Search

የመገናኛው ድንኳን ጥናት፤

የዕጣኑ መሰውያ

ተዛማጅ ስብከቶች

· የዕጣኑ መሰውያ፡፡ ‹‹ ዘጸዓት 30፡1-10 ››

የዕጣኑ መሰውያ፡፡
‹‹ ዘጸዓት 30፡1-10 ››
‹‹የዕጣን መሠዊያውን ሥራ፤ ከግራር እንጨት አድርገው፡፡ ርዝመቱ አንድ ክንድ፣ ስፋቱም አንድ ክንድ አራት ማዕዘን ይሁን፤ ከፍታውም ሁለት ክንድ ይሆናል፤ ቀንዶቹም ከእርሱ ጋር በአንድነት የተሠሩ ይሁኑ፡፡ ላይኛውንና የግድግዳውንም ዙሪያ ቀንዶቹንም በጥሩ ወርቅ ትለብጠዋለህ፤ በዙሪያውም የወርቅ ክፈፍ ታደርግለታለህ፡፡ ከክፈፉም በታች ሁለት የወርቅ ቀለበቶች አድርግለት፡፡ በዚህና በዚያ በሁለቱ ጎን ታደርጋቸዋለህ፤ ለመሸከምም የመሎጊያዎች ስፍራ ይሁኑ፡፡ መሎጊያዎቹንም ከግራር እንጨት አድርግ፤ በወርቅም ለብጣቸው፡፡ በምስክሩ ታቦት አጠገብም ካለው መጋረጃ በፊት ታኖረዋለህ፡፡ ይህንም አንተን በምገናኘበት ከምስክሩ በላይ ባለው በስርየት መክደኛ ፊት ታኖረዋለህ፡፡ አሮንም የጣፋጭ ሽቱ ዕጣን ይጠንበት፤ በማለዳ በማለዳ መብራቶቹን ሲያዘጋጅ ይጠነው፡፡ ይህ በእግዚአብሄር ፊት ለልጅ ልጃችሁ የዘወትር ዕጣን ይሆን ዘንድ አሮን በማታ ጊዜ መብራቶቹን ሲያበራ ያጥነዋል፡፡ ሌላም ዕጣን፣ የሚቃጠለውንም መስዋዕት፣ የእህሉንም ቁርባን አታቀርብበትም፤ የመጠጥም ቁርባን አታፈስስበትም፡፡ አሮንም በዓመት አንድ ጊዜ በቀንዶቹ ላይ ማስተሰርያ ያደርጋል፤ በዓመት አንድ ጊዜ ለልጅ ልጃችሁ ማስተሰርያ በሚሆን በሐጢአት መሥዋዕት ደም ማሰተሰርያ ያደርግበታል፡፡ ለእግዚአብሄር ቅድስተ ቅዱሳን ናት፡፡›› 
 
የዕጣኑ መሰውያ
 

የዕጣኑ መሰውያ የጸሎት ስፍራ ነበር፡፡ 

 
የዕጣኑ መሰውያ ከግራር እንጨት የተሰራና ርዝመቱና ወርዱ አንድ ክንድ (1.5 ጫማ) ቁመቱ ደግሞ ሁለት ክንድ የሆነ አራት ማዕዘን ነበር፡፡ በቅድስቱ ስፍራ ውስጥ የተቀመጠው የዕጣኑ መሰውያ ሙሉ በሙሉ በወርቅ የተለበጠና ዙሪያውን የወርቅ ክፈፍ ያለው ነበር፡፡ ከክፈፉ በታች ለሸከም የሚያገልሉ መሎጊያዎችን የሚይዙ አራት የወርቅ ቀለበቶች ተደርገውበታል፡፡ በዚህ የዕጣን መሰውያ ላይ ከቅዱሱ ቅብዓ ዘይትና ከጣፋጩ ዕጣን በስተቀር ሌላ አንዳች ነገር አይደረግም፡፡ (ዘጸዓት 30፡22-25)
 
የዕጣኑ መሰውያ የጸሎት ዕጣን ለእግዚአብሄር የሚቀርብበት ቦታ ነው፡፡ ነገር ግን በዕጣኑ መሰውያ ላይ ከመጸለያችን በፊት አስቀድመን በዚህ መሰውያ ላይ ለመጸለይ ብቁ መሆናችንንና አለመሆናችንን ማወቅ አለብን፡፡ ቅዱስ ወደሆነው አምላክ ለመጸለይ ብቁ መሆን የሚሻ ማንኛውም ሰው በመጀመሪያ በእምነት ከሐጢያቶቹ በመታጠብ ሐጢያት አልባ መሆን አለበት፡፡ ይህንን ለማድረግ አንድ ሰው በሚቃጠለው መስዋዕትና በመታጠቢያው ሰን ከሐጢያቶቹ ሁሉ በእምነት መንጻት አለበት፡፡
 
እግዚአብሄር የሐጢያተኞችን ጸሎቶች አይሰማም፡፡ (ኢሳይያስ 59፡1-3) ለምን? ምክንያቱም እግዚአብሄር የሚቀበለው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ የታጠቡትን ብቻ ነውና፡፡ እግዚአብሄር በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጠው እውነት ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አንጽቶናል፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር የሚደሰተው የጻደቃንን ጸሎቶች በመስማት ብቻ ነው፡፡ (መዝሙረ ዳዊት 34፡15፤1ኛ ጴጥሮስ 3፡12)
 
 
የሰብዓዊ ፍጡራን ሁሉ ባህርይና ማንነት፡፡ 
 
በቅርበት ስንመለከት ሰብዓዊ ፍጡራን በሙሉ እናንተንና እኔን ጨምሮ በመሰረቱ የተወለድነው ሐጢያተኛ ዘር ሆነን ስለሆነ ሁሉም ሐጢያት ይሰራል፡፡ እያንዳንዱ ሰው የክፉ አድራጊ ዘር ነው፡፡ ሰዎች ከመጀመሪያውኑም በሐጢያት ስለተወለዱ ሕይወታቸውን የሚኖሩት ክፉ ምግባሮችን በማድረግ ነው፡፡ ማንም ብትሆኑም ስለ ራሳችሁ አስቡ፡፡ እኛ ወደ ሲዖል ከመጣል ማምለጥ የማንችል ክፉዎች እንደነበርን በእግዚአብሄር ፊት ማመን እንችላለን፡፡ ከሁሉም በላይ ምግባሮቻችንን በእግዚአብሄር ፊት ለፍርድ ሲቀርቡ የሐጢያት ደመወዝ ሞት መሆኑን በሚያውጀው በእግዚአብሄር ሕግ መሰረት ጻድቅ ከሆነው የእርሱ የሐጢያት ፍርድ ማምለጥ አንችልም፡፡
ከሰው ዘር ልብ ውስጥ የሚወጣው ክፉ አሳብ፣ ነፍስ ማጥፋት፣ ምንዝርና፣ ትዕቢት፣ ስንፍናና ወ.ዘ.ተረፈ በመሆኑ ዕድል በሚያገኝበት ጊዜ ሁሉ ይህንን ያደርጋል፡፡ (ማርቆስ 7፡21-22) ከመነሻው የክፉ አድራጊዎች ዘር ሆነው የተወለዱና አጋጣሚዎች በሚፈቅዱላቸው ጊዜ ሁሉ ሐጢያት ከመስራት ሌላ ማድረግ የማይችሉ ሰብዓዊ ፍጡራን ልብ በእግዚአብሄር ፊት ዕፍረት የሚሰማው መቼ ነው? ይህ በሰው ሰራሽ ጥረቶች የማይቻል ነው፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሄር ፊት እንዳናፍር የሚፈቅድልን አንድና ብቸኛ እምነት አለ፡፡ እርሱም ይኸውላችሁ፤ ሁላችንም ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከጥሩ በፍታ የተሰራውን እውነት ማወቅና ማመን አለብን፡፡ ይህ እውነት ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንድንነጻ ስለሚያስችሉም ያለ ሐፍረት በእግዚአብሄር ፊት እንቆማለን፡፡ ስለዚህ ሁላችንም የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ፈጽሞ ያስፈልገናል፡፡
 
ማናችንም ብንሆን በሐጢያቶቻችን ምክንያት ለሲዖል የታጨን የነበርን የመሆናችንን እውነት መካድ አንችልም፡፡ ይህንን ዕድል ፈንታ መቀበል አለብን፡፡ ለሲዖል የታጩ መሆናቸውን በእግዚአብሄር ፊት ለሚውቁ እግዚአብሄር የሰጣቸውን ደህንነት በልቦቻቸው ማመን አይከብዳቸውም፡፡ ከእግዚአብሄር ጋር በእውነትና በቅንነት ስንገናኝ ልቦቻችን አታላይ በሆነ መልኩ ከእርሱ መደበቅ አንችልም፡፡ በዚህም የእግዚአብሄርን ፍትህና ጽድቅ ወደ ማወቅ እንመጣለን፡፡ ሁሉም ሰው እንዲህ ባለ ስፍራ ላይ የተቀመጠ በመሆኑ በእግዚአብሄር የጽድቅ ፍርድ ለሐጢያቶቻቸው ከመቀጣት ማምለጥ አይችሉም፡፡
 
የሐጢያት ደመወዝ ሞት መሆኑን የሚያውጀው የእግዚአብሄር ጻድቅ ሕግ ሐጢያተኞች በሙሉ በራሳቸው አስተሳሰቦች ወይም የሐይማኖት እምነት ሊያለዝቡት የሚችሉት ሕግ አይደለም፡፡ የእግዚአብሄር ሕግ በዝርዝር የቀረበ ትክክለኛና ጻድቅ ስለሆነ በፊቱ የሚቆመውን ማንኛውንም ሰው በሐጢያቶቹ ምክንያት ለሲዖል የታጨ እንደሆነ እንዲያምን ያስገድደዋል፡፡ ሐጢያተኞች በሙሉ ከሐጢያቶቻቸው እጅግ ቅንጣት ለሆነችው እንኳን ከእግዚአብሄር ፍርድ ማምለጥ እንደማይችሉ ወደ መረዳት መጥተዋል፡፡
 
ስለዚህ ሁላችንንም ከሐጢያት የሚያድነን አዳኝ ያስፈልገናል፡፡ ይህ አዳኝ ማን እንደሆነም ማወቅ አለብን፡፡ ይህ የሰው ዘር ሁሉ አዳኝ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ እርሱ ወደዚህ ምድር የመጣ፣ የዓለምን ሐጢያቶች ለመውሰድ በዮሐንስ የተጠመቀ፣ በመስቀል ላይ በመሰቀልና ደሙን በማፍሰስም የሐጢያተኞችን ሐጢያቶች በሙሉ ተሸክሞ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ያዳነን አዳኝ ነው፡፡
 
ሁላችንም የሐጢያት ስርየትን መቀበል እጅግ አዳጋች ነው በሚል የተሳሳተ ግንዛቤ ይዘናል፡፡ እንዲያውም መዳን የምንችለው መጽሐፍ ቅዱስን በሙላቱ ስናውቅ ብቻ ነው፤ ወይም ደህንነታችን አንዳች መልካም ምግባሮችን ይጠይቃል ብለን አስበናል፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር የሰጠው የደህንነት እውነት የተለየ ነበር፡፡ ይህ የደህንነት እውነት በእግዚአብሄር ፊት ሕሊናችንን በመመርመር በልቦቻችን ውስጥ የሚገኙትን ሐጢያቶች በሙሉ በማወቅና በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ከሐጢያቶቻችን የምንድንበትን መንገድ ከፍቶ አሳይቶናል፡፡ ይህ እውነት በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር ተመስሎዋል፡፡
 
የሰው ዘር የሐጢያት ስርየት የሚያገኘው በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ አማካይነት ከተፈጸመው ክቡር የደህንነት እውነት ነው፡፡ ሁሉም ለአንዴና ለመጨረሻ የሐጢያት ስርየትን ማግኘት የሚችሉት በዚህ እውነት በማመን ነው፡፡ ይህንን ለማደረግ እያንዳንዱ ሰው በሐጢያቶቹ ምክንያት ለሐጢያት የታጨ መሆኑን ማመንና በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው የወንጌል እውነት ውስጥ የሚገኝ ወንጌል ነው፡፡
 
ሁሉም በዚህ የእውነት ወንጌል ማመን አለበት፡፡ በዚህ ወንጌል ውስጥ ያለውን እውነት የማያምኑ ከሆነ ከሐጢያቶቻቸው ነጻ ሊወጡ አይችሉም፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በፈጸመው በዚህ የደህንነት እውነት የሚያምኑ ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ድነው የራሱ የእግዚአብሄር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ብቁ ናቸው፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ፊት ቀርበው መጸለይ የሚችሉ ሰዎች ለመሆን በመጀመሪያ የሐጢያት ስርየት ወንጌል በሆነው የውሃና የመንፈስ ወንጌል ማመን አለባቸው፡፡ እውነተኛውን ወንጌል በማወቅና በእርሱም ከልቦቻችን በማመን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ስንድን ወደ እግዚአብሄር ለመጸለይ ብቁ እንሆናለን፡፡ ወደ እግዚአብሄር እንድንጸልይ የሚያስችለንን እምነት የምናገኘው ከእግዚአብሄር የመጣውን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በማመን ነው፡፡
 
በመገናኛው ድንኳን የመጋረጃ በር የተገለጠውን የሰማያዊውን፣ የሐምራዊውንና የቀዩን ማግ እውነት የሚያውቅና የሚያምን እምነት ሳይኖር ወደ እግዚአብሄር መጸለይ ስህተት ነው፡፡ የዚህ ዓይነቱ እምነት የስድብ ሐጢያቶችን ከመስራትና በእግዚአብሄር ላይ ከማላገጥ ጋር የሚመሳሰል ነው፡፡ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የተገለጠውን እውነት በልቦቻችን ለማመን እምቢተኞች ሆነን እንዴት የእግዚአብሄር ጠላት እንሆናለን?
 
በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ እውነት በመጣው በኢየሱስ ክርስቶስ ለማመን እምቢተኞች ስትሆኑ የእግዚአብሄር ጠላት ለመሆን አቋራጭ መንገድ ታገኛላችሁ፡፡ ይህ እግዚአብሄርን የሚቃወም አስከፊ የሆነ የአለማመን ድርጊት ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ቅድስና የመናቅ ሐጢያትን በመስራት የሚቀጥሉ ሰዎች እግዚአብሄር የፈጸመላቸውን ደህንነት የማያምኑ ነገር ግን እንደ ራሳቸው አስተሳሰብና በራሳቸው ስምምነት የሚያምኑ ሰዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ነፍሳቶች ራሳቸውን ‹‹ግብዝነት›› ተብሎ በሚጠራ የበለስ ቅጠል መጎናጸፊያ ሸፍነው የእግዚአብሄርን ፍቅርና ምህረት የሚንቁ ናቸው፡፡
 
ነገር ግን እነዚህ ሰዎች የራሳቸውን ልብ ማታለል ቢችሉም ከእግዚአብሄር ፍርድ ማምለጥ አይችሉም፡፡ በዚህ ዓይነቱ አለማመን የተያዙ ሰዎች በእግዚአብሄር የጽድቅ ሕግ መሰረት አስፈሪው የሐጢያት ቅጣት ይቀበሉ ዘንድ ይኮነናሉ፡፡ ለምን? ምክንያቱም እግዚአብሄር ሐጢያቶቻቸውን የደመሰሰበትን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ለማወቅም ሆነ በዚህ ወንጌል ለማመን አልፈለጉምና፡፡
 
ሕሊናችን በዓይኖቻችን ፊት እንኳን ርካሽ ሆኖ ሳለ ሐጢያቶቻችንን ከቅዱሱ አምላክ እንዴት መደበቅ እንችላለን? ይህ በአጭሩ የማይቻል ነው! ሐጢያቶቹን መሸፈን የሚሻ ማንኛውም ሰው ከእግዚአብሄር ፍቅርና ምህረት ውጪ ይሆናል፡፡ ልቦቻቸውን የሚያስቱ ሰዎች መጨረሻቸው እግዚአብሄርንና ወገኖቻቸውን ሰብዓዊ ፍጡራን እንደሚያታልሉት እንደ ዲያብሎስ አገልጋዮች መሆን ነው፡፡ የራሳቸውን ዓይኖች በመሸፈን እግዚአብሄርን ማታለል የሚችሉ የመሆኑ አሳብ ከንቱ ከሆኑት አስተሳሰቦቻቸው የመነጨ የዕብሪታቸው ነጸብራቅ ነው፡፡ እንዲያውም በራሳቸው አስተሳሰብ የሚደግፉ ሰዎች የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል የሚቃወሙና በገዛ ፈቃዳቸው የሰይጣን ባሮች ለመሆን የሚሹ ሰዎች ናቸው፡፡
 
ሰዎች የራሳቸውን ልቦች ማታለል የሚችሉ ቢሆኑም እግዚአብሄርን ፈጸሞ ማታለል እንደማይችሉ መገንዘብ አለባቸው፡፡ በእግዚአብሄር ቃል መሰረት ለማመንም አእምሮዋቸውን መለወጥ አለባቸው፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ሳያምኑ እንዴት ከሐጢያቶቻቸው መንጻት ይችላሉ? የሐጢያት ደመወዝ ሞት እንደሆነ በተጻፈው መሰረት በእግዚአብሄር ፊት ልቡን የሚያስት ሐጢያተኛ ከእግዚአብሄር ፍርድ ማምለጥ አይችልም፡፡ የእግዚአብሄርን ሕግ የምናውቅ ከሆንን ሁላችንም ስለ ሐጢያቶቻችን ለሲዖል የታጨን መሆናችን ግልጽ ነው፡፡ ስለዚህ ወደ እግዚአብሄር መቅረብ የሚሹ ሁሉ በመገናኛው ድንኳን የመግቢያ በር በተገለጠው የወንጌል እውነት በማመን መዳን አለባቸው፡፡
 
ነገር ግን ብዙዎች ስለ ሐጢያቶቻቸው መኮነን ያለባቸው የመሆኑን እውነታ መረዳት ስለተሳናቸው በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ እውነት የመጣውን የደህንነት ወንጌል በልቦቻቸው መቀበል ተስኖዋቸዋል፡፡ ከዚህ የተነሳም ሁሉም ወደ ሲዖል እየነጎዱ ነው፡፡ አስቀድመው ክርስቲያን ሆኑም አልሆኑም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የማያምኑ ተመሳሳይ ቅጣት ይገጥማቸዋል፡፡ ስለዚህ በእግዚአብሄር ፊት ሕሊናችንን አናስት፡፡ ነገር ግን በልቦቻችን ለውሃውና ለመንፈሱ ወንጌል በመማረክ ይህንን የወንጌል እውነት አውቀን እንመነው፡፡
 
 

በእውነት ቃል በማመን ሐጢያቶቻችንን ማንጻት አለብን፡፡ 

 
ሰዎች ሁለት ሕሊና አላቸው፡፡ አንዱ የሥጋ ሕሊና ሲሆን ሌላው የወንጌልን እውነት በሚመለከት የእምነት ሕሊና ነው፡፡ ለእነዚህ ለሁለቱ ግዛቶች እውነተኞች መሆን አለብን፡፡ ነገር ግን ከእነዚህ ከሁለቱ በተለይ የእውነትን ወንጌል የሚያወቀውን የእምነት ሕሊና ማጣት አይኖርብንም፡፡ በእግዚአብሄር ቃል ፊት የእምነት ሕሊናችንን መመርመር አለብን፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን እንደተቀበለ፣ በመስቀል ላይ እንደተኮነነና እንዳዳነን በዚህ እምነትም የሕሊና ሐጢያቶችንን እንዳጠበ ማመን አለብን፡፡ ይህ እውነት ከዚህ በላይ ግልጽ ሊሆን እንደማይችል እየታወቀ በዚህ የእውነት ወንጌል የማያምኑ ሰዎች አሁንም ድረስ መኖራቸው ያስቆጣኛል፡፡
 
ሕሊናዎቻችንን የሚያነጻ የእምነት ቅደም ተከተል አለ፡፡ በመጀመሪያ ለሲዖል የታጨን የመሆናችንን እውነት ማወቅና ማረጋገጥ አለብን፡፡ ሁለተኛ አዳኛችን ወደዚህ ምድር መጥቶ ለሐጢያቶቻችን በዮሐንስ እንደተጠመቀ፣ በመስቀል ላይ እንደሞተና በዚህም ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንዳዳነን በልቦቻችን ማመን አለብን፡፡ ሐጢያተኞች በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው የውሃና የመንፈስ ወንጌል እምነታቸው ከሐጢያቶቻቸው ድነው የዘላለምን ሕይወት ማግኘት አለባቸው፡፡
 
ከሐጢያቶቻችን መዳን የሚገባን ሆኖ ሳለ አንዳንድ ሰዎች በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ አማካይነት ስለተፈጸመው የሐጢያት ስርየት ቢያውቁም አሁንም ድረስ አያምኑም፡፡ እንዴት ይህንን ሊያደርጉ ይችላሉ? በአለማመናቸው ምክንያት ለሚመጡት ውጤቶች በሙሉ ተጠያቂዎች መሆን እንዳለባቸው እርግጥ ነው፡፡ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ የተገለጠውን እውነት አውቀን ካላመንበት ሐጢያተኞች ሆነን እንቀራለን፡፡ አሁንም ሐጢያተኞች ከሆንን በእግዚአብሄር ሕግ መሰረት ለሐጢያቶቻችንን አንኮነንምን? እያንዳንዳችን ወንድም ሆነን ሴት እግዚአብሄር በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ አማካይነት በፈጸመው እውነት ከልባችን በማመን ከሐጢያት መዳን አለብን፡፡
 
ሰዎች ከሐጢያቶቻቸው የሚያድናቸው የእምነት ዓይነት ሊኖራቸው ይገባል፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ብቻ የሚያምን እምነት ሊኖራቸው ይገባል፡፡ ጌታ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ተሸክሞ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ እኛን ባዳነበትና በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው ወንጌል ታምናላችሁን? በመጀመሪያ ስለ ራሳችሁ ስታስቡ እናንተ በእርግጥም ለሲዖል የታጫችሁ እንደነበራችሁ ታምናላችሁን? እኛ ለሲዖል ታጭተን ሳለን ጌታ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው እውነት ከሐጢያቶች እንዳዳነን ትገነዘባላችሁን?
 
ጌታ ወደዚህ ምድር መጥቶ የተጠመቀውና ደሙን ያፈሰሰው ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ለማስወገድ እንደነበር ማወቅ አለባችሁ፡፡ ጌታችን የእናንተንና የእኔን ሐጢያቶች ለመደምሰስ የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ መጣ፡፡ በ30 ዓመቱ በዮርዳኖስ ወንዝ በዮሐንስ በመጠመቅ የመላውን ሰው ዘር ሐጢያቶች በሙሉ በገዛ ሥጋው ተቀበለ፡፡ በመስቀል ላይ በመሰቀልና ደሙን በማፍሰስም ለአንዴና ለመጨረሻ የሐጢያትን ኩነኔ ተሸከመ፡፡
 
በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው እውነት በማመን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ መዳን እንችላለን፡፡ በዚህ እውነት በእርግጥ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ የዳንን መሆን አለመሆናችንን መመርመርና ማረጋገጥ አለብን፡፡ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ አማካይነት አዳኝ ሆኖ በመጣው በኢየሱስ ክርስቶስ የሚያምን እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሰው በልቡ አምኖ ይጸድቃልና በአፉም መስክሮ ይድናልና፡፡›› (ሮሜ 10፡10) ሮሜ 10፡17ም እንዲህ ይላል፡- ‹‹እንግዲያስ እምነት ከመስማት መስማትም በእግዚአብሄር ቃል ነው፡፡››
 
ይህ የክርስቶስ ቃል በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተፈጸመው ደህንነት በማመን እንደዳንን ይነግረናል፡፡ የሐጢያት ስርየት በራሳችን አስተሳሰቦች በማመን የሚገኝ ሳይሆን በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በመጣው ደህንነት በልቦቻችን በማመን የሚገኝ ነው፡፡ በእርግጥ ከሐጢያት የሚያድነን እምነት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምን እምነት ነው፡፡
 
እምነታችንን በዚህ እውነት ላይ አድርገን ወደ እግዚአብሄር መጸለይ አይገባንምን? ይገባናል! ወገባችንን በእውነት ታጥቀን ዘወትር በመንፈስ መጸለይና መማለድ ይኖርበናል፡፡ (ኤፌሶን 6፡14-18) ነገር ግን ይህ እውነት ምንድነው?
 
ጌታችን እኛን ለማዳን ወደዚህ ምድር መጥቶ በ30 ዓመት በአጥማቂው ዮሐንስ መጠመቁን፣ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ መሸከሙን፣ ሁለቱም እጆቹና እግሮቹ መቸንከራቸውን፣ የተተፋበት መሆኑን፣ ደሙን ማፍሰሱንና በዚህም ሐጢያቶቻችንን ማስወገዱን የሚነግረን ወንጌል ነው፡፡ የሐጢያት ስርየታችን የተፈጸመው በዚህ እውነት በማመናችን መሆኑን መመስከር አለብን፡፡ ጌታችን በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ አማካይነት በመኮነን ከሐጢያቶቻችን አድኖናል፡፡
 
‹‹አቤቱ አብዝተህ ስለወደድኸኝ የራሱ የእግዚአብሄር ልጅ አደረግኸኝ፡፡›› እምነታችንን መመስከር የሚገባን እንደዚህ ነው፡፡ የነበረን ነገር ሁሉ ሐጢያት ሆኖ ሳለ ጌታችን በጥምቀቱና በስቅለቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በማስወገድ መንግሥተ ሰማይ የምንገባበትን ብቃት ሰጠን፡፡ ሁላችንም በዚህ እውነት በማመን የዘላለምን ሕይወት መቀበል አለብን፡፡
 
በዚህ እውነት ላለማመን ምክንያታችሁ ምንድነው? እኔን በሚመለከት ግን ጌታ በዚህ ሁኔታ ተጠምቆ ከሐጢያቶቼ ባያድነኝ ኖሮ የምለው አንዳች ነገር አይኖረኝም ነበር፡፡ ነገር ግን ለእኔ ሲል ተጠመቀ፤ ደሙንም አፈሰሰ፡፡ በዚህም ከሐጢያቶቹ አዳነኝ፡፡ ስለዚህ አምናለሁ! ሁላችንም በዚህ ወንጌል የማናምንበት ምክንያት የለም፡፡ ሐጢያተኞች በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ባያምኑ በእርግጥም ወደ ሲዖል ይጣላሉ፡፡ እኔ ግን እያንዳንዳችሁ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በማመን አሁኑኑ ከሐጢያት እንድትድኑ እሻለሁ፡፡
 
እኔ ራሴ በኢየሱስ አምናለሁ እያልሁ ሐጢያተኛ ሆኜ የቀረሁበት ጊዜ ነበር፡፡ ጥሩ ክርስቲያን ለመሆን ስለፈለግሁ ከሰማይ በታች ሐፍረት የሚባል አንዳች ነገር እንዳይኖርብኝ ብዙ ጥሬያለሁ፡፡ ነገር ግን ከፍላጎቶቼ በተቃራኒ በየጊዜው ሐጢያት መስራቴን ቀጠልሁ፡፡ ብቸኛው መጽናኛዬ ራሴን ከሌሎች ጋር ሳወዳድር ቢያንስ በመጠኑም ቢሆን ከእነርሱ የተሻልሁ እንደሆንሁ ማሰቤ ነበር፡፡ ነገር ግን ሕሊናዬ አሁንም ሐጢያት እንዳለብኝ ይነግረኝ ነበር፡፡ በእግዚአብሄር ሕግ መሰረት የሐጢያት ደመወዝ ሞት በመሆኑ እኔ በሐጢያቶቼ ምክንያት ለሲዖል የታጨሁ ሰው ነበርሁ፡፡
 
ከአስር ዓመታት አሰልቺና በሕግ ላይ የተመሰረተ ሕይወቴ በኋላ መንፈሳዊ ሙት ወደ መሆኑ ተቃርቤ ነበር፡፡ ሆኖም እግዚአብሄር ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኔ ተጠምቆ ሐጢያቶቼን ስለ መውሰዱ በጸጋው አነቃኝ፡፡ እርሱ የወሰደው የእኔን ሐጢያቶች ብቻ ሳይሆን በመላው ዓለም ላይ የሚኖረውን የእያንዳንዱን ሰው ሐጢያቶችም ሁሉ ነው፡፡ ከዚያም እነዚህን ሐጢያቶች በመስቀል ላይ ተሸክሞ በመሰቀልና በመሞት የእነዚህን ሐጢያቶች ኩነኔ ተሸከመ፡፡ ዳግመኛም ከሙታን ተነሳ፡፡ በዚህም አሁን በሕይወት የሚኖር እውነተኛ አዳኜ ሆነ፡፡ ይህን የወንጌል እውነት ወደ ማወቁ በመጣሁ ጊዜ አመንሁበት፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ አማካይነት የደህንነቴ አምላክ መሆኑን በማመኔ ሐጢያቶቼ በሙሉ ተወግደዋል፡፡ በእምነትም የሐጢያትን ስርየት ወደ ልቤ አስገብቻለሁ፡፡
 
የሐጢያቶቼን ስርየት ያገኘሁት የእግዚአብሄርን ቃል በሚገባ በማወቄ አይደለም፡፡ ከሐጢያቶቼ የነጻሁት የሕሊናዬን ሐጢያቶች አውቄ እነዚህን ሐጢያቶች በጥምቀቱ አማካይነት ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ስላሻገርሁና ኢየሱስ የሐጢያቶቼን ዋጋ ለመከፈል በመስቀል ላይ መኮነኑን በልቤ ስላመንሁ ነው፡፡ አሁን ወንጌልን እየሰበክሁ ሕይወቴን የምኖረው ይህንን የሐጢያት ስርየት ስለተቀበልሁ ነው፡፡ እናንተና እኔ ተመሳሳይ ነን፡፡ በእርግጥ በእኛ መካከል ልዩነት የለም፡፡
 
እኔም እንደ እናንተ ወደ ሲዖል ስንደረደር ነበር፡፡ እኔም እንደ እናንተ ተመሳሳይ በሆነው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል በማመን የሐጢያትን ስርየት ተቀብያለሁ፡፡ ጌታ ሐጢያቶቻችንን በደመሰሰበት ወንጌል በማመን እናንተና እኔ ሁለታችንም በእምነት ድነናል፡፡ ስለዚህ ጌታን አመስግነዋለሁ፡፡ አሁን ወደ እግዚአብሄር መቅረብና የሐጢያት ስርየትን የተቀበሉ የራሱ ልጆች ሆነን መጸለይ የምንችለው አሁን በዚህ መንገድ በውሃውና በመንፈሱ አማካይነት ፍጹም የሆነ የሐጢያት ስርየት ተቀብለን የእምነት ሕሊና ስላለን ነው፡፡
 
በዕጣኑ መሰውያ ላይ የሚቀርበው መልካም መዓዛ የተሰራው ከቅዱስ ቅብዓ ዘይት መሆኑን መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነግረን ሁሉ ኢየሱስም ቅዱስ በሆነው የእውነት ወንጌል ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በማስወገድ ንጹህ አድርጎናል፡፡ በጥንቱ የብሉይ ኪዳን ዘመን የእስራኤል ሕዝብ ይህንን ዕጣን አዘጋጅተው እግዚአብሄር ባዘዘው መሰረት በትክክል በመሰውያው ላይ ማጤስ ነበረባቸው፡፡፡ ስለዚህ በቅድስቱ ስፍራ ውስጥ ዕጣን ይጤሳል፡፡ መልካም መዓዛውም በየቀኑ ይወጣል፡፡ ይህ ዕጣን ወደ እግዚአበሄር መጸለይን ያመለክታል፡፡
 
በአዲስ ኪዳን ዘመን እናንተ ይህንን ዕጣን በቅድስቱ ስፍራ ውስጥ ለማጤስ በመጀመሪያ በእውነት ወንጌል ማመንና በልቦቻችሁ ውስጥ የሐጢያት ስርየትን መቀበል አለባችሁ፡፡ በሌላ አነገገር አንድ ሰው የጸሎትን ዕጣን ማጤስ የሚችለው በእውነት ወንጌል በማመን ነው፡፡ ዕጣን በብሉይ ኪዳን ዘመን በሚጤስበት ተመሳሳይ መንገድ ለማጤስ የምንችልበት ሌላ መንገድ ምንድነው? እንደ ሚቃጠለው መስዋዕት መሰውያና የዕጣን መሰውያ ያሉ የመገናኛው ድንኳን ዕቃዎች አሁን በፊታችን በሌሉበት ሁኔታ እናንተና እኔ የምናዘጋጀውና በመሰውያው ላይ ማጤስ የምንችለው እንዴት ነው? የጸሎትን ዕጣን በእምነት ማጤስ እንችላለን፡፡ ምክንያቱም ኢየሱስ ክርስቶስ ሐጢያቶቻችንን ደምስሶ አድኖናልና፡፡ የሐጢያትን ስርየት በተቀበልን ጊዜ ልቦቻችን በእምነት ስለነጹ አሁን በእግዚአብሄር ፊት ትኩስ በሆኑት ጸሎቶቻችን ዕጣን ማጤስ እንችላለን፡፡
 
በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ከሙሉ ልባችን በማመናችን ሐጢያቶቻችን በሙሉ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ እንደተሻገሩና ኢየሱስ ክርስቶስም በእኛ ምትክ የሐጢያቶቻችንን ኩነኔ በይፋ እንደተሸከመ እናምናለን፡፡ በዚህም የእናንተና የእኔ ልቦች በሙሉ ነጽተዋል፡፡ በልቦቻችን ውስጥ ያሉት ሐጢያቶቻችን በሙሉ ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀት አማካይነት ወደ ኢየሱስ ከተሻገሩ ሐጢያቶቻችሁ በሙሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ስለተወገዱና ስለተደመሰሱ በልቦቻችሁ ውስጥ ከእንግዲህ የሚቀር አንድም ሐጢያት የለም፡፡ ወንጌልን በማመን ሐጢያቶቻችን ስለተደመሰሱና ስለነጹ አሁን ወደ ቅዱስ እግዚአብሄር ቀርበን የእርሱን ዕርዳታ መጠየቅ እንችላለን፡፡ ወደ እግዚአብሄር መጸለይ መቻላችን በእምነታችን ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ አሁን በቅን ልቦቻችን ውስጥ በተለቀቀው ወንጌል በተጨባጭ በማመን የሐጢያትን ስርየት ተቀብለናል፡፡
 
ወንድሞችና እህቶች ወደ ዕጣኑ መሰውያ ቀርባችሁ ሳታቋርጡ ጸልዩ፡፡ ‹‹አባት ሆይ እባክህ እርዳኝ፤ ያለሁበት ሁኔታ ይህ ነው፡፡ የምፈልገውም ይህንን ነው፡፡ እውነተኛውን ወንጌል ማሰራጨትና በጽድቅ መኖር እፈልጋለሁ፡፡ ከልቡ የሐጢያት ይቅርታ እንዳገኘ ሰው ሆኜ በጎ ሕይወትን መኖር እሻለሁ፡፡ የጽድቅ ፍሬዎችንም ማፍራት እፈልጋለሁ፡፡ በአንተ የሚያምን እምነት ስጠኝ፡፡ በአንተ ፈቃድ መሰረት ሕይወቴን መኖር እፈልጋለሁ፡፡›› ጸሎት ማለት አንድ ሰው የሚፈልገውን መጠየቅ ማለት ነው፡፡ በእርሱ ጽድቅ መሰረት የእግዚአብሄርን ዕርዳታ መለመን ማለት ነው፡፡
 
እናንተም ምናልባት የተለያዩ መሻቶችና ፍላጎቶች ይኖሩዋችሁ ይሆናል፡፡ እኛ ባጸደቀን የውሃና የመንፈስ ወንጌል በማመናችን ጻድቃን ስለሆንን አሁን በጸሎታችን ከእግዚአብሄር ዘንድ ሁሉን መጠየቅ ይቻለናል፡፡ እግዚአብሄር እንዲረዳቸው የሚጸልዩ ሰዎች ደስተኞች ናቸው፡፡ አሁን ሁላችንም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የሐጢያቶቻችንን ስርየት ስላገኘን ሁላችንም ወደ እግዚአብሄር መጸለይ እንደምንችል አያጠራጥርም፡፡
 
በእግዚአብሄርና በውሃው በመንፈሱ ወንጌል ባላቸው እምነት የሐጢያት ስርየትን በልቦቻቸው የተቀበሉ ቢያንስ ቅዱስ ወደሆነው አምላክ ቀርበው የእርሱን ዕርዳታ ለመጠየቅ ብቁ ናቸው፡፡ ሕጻን ልጅ ችግር ውስጥ በወደቀ ጊዜ የወላጆቹን ዕርዳታ ፈልጎ እንደሚያለቅስ ሁሉ ዳግመኛ የተወለዱ ምዕመናንም በሙሉ የአብን ረድኤት ፈልገው ያለ ማመንታትና በደመ ነፍስ ለጸሎት ይቀርባሉ፡፡ የሐጢያት ስርየት ያስገኘላቸው እምነታቸው እግዚአብሄርን አባት ብለው እንዲጠሩት ያስቻላቸው እምነት ብቻ ሳይሆን እንደ ራሱ ወንድ ልጆችና ሴት ልጆች ዘወትር የአብን ረድኤት ፈልገው እንዲጸልዩ የሚያስችላቸው እምነት ነው፡፡ እግዚአብሄር በእርግጥም በእምነት አባታችን ስለሆነልን አሁን እንደ ፍላጎታችን በጸሎታችን አማካይነት የእርሱን ረድኤት ለመጠየቅ ብቁ ነን፡፡
 
የሐጢያት ስርየታችሁን ከተቀበላችሁ በኋላ የግል ጸሎቶቻችሁ ምን እንደነበሩ ወይም እግዚአብሄር እንዴት እንደመለሰላችሁ በእርግጥ አላውቅም፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር ከራሱ ቤተክርስቲያን ጋር እንዲያቆራኘንና ወንጌልን እንድናሰራጭ ወደ እግዚአብሄር ስንጸልይ በእርግጠኝነት ጸሎታችንን እንደሚመልስ አውቃለሁ፡፡ ለሌሎች ወደ መጸለይ የምንመጣው በዚህ ሒደት ውስጥ ነው፡፡ በመጀመሪያ ሰው ሁሉ የሚጸልየው ለራሱ የሥጋ ፍላጎቶች ብቻ ነው፡፡ ነገር ግን በመንፈስ ቅዱስ ሥራዎች አማካይነት ለሌሎችም እንድንጸልይ የሚያስቸኩል ነገር እንዳለ ወደ መረዳት እንመጣለን፡፡ በዚህም ሌሎች ነፍሳቶች እንዲድኑና የውሃውና የመንፈሱም ወንጌል በመላው ዓለም እንዲሰራጭ ለጸሎት ራሳችንን እንቀድሳለን፡፡ ለምን? ምክንያቱም ዳግመኛ የተወለዱ ቅዱሳን የሚጸልዩዋቸው ጸሎቶች በመንፈስ ቅዱስ የተመሩ ናቸውና፡፡ ጌታ እንዲህ ሲል ነግሮናል፡- ‹‹አስቀድማችሁ የእግዚአብሄርን መንግሥት ጽደቁንም ፈልጉ፤ ይህም ሁሉ ይጨመርላችኋል፡፡›› (ማቴዎስ 6፡33)
 
ነገር ግን ዳግመኛ በተወለዱት መካከል ገናም በመንፈሳዊ ሁኔታቸው ያልበሰሉት ትክክለኛ ነገሮችን እንዴት በጸሎት እንደሚያቀርቡ አያውቁም፡፡ ምክንያቱም ለጸሎቶቻቸው የእግዚአብሄርን መልሶች አልተለማመዱምና፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት እነርሱ አሁንም ድረስ በእግዚአብሄር ጽድቅ ውስጥ ያለ እምነት ምን ያህል ብርቱ እንደሆነ አያውቁምና፡፡ እምነተ ጎዶሎ የሆኑ ሰዎች ጸሎቶቻቸው ይመለሱ ወይም አይመለሱ እንደሆነ የማያውቁ ብቻ ሳይሆኑ በጥርጣሬዎችም ግራ የተጋቡ ናቸው፡፡
 
ስለዚህ ከእነርሱ ቀደም ብለው ካመኑት ጋር አብረው መጸለይ አለባቸው፡፡ በእምነት ያልበሰሉ ሰዎች ወደ እግዚአብሄር ለመጸለይ ያመነታሉ፡፡ በሚጸልዩበት ጊዜም የሚጠይቁት የሚፈልጉትን ብቻ ነው፡፡ ‹‹ስጠኝ፤ ስጠኝ፤ ስጠኝ›› ይላሉ፡፡ ነገር ግን በእምነት ያልጠነከሩት በእግዚአብሄር ላይ ትልቅ እምነት ባይኖራቸውም ከቤተክርስቲያን ጋር ቢቆራኙ እውነተኛ ጸሎት ምን እንደሆነ መማር ይችላሉ፡፡ ምክንያቱም በቤተክርስቲያን ውስጥ ከእነርሱ ቀድመው የገቡ የእምነት አጋሮቻቸው ስለ እግዚአብሄር ይጸልያሉና፡፡ መንፈስ ቅዱስ ከቤተክርስቲያን ጋር ለተቆራኙ የእምነትን ጸሎት ስለሚሰጥ ቀስ በቀስ የእግዚአብሄርን ጽድቅ ለማግኘት ይጸልያሉ፡፡ ‹‹የጻድቅ ሰው ጸሎት በሥራዋ እጅግ ሐይል ታደርጋለችና፡፡›› (ያዕቆብ 5፡16)
 
በእግዚአብሄር ፊት ለመጸለይ መብት ያላቸው ዳግመኛ የተወለዱ ሰዎች የሚጸልዩት የታመነ ጸሎት እጅግ ሐይል አለው፡፡ በእግዚአብሄር እምነት ያላቸው ሰዎች የሚጸልዩዋቸው ጸሎቶች በእርግጥም ከእግዚአብሄር ዘንድ ምላሽን ያገኛሉ፡፡ ምክንያቱም አብ ጸሎቶቻቸውን ይመልስ ዘንድ በመጀመሪያ እግዚአብሄር አባታቸው መሆኑንና ጸሎቶቻቸውንም እንደ እምነታቸው መጠን በትክክል እንደሚመልስ ማመን አለባቸው፡፡ ስለዚህ የእምነት ፋና ወጊዎች በአንድነት ተባብረው የእነርሱን ዱካዎች የሚከተሉት ለወንጌል ስርጭት የጽድቅ ሥራዎች በሚጸልዩበት ጊዜ ታላላቅ ሥራዎችን ይለማመዳሉ፡፡ በእግዚአብሄር ከሚያምኑት የእምነት ፋና ወጊዎቻችሁ ጎን ስትቆሙ በእምነታችሁ በአያሌው ትበረታላችሁ፡፡ እግዚአብሄር በደህንነት ጸጋ ላይ ብቻ ሳይሆን በሌሎች የሕይወት ምዕራፎች ላይም ብዙ ዕርዳታ እንደሚያስፈልገን ስለሚያውቅ ጸሎቶቻችንን ይመልሳል፡፡ ሁላችንም ከእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ጋር የሚቆራኝ እምነት የሚያስፈልገን ለዚህ ነው፡፡
 
እግዚአብሄርን ስለሚያስደስቱ ነገሮች ስንጸልይ እምነታችን በአያሌው ይጠነክራል፡፡ ጸሎትን የሚኮርጁ መንፈሳዊ ልጆች ውለው አድረው እነዚህን ጸሎቶች የራሳቸው አድርገው በመውሰድ እንደሚበስሉ ሁሉ እኛም እንደዚሁ ወደ በኋላ ስለ ችግሮቻችንን ወደ እግዚአብሄር አብ መጸለይ እንችላለን፡፡ ይህንን በማድረግ ከልባቸው በእግዚአብሄር የሚያምኑ ትክክለኛውን እውነት በመከተል በጎዳናው ላይ በእምነት ይራመዳሉ፡፡ ጻድቅ የሚኖረው በእምነት ብቻ እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ስለሚነግረን እነርሱ ለሌሎች ነፍሳት ደህንነት እንጂ ለራሳቸው ብቻ አይኖሩም፡፡
 
ወደ እግዚአብሄር የምንጸልይበትን ብቃት እንዴት አገኘነው? ያገኘነው በእግዚአብሄር በተሰጠው የውሃና የመንፈስ ወንጌል አምነን ዳግመኛ በመወለድ ነው፡፡ ወደ እግዚአብሄር አብ መጸለይ የሚያስችል ደፋር እምነት የሚሰጠው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን የሐጢያት ስርየት ላገኙት ብቻ ነው፡፡ እምነት የእግዚአብሄር ስጦታ ነው፡፡ የመጸለይን ብቃት ማግኘት ማለት ከእግዚአብሄር ዘንድ ታላቅ በረከት ማግኘት ማለት ነው፡፡
 
በዚህች ፕላኔት ላይ ከሚኖሩት ብዙ ክርስቲያን ምዕመናን መካከል እንዲህ ባለ እምነት ለመጸለይ ብቃት ያላቸው ምን ያህሎቹ ናቸው ብላችሁ ታስባላችሁ? ብዙ አይደሉም! ከእግዚአብሄር እጅግ ብሩክ ስጦታዎች አንዱ ከሁሉ በፊት በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ በተገለጠው እውነት አማካይነት ከሐጢያቶቻችን ያዳነን እምነት ማግኘታችን ነው፡፡ ሁለተኛው የእርሱ ልጆች ሆነን ወደ እግዚአብሄር ለመጸለይ ሥልጣንና ብቃት መቀበላችን ነው፡፡ ሦስተኛው የእግዚአብሄር ሰራተኞች ሆነን እንድንኖር የሚፈቅድልንን እምነት ማግኘታችን ነው፡፡
 
 

እግዚአብሄር የሐጢያተኞችን ጸሎቶች አይመልስም፡፡ 

 
አንዳንድ ሐጢያተኞች በኢየሱስ እናምናለን ብለው ተራራ ላይ ወጥተው የጌታን ስም ያለ ማቋረጥ በጩኸት በመጥራት ሐጢያቶቻቸውን እንዲደመስስላቸው ወደ እግዚአብሄር ይጸልያሉ፡፡ ቀዝቃዛና ነፋሻማ በሆኑ ሌሊቶችም ሳይቀር ሰውነታቸውን ከላስቲክ በተሰሩ አንሶላዎች ሸፍነው አሁንም ወደ ተራራ ይወጣሉ፡፡ ብዙውን ጊዜ በፍርሃት የተሞሉ ቢሆኑም ባለ በሌለ ሐይላቸው ሁሉ በትጋት ይጸልያሉ፡፡ ነገር ግን ጸሎቶቻቸው ባዶ በሆነው ሕዋ ውስጥ ያለ ዋጋ ይሽከረከራሉ፡፡
 
ሌሊቱን በሙሉ ቢጸልዩም እግዚአብሄር በእርግጥም ጸሎቶቻቸውን እንደሚመልስላቸው አያምኑም፡፡ እምነተ ጎዶሎ ሆነው በትጋት የሚጸልዩት ጸሎቶቻቸውን ለሰዎች እንደ አውደ ርዕይ ለማሳየት ስለሚፈልጉ ነው፡፡ ጸሎቶቻቸው መልስ የሌላቸው ጸሎቶች ናቸው፡፡ እንዲያውም ጸሎቶቻቸው ወደ እግዚአብሄር እንደማይደርሱ በሕሊናቸው ያውቃሉ፡፡ ምክንያቱም አሁንም ድረስ በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት አለባቸው፡፡ ገና የሐጢያቶቻቸውን ስርየት ስላልተቀበሉ ምንም ያህል ቢጸልዩ፣ ቢጮሁ፣ ቢያለቅሱ፣ ላንቃቸው እስኪሰነጠቅ ድረስ ቢንጫጩና የሚፈልጉትን ለማግኘት ሲሉ እግዚአብሄርን ለመለመን ሁሉን ቢያደርጉ ለብዙ ጸሎቶቻቸው ምላሽ አያገኙም፡፡
 
እነርሱ ማወቅ የሚያስፈልጋቸው ነገር ቢኖር ወደ እግዚአብሄር ለመጸለይ ቅድመ መስፈርቱ በመጀመሪያ የሐጢያት ስርየትን መቀበል ብቻ ነው፡፡ ነገር ግን ብዙዎቹ ሐጢያተኞች የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ወደ ማወቅ እስኪደርሱ ድረስ አማራጭ ስለሌላቸው ሐጢያተኞች ሆነው የእምነት ሕይወታቸውን ከመኖር በስተቀር ሊያደርጉት የሚችሉት ነገር የለም፡፡ ሰዎች በጌታ የተሰጠውን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በልቦቻቸው በማመን ለአንዴና ለመጨረሻ ካልነጹ ጸሎቶቻቸው በሙሉ በእርግጥም ከንቱ ናቸው፡፡ ሐጢያተኞች ወደ እግዚአብሄር ለመጸለይ በሚሞክሩበት ጊዜ ሁሉ ሕሊናቸው ‹‹ጸሎቶችህ ወደ እግዚአብሄር ይደርሳል ብለህ ታስባለህን? ማለምህን ቀጥል! ሁሉም ከንቱ ናቸው!›› በማለት ይጮሃል፡፡ ‹‹ይህንን ስጠኝ፤ ያንን ስጠኝ›› እያሉ ወደ እግዚአብሄር መጸለያቸውን ቢቀጥሉም እንኳን ጸሎቶቻቸው በተጨባጭ ከንቱ ናቸው፡፡
 
‹‹ወደ እኔ ከመጸለይህ በፊት በመጀመሪያ የሐጢያቶችህን ስርየት ተቀበል፡፡›› የእግዚአብሄር ፈቃድ ይህ ነው፡፡ የሐጢያት ስርየትን ያላገኙ ሰዎች ወደ እግዚአብሄር በሚጸልዩበት ጊዜ ልምዳቸውና ሕሊናቸው ከእሳቤያቸው ጋር እንደማይስማማ ይገነዘባሉ፡፡ ሐጢያተኞች ሲጸልዩ፡- ‹‹ጌታ ሆይ ይህንን ስጠኝ፤ ያንንም ደግሞ ስጠኝ›› ማለታቸውን አያቆሙም፡፡ ነገር ግን ጸሎቶቻቸው መልስ የላቸውም፡፡ ከዚህ ርቆ ሕሊናቸው የሚነግራቸው ‹‹ይቅርባችሁ! ጸሎቶቻችሁ መልስ አያገኙም፡፡ ምክንያቱም ሐጢያተኞች ናችሁና!›› የሚለውን ብቻ ነው፡፡ ሐጢያተኞች የራሳቸውን ሕሊና እየተቆጣጠሩ እንኳን እምነታቸውን ማለዘብ የማይችሉ ከሆነ እግዚአብሄርን እንዴት ሊያታልሉት ይችላሉ? እርሱስ እንዴት ሊቀበላቸው ይችላል? ጸሎቶቻቸውስ እንዴት ሊመለሱ ይችላሉ? ሐጢያተኞች በአጭሩ ወደ እግዚአብሄር ለመጸለይ የበቁ አይደሉም፡፡ የራሳቸው ልቦች እንኳን በጸሎቶቻቸው አያምኑም፡፡
 
 

ጸሎቶቻችን መልስ ማግኘት የሚጀምሩት በእምነት ጻድቃን ስንሆን ነው፡፡ 

 
ከዚህ ቀደም ሐጢያተኞች የነበሩ የብዙዎች ጸሎቶች ምላሽ ማግኘት የሚጀምሩት በመገናኛው ድንኳን ሰማያዊ፣ ሐምራዊና ቀይ ማግ በተገለጠው የውሃና የመንፈስ ወንጌል በማመን የሐጢያቶቻቸውን ስርየት እንደተቀበሉ ወዲያውኑ ነው፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ከሙሉ ልባቸው የሚያምኑ በራሳቸው ብቁዓን ላይሆኑ ይችላሉ፤ ነገር ግን በእምነት ወደ እግዚአብሄር መቅረብ ይችላሉ፡፡ በእምነትም የሚፈልጉትን እንዲሰጣቸው በመለመን በድፍረት ወደ እርሱ መጸለይ ይችላሉ፡፡ የሐጢያት ስርየታቸውን በእምነት ያገኙ እንደ ፈቃዱ ወደ እግዚአብሄር ሲጸልዩ በድፍረት ይጸልያሉ፡፡
 
ነገር ግን ስለ ሥጋቸው በሚጸልዩበት ጊዜ አንዳንዴ ጥሩ ስሜት አይሰማቸውም፡፡ እኛ ጻድቃኖች ለውሃውና ለመንፈሱ ወንጌል መሰራጨትና ለሌሎች ነፍሳቶች በምንጸልይበት ጊዜ እጅግ ደስተኞች ነን፡፡ ወንጌል በሥጋ እንቅፋት ሳይጠመድ በብርቱ ሁኔታ እንዲሰራጭ በምንጸልይበት ጊዜ ያኔ በእምነት ጸሎቶች አማካይነት ያገዱንን እንቅፋቶች ማሸነፍ እንችላለን፡፡ አንዳንዴ ግን እንዲህ ያሉትን እንቅፋቶች በእምነት ማሸነፍ ሲያቅተን እንረበሻለን፡፡ እንዲህ ባለ ጊዜ ማድረግ የምንችለው ነገር ቢኖር እግዚአብሄር ውሎ አድሮ ምላሽ እንዲሰጥ መጸለይና ማመን ነው፡፡ ይህ ጸሎት በእርግጥም ከእግዚአብሄር ዘንድ ምላሽ እንደሚያገኝ በወቅቱ በእርግጠኝነት እናያለን፡፡
 
እኛ ማድረግ ያለብን መጸለይና መጠበቅ ነው፡፡ ጸሎቶቻችን ለምን አሁኑኑ አልተመለሱም በማለት መብሰክሰክ የለብንም፡፡ እግዚአብሄር በእምነት እንድንጸልይ ይፈልጋል፡፡ ጊዜው ሲደርስም መልስ ይሰጣል፡፡ የሐጢያት ስርየትን በእምነት ስንቀበልና በሕይወታችንም በእምነት ስንጸልይ ብዙዎቹ ጸሎቶቻችን በእርግጥም ምላሽ እንዳገኙ ከግል ልምዳችን እናያለን፡፡
 
ነገር ግን ልክ እንደዚህ በእምነት ኖራችኋልን? እንደዚያ ከሆነ ከልባችሁ ወደ እግዚአብሄር መጸለይ ትችላላችሁ፡፡ ራሳችንን ደግመን ስንመረምር ለሲዖል የታጨን እንደነበርን እንገነዘባለን፡፡ ለጸሎት ብቁ መሆን የምንችለውም በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ላይ ባለን እምነት አማካይነት የሐጢያት ስርየትን በመቀበል ብቻ እንደሆነ ደግመን እንረዳለን፡፡ ስለዚህ መጸለይ የሚችሉት ጌታ የዕድሜ ዘመናቸውን ሐጢያቶች በሙሉ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የደመሰሰላቸው መሆኑን በማመን የሐጢያት ስርየትን ያገኙ መሆናቸውን በእርግጠኝነት አስታውሱ፡፡
 
ገና ዳግመኛ ባልተወለዱት መካከል በራሳቸው የሚታበዩ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ እናንተስ? የምትታበዩበት አንዳች ነገር አላችሁን? ክንዶቻችሁ ጠንካሮች ናቸውን? ሰውነታችን ምንም ያህል ጠንካራ ቢሆንም የጉንፋን ቫይረሶችን እንኳን መቋቋም አይችልም፡፡ እውነተኛ ድካሙን የሚያጋልጠውን በጥቂቱ ጠንካራ የሆነ ማንኛውንም አካላዊ ጉልበትም መቋቋም አይችልም፡፡ ሰብዓዊ ፍጡራን ምን ያህል ደካሞች እንደሆኑ ታውቃላችሁን? አንዲት የወባ ትንኝ ብትነድፈን እንሞታለን፡፡ ወይም በጉዞ ላይ እያለን በተወረወረ ድንጋይ ብንመታ እንሞታለን፡፡ አንድ ሰው ኩራታችንን የሚያቆስል አንድ ሐረግ ቢናገር ልቦቻችን በጣም ስለሚጎዱ በከፊል እንሞታለን፡፡ ነገሩ እንዲህ አይደለምን? በእርግጥም ነው!
 
60 ዓመት ሳይሞላቸው እንኳን ምን ያህል ሰዎች ይሞታሉ? 30 ዓመት ሳይሞላቸው እንኳን የሚሞቱ እጅግ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ሰብዓዊ ፍጡራን ይህን ያህል ደካማ ፍጥረታት ናቸው፡፡ ዘላለማዊ ጉልበት ያላቸው ሰብዓዊ ፍጡራን የትም ቦታ አይገኙም፡፡ እንዲህ ያሉ ደካማ ፍጡራን ልቦቻቸውን አደንድነው ከሙሉ ልባቸው የእግዚአብሄርን ቃል አለማመን ይገባቸዋልን? ሰብዓዊ ፍጡራን የሚታበዩበት ምንም ነገር የላቸውም፡፡ ጠንካሮች ስለመሆናቸውም ማስመሰል አይችሉም፡፡
 
ስለዚህ ድካሞቻችንን በመገንዘብና አለመብቃቶቻችንንና ሐጢያቶቻችንን በማወቅ በልቦቻችን በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ አማካይነት በተፈጸመው የእውነት ወንጌል በማመን ወደ እግዚአብሄር ለመጸለይ ብቃትን ማግኘት አለብን፡፡ በእግዚአብሄር ማመን አለብን፡፡ እግዚአብሄር የሚደሰትበትን ይህንን እምነት ከሙሉ ልብ ለማግኘት ሰዎች በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ማመን አለባቸው፡፡ ነገር ግን አሁንም ድረስ በዚህ የማያምኑ ብዙዎች አሉ፡፡ ከዚህ የውሃና የመንፈስ ወንጌል ውጭ ወደ እግዚአብሄር የምትጸልዩበትን መብት ከሌላ ወንጌል ማግኘት ችላችኋልን? ኢየሱስ ወደዚህ ምድር መጥቶ ስለ እናንተ ሲል በመጠመቅ ሐጢያቶቻችሁን ባይወስድ ኖሮ ሐጢያቶቻችሁ መደምሰስ ይችሉ ነበርን? ኢየሱስ በተቀበለው ጥምቀት ሳታምኑ የልቦቻችሁን ሐጢያቶች ወደ ኢየሱስ ማሻገርና ማስወገድ ይቻላችሁ ነበርን?
 
መልሶቹ አይሆንም፣ አይሆንም፣ በፍጹም አይሆንም! የሚሉት ናቸው፡፡ ኢየሱስ የተሰቀለውና በደሙ የሐጢያቶቻችን ኩነኔ ሁሉ የተሸከመው የዓለምን ሐጢያቶች ከዮሐንስ በተቀበለው ጥምቀቱ ስለተሸከሙ ነበር፡፡ ታዲያ ያለ ኢየሱስ ጥምቀትና መስቀል መዳን ትችሉ ነበርን? በእርግጥ አትችሉም! ኢየሱስ የተጠመቀው ሐጢያቶቻችንን ለአንዴና ለመጨረሻ ለመውሰድ፣ ለማስወገድና ሐጢያቶቻችንን ለማንጻት ነው፡፡ እርሱ የተሰቀለው የሐጢያቶቻችንን ቅጣት ለመሸከም ነበር፡፡ ከሐጢያቶቻችን ሁሉ የነጻነው በዚህ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል እውነት በማመን ነው፡፡
 
በዚህም በማናቸውም ጊዜ ወደ እግዚአብሄር ቀርበን ‹‹አቤቱ እኔ ይህን ያህል ብቁ ያይደለሁ ነኝ፡፡ ነገር ግን በውሃህና በደምህ ስላዳንከኝ አሁን ሐጢያት አልባ ነኝ፡፡ አንተ ወደዚህ ምድር መጥተህ በመጠመቅ በአንድ ጊዜ ሐጢያቶችን በሙሉ ወሰድህ፡፡ እነዚህንም የዓለም ሐጢያቶች በመስቀል ላይ ተሸከምህ፡፡ ስለ እነርሱም ተቀጣህ፡፡ ዳግመኛም ከሙታን ተነሳህ፡፡ አቤቱ ይህንን በማድረግ በእርግጥም የደህንነቴ አምላክ ሆነሃል፡፡ በአንተ የማምነው በዚህ እውነት በማመኔ ነው›› በማለት በድፍረት እንመሰክራለን፡፡ በሌላ አነጋገር እምነታችን ስንጠብቅ ብቁ ባንሆንም ሁልጊዜም ወደ እግዚአብሄር ቀርበን መጸለይ እንችላለን፡፡ ለመንግሥቱ መስፋፋት መጸለይ እንችላለን፡፡ ለወንድሞቻችንና ለእህቶቻችን መጸለይ እንችላለን፡፡ ገና የሐጢያት ስርየትን ላልተቀበሉ ሌሎች ነፍሳቶች መጸለይ እንችላለን፡፡
 
ሰዎች ከሰማያት በታች ሁልጊዜም ያለ ሐፍረት መኖር የሚችሉት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ሲያምኑ ብቻ ነው፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ሰዎች በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል እምነት ሳይኖራቸው ክፍተቱን በሌላ አንዳች ነገር ለመሙላት ይሞክሩ ይሆናል፡፡ እንደዚህ ያሉ ጥረቶች ፈጽሞ ዋጋ እንደሌላቸው መረዳት ይኖርባችኋል፡፡ ልቦቻቸው ተጨንቀውና ተሰቃይተው ሕይወታቸውን አስከፊ ያደረጉባቸው ለዚህ ነው፡፡ እያንዳንዱ ሰው በእውነትም ይሁን በውሸት በሆነ አንድ ነገር ማመን ይፈልጋል፡፡ ራሳችሁን መርምሩ፡፡
 
በእርግጥ የውሃውንና የመንፈሱን ወንገል በሚያምን እምነት ጌታን ታምኑ እንደሆነ ወይም በዚህ የውሃና የመንፈስ ወንጌል አታምኑ እንደሆነ ለማወቅ ራሳችሁን መርምሩ፡፡ ጌታ በውሃውና በደሙ ሐጢያቶቻችሁን ደምስሶዋል፡፡ በዚህ የምታምኑ ከሆነ አሁንም በልቦቻችሁ ውስጥ ሐጢያት ይኖራልን? በዚህ የውሃና የመንፈስ ወንጌል ከሙሉ ልባችሁና መንፈሳችሁ የምታምኑ ከሆነ ፈጽሞ ሐጢያት ሊኖር አይችልም፡፡ በዚህ እውነት ከሙሉ ልባችሁ በማመን አሁኑኑ የሐጢያቶቻችሁን ስርየት ተቀበሉ፡፡
 
እግዚአብሄር በሰማያዊው፣ በሐምራዊው፣ በቀዩ ማግና በጥሩው በፍታ በተገለጠው እውነት አማካይነት የሐጢያት ስርየትን ስለሰጠን አሁን ይህንን የሐጢያት ስርየት ተቀብለናል፡፡ ከዚህ የተነሳ በዚህ እውነት የሚያምኑ ወደ እርሱ መቅረብ የሚያስችላቸውን ጸጋ ለብሰው የራሱ የእግዚአብሄር ልጆች ሆነዋል፡፡ ስለዚህ እስከ መጨረሻው ድረስ እርስ በርሳችን መዋደድና የእርስ በርሳችንን አለመብቃቶች መረዳትና የእግዚአብሄርን ሥራዎች መስራትና ከዚያም ወደ እርሱ ቀርበን በፊቱ መቆም ይኖርብናል፡፡
 
የሐጢያት ስርየትን የተቀበሉ ሰዎች ሐጢያተኞችን ይወዳሉ፡፡ የጻድቃን ልብ እያንዳንዱ ሐጢያተኛ በሰማያዊው፣ በሐምራዊውና በቀዩ ማግ የተገለጠውን እውነት እንዲያውቅና ዳግመኛ እንዲወለድ ይሻል፡፡ ነገር ግን ሰዎችን በተጨባጭ መውደድ የማይችል የሆነ ሕዝብ አለ፡፡ እነዚህ አንገተ ደንዳና ሐጢያተኞች ናቸው፡፡ እነዚህ የእምነት ሕሊናቸውን የሳቱና ገናም ሐጢያተኞች ሆነው ሳሉ በእግዚአብሄር እናምናለን ብለው በማሰብ ራሳቸውን ያታለሉ ክርስቲያኖች ናቸው፡፡
 
የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በማመንና የሐጢያትን ስርየት በልቦቻችን ውስጥ በመቀበል ሁላችንም የእምነት ሕሊናችንን በመጠበቅና እምነታችንን ባለማጣት እስከ መጨረሻው ድረስ ሩጫችንን በሚገባ እንሩጥ፡፡ አንድ ሰው በመንፈሳዊ ሁኔታው በችግር ውስጥ የሚያልፍ ሲመስለን እርስ በርሳችን በመረዳዳት እርስ በርሳችን በጽናት እንቁም፡፡ ምንም ነገር ቢመጣ ጻድቃን ቤተክርስቲያንን መልቀቅ የለባቸውም፡፡ ጻድቃን የእግዚአብሄርን ቤተክርስቲያን ትተው ሲወጡ ወዲያውኑ ይሞታሉ፡፡ የእግዚአብሄርን ቤተክርስቲያን ትቶ መውጣት የራሳችሁን ቤት እንደ ማጣት ነው፡፡ የራሳችሁን ቤት ማጣት ማለት መሸሸጊያችሁን ማጣት ማለት ነው፡፡ ከዚህ የተነሳ ልቦቻችሁ በየትም ስፍራ ዕረፍትንና መጽናናትን አያገኙም፡፡ በመጨረሻም ትሞታላችሁ፡፡
 
የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን የእርሱ በጎች የሚመገቡባት፣ ዕረፍትና እፎይታ የሚያገኙባት ስፍራ ነች፡፡ ስለዚህ በጎቹ ጉልበት ሲያንሳቸውና በጣም ሲዳከሙ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያን ቃሉን በመስማት ልቦቻቸው እንዲበረቱ ታግዛቸዋለች፡፡ ቃሉን በልቦቻችሁ በማመን ስትቀበሉ በውስጣችሁ ያለው መንፈስ ቅዱስ ይደሰታል፡፡ ልባችሁም ደግሞ ይበረታል፡፡ በመጨረሻም የዘላለምን ሕይወት ትቀበላላችሁ፡፡
 
ጻድቃን የሆንን ሁላችን እግዚአብሄርን እናመሰግናለን፡፡ ለመጸለይ ብቁ እንሆን ዘንድ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ስለሰጠን ጌታን እናመሰግነዋለን፡፡ ሐሌሉያ! በእርሱ መታመን እንድንችልና በእምነት እንድንኖር ወደ ሕያው አምላክ እጸልያለሁ፡፡