይ ባለው በሁለቱ ኪሩቤል መካከል በስርየት መክደኛውም ላይ ሆኜ አነጋግርሃለሁ፡፡›› እናንተስ የስርየት ወንጌል ወደሆነው ወደ ውሃውና ወደ መንፈሱ ወንጌል ምን ያህል ቀርባችኋል? ጌታ ኢየሱስን አዳኝ አድርገው ለሚያምኑት የሚናገራቸው ከየት ቦታ ነው? በዘጸዓት 25፡22 ላይ ትዕዛዛቶቹን ሁሉ ከምስክሩ ታቦት በላይ ካለው የስርየት መክደኛ እንደሚሰጣችሁ ተናግሮዋል፡፡ በብሉይ ኪዳን የነበሩት የእስራኤል ሕዝቦች እግዚአብሄር ከስርየት መክደኛው ላይ ሆኖ እንደሚናገራቸው ተናግሮዋል፡፡
 
እግዚአብሄር ሕጋዊ በሆነው የመስዋዕት ቁርባን አማካይነት የሐጢያቶቻችሁን ስርየት ከሰጣችሁና የራሱ ሕዝብ ካደረጋችሁ በኋላ ሕይወታችሁን እንደሚመራ የሰጠው ተስፋው ይህ እንደሆነ መረዳት አለባችሁ፡፡ እግዚአብሄር በክርስትና የምታምኑ ምንም ያህል በጌታ ለመመራት ብትሞክሩም የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል እውነት ሳታውቁ በኢየሱስ የምታምኑ ከሆነ እርሱ ሊመራችሁ እንደማይችል እየነገራችሁ ነው፡፡ ስለዚህ በእርግጥ በጌታ ለመመራት የምትፈልጉ ከሆናችሁ በመጀመሪያ ሐጢያቶቻችሁን በአንድ ጊዜ ያስቀረውን የሐጢያት ስርየት እውነት ማወቅና ማመን ከዚያም የእርሱን ምሪት መጠበቅ አለባችሁ፡፡
 
አንድ ልነግራችሁ የምፈልገው ነገር አለኝ፡፡ ይህም የእግዚአብሄር ልጆች መሆን ከፈለጋችሁና የእርሱ ቤተክርስቲያን አባል መሆን የምትፈልጉ ከሆነ በመጀመሪያ የሰማያዊው፣ የሐምራዊውና የቀዩ ማግ ምስጢር በሆነው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል በማመን ከሐጢያቶቻችሁ መዳን አለባችሁ፡፡ ከምስክሩ ታቦት በላይ የተነገራችሁን የጌታን ትዕዛዛቶች መቀበል የምትችሉት ከዚህ በኋላ ብቻ ነው፡፡
 
ጌታ ሁልጊዜ የሚያዘንና ሕይወታችንን የሚመራው የሐጢያት ስርየትን እንድንቀበል ባስቻለን የውሃና የመንፈስ ወንጌል እምነት ሲኖረን እንደሆነ ማስታወስና ማመን አለብን፡፡ አሁን ከስርየት መክደኛው በላይ የተሰጣችሁን የጌታን ትዕዛዛቶች እየተቀበላችሁ ነውን? ወይስ ጌታን የምትከተሉት በራሳችሁ ስሜቶች ላይ ተመረኩዛችሁ ነው?
 
የእናንተ ስሜቶች እምነታችሁን ሊገነቡላችሁ አይችሉም፡፡ ነገር ግን ወደ ግራ መጋባት ብቻ ይነዱዋችኋል፡፡ ከምስክሩ ታቦት ላይ የተነገሩዋችሁን የእግዚአብሄር ትዕዛዛቶች ለመከተል የምትሹ ከሆነ ከመገናኛው ድንኳን ውስጥ የተነገሩት ሰማያዊው፣ ሐምራዊው፣ ቀዩ ማግና ጥሩው በፍታ እግዚአብሄር የሰጠን የሐጢያት ስርየት መሆናቸውን መረዳትና ማመን አለባችሁ፡፡
 
ሐሌሉያ! እኔ ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ ስላዳነን የጌታ ጥምቀት፣ የመስቀል ላይ ደሙ፣ ሐይሉና ፍቅሩ እግዚአብሄርን አመሰግነዋለሁ፡፡