Search

ስብከቶች፤

ርዕስ 10፡ ራዕይ (በራዕይ ላይ የተሰጡ ሐተታዎች)

[7-2] የተጋድሎ እምነት ይኑረን፡፡ ‹‹ ዮሐንስ ራዕይ 7፡1-17 ››

የተጋድሎ እምነት ይኑረን፡፡
‹‹ ዮሐንስ ራዕይ 7፡1-17 ››
 
የዘመኑ ክርስቲያኖች የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት በትክክል ማወቅ አለባቸው፡፡ በተለይ በራዕይ ቃል አማካይነት የቅዱሳንን ንጥቀት ትክክለኛ መረዳት ማግኘትና በትክክለኛ እምነት መኖር ይገባናል፡፡ 
 
በመጀመሪያ ንጥቀት የሚሆነው በሰባቱ ዓመት ክፍለ ጊዜ ውስጥ የመጀመሪያውን ሦስት ዓመት ተኩል ጥቂት አልፎ በታላቁ መከራ አጋማሽ ላይ መሆኑን መረዳት አለብን፡፡ ስለዚህ ቤተክርስቲያኖችና ቅዱሳን እግዚአብሄር በኢየሱስ ክርስቶስ እንዳቀደው የሰውን ዘር ከሐጢያት ለማዳንና የዘላለምን ሕይወት ለመስጠት ያለውን ፈቃድ ይፈጽሙ ዘንድ በመጨረሻው ዘመን የሚጋደል እምነት ሊኖራቸው ይገባል፡፡ 
 
እግዚአብሄር የጸረ ክርስቶስን ተግባሮች የፈቀደው ይህንን ፈቃዱን ለመፈጸም ነው፡፡ ጸረ ክርስቶስ በብርቱ የሚሰራበት ክፍለ ጊዜ የሰባቱ ዓመት ታላቁ መከራ ሦስት ዓመት ተኩል ነው፡፡ እግዚአብሄር ጸረ ክርስቶስ በዚህ ክፍለ ጊዜ ወቅት ሥራውን በትጋት እንዲሰራ ፈቅዶለታል፡፡ ለምን? ምክንያቱም እግዚአብሄር ለእኛ ያቀዳቸውን ታላላቅ ዓላማዎቹን ለመፈጸም ሰይጣንን በጥልቁ ጉድጓድ ውስጥ ማሰር አለበትና፡፡ ይህንን ለማድረግም ጌታ ራሱ በአካል ወደዚህ ምድር መምጣት አለበት፡፡ አምላካችን ጸረ ክርስቶስ በሰባቱ ዓመት ታላቅ መከራ ወቅት በመጀመሪያዎቹ ሦስት ዓመታት ውስጥ ተግባሮቹን በሐይል እንደሚፈጽም የሚፈቅድለት ለዚህ ነው፡፡ 
 
እግዚአብሄር ለእያንዳንዱ ሰው ከሐጢያት የሚድንበትን ቃልና የዘላለምን ሕይወት ሰጥቷል፡፡ ይህንን ቃል ለመፈጸምም ታላቁን መከራ አቀደ፡፡ በዋናው ምንባብ ላይ እንዲህ ተጽፎዋል፡፡ ‹‹ከዚህ በኋላም በአራቱ በምድር ማዕዘን ቆመው አራት መላዕክት አየሁ፡፡ እነርሱም ነፋስ በምድር ቢሆን ወይም በባሕር ወይም በማንም ዛፍ እንዳይነፍስ አራቱን የምድር ነፋሳት ያዙ፡፡›› እግዚአብሄር ከእስራኤል ሕዝብ 144,000 የሚሆኑትን ከጥፋታቸው ለማዳን አቅዶዋል፡፡ ምክንያቱም ለአብርሃም አምላኩና የዘሮቹ አምላክ እንደሚሆን ተስፋ ሰጥቶዋልና፡፡ እግዚአብሄር ይህንን ተስፋ ለመፈጸም የደህንነት ጸጋውን ለእስራኤል በመለገስ በመጨረሻው ዘመን የአብርሃም ዘሮች የሆኑትን 144,000 ያድናል፡፡ 
 
እግዚአብሄር ለቅዱሳን የሺህ ዓመት መንግሥቱንና አዲስ ሰማይና ምድር ለመስጠት በዚህ ምድር ላይ ታላቁ መከራ እንዲመጣ በእርግጠኝነት ይፈቅዳል፡፡ እግዚአብሄር በታላቁ መከራ ወቅት የጸረ ክርስቶስን ዘመን ከፈቀደ በኋላ ሰይጣንን ይይዘውና በጥልቅ ጉድጓድ ውስጥ ይዘጋበታል፡፡ እግዚአብሄር ጸረ ክርስቶስና ታላቁ መከራ እንዲመጣ የሚፈቅደው እስራኤልን ለማዳን የገባውን የተስፋ ቃል ለመፈጸምና በታላቁ መከራ ውስጥ ነጭ ልብስ ለሚለብሱት አሕዛቦች የዘላለም ሕይወት የመለገስ ጸጋውን ለመስጠት ነው፡፡
 
ስለዚህ ታላቁ መከራና የጸረ ክርስቶስ ንግሥና እኛ ሳንሳሳት ልናልፍባቸው የሚገቡን ደረጃዎች ናቸው፡፡ እግዚአብሄር የፈቀዳቸው እነዚህ ነገሮች ሁሉ ሁላችንንም ለማዳንና በክርስቶስ መንግሥት ውስጥም ዘላለማዊ በሆነው የሕይወት ጸጋ ሊሸፍነን ያቀደበት ዕቅዱ ክፍል ናቸው፡፡ ስለዚህ አሁን በየትኛው ዘመን ላይ እየኖርን እንደሆነ በትክክል መለየትና በመኖር ለመቀጠልም ምን ዓይነት እምነት ሊኖረን እንደሚገባ ራሳችንን መጠየቅ አለብን፡፡ በአጭሩ እምነታችን ግልጽና እርግጠኛ መሆን አለበት፡፡ 
 
እኛ በእግዚአብሄር ቃል እናምናለን፡፡ ይህ ቃል በሙሉ በአካልም በመንፈስም እንደሚፈጸም እናምናለን፡፡ ይህ ዘመን ወደ መጨረሻው ዘመን እየሮጠ ያለ ዘመን ነው፡፡ በመጨረሻው ዘመን ጸረ ክርስቶስና ብዙ ተከታዮቹ ሲነሱ እምነታችንን ለመጠበቅ ስንል ሕይወታችንን ሰማዕት አድርገን እስከ መስጠት ድረስ ልንዋጋቸው ይገባናል፡፡ ይህ ዘመን በጣም እየቀረበን ነው፡፡ በቃሉ የምናምን ከሆንን ታላቁን ጠላት ጸረ ክርስቶስንና ተከታዮቹን መዋጋት አለብን፡፡ የሚጋደል እምነት ይህ ነው፡፡
 
መጋደል ማለት መዋጋት ማለት ነው፡፡ መዋጋት ስል አካላዊ ጥቃት፣ መምታት ወይም ማነካከት ማለቴ አይደለም፡፡ እዚህ ላይ ተጋድሎ ማለት ጌታ የሰጠንን የደህንነት ወንጌል የሚቃወመውንና ምዕመናንን በሚያሳድደው የሰይጣን አገልጋይ በጸረ ክርስቶስ ሥር ሳያጎበድዱ እምነትን መጠበቅ ማለት ነው፡፡ በመጨረሻው ዘመን ሰማዕት የሚሆኑ ሰዎች የኢየሱስ ምስክር ያላቸውና የእግዚአብሄርን ቃል የጠበቁ ሰዎች ናቸው፡፡ የሚመሰክሩት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የመጣውን ኢየሱስን ነው፡፡
 
መጋደል ማለት የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል መጠበቅ ማለት ነው፡፡ ይህንን ወንጌል ለመጠበቅ ጌታ በሰጠው የውሃና የመንፈስ ወንጌል በማመን ዳግመኛ የተወለዱ ሰዎች ዳግመኛ በተወለዱ የእግዚአብሄር ቤተክርስቲያኖች ውስጥ ከሌሎች ዳግመኛ የተወለዱ ሰዎች ጋር መተባበር አለባቸው፡፡ እምነታችንን ለሌሎች ለማሰራጨትና ነፍሳቸውን ለማዳን በማይታጠፍ ውሳኔ ተጋድሎው ውስጥ በጀግንነት ለመግባት ቆራጦች መሆን አለብን፡፡ ሙሉ በሙሉ ለተጋድሎ መዘጋጀት ማለት እምነታችንን መጠበቅና ሌሎች ነፍሳቶችን ማዳን ማለት ነው፡፡ ይህ የቤተክርስቲያን እምነት እግዚአብሄርን የሚያስደስት ወደ ድል የሚመራ መንገድ ነው፡፡ የእግዚአብሄር አገልጋዮችና የእርሱ ቅዱሳን ሁልጊዜም የተጋድሎ እምነታቸውን መጠበቅ አለባቸው፡፡ 
 
ለተጋድሎ ዝግጁ በሆነ አእምሮና እምነት ልንኖርበት የሚገባን የዛሬው ዘመን እንዴት ነው? የአሁኑ ዘመን በብዙ ለውጦች ውስጥ በግልጽ ያልፋል፡፡ ንጥቀትንና የክርስቶስን ዳግመኛ ምጽዓት የሚመለከቱ ብዙ ‹‹ጽንሰ አሳቦች›› ብቅ ብለው ጠፍተዋል፡፡ ከእነርሱም ጋር አብሮ የሰዎችም እምነት እንደዚሁ ሲለዋወጥ ቆይቷል፡፡
 
በ1800ዎቹ መግቢያ ላይ አዲስ የንጥቀት ጽንሰ አሳብ ተቀባይነት ከማግኘቱ በፊት ሁሉም ሰው ክርስቶስ የሚመጣው ቅዱሳን በታላቁ መከራ ውስጥ ካለፉ በኋላ ነው፤ ንጥቀታቸውና ትንሳኤያቸው የሚሆነውም በዚህ ክርስቶስ በሚመለስበት ዘመን ላይ ነው ብሎ በሚከራከረው የድህረ መከራ ንጥቀት ሲያምንና ሲሰብክ ነበር፡፡ ነገር ግን በ1800ዎቹ መግቢያ ላይ ቀስ በቀስ ተቀባይነት ያገኘው የቅድመ መከራ ንጥቀት ጽንሰ አሳብ የድህረ መከራ ንጥቀት ጽንሰ አሳብን ሙሉ በሙሉ ገለበጠው፡፡
 
የቅድመ መከራ ንጥቀት ጽንሰ አሳብ በኢየሱስ የሚያምኑ ምዕመናን የሰባቱ ዓመት ታላቅ መከራ ከመጀመሩ በፊት ወደ ሰማይ ይነጠቃሉ ሲል ይከራከራል፡፡ ይህ ጽንሰ አሳብ ከመነሻው በብዙዎች ዘንድ ተቀባይነት ባያገኝም አሁን ግን ከጥቂቶች በቀር ሁሉም ሰው በቅድመ መከራ ንጥቀት ጽንሰ አሳብ የሚያምን ሆንዋል፡፡ ነገር ግን የቅድመ መከራ ንጥቀት ጽንሰ አሳብ ከእግዚአብሄር ቃል ጋር ፈጽሞ የማይስማማ ብቻ ሳይሆን የእግዚአብሄርን ቃልና ዕቅዱንም ትርጉም አልባ የሚያደርግ ነው፡፡ ሆኖም መጽሐፍ ቅዱስን በማያውቁ ሰዎች አስተሳሰቦችና አእምሮዎች ውስጥ ይህ የቅድመ መከራ ንጥቀት ጽንሰ አሳብ ቀድሞውኑም ጽኑ ሆኖ ተተክሎዋል፡፡
 
የጥንት ሐዋርያት የእግዚአብሄርን ዘመኖች በሁለት ዘመኖች ከፍለዋቸዋል፡፡ እነዚህም በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን ደህንነት የሚገኝበት የመጀመሪያው ዘመንና የመጀመሪያውን ዘመን ተከትሎ የሚመጣው ሁለተኛው የታላቁ መከራ ዘመን ነበሩ፡፡ የዘመኑ ሊቃውንቶች በኢየሱስ በማመን ደህንነት የሚገኝበትን የመጀመሪያውን ዘመን እንደሚረዱት ቢናገሩም ኢየሱስ ክርስቶስ የሚመጣበትንና የቅዱሳን ንጥቀት ዘመን የሚሆንበትን የታላቁን መከራ ዘመን መረዳት ግን በጣም አስቸጋሪ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡
 
ዘመናትን ባለማወቅ በቅድመ መከራ ንጥቀት ጽንሰ አሳብ የሚያምኑ ብዙዎቹ ክርስቲያኖች እምነታቸው የተሳሳተ ነው፡፡ የክርስቶስን ምጽዓት በሚመለከት የራሳቸውን ቀንና ዘመን በግብታዊነት የተነበዩት ወይም ከታላቁ መከራ በፊት እንደሚነጠቁ በማሰብ እምነታቸው በከንቱ እንዲደክም የፈቀዱት በዚህ የቅድመ መከራ ንጥቀት ጽንሰ አሳብ በማመናቸው ነው፡፡ በጣም ብዙ ክርስቲያኖች ‹‹ዓለም ችግር ቢገጥመው ምን አገባኝ? እኔ ታላቁ መከራ ከመምጣቱ በፊት ስለምነጠቅ ሁሉ ነገር መልካም ይሆናል›› ብለው በማሰብ በመንፈሳዊ ስንፍና ውስጥ ወድቀዋል፡፡ ይህ ሁሉ ግራ መጋባት የመጣው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተመሰረተ ትክክለኛ እውቀት ስለጎደላቸው ነው፡፡
 
ስኮፊልድ የቅድመ መከራን ንጥቀት ጽንሰ አሳብ አቀነቀነ፡፡ ከዚህ የተነሳም በዚህ ጽንሰ አሳብ የሚያምኑ ሰዎች ‹‹ታላቁ መከራ በዚህ ምድር ላይ ከመምጣቱ በፊት ስለምነጠቅ አሁን በተቻለኝ መጠን በምቾት ለመኖር ልሞክር›› ብለው በማሰብ በራሳቸው የምቾት አቅጣጫ ውስጥ እየተንገዋለሉ ነው፡፡ በዚህም እምነታቸው ሥራ ፈት ሆንዋል፡፡
ነገር ግን መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ታላቁ መከራና ንጥቀት ምን ይላል? መጽሐፍ ቅዱስ በመከራው አጋማሽ ላይ ስለሚሆን ንጥቀት ይናገራል፡፡ በኢየሱስ በተሰጠው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ እስራኤሎችና አሕዛቦች በሐመሩ ፈረስ ዘመን ወቅት በታላቁ መከራ በመጀመሪያዎቹ ሦስት ዓመታቶች ውስጥ ሲያልፉ ጸረ ክርስቶስ በሚያደርስባቸው ስደቶች እንደሚሰቃዩ ይነግረናል፡፡
 
መጽሐፍ ቅዱስ ከታላቁ መከራ የመጀመሪያ ሦስት ዓመት ተኩል በኋላ ጸረ ክርስቶስ ቅዱሳኖችን እንደሚገድል ማለትም ቅዱሳን ሰማዕት እንደሚሆኑ ይነግረናል፡፡ እንደዚሁም ሰማዕት ያልሆኑት ቅዱሳን ክቡር ሥጋ ለብሰው አብረው እንደሚነሱና በአየር ላይ እንደሚነጠቁም ይነግረናል፡፡ ቅዱሳን በታላቁ መከራ አጋማሽ ላይ ሲነጠቁ ይህ ዓለም የሰባቱ ጽዋዎች መቅሰፍቶች ይወርድበትና ወደ ፍጻሜ ይመጣል፡፡ ያን ጊዜ ሰይጣንን፣ ጸረ ክርስቶስንና የእርሱን ተከታዮች ለመፍረድ ወደዚህ ምድር ይመጣል፡፡
 
ራዕይ 13 ስሞቻቸው በሕይወት መጽሐፍ ላይ ያልተጻፈላቸው ሰዎች ለጸረ ክርስቶስና ለእርሱ ጣዖታት እንደሚማረኩ ይነግረናል፡፡ በሌላ አነጋገር ለጸረ ክርስቶስና ለተከታዮቹ የማይማረኩት ስሞቻቸው በሕይወት መጽሐፍ ላይ የተጻፈላቸው ሰዎች ብቻ ናቸው፡፡ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በልባቸው ለማመን እምቢተኞች ሆነው ስሞቻቸው በሕይወት መጽሐፍ ውስጥ ያልጻፈላቸው ሰዎች መጨረሻቸው ለሰይጣንና ለጣዖታቱ በመስገድና በመማረክ ያበቃሉ፡፡
 
መጽሐፍ ቅዱስ ቅዱሳን በታላቁ መከራ ወቅት በምድር ላይ እንደሚቆዩና የመከራው አጋማሽ ጥቂት ሲያልፍ በአየር ላይ እንደሚነጠቁ የሚናገረው ለዚህ ነው፡፡ በሰባቱ ዓመት ታላቁ መከራ ዘመን ለሰይጣን የሚማረኩና የጸረ ክርስቶስን ምልክት የሚቀበሉ ሰዎች በሙሉ ወደ እሳትና ዲን ባህር ውስጥ ይጣላሉ፡፡ ስሞቻቸው በሕይወት መጽሐፍ ውስጥ የተጻፉላቸውና ለጣዖት ያልሰገዱ ሰዎች በታላቁ መከራ አጋማሽ ላይ ይነጠቃሉ፡፡
 
እውነተኛው ንጥቀት የሚሆነው በሰባቱ ዓመት ታላቅ መከራ አጋማሽ ጥቂት አለፍ ብሎ ነው፡፡ ለንጥቀት ዘመን ዝርዝር የግርጌ ማመሳከሪያዎች በዚህ መጽሐፍ ተከታይ ሁለተኛ ቅጽ ላይ ይዳሰሳሉ፡፡ ነገር ግን ንጥቀት በጣም በቅርቡ ይሆናል በሚል ፕሮግራም ስለ ቅድመ መከራ ንጥቀት የሚናገሩ ብዙ ሰዎች አሉ ወይም ይህንን ንጥቀት እንዲያው በደፈናው ፕሮግራም በማድረግ ስለ ድህረ መከራ ንጥቀት ይናገራሉ፡፡ ሊቃውንቶች ዋጋ ያለው መሆኑን ሳያምኑም እንኳን ስለ ቅድመ መከራ ንጥቀት ጽንሰ አሳብ ይናገራሉ፡፡ ነገር ግን ወደ ቤተክርስቲያን የሚሄዱ ብዙ ሰዎች ይህንን ጽንሰ ኣብ አጥብቀው ይዘው ያምኑበታል፡፡ እንዲያውም አንዳንድ ሰዎች ያሉዋቸውን ጥሪቶች በሙሉ ለቤተክርስቲያኖቻቸው ይለግሳሉ ወይም የክርስቶስ ምጽዓት ተብሎ የተገመተውን የዘፈቀደ ቁርጥ ቀን በአክራሪነት ይጠብቃሉ፡፡
 
በቅርቡ የአንድ የእምነት ድርጅት አባሎች አንድ ቀን መርጠው ክርስቶስ እነርሱ በመረጡት በዚህ ቀን እንደሚመጣ አመኑ፡፡ ስለዚህም ሁሉም ወደ ተራራ ላይ ወጥተው ሰውነቶቻቸውን በአንድ ላይ በገመድ በማሰር በእኩለ ሌሊት የሚሆነውን ንጥቀታቸውን ጠበቁ፡፡ ጊዜው ነጎደ፡፡ ነገር ግን ምንም ያህል በጉጉት ቢጠብቁም ኢየሱስ አልመጣም፡፡ በመጨረሻ ተስፋ ቆርጠው ገመዶቻቸውን በመፍታት ከተራራው ላይ በሐፍረት ወረዱ፡፡ የዚህ ዓይነቱ ግራ መጋባት አሁን በክርስትናው ዓለም ውስጥ የተለመደ መሆኑ አሳዛኝ ነው፡፡ እንዲህ ያሉ የማይመስሉ ክስተቶች በኮርያ ብቻ የተወሰኑ ሳይሆኑ አዘውትረውም በመላው ዓለም በአውሮፓ፣ በአሜሪካ፣ በእስያና በየቦታው ይከሰታል፡፡
 
ስለዚህ በግልጽ ልናውቀው የሚገባን ነገር እግዚአብሄር የእርሱ ለሆኑት የእምነት ቅዱሳን ሳይቀር ታላቁን መከራ በግልጽ የሚፈቅድ መሆኑ ነው፡፡ ይህ የእግዚአብሄር ዕቅድ ነው፡፡ እግዚአብሄር ታላቁን መከራ በቅዱሳን ላይ የሚፈቅደው ተስፋዎቹን ሁሉ ለመፈጸም -- በመከራው አማካይነት ሰይጣንን ወደ ዘላለም እሳት ለመጣል፣ ቅዱሳን ከእርሱ ጋር ለሺህ ዓመት የሚነግሱበትን የክርስቶስን መንግሥት በመመስረት ይህችን ምድር ወደ አዲስ ዓለም ለመለወጥና በኢየሱስ ለሚያምኑት ምዕመናኖች አዲስ ሰማይና ምድር ለመስጠት ነው፡፡ ታላቁ መከራ ሆነ ተብሎ በዓላማ እንዲመጣብን የፈቀደው የእግዚአብሄር ፈቃድ ይህ ነው፡፡
 
የታላቁ መከራ ሰባት ዓመት ገና አልጀመረም፡፡ እስከ አሁን ድረስ የደረሱብን የተፈጥሮ ጥፋቶች የእሳት አደጋ ሰራተኞች በቀላሉ ሊያጠፉ ከሚችሉዋቸው እሳቶች ጋር ሊነጻጸር ይችላል ብለን ብንገምት ዓለምን በታላቁ መከራ ውስጥ የሚጠብቁዋት ጥፋቶች ፈጽመው የተለዩ ናቸው፡፡ ይህም የዓለምን ዛፎች ሲሶ ከሚያቃጥል እሳት ጋር ይነጻጸራል፡፡ 
 
እነዚህ ጥፋቶችና መቅሰፍቶች ዓለምን ሲመቱ እንዳይናወጡና ጸንተው እንዲቆሙ የእግዚአብሄር አገልጋዮችና ቅዱሳን የሚጋደል እምነት ሊኖራቸው ይገባል፡፡ እኛ እስከ ታላቁ መከራ አጋማሽ ድረስ በዚህ ምድር ላይ ስለምንኖር በመጨረሻው ዘመን ውስጥ መኖር ያለብን ፈጽሞ ለጸረ ክርስቶስና ለተከታዮቹ እጁን በማይሰጥ እምነት ውስጥ ነው፡፡ እናንተም ወደ ውጊያ ውስጥ የሚገባ ወታደር ያለው ዓይነት ቆራጥ ልብ ይዛችሁ አንዲት ነፍስ የራሳችሁንም ቤተሰብ ጨምራችሁ ለማዳን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል በመላው ዓለም ሁሉ መስበክ አለባችሁ፡
 
ዓለም ሁልጊዜም ሰላማዊ አይደለችም፡፡ ነገር ግን በዚህ ዓለም ላይ ግራ መጋባት ሲነግስና በሕይወታችን ውስጥም መከራ ሲበዛ እግዚአብሄር እስከ መጨረሻዋ ቀን ድረስ እንደሚጠብቀን በማመን ሁልጊዜም በታማኝነት መኖር አለብን፡፡ የዓለምና የሰይጣን ሐይማኖቶች ከሰዎች በመዝረፍና በመጨረሻም ነፍሳቸውን ወደ ሲዖል በማውረድ በሁሉም ዓይነት የሚያባብሉ ቃሎች ያስቱዋችኋል፡፡
 
አሁንም እንኳን ብዙ ሰዎች በትላልቅ የእምነት ድርጊት ውስጥ ያሉ ሰዎች የስኮፊልድን የቅድመ መከራ ንጥቀት ጽንሰ አሳብ በማመን ሌሎች ብዙዎችን ወደተሳሳተ እምነታቸው ነድተዋቸዋል፡፡ ከታላቁ መከራ በፊት እንደሚነጠቁ የሚያምኑ ሰዎች በታላቁ መከራ ውስጥ ለማለፍ እምነታቸውን ማዘጋጀቱ አስፈላጊ መስሎ አይታያቸውም፡፡ እነርሱ ማድረጉ የሚኖርባቸው አሁን ባለው ሕይወታቸው ታማኝ መሆንና ጌታ ጥሪውን በሚያደርግበት ጊዜም በአጭሩ መነጠቅ ብቻ እንደሆነ ያስባሉ፡፡ የቅዱሳን ንጥቀት የሚሆነው ግን የታላቁ መከራ የመጀመሪያ የሦስት ዓመት ተኩል ሲያልፍ ነው፡፡ ስለዚህ ክርስቶስ መቼም ይምጣ ለመከራው እምነታቸውን ማዘጋጀት አለባቸው፡፡ እግዚአብሄርን የእስራኤልን ሕዝብና ከአሕዛቦችም ብዙዎችን በታላቁ መከራ የሰባት ዓመት ጊዜ ውስጥ እንደሚያድናቸው ማመን አለብን፡፡
 
ቁጥር 14 እንዲህ ይነግረናል፡- ‹‹እነዚህ ከታላቁ መከራ የመጡ ናቸው፡፡ ልብሳቸውንም አጥበው በበጉ ድም አነጹ፡፡›› ይህ ሰማዕትነትን ያመለክታል፡፡ ሰማዕትነት ማለት በሰውየው እምነት መሰረት ለጽድቅ ሥራ መሞት ማለት ነው፡፡ ከሐጢያት ለዳኑ ቅዱሳን እጅግ ትክክለኛው እምነት ጌታ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ባስወገደበት ወንጌል ማመንና ይህንን እምነት መጠበቅ ነው፡፡ ሰይጣን ግን ሁልጊዜም የቅዱሳንን እምነት ለማጥፋት ይሞክራል፡፡ ስለዚህ በሰይጣን ላይ የእምነት ጦርነትን ማፋፋም አለብን፡፡
 
በዚህ ጦርነት ውስጥ ለሰይጣን እጃችንን ከሰጠን የእርሱ አገልጋዮች በመሆናችን እጃችንን ከሰጠን የእርሱ አገልጋዮች በመሆናችን ከዲያብሎስ ጋር አብረን ወደ ሲዖል እንጣላለን፡፡ ነገር ግን ሕይወታችንን በመክፈል ብንዋጋና እምነታችንን ብንጠብቅ ሰማዕት ሆነን በዚህ የሰማዕትነት እምነት ወደ እግዚአብሄር መንግሥት እንገባለን፡፡ እኛ እምነታችንን ለመጠበቅ ይህንን የእምነት ጦርነት እየተዋጋን በመሆኑ ሞታችን የጽድቅና የክብር ሞት ይሆናል፡፡
 
ስለዚህ ለጽድቅ ሥራዎች የሚዋጋ እምነት ሊኖረን ይገባል፡፡ የሌሎችን ነፍስ ለማዳንም በዚህ ጦርነት ውስጥ እንደገባን ማመን አለብን፡፡ እስከ መጨረሻው ድረስም እምነታችንን መጠበቅና እነዚህን ነፍሳቶች ወደ ሰማይ ለመውሰድ በዚህ ጦርነት ውስጥ መሸነፍ አለብን፡፡ የድልን አክሊል እስከምናገኝ ድረስ ከእርሱ ጋር በምናደርገው ውጊያ ሰይጣንን በጌታችን ቃለ ሰይፍ ማሸነፍ አለብን፡፡
 
ሰዎች የሚወለዱት አንድ ጊዜ ነው፡፡ የሚሞቱትም አንዴ ነው፡፡ የሕክምናው ሳይንስ ምንም ያህል ቢያድግም ሰው ሁሉ ውሎ አድሮ ይሞታል፡፡ ሰዎች በ10 ወይም በ80 ዓነት ይሙቱ ሁሉም ከእግዚአብሄር ዘንድ የሐጢያት ፍርድ ይገጥማቸዋል፡፡ በዚህ ምድር ላይ ጌታ በሰጠው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ሳያምኑ የሞቱ ሰዎች ፍርድ ይገጥማቸዋል፡፡ ወደ ዘላለም እሳት እንዲጣሉም ይኮነናሉ፡፡ ሐጢያቶቻቸው በሙሉ በውሃውና በኢየሱስ ደም ታጥበው እንደ በረዶ ነጭ ቢሆኑም በዚህ እውነት ያለማመን ሐጢያታቸው ይቅር ስላልተባለ እነዚህ አላማኒዎች በዚህ ምድር ላይ ሳሉ ለሰሩዋቸው ሐጢያቶች በሙሉ በእግዚአብሄርና በሰዎች ፊት ተፈርዶባቸው ዋጋ ይከፍላሉ፡፡
 
በእግዚአብሄር ፊት በሲዖል እሳት ውስጥ መኮነንን ለማምለጥ ከሐጢያቶቻችን በሙሉ በሚያድነንና በኢየሱስ በተሰጠው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ማመን አለብን፡፡ ለሐጢያቶቻችን ሁሉ ስርየትን የሚሰጠን የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል በመስቀሉ ደም ብቻ ከሚያምነው ወንጌል የተለየ ነው፡፡ እኔ በአጋጣሚም ሆነ በሌላ የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ሁልጊዜም ሰብኤያለሁ፡፡ መንፈስ ቅዱስን የምንቀበለውና የእግዚአብሄር ልጆች የመሆንን በረከት የምናገኘው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን ብቻ ነው፡፡ በኢየሱስ ስናምን ከመስቀሉ ደም ብቻ ከተፈጠረ ሐሰተኛ ወንጌል መራቅና አለማመን አለብን፡፡
 
ብሉይ ኪዳን በእጆች መጫንና በመታጠቢያው ሰን ስለ እውነተኛው ወንጌል ይናገራል፡፡ በአዲስ ኪዳን የእግዚአብሄር ቃል ሐጢያቶቻችን ክርስቶስ በተቀበለው ጥምቀት አማካይነት በአንድ ጊዜ ወደ እርሱ እንደተላለፉ ይግረናል፡፡ የብሉይ ኪዳን የመታጠቢያ ሰንና የአዲስ ኪዳኑ ጥምቀት ሁለቱም የሚያመለክቱት ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ባዳነን የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል -- ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በራሱ ላይ በተቀበለው የኢየሱስ ጥምቀት፣ የመስቀል ላይ ሞቱና ትንሳኤው የማመንን ተመሳሳይ እምነት ነው፡፡ ማንም ሰው በዚህ የውሃና የመንፈስ ወንጌል ካልሆነ በቀር መዳን አይችልም፡፡
 
ወደ ታላቁ መከራ አጋማሽ ላይ እስከምንደርስ ድረስ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ላይ ባለን እምነታችን በመኖር መቀጠል አለብን፡፡ ይህንን ዘመን ለይተን ማወቅ አለብን፡፡ በቀሩት የመጨረሻ ጥቂት ቀናቶችም እግዚአብሄር እንደሚፈልግብን የእግዚአብሄርን መንግሥት እየሰበክንና የምስራቹን ለሰዎች ሁሉ እያቀረብን መኖር አለብን፡፡ ጌታ በእነዚህ የመጨረሻ ቀኖች ወቅትም ብዙ ሰዎች እንደሚድሙ ነግሮናል፡፡
 
ውሃ በሌለበት ነገር ግን አሸዋና የሚያቃጥል የጸሐይ ብርሃን ባለበት ምድረ በዳ ውስጥ መቆየት የሚችሉ ጥቂት ተክሎች አሉ፡፡ ነገር ግን በትኩሳት፣ በደረቅ አቧራና አሸዋ በተሞላ በዚህ ባድማ የሆነ ምድረ በዳ ውስጥ ዝናብ ቢዘንብ ተክሎች በሳምንት ውስጥ ሊበቅሉ፣ ሊያብቡና ፍሬ ሊይዙ ይችላሉ፡፡ ምድረ በዳ ውሃ የለበትም፡፡ ከአሸዋ ውስጥ የተቀበሩት ዘሮች ገና መብቀል ባይችሉም ሕያዋን ናቸው እንጂ አልሞቱም፡፡ ዝናብን እየጠበቁ ነው፡፡ በእነዚህ የደረቁ ዘሮች ላይ ጤዛ ሲመጣ ወዲያውኑ ይበቅላሉ፡፡ ዘሮቹ በአንድ ቀን አጎንቁለው በቀጣዩ ቀን ሊያድጉ፣ በሦስተኛውም ቀን ሊያብቡና ፍሬ ሊይዙ ይችላሉ፡፡ በመጨረሻው ቀናቸው እነዚህ ተክሎች ዘሮቻቸውን ወደ ምድር ያዘነብላሉ፡፡ የጠነከሩት ዘሮችም እንደገና ከአሸዋው በታች ይደበቃሉ፡፡
 
ትንሽ ችግር እንኳን መቋቋም የማይችሉ የሚመስሉ የምድረ በዳ ተክሎች ውሃ ሲያገኙ መብቀል እንደሚችሉ ሁሉ በዘመኑ መጨረሻም ከውሃውና ከመንፈሱ ወንጌል ውሃ ጋር እጅግ በጥቂቱ ቢገናኙ ምድረ በዳ በሚመስለው ዓለም ዙሪያ ነፍሳቶች እንደሚኖሩ እናምናለን፡፡ የሰባቱ መለከቶች መቅሰፍቶች ተግባራዊ በሚሆኑበት ጊዜ በቃሉ አማካይነት ቀደም ብለው ስለ ታላቁ መከራ የሰሙ ብዙዎች በውስጣቸው የተተከለውን ወንጌል አውቀው ይጠብቁታል፡፡ ብዙም ሳይቆዩ የሰማዕትነትን እምነት ያበቅላሉ፡፡
 
ስለዚህ እናንተና እኔ እምነታችንን ለመጠበቅ ሰማዕት ስንሆን በደረቅ መሬቶች ላይ ወዲያው እንደሚበቅሉ የምድረ በዳ ተክሎች የሚበቅሉና ምልክቱን ለመቀበልና ጣዖትን ለማምለክ አሻፈረኝ በማለታቸው ከእኛ ሰማዕትነት ጋር የሚቀላቀሉ ሌሎች ብዙ የእምነት ሰዎች ይኖራሉ፡፡ አሁን እኛ እያሰራጨነው ያለነው ይህ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል ብዙ ሰዎች ሰማዕትነትን ለመቀበል በአጭር ጊዜ ውስጥ እምነታቸውን እንዲያሳድጉ ያስችላቸዋል፡፡ የሚጋደሉ የእግዚአብሄር ሰራተኞች አድርጎም ይለውጣቸዋል፡፡ 
 
እኛ ከልጆች ጀምሮ እስከ ሽማግሌዎች ድረስ ሁላችንም በጌታ ሰራዊት ውስጥ ወታደሮች ነን፡፡ እኛ ሁልጊዜም ልባችንን ለውጊያ በማዘጋጀት እንደ ክርስቶስ ሕዝብ በማናቸውም ውሸቶች ሳንታለል በትክክለኛ እምነት መኖር አለብን፡፡ እግዚአብሄር ጦርነቱን ለምናሸንፍ ሰዎች የድል አክሊልንና በቋንቋ ሊገለጡ የማይችሉ ሽልማቶችን ይሰጠናል፡፡ ስለዚህ ሰይጣንን፣ የእርሱን ውሸቶችና የዓለምን ክፋት ሁሉ በሚዋጋ እምነት የእግዚአብሄርን የጽድቅ ሥራዎች እየሰራን ሕይወታችንን መኖር አለብን፡፡
 
 

እግዚአብሄር በመከራ ዘመን ደፋር እምነትን ይሰጠናል፡፡ 

 
የሐመሩ ፈረስ ዘመን ሲመጣ እግዚአብሄር ምልክቶቹን ይሰጠናል፡፡ ቁጥር 1 እንዲህ ይላል፡- ‹‹ከዚህ በኋላም በአራቱ በምድር ማዕዘን ቆመው አራት መላዕክት አየሁ፡፡ እነርሱም ነፋስ በምድር ቢሆን ወይም በባሕር ወይም በማንም ዛፍ እንዳይነፍስ አራቱን የምድር ነፋሳት ያዙ፡፡›› እዚህ ላይ ነፋስ የሚያመለክተው እግዚአብሄር የሚያስነሳውን የመከራ ነፋስ ነው፡፡ ዮሐንስ ራዕይ 7፡1-8 እግዚአብሄር የእስራኤልን ሕዝብ ለማዳን እንደሚያትማቸውና ነፋሱንም ለጥቂት ጊዜ እንደሚይዘው ይነግረናል፡፡ ነገር ግን ጊዜው ሲደርስ ማለትም ከሰባቱ የእግዚአብሄር ዘመኖች መካከል የረሃብ ዘመን የሆነው የጉራቻው (ጥቁሩ) ፈረስ ዘመን ሲያልፍ እግዚአብሄር የሐመሩን ፈረስ ዘመን ይጀምረዋል፡፡ ያን ጊዜ አራቱ የምድር ነፋሳቶች በዓለም ላይ የመከራን ነፋስ ለማምጣት ይነፍሳሉ፡፡
 
የሐመሩ ፈረስ ዘመን የሚከፈትበት ዘመን ሲመጣ አስፈሪው የመከራ ነፋስ መንፈስ ይጀምራል፡፡ ብዙ እስራኤላውያንም ይገደላሉ፡፡ እኛን ጨምሮም ብዙ አሕዛቦችም እንደዚሁ ይገደላሉ፡፡ ይህ የሐመሩ ፈረስ ዘመን ሲመጣ የመከራው ዘመን ያለ ምንም መሳሳት ይጀምራል፡፡
 
አሁን ዘመኑ የጉራቻው ፈረስ ዘመን ስለሆነ የረሃብ ነፋስ በዓለም ዙሪያ እየነፈሰ ነው፡፡ ይህ ዘመን ሲያበቃ የሐመሩ ፈረስ ዘመን ይጀምርና የመከራን ነፋስ ያስነሳል፡፡ የመከራው ነፋስ የሰባት ዓመቱን የታላቅ መከራ ሙሉ ጅማሬ ያበስራል፡፡ እግዚአብሄር ዩኒቨርስንና የሰውን ታሪክ መጀመሪያ ከፈጠረበት ጊዜ አንስቶ ለመጀመሪያ ጊዜ ታላቁን መከራ በዚህ ዓለም ላይ ሲያመጣ ማለትም በሐመሩ ፈረስ ዘመን ጅማሬ የመከራው ነፋስ ሲነፍስ ሁሉም ነገር ያበቃል፡፡ ሁሉም ነገር ደግሞ ታድሶ እንደገና ይጀምራል፡፡
 
የሐመሩ ፈረስ ዘመን ሲመጣ የመከራውም ዘመን እንዲሁ እንደሚመጣ መረዳት አለብን፡፡ በዓለም ዙሪያ ያሉ መሪዎች ሲተባበሩ የተወሰኑ ፖለቲከኞች ፍጹማዊ ሥልጣንን ይይዛሉ፡፡ የእነርሱን ትዕዛዞችና ሕጎች የማይታዘዙ ሰዎች በሰባቱ መለከቶች መቅሰፍቶች በተፈጠሩት የተፈጥሮ ጥፋቶች ታላላቅ ችግሮች ስለሚገጥሙዋቸው በሐመሩ ፈረስ ዘመን ውስጥ መኖር በጣም ያዳግታቸዋል፡፡ ነገር ግን ይህንን መከራ ማብዛት በጣም አስጊ የሆኑ የዘመኑ የፖለቲካ ሁነቶች ይሆናል፡፡ ሆኖም በዚህ ሁኔታ ውስጥም ቢሆን እግዚአብሄር ብዙ ቁጥር ያላቸውን አሕዛቦች ወደ ደህንነት በማምጣት በሰዎች መካከል መስራቱን ይቀጥላል፡፡
 
በሐመሩ ፈረስ ዘመን የመከራው ነፋስ ሲነፍስ ተስፋ ሊገኝ የሚችለው በአንድ ሥፍራ ብቻ ነው፡፡ ቃሉ፡- ‹‹በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ለአምላካችንና ለበጉ ማዳን ነው›› ብሎ ስለሚነግረን ይህ ብቸኛው ተስፋ የሚገኘው በአምላካችን አብና በኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ አስፈሪው የመከራ ነፋስ ሲነፍስ ጸረ ክርስቶስ በዚህ ምድር ላይ ተገልጦ ከኢኮኖሚ እስከ ባህልና ሐይማኖት ድረስ የዓለምን የፖለቲካ ክልል ብቻ ሳይሆን ማህበራዊ ክልሎችንም በአንድ ዓለም አቀፍ ጥምረት ያስተባብራል፡፡ መከራ ማለት በአስፈሪ ስደት ውስጥ ማለፍ ማለት ነው፡፡ የሚነፍሰው ነፋስ ይህ ነው፡፡ እነዚህ ነገሮች ሁሉ በድንገት ይሆናሉ፡፡
 
የኢኮኖሚ ጥምረት ነፋስ በዛሬው ዓለም ላይ እየነፈሰ ነው፡፡ በተለያዩ የንግድ ድርጅቶች ውስጥ አባል በሆኑ አገሮች መካከል የታሪፍ ግድግዳዎችን ለማፍረስ ወደ ነጻ ንግድ የሚደረግ ጠንካራ እንቅስቃሴ አለ፡፡ ከለላ በሚሰጥ የንግድ አሰራር ሥርዓት ሥር የአንድ አገር ምርቶች በሌላው አገር ውስጥ የዋጋ ተወዳዳሪነታቸውን ለመጠበቅ አስቸጋሪ መሆኑ የተለመደ ነው፡፡ ምክንያቱም በወጪና በገቢ ንግድ ሒደቶች ወቅት የተጣሉት ታሪፎች የውጭ ንግዶቹ የመነሻ ዋጋዎች ምንም ያህል ዝቅተኛ ቢሆኑም ዋጋቸው ይጨምራል፡፡
 
ነገር ግን እንደዚህ ያሉ የታሪፍ ግድግዳዎች እየተደረመሱ ነው፡፡ ጥሩ ምሳሌ ታሪፎች በላሉበት በአውሮፓ ውስጥ ማግኘት ይቻላል፡፡ ለምሳሌ በአውሮፓ ሕብረት (አሕ) አባል አገሮች መካከል ከእንግዲህ ወዲህ ታሪፍ የሚባል ነገር የለም፡፡ ይህም የፖለቲካና የባህል ጥምረት አነሳስን የሚያመለክት ሊመጣ ያለው ታላቅ ጥምረት ጅማሬ ነው፡፡ ይህ አስገራሚ ለውጥ ነው፡፡ ታሪፍ ከሌለ አንድ አገር ምርቶቹን በማንኛውም ሌላ አገር ውስጥ መሸጥ ይችላል፡፡ ይህ በዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ሥነ ምህዳር ውስጥ ወሳኝ መሰረታዊ ለውጥ ነው፡፡ የአውሮፓ ሕብረት የኢኮኖሚ ጥምረቱን በስኬት የሚያጠናቅቅ ከሆነ ዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ጥምረት ይበልጥ ይፋጠናል፡፡
 
በቅርቡ ኮርያ፣ ቻይናና ጃፓን ወደፊት ልክ በ1997 ዓ.ም አካባቢውን ያጥለቀለቀ ዓይነት የገንዘብ ቀውስ በእስያ ቢፈጠር እርስ በርሳቸው የድንገተኛ ጊዜ ብድሮችን ለማቅረብ ስምምነት ላይ ደርሰዋል፡፡ በ1997 ዓ.ም በእስያ ለተከሰተው ቀውስ የገንዘብ ድጋፍ ያደረገችው አሜሪካ ነበረች፡፡ በዚህ ስምምነት ግን ተሳታፊ የሆኑት ሦስቱ አገሮች ፈራሚው አገር የገንዘብ ወይም የኢኮኖሚ ቀውስ ቢገጥመው አንዳቸው ለሌላቸው የገንዘብ የገንዘብ ድጋፍ ለማድረግ ቃል ገብተዋል፡፡ ይህ ማለት የኢኮኖሚ ጥምረት መመስረት ማለት ነው፡፡ የአውሮፓ አገሮች በአውሮፓ ሕብረት በኩል አባል ለሆኑት አገሮች የላቀ ብልጥግናን በመሻት ታሪፎችን አስወግደው የኢኮኖሚ ጥምረትን እንደተከተሉ ሁሉ ሦስቱ የሩቅ ምስራቅ አገሮችም እንደዚሁ ዕምቅ ሐብቶቻቸውን በአንድ ላይ አቀናጅተዋል፡፡ የዚህ ዓይነቱ የተናጥል አገሮች ጥምረትና ድርጅታዊ ዕድገት ውሎ አድሮ ወደ ፖለቲካዊ ጥምረት ያመራል፡፡
 
ታሪፍን በማስወገድ የኢኮኖሚ ጥምረትን መፍጠር ማለት በተናጥል ያሉ አገሮችን ጥምረት አፍርሶ ወደ ልዕለ ብሄራዊ አካል መጣመር ማለት ነው፡፡ የሰባቱ መቅሰፍቶች የተፈጥሮ ጥፋቶች ሲወርዱና በዓለም ላይ ሁከት ሲፈጠር የእነዚህ ዓለም አቀፍ ድርጅቶችና ተቋሞች ወኪሎች አንድ አምባገነን መሪ ለመምረጥ ይተባበራሉ፡፡ በሌላ አነጋገር ዓለምን በአንድ የፖለቲካ አካል በማደራጀትና አምባገነን ሥልጣን ያለውን መሪ በማስነሳት ግራ የተጋባውን ዓለም ሥርዓት ያሲዙታል፡፡
 
በዚህ ሒደት ውስጥ የመከራ ነፋስ ይነፍሳል፡፡ የግለሰብ መብቶችን በማክበር ፋንታ ለአብዛኛው ሕዝብ ሲባል የጥቂቶችን መብቶች መደፍጠጥ ተቀባይነት ያለው ብቻ ሳይሆን የሚጠበቅም ይሆናል፡፡ የሐመሩ ፈረስ ዘመን ሲመጣ ይህ ነፋስ ይነፍሳል፡፡ ለእነዚህ ሁነቶች መሰረቱ የሚጣለው በጉራቻው ፈረስ ዘመን ይሆናል፡፡ በተጨባጭ የሚከናወኑትም በሐመሩ ፈረስ ዘመን ይሆናል፡፡
 
በዚህ ሒደት ውስጥ የመከራ ነፋስ ይነፍሳል፡፡ የግለሰብ መብቶችን በማክበር ፋንታ ለአብዛኛው ሕዝብ ሲባል የጥቂቶችን መብቶች መደፍጠጥ ተቀባይነት ያለው ብቻ ሳይሆን የሚጠበቅም ይሆናል፡፡ የሐመሩ ፈረስ ዘመን ሲመጣ ይህ ነፋስ ይነፍሳል፡፡ ለእነዚህ ሁነቶች መሰረቱ የሚጣለው በጉራቻው ፈረስ ዘመን ይሆናል፡፡ በተጨባጭ የሚከናወኑትም በሐመሩ ፈረስ ዘመን ይሆናል፡፡
 
ኮርያ በ1997ቱ ቀውስ ተመትታ በዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም ጥበቃ ሥር በነበረችበት ጊዜ አውዳሚ በሆኑ የኢኮኖሚ መቅሰፍቶች ተጥለቅልቃ ነበር፡፡ የሪል ኢስቴት ዋጋዎች ዘቀጡ፡፡ ሰዎችም በአንድ ሌሊት ከሥራቸው ተፈናቀሉ፡፡ መካከለኛ ገቢ ያለው ሕዝብም ወደ ጎዳና ወጣ፡፡ እንደዚህ ያሉ የኢኮኖሚ መቅሰፍቶች በዓለም ሁሉ የተለመዱ ስለሆኑ በሌላ አገር ውስጥ ስለተከሰተ ሌላ የገንዘብ ቀውስ ሳይሰማ አንድም ቀን አያልፍም፡፡ ይህ ነፋስ የረሃብ ነፋስ ነው፡፡ የምንኖረው በዚህ ዘመን ውስጥ ነው፡፡ በዚህ ዘመን ገንዘብ ከሌላችሁ ሕይወታችሁ ዋጋ የለውም፡፡ በቅርቡም ይህ የረሃብ ነፋስ ሙሉ በሙሉ በሚነፍስ የመከራ ነፋስ ይተካል፡፡
 
እግዚአብሄር በአራቱ ማዕዘናት ያሉትን ነፋሳቶች ለጥቂት ጊዜ በመያዝ ከሕዝበ እስራኤል መካከል 144,000ዎችን አተመ፡፡ በእነርሱ ላይ አንዳች ጉዳት እንዳይደርስ ከተከላከለ በኋላ የመከራውን ነፋስ ለቀቀው፡፡ ይህ የመከራው ነፋስ ከመላዕክቶቹ እጅ ሲለቀቅ የታላቁ መከራ ነፋስ ይነፍሳል፡፡ የመከራው ነፋስ በጸረ ክርስቶስ መነሳት ሙሉ በሙሉ የሰይጣን ግዛት የሚሆነውን ዓለም ያስተባብረዋል፡፡ በሰባቱ መለከቶች መቅሰፍቶች አማካይነት በሚመጡት የሰባት ዓመት ታላላቅ የተፈጥሮ ጥፋቶች ውስጥም ያልፋል፡፡ እነዚህን ተከትሎም የሰባቱ ጽዋዎች መቅሰፍቶች ይመጣሉ፡፡
 
በዚህ የጸረ ክርስቶስ የግፍ አገዛዝና የእምነት ነጻነት ዕጦት ወቅት ረሃብና ቀጣና እጅግ አስከፊ ደረጃ ላይ ስለሚደርስ ሰዎች መንግሥት በሚሰጠው ምግብ ብቻ እንዲኖሩ ይገደዳሉ፡፡ በዓለም ላይ የሚኖር እያንዳንዱ ሰው ከዚህ ዘመን ጋር ይገጣጠማል፡፡ የራዕይ 7 ቃል ሊመጡ ስላሉት ስለ እነዚህ ነገሮች ጠቅለል ያለ ስዕል ይሰጠናል፡፡
 
በዚህ ዘመን ሌላስ ምን ይጠብቀናል? የሐመሩ ፈረስ ዘመን የሚታወቀው እጅግ ብዙ ቁጥር ያላቸው እስራኤሎችና አሕዛብ ሰማዕትነትን የሚቀበሉበት በመሆኑም ነው፡፡ ታላቁ መከራ ሲመጣ የሚቀረው ተስፋ ብቻ ነው፡፡ ቁጥር 10 እንዲህ ይነግረናል፡- ‹‹በታላቅ ድምጽም እየጮሁ፡- በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ለአምላካችንና ለበጉ ማዳን ነው አሉ፡፡›› በሌላ አነጋገር ደህንነታችን የሚገኘው በዙፋኑ ላይ በተቀመጠው በአምላካችንና በበጉ ብቻ ነው፡፡ ከምዕራፍ 4 ማየት እንደምንችለው ለኢየሱስ ክርስቶስ ዙፋን እንዳዘጋጀለትና በዙፋኑ ላይ የተቀመጠውም ኢየሱስ ክርስቶስ ደካማ ሆኖ ሳይሆን የእግዚአብሄር ልጅ ሁሉን ቻይ አምላክና የሁሉ ፈራጅ ሆኖ እንደተቀመጠ ይነግረናል፡፡ እግዚአብሄር አብ አሁንም በዙፋኑ ላይ ተቀምጦዋል፡፡ ስለዚህ ስለ ስላሴ አምላክ ስንናገር እግዚአብሄር አብ፣ ወልድና መንፈስ ቅዱስ ሁሉም ተመሳሳይ አምላክ ስለመሆናቸው መናገራችን ነው፡፡ ስለዚህ ትክክለኛው ደህንነታችን የአምላካችንና የበጉ በአጭሩ የኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡
 
አስፈሪው መከራ ሲመጣ ተስፋን ማግኘት የምንችለው ከየት ነው? ጸረ ክርስቶስ በታላቁ መከራ ወቅት ሲነሳ ለራሱ ምስልን ያሰራል፡፡ ለምስሉ መስገድን እምቢ የሚሉትንና የስሙን ምልክት በእጆቻቸው ወይም በግምባሮቻቸው ላይ የማይቀበሉትን ሁሉ ለመግደል ይዝታል፡፡ (ዮሐንስ ራዕይ 13
 
ሥነ ምህዳርን በሚመለከት የተፈጥሮ ሁኔታዎች እጅግ አስከፊ ደረጃ ላይ ይደርሳሉ፡፡ እሳትና በረዶ ከሰማይ ይዘንባሉ፡፡ የመሬት መናወጥ ይነሳል፡፡ ሌሎች መቅሰፍቶችም ይከተላሉ፡፡ መቅሰፍቶች የማይነካው ስፍራ በዚህ ምድር ላይ አይገኝም፡፡ ምድር በመሬት መናወጥ በምትሰጠነቅበት፣ ጸሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብት በሚጨልሙበት፣ ባህሮችና ወንዞች በመቅሰፍቶች በሚመቱበት በዚህ የከፋ ሥነ ምህዳር ሁኔታ ውስጥ የወቅቱ የፖለቲካ ሁኔታም በዓይነቱ እጅግ የከፋ ይሆናል፡፡ ጸረ ክርስቶስ አምባገነን ሥልጣን ስለሚይዝና የዓለምን መሪዎች በሙሉ በራሱ አገዛዝ ሥር ስለሚያደርግ እጅግ ጨቋኝ በሆነ አገዛዝ ይገዛል፡፡
 
 
ጸረ ክርስቶስ የሚመጣው ለምንድነው? 
 
ሰይጣን የመጨረሻ ምኞቱን ማለትም ከእውነተኛው አምላክ በላይ ከፍ ብሎ ለመታየት በሕዝቡ እንደ አምላክ የመጠራቱን ምኞት ለመፈጸም በሚያደርገው ሙከራ ለጥቂት ጊዜ ሥልጣኑን ለጸረ ክርስቶስ ይስጠዋል፡፡ ነገር ግን ይህ ምኞት እንደማይፈጸም ሰይጣን ራሱ ያውቃል፡፡ ሆኖም ለመጨረሻ ጊዜ እርሱን የማይታዘዙትን በመግደል በሰው ዘር በኩል ለመክበር ይሞክራል፡፡ በቅዱሳን ላይ ከሚመጡት ወዮታዎች ሁሉ እጅግ አስከፊው ይህ ነው፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱሳኖች ከመሞት በቀር ሌላ ምርጫ የላቸውም፡፡ የሚታመኑበትና ተስፋቸውን የሚጥሉበት ብቸኛው አካል የደህንነታችን አምላክ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በኩል ያዳነን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው፡፡ በዚህ አምላክ ላይ መደገፍ እንችላለን፡፡ በእነዚህ አስፈሪ መቅሰፍቶችና መከራዎች መካከል ከሞት መዳን የምንችለው በእርሱ በማመን ብቻ ነው፡፡
 
በእነዚህ የመጨረሻ ቀኖች ውስጥ ብቸኛው ተስፋችን ‹‹በዙፋኑ ላይ በተቀመጠው አምላካችንና የእግዚአብሄር በግ›› ላይ ያለን ተስፋ ነው፡፡ ቅዱሳን በአምላካችን በማመን ሰማዕት ይሆናሉ፡፡ በእርሱ ላይ ባላቸው እምነትም ከአስፈሪዎቹ መቅሰፍቶችና ሞት ይድናሉ፡፡ ስለዚህ ራዕይ 7 በሰባቱ ዓመት ታላቅ መከራ ወቅት የሚሆኑትን ዝርዝሮች በሙሉ አቅርቦልናል፡፡
 
የመከራው ነፋስ የሚያመጣቸውን ሁነቶች በማየት እንቀጥል፡፡ ቁጥር 9-10 እንዲህ ይነግረናል፡- ‹‹ከዚህ በኋላ አየሁ፤ እነሆም አንድ እንኳ ሊቆጥራቸው የማይችል ከሕዝብና ከነገድ፣ ከወገንም፣ ከቋንቋም ሁሉ እጅግ ብዙ ሰዎች ነበሩ፡፡ ነጭ ልብስም ለብሰው የዘንባባንም ዝንጣፊዎች በእጆቻቸው ይዘው በዙፋኑና በበጉ ፊት ቆሙ፡፡ በታላቅ ድምጽም እየጮሁ፡- በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ለአምላካችንና ለበጉ ማዳን ነው አሉ፡፡›› እነዚህ ከነገዶችና ከቋንቋዎች መጥተው ነጭ ልብስ የለበሱና ጌታን የሚያመሰግኑ ብዙ ሰዎች ማን እንደሆኑ በተጠየቀ ጊዜ ከ24 ሽማግሌዎች አንዱ እንዲህ ሲል መለሰ፡- ‹‹እነዚህ ከታላቁ መከራ የመጡ ናቸው፡፡ ልብሳቸውንም አጥበው በበጉ ደም አነጹ፡፡››
 
እጅግ ብዙ ቁጥር ያላቸው ሰማዕታት ከወገኖች፣ ከነገዶችና ከቋንቋዎች በሚነሱበት በታላቁ መከራ መካከል ብዙ ቁጥር ያላቸው ሰዎች እንደሚድኑ ይህ ይነግረናል፡፡ በሌላ አነጋገር ከወቅቱ መከራዎችና መቅሰፍቶች ሁሉ ወጥተው እግዚአብሄርን ብቸኛው አዳኛቸው አድርገው የሚያምኑ ብዙ ሰዎች ይኖራሉ፡፡ ይህ ማለት በአጭሩ ደህንነት የሚገኘው በሥላሴ አምላክ ብቻ ነው ማለት ነው፡፡
 
እግዚአብሄር ከሐጢያቶቻችን የዳንበትን የውሃውንና የመንፈሱን ወንጌል ስለሰጠንና እኛም በዚህ ወንጌል ስለምናምን ጸረ ክርስቶስ መጥቶ እጃችንን ለእርሱ እንድንሰጥና አምላክ ብለን እንድንጠራው በዛቻ መልክ ሲጠይቀን ለእርሱ አንማረክም፡፡ ከዚህም በላይ አንዳንዶቻችን እጃችንን ለጸረ ክርስቶስ ብንሰጥም እንኳን ለመትረፋቸው ምንም ዋስትና የላቸውም፡፡ ምክንያቱም በሚያወድሙ መቅሰፍቶችና በእልህ አስጨራሽ የሰይጣን አክራሪነት ውስጥ ያልፋሉና፡፡ በዚህ ዘመን ውስጥ ዋስትና ያለው ምንም ነገር የለም፡፡
 
ስለዚህ ባዳነን በእግዚአብሄር ከማመን ውጭ ምርጫ የለንም፡፡ የሺህ ዓመት መንግሥቱንና አዲሱን ሰማይና ምድር በሚሰጠን አምላክ በማመን ሰማዕትነታችንን በድፍረት እንቀበላለን፡፡ እርሱ ዳግመኛ ያስነሳናል፤ ይነጥቀናል፡፡ የአዲሱን ሰማይና ምድር ክብርና በረከት ሁሉ ይሰጠናል፡፡ በበጉ ደም ታጥበው ልብሳቸውን ያነጹ ብዙ ሰዎች የታዩት ለዚህ ነው፡፡ 
 
በእርግጥም በእግዚአብሄር ባላቸው እምነት የሚሞቱ ብዙ ሰማዕታት ይኖራሉ፡፡ በዚህ ዘመን ያሉና ከመላው የዓለም አገር የወጡ ቅዱሳንና ሰማዕታት ሁሉ በእግዚአብሄር ላይ ባላቸው እምነት ሕይወታቸውን መስዋዕት ያደርጋሉ፡፡ አሁን እኛ እየሰበክነው ባለው በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ሰዎች ከወቅቱ የመከራዎችና የመቅሰፍቶች ፍርሃት ሁሉ በሚያድናቸው በእግዚአብሄር በማመን ሰማዕትነታቸውን ይቀበላሉ፡፡ ከእነዚህ አስፈሪ መቅሰፍቶች ሊያድነን የሚችለው እግዚአብሄር ብቻ ነው፡፡
 
በሰባቱ ዓመት ታላቅ መከራ ወቅት የሚሆኑትን ወሳኝ ሁነቶች በሙሉ እነግራችኋለሁ፡፡ የመከራው ነፋስ በዚህ ዓለም ላይ ሲነፍስ በዚህ ምድር ላይ ተስፋ የሚደረግ ነገር አይኖርም፡፡ አሁን የምናውቀው ዓለም አይኖርም፡፡ ሰማይና ምድርም እንደ መጽሐፍ ተጠቅልለው ይጠፋሉ፡፡
 
ያን ጊዜ እግዚአብሄር በዚህ ምድር ላይ አዲስ ሰማይና ምድር ይፈጥርና የሰማዕታት እምነት ለሺህ ዓመት እንዲነግስበት ያደርጋል፡፡ ይህ ሺህ ዓመት ሲፈጸምም ወደ ዘላለማዊው መንግሥቱ ያዛውራቸዋል፡፡ ያለውም ከሐጢያቶቻችን ያዳነን፣ ከታላቁ መከራ ሞትና ጥፋት የሚያድነንና ተስፋን ሊሰጠን የሚችል አምላካችን ብቻ ነው፡፡ የሰማዕትነቱ ዘመን ሲመጣ እናንተና እኔ እንደዚሁም ወንጌልን ሰምተው ያመኑ በመላው ዓለም የሚገኙ ሕዝቦች ከሐጢያቶቻችን ባዳነን አምላክ በማመናቸው በጀግንነት ሰማዕትነትን ይቀበላሉ፡፡ እኛም ባለን ደፋር እምነትና ተስፋ ሰማዕትነታችንን እንቀበላለን፡፡ ከአስፈሪዎቹ መቅሰፍቶችና መከራዎች የሚያድነን እርሱ በዙፋኑ ላይ የተቀመጠው አምላካችን ነው፡፡ 
 
ስለዚህ ከሐጢያቶቻችን ያዳነን እግዚአብሄር ከእነዚህ አስፈሪ መቅሰፍቶች የሚያድነን አምላክ መሆኑን ሳናምን ሰማዕት መሆን አንችልም፡፡ የዚህ ዘመን ሰማዕታት ስሞቻቸው በበጉ የሕይወት መጽሐፍ ውስጥ የተጻፉላቸው ናቸው፡፡ ስሙ በሕይወት መጽሐፍ ውስጥ የማይገኝ ማንኛውም ሰው ሰማዕት መሆን አይችልም፡፡
 
ይህ ወንጌል ሁልጊዜም በመላው ዓለም ይሰብካል፡፡ በዓለም ዙሪያ ያለ ሁሉም በእርግጠኝነት ያደምጠዋል፤ ያውቀውማል፡፡ እኛ አሁን ያለ ማቋረጥ ይህንን ወንጌል እያሰራጨን በመሆናችን የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል በዓለም ሁሉ እየተመሰከረ ነው፡፡ በዚህ ዓለም ታላቁ መከራ ሲመጣ ተስፋቸውን በበጉ ላይ የሚያደርጉ ሕይወታቸውን አደጋ ላይ ጥለው በእግዚአብሄር የሚያምኑና ሰማዕትነታቸውን የሚቀበሉ ብዙ ነፍሳቶች አሉ፡፡ የምዕመናኖቹን ስሞች በሕይወት መጽሐፍ ላይ እንዲጻፍ የሚያስችለው የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል መስበኩን ይቀጥላል፡፡
 
በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ሰዎች በመጨረሻው ዘመን ሰማዕት ይሆናሉ፡፡ ዮሐንስ ራዕይ 13፡8 እንዲህ ይነግረናል፡- ‹‹ከዓለም ፍጥረት ጀምሮ ስሞቻቸው በሕይወት መጽሐፍ ያልተጻፉ በምድር የሚኖሩ ሁሉ ይሰግዱለታል፡፡›› ስሙ በሕይወት መጽሐፍ ላይ ያልተጻፈ ሰው ሁሉ ያለ ምንም ማመንታት ለአውሬው እንደሚማረክ የተረጋገጠ እውነት ነው፡፡
 
ከመጨረሻው ዘመን መከራ ሊያድነን የሚችለው ኢየሱስ ክርስቶስና የእርሱ አባት እግዚአብሄር ብቻ ናቸው፡፡ አሁን መንፈስ ቅዱስ በልባችን ውስጥ ያድራል፡፡ እኛ በእግዚአብሄር እንደዳንን አምናለሁ፡፡ ለእርሱ ስንል ብንሞትም እግዚአብሄር ዳግመኛ ከሙታን ያስነሳናል፤ ይነጥቀናል፡፡ በምድር ላይ ያለውን እያንዳንዱን ነገር ሁሉ ያድሳል፡፡ በሺህው ዓመት መንግሥቱ ውስጥ እንድንኖርም ይፈቅድልናል፡፡
 
ይህ እንዲህ ባለው የመከራ ነፋስ የሚመሰቃቀለው የሐመሩ ፈረስ ዘመን ፈጥኖ ወደ እኛ እየቀረበ ነው፡፡ የጉራቻው (ጥቁር) ፈረስ ዘመን በፍጥነት እያበቃ ነው፡፡ ያ ዘመን ሲጠናቀቅ ሐመሩ ፈረስ ብቅ ይላል፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ መላው ዓለም ወደ ሰባቱ ዓመት ታላቅ የመከራ ዘመን ውስጥ ይገባል፡፡ ከሰባት ዓመት የማይበዛና የማያንሰው ይህ የታላቁ መከራ ዘመን በእርግጥም ይመጣል፡፡ ምክንያቱም የእግዚአብሄር ዕቅድ ነውና፡፡
 
ለጥቂት ጊዜ ታላቁ መከራ በእርግጥም ጀምሮዋል ብለን እናስብ፡፡ በዙሪያችንና በመላው ዓለም ያሉ ዛፎችና ሳሮች እየተቃጠሉ ሰማይ በጢስ ታፍኖ ጸሐይ ጥቅጥቅ ባለ የጢስ ደመና ተሰውራ በቀን ጨለማ ሲወርሰን፣ ሰዎች በየቦታው ሲሞቱ፣ እኛን የሚከታተሉ ሰዎችንም ድምጽ ስንሰማ እናስብ፡፡ የምንታመነው ማንን ይሆናል? ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ባዳነን፣ ለጸረ ክርስቶስ ያላጎበደዱ ሰማዕታቶችን እንደገና ሕያው ለማድረግ ቃል በገባው፣ እኛን ለማስነሳትና ለመንጠቅ ዳግመኛ ወደዚህ ምድር በሚመጣውና ወደ አዲሱ ሰማይና ምድር በሚወስደን አምላክ ትታመናላችሁ ወይስ በእርሱ አትታመኑም? በእርግጥ በእግዚአብሄር እንታመናለን! ብቸኛው ተስፋችን እግዚአብሄር ብቻ ነው! ጸረ ክርስቶስን ማወደስም ሆነ በራሳችን መታመን ሊያድነን አይችልም፡፡ በዋሻዎች ውስጥ መደበቅም ሆነ ምድርን ለቆ ወደ ጠፈር ጣቢያ መሸሽም አያድነንም፡፡ ከእግዚአብሄር በስተቀር ሌላ ምንም ነገር አያድነንም!
 
ይህችን ምድር ተወርዋሪ ኮከቦች ሲመቱዋት ፍርስራሹ በሙሉ ምድር ላይ ይወድቃል፡፡ እግዚአብሄር በመጀመሪያ የፈጠረው ነገር ሁሉ ይወድማል፡፡ ያን ጊዜ እውነተኛ ተስፋ በልቦቻችን ውስጥ ይበቅላል፡፡ እንዲህ ባለ ተስፋ አስቆራጭ ሁኔታ ውስጥ ተስፋችንን የምንጥለው በማን ላይ ነው? ተስፋ የምናደርግበትና እርዳታን የምንሻበት ብቸኛው አምላክ እግዚአብሄር ነው፡፡ ያዳነን እግዚአብሄር እንጂ ማንም አይደለም!
 
በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ቃል በማመን ስለዳንን ለዚህ ደህንነት እግዚአብሄርን እናመሰግነዋለን፡፡ ታላቁ መከራ ሲመጣ ግን ከአስፈሪዎቹ መቅሰፍቶችና ሞት ስላዳነን ባለን ነገር ሁሉ እግዚአብሄርን እናመሰግነዋለን፡፡ ከጸረ ክርስቶስ እጅ ሊያድነን የሚችለው እግዚአብሄር ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር እንጂ ሌላ ማንም አያድነንም፡፡ እኛ እምነታችንንና ተስፋችንን በዚህ አምላክ ላይ ስላኖረን እግዚአብሄር እንደሚያስነሳንና በሺህው ዓመት መንግሥቱና በአዲሱ ሰማይና ምድር ውስጥ በዘላለም ደስታ እንድንኖር ስለሚፈቅድልን የሚመጡትን መከራዎች ሁሉ መቋቋምና ማሸነፍ እንችላለን፡፡
 
ጸረ ክርስቶስ ጎትቶ ወስዶን በምስሉ ፊት በማቆም ‹‹በዚህ ምስል ፊት ተጎንበሱ፤ እኔንም አምላክ ብላችሁ ጥሩኝ፡፡ ኢየሱስ አምላክ አይደለም፡፡ አምላክ እኔ ነኝ፡፡ የማድናችሁም እኔ ነኝ›› በማለት የሚጠይቅበት ዘመን ይመጣል፡፡ ጸረ ክርስቶስ ለእርሱ እንድንሰግድ ሲጠይቀን እንፈራ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ዳግመኛ የተወለድን ማናችንም መቼም ቢሆን ለምስሉ አንንበረከክም፡፡ ለምን? ጸረ ክርስቶስ ምልክቱን እንድንቀበል ካስገደደን በኋላ ባሪያዎቹ ያደርገናል፡፡ ሰዎችን እንድንገድል ይጠቀምብናል፡፡ በመጨረሻም እኛኑ ደግሞ ይገድላል፡፡
 
ይህ ጸረ ክርስቶስ ራሱን አምላክ ብሎ ለማወጅ የሚቆምበት ዘመን ይመጣል፡፡ ጸረ ክርስቶስ ራሱን የሚመስሉ ታላላቅ ምስሎች በመስራት በዓለም ላይ ያለ ሰው ሁሉ አምላክ ብሎ እንዲጠራውና እርሱን የሚያወድሱ መዘምራኖችንም የሚያደራጅበት ጊዜ በጣም ሩቅ አይደለም፡፡ በዚህ ዘመን ላይ ሰላም ካለ የተፈጥሮ ምህዳርም ጤናማና ውብ ከሆነ አዲስ ዓለም እንደተሰራ የሚያስብ ሰው ሊኖር ይችላል፡፡ ነገር ግን ደኖች ተቃጥለው፣ ጸሐይ ጨልማ፣ ምድርም በጨለማ ውስጥ ሆና፣ ሰዎች በሞት ሰቆቃ ተይዘውና በየመንገዱ ቆሻሻውና በከፊል የሞቱ ሬሳዎች ሞልተው እያለ ማናችንም በምስሉ ፊት እንድንበረከክና እርሱንም አምላክ ብለን እንድንጠራው የሚሰጠንን የጸረ ክርስቶስ ትዕዛዝ መቼም ቢሆን ልንታዘዘው አንችልም፡፡ በዚህ ጊዜ እያንዳንዱ ዳግመኛ የተወለደ ምዕመን እርሱ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ትንቢት የተነገረለት ጸረ ክርስቶስ እንደሆነ ያውቀዋል፡፡
 
መንፈስ ቅዱስም ደግሞ ያስተምረናል፡፡ እርሱ እጅ የማይሰጥ ልብ ሰጥቶናል፡፡ ‹‹ልትገድለኝ ካለብህ ግደለኝ፡፡ እኔ ብሞት ግን ጌታ ሞቴን በአንተ ላይ ይበቀላል፡፡ በእርግጠኝነትም ከሞት ያስነሳኛል!›› የሚል ደፋር ልብ ሰጥቶናል፡፡ ጌታችን በሦስት ቀን ውስጥ ከሙታን እንደተነሳ ሁሉ እኛም ዳግመኛ ሕያዋን እንደምንሆን እናምናለን፡፡ ጌታም ያለ ችግር ይነጥቀናል፡፡
 
 

ጻድቃን በፍጹም ለጸረ ክርስቶስ አያጎበድዱም፡፡ 

 
እግዚአብሄር ጻድቃን ለሺህ ዓመት ይነግሱበት ዘንድ የመጀመሪያውን ዓለም አጥፍቶ በምትኩ የሺህ ዓመት መንግሥቱን የሚገነባ የመሆኑን ይህንን የተስፋ ቃል የሰሙና በዚህ በማመን ዳግመኛ የተወለዱ ሰዎች ፈጽሞ ለጸረ ክርስቶስ አያጎበድዱም፡፡ ምክንያቱም መንፈስ ቅዱስ በልባቸው ውስጥ ስለሚኖር ሁሉን ነገር ያውቃሉና፡፡ መንፈስ ቅዱስ የሌላቸው ግን ለሕይወታቸው ስለሚሳሱ በመጀመሪያ ሙሉ በሙሉ አዲስ ዓለም የሚመስለውን ሕልቆ መሳፍርት ለመከተል እምቢ ቢሉ እንደሚሞቱ ስለሚፈሩ ለሰይጣን ያጎበድዳሉ፡፡ ሰው ሁሉ እንዲህ ሞትን ሲፈራና የእርሱ አገልጋይ ሲሆን ከዚህ የሞት ፍርሃት ነጻ ሆነው እንደ ጸሐይ ብሩህ በሆነ ምግባር በድፍረት ሰማዕትነታቸውን የሚቀበሉት ዳግመኛ የተወለዱት ብቻ ናቸው፡፡
 
ዳግመኛ የተወለዱ ሰዎች ይህንን ማድረግ የሚችሉት አዲስ አካል ለብሰው እንደሚነሱ ተስፋ ስላላቸው ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ የሚያድርባቸው ሰዎች ሞትን የማይፈሩ ብቻ ሳይሆኑ ጸረ ክርስቶስን የሚቃወሙና ከመንፈስ ቅዱስ በሚፈልቁ የድፍረት ቃሎችም ሚዛኑን የሚያስቱት ለዚህ ነው፡፡ አሁን ፈሪዎች ሊሆኑ ይችላሉ፤ ነገር ግን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል በማመን በመንፈስ ቅዱስ የታተሙ ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ አማካይነት ጠላቶቻቸው መልስ ሊሰጡ የማይችሉባቸውን ቃሎች ይናገራሉ፡፡ እኛ በዚህ የእግዚአብሄር ቃል እናምናለን፡፡
 
ቅዱሳን ‹‹አንተ ራስህን አምላክ ብለህ ለመጥራት እንዴት ደፈርህ! ከሰማይ ተባረህ ነበር፤ በቅርቡም ከምድርም ደግሞ ትባረራለህ! አሁን ቀኖችህ ተቆጥረዋል!›› ሲሉት ጸረ ክርስቶስ ይበሳጫል፡፡ ጥቂቶች ሳይሆኑ ነገር ግን በመላው ዓለም አገሮች የሚገኙ ብዙ ቁጥር ያላቸው ሰዎች በጸረ ክርስቶስ ላይ ተነስተው ይቃወሙታል፡፡ ያን ጊዜ ጸረ ክርስቶስ ሁሉንም ይገድላቸዋል፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱሳን ቢገደሉም እንኳን አያርፉም፡፡ የእግዚአብሄር ቃል ‹‹በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ለአምላካችንና ለበጉ ማዳን ነው›› ብሎ እንደሚነግረን በተስፋና ከመንፈስ ቅዱስ የሚፈልቀውን የእምነት እርግጠኝነት ይዘን እንሞታለን፡፡
 
የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ እንደሚመሰክረው እስጢፋኖስ እስከ ሞት ድረስ ሲወገር ወደ ሰማይ ቀና ብሎ የእግዚአብሄርን ዙፋንና ኢየሱስም እርሱን ሊቀበለው በቀኙ ቆሞ በራዕይ ተመለከተ፡፡ እስጢፋኖስ በሞት አፋፍ ላይ ሆኖ እንኳን ኢየሱስ እርሱን ለሰቀሉት ሰዎች ይቅርታን እንደጠየቀላቸው ሁሉ የሚወግሩት ሰዎች ይቅርታን እንዲያገኙ ጸለየላቸው፡፡
 
በመጨረሻው ዘመን ሰማዕት የሆኑት ቅዱሳንም ልክ እንደ እስጢፋኖስ በመንፈስ ቅዱስ ተሞልተው ይጀግናሉ እንጂ አይናወጡም፡፡ አሁን ፈሪዎችና እምነታቸውም ደካማ ቢመስልም አሁን ይህንን ቃል የሚሰሙ ሁሉ ይህ ዘመን ሲቃረብ ደፋር እምነት ይኖራቸዋል፡፡
 
አትፍሩ፤ የሚያስፈራ ምንም ነገር የለም፡፡ ከጸረ ክርስቶስ መነሳት እስከ መከራው ነፋስ ድረስ ያሉት እነዚህ ሁሉ ነገሮች የሚመጡት በእግዚአብሄር ፈቃድና በራዕይ 6 ላይ በተገለጠው ዕቅዱ ውስጥ ብቻ ነውና፡፡
 
ሰማዕትነት በሥጋችን ጉልበት አይመጣም፡፡ ሰማዕትነት ተግባራዊ ሊሆን የሚችለው በመንፈስ ቅዱስ ሐይልና በእውነት ላይ ባለን እምነት ብቻ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር በእግዚአብሄር፣ በተስፋ ቃሉና ሁሉን ቻዩ አምላክ አምላካችን በመሆኑ እውነታ በማመን ሰማዕት መሆን እንችላለን፡፡ 
 
እግዚአብሄር በዕቅዱ ውስጥ ባሉት በሰባቱ ዘመኖች ውስጥ የፈቀደው ሰማዕትነት የእግዚአብሄር መሰናዶ እንደሆነ አሁኑኑ መረዳት አለባችሁ፡፡ እግዚአብሄር ለእኛ ባለው ዕቅዱ ውስጥ አንዱ ስለሆነው ሰማዕትነታችን በስሜት አናስብ፡፡ ነገር ግን እንደ እግዚአብሄር ፈቃድ በልባችን እንመነው፡፡ ሰማዕት የምንሆንበት ጊዜ ሲመጣ እግዚአብሄር ይህንን የምንጋፈጥበትን በቂ ጉልበት እንደሚሰጠን በማሰብ በእግዚአብሄር ቃል እንመን፡፡
 
በእያንዳንዱ ዓለም ውስጥ አምባገነን መሪ አለ፡፡ ዳግመኛ የተወለዱት የሚመሩት በእግዚአብሄር ነው፡፡ ዳግመኛ ያልተወለዱት ግን የሚመሩት በሰይጣን መንፈስ ነው፡፡ የዘመኑ መጨረሻ ሲመጣ በእግዚአብሄር የሚመሩት ዳግመኛ የተወለዱ ሰዎች ችግሮችንና መከራዎችን የሚሸከሙበትን ጉልበት ከእርሱ ያገኛሉ፡፡ በአንጻሩ በሰይጣን የሚገዙ ሰዎች ቢፈልጉም ባይፈልጉም የእርሱን ፈቃድ ከመከተል ውጭ ምርጫ አይኖራቸውም፡፡ ምክንያቱም በሰይጣን አገዛዝ ስር ናቸውና፡፡
 
ነገር ግን በእርግጥ የላቀው ሐይል የማነው? መባረካችን ወይም መረገማችን የሚወሰነው በእግዚአብሄርና በሰይጣን መካከል ታላቁ ሐይል የማነው በሚለው ጉዳይ ላይ ነው፡፡ በመጨረሻው ዘመን የመዳን ጉዳይ የሚወሰነው ማንን እንደምናምንና እንደምንከተል እንደዚሁም በማን ቃሎች እንደምንታመን ባለን እምነት ላይ ነው፡፡ በእግዚአብሄርና በቃሉ የሚያምኑ ሰዎች ሁሉን በሚችለው አምላክ ሐይልና ሥልጣን ለዘላለም ይጠበቃሉ፤ ይባረካሉ፡፡ የዘላለም ሕይወትም ይሰጣቸዋል፡፡ ነገር ግን የሰይጣንን ቃሎች የሰሙና ለእርሱ ያጎበደዱ ሰዎች እነርሱን ከሲዖል ለማዳን ሐይል ከሌለው ከእርሱ ጋር አብረው ሲዖል ይወረወራሉ፡፡ እግዚአብሄር በራዕይ 1-7 አማካይነት ቃሉን የሰጠው ለዚህ ነው፡፡
 
ከምዕራፍ 8 ጀምሮ ራዕይ በሐመሩ ፈረስ ዘመን ምን እንደሚሆን በዝርዝር ተመዝግቦዋል፡፡ በመጀመሪያ የሰባቱ መለከቶች መቅሰፍቶች በምድር ላይ ይወርዳሉ፡፡ ከእነዚህ ሰባት መቅሰፍቶች ውስጥ በቁጥር 7 ላይ ወደሚገኘው የመጀመሪያ መቅሰፍት እንለፍ፡- ‹‹ፊተኛወም መልአክ ነፋ፤ ደምም የተቀላቀለበት በረዶና እሳት ሆነ፡፡ ወደ ምድርም ተጣለ፡፡ የምድርም ሲሶው ተቃጠለ፡፡ የዛፎችም ሲሶው ተቃጠለ፡፡ የለመለመም ሣር ሁሉ ተቃጠለ፡፡›› በዚህ በፊተኛው መለከት መቅሰፍት ከእሳትና ከደም ጋር የተቀላቀለ በረዶ በምድር ላይ ይዘንባል፡፡ ፕላኔት ምድር ከዚህ ቀደም በብዙ አጋጣሚዎች በተወርዋሪ ኮከቦች ተመትታለች፡፡
 
እስከ አሁን ድረስ ከእነርሱ አንዳቸውም መላውን ዓለም ለማውደም ያን ያህል አጥፊዎች አይደሉም፡፡ ነገር ግን የሐመሩ ፈረስ ዘመን ሲመጣ ሙሉ በሙሉ የሚነፍሰው የመከራው ነፋስ በምድር ሁሉ ላይ ይነፍሳል፡፡ ይህ ነፋስ እንደ ጦሮ አውሎ ነፋስ (ቶርኔዶ) ሲነፍስና ተፈጥሮን ሲጠራርግ እሳት በዚህ ምድር ላይ ይወርድና የዛፎችን ሲሶና ሳርን ሁሉ ያቃጥላል፡፡ ሰው ሁሉ የሚነደውን እሳት ለማጥፋት ይሮጣል፡፡
 
የእግዚአብሄር ቃል የዓለም ደኖች በመጀመሪያው መቅሰፍት ከተቃጠሉ በኋላ በእሳት የሚቃጠል ታላቅ ተራራ -- ይህ ተወርዋሪ ኮከብን ይመስላል -- ባህር ላይ ይወድቃል፡፡ ይህ በሦስተኛው መቅሰፍት ላይ ይበልጥ ተብራርቷል፡፡ ‹‹ሦስተኛውም መልአክ ነፋ፤ እንደ ችቦም የሚቃጠል ታላቅ ኮከብ ከሰማይ ወደቀ፡፡ በወንዞችና በውሃ ምንጮች ሲሶ ላይ ወደቀ፡፡›› በሌላ አነጋገር አንድ ተወርዋሪ ኮከብ ከምድር ጋር ይላተማል፡፡ ዲፕ ኢምፓክት የሚለው ፊልም እንደሚያሳየው አንድ ተወርዋሪ ኮከብ ባህር ውስጥ ይወድቅና ግዙፍ የሆኑ የባህር ማዕበሎችን ያስነሳል፡፡ ሦስተኛው መቅሰፍትም ተመሳሳይ ጥፋትን ያመጣል፡፡ መቅሰፍቱ በዚህ ፊልም ውስጥ እንደሚታየው አውዳሚ አይሆን ይሆናል፡፡ ነገር ግን የተለያዩ የምድር ስፍራዎችን የሚመቱት ተወርዋሪ ኮከቦች በፕላኔት ምድር ላይ የማይናቁ ውድመቶችን ያመጣሉ፡፡ የባህር ማዕበሎችም በባህር ውስጥ ያሉትን ሲሶ ሕያዋን ፍጥረታት ይገድላሉ፡፡ የመርከቦችንም ሲሶ ያወድማሉ፡፡
 
ይህ የመከራ ነፋስ ሲነፍስ የሐመሩ ፈረስ ዘመን መቅረቡን እንገነዘባለን፡፡ ወደፊት እሳት ከሰማይ እየዘነበ እንደሆነና የዓለም ደኖች ሲሶም እንደተቃጠለ የሚነግራችሁ ሰበር ዜና በቴሌቪዥናችሁ መስኮት ውስጥ ሲታይ በመጨረሻ የተጠበቀው እንደመጣ ልትገነዘቡ ይገባችኋል፡፡ መንግሥታቶች ከልጅ እስከ አዋቂ ድረስ እሳቱን ለማጥፋት ሰዎችን ሲያሰማሩ የፍጻሜው መጀመሪያ በመጨረሻ እንደመጣ በእርግጠኝነት ልታውቁ ይገባችኋል፡፡
 
አሁን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የምናምን ሰዎች ከእነዚህ አስፈሪ መቅሰፍቶች የሚያድነን የደህንነት ተስፋ ሊገኝ የሚችለው ሁሉን በሚችለው አምላክ ብቻ ነው፡፡ ጸረ ክርስቶስ ሲገድለን እርሱን መቋቋም የሚችል ምድራዊ ሐይል ስለሌለን ሰማዕት እንሆናለን፡፡ ነገር ግን ሰማዕት የምንሆነው በታላቅ ደስታ ነው፡፡ ሁሉን የሚችለው አምላክ በዚህ አስደንጋጭ መከራ መካከል ሰማዕትነትን በእምነት የምንቀበለውን ሰዎች ከሙታን ያስነሳናል፡፡ ጌታም እረኛችን ይሆናል፡፡ ወደ ሕይወት ውሃም ይመራናል፡፡
 
እግዚአብሄር ዳግመኛ በፍጹም በእሳት የማንቃጠልበት፣ የማንጠማበት፣ በጸሐይ የማንተኮስበት የአምላክ መንግሥት ከገነባ በኋላ ወደዚያ ይወስደናል፡፡ ቃሉ እንደሚነግረን እግዚአብሄር በዚህ መንግሥት ውስጥ አብሮን ይኖራል፤ ያጽናናናል፡፡ ዕንባዎቻችንንም ያብሳል፡፡ ለዘላለምም በክብር እንድንኖር ይፈቅድልናል፡፡ ፈጽሞም ዳግመኛ አንሰቃይም፡፡
 
 
በተስፋው ቃል ላይ ጸንታችሁ ቁሙ፡፡ 
 
በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ሳርፍ ልቤ በተስፋና በመንፈስ ቅዱስ ይሞላል፡፡ እግዚአብሄር ብቻ ከእነዚህ አስፈሪ መቅሰፍቶች ሊያድነን እንደሚችልም እንገነዘባለን፡፡ ‹‹ጌታ ኢየሱስ ሆይ ና!›› እኔ በጌታችን አምናለሁ፡፡ እርሱ ከሐጢያቶቼ ሁሉ እንዳዳነኝ ከዚህ አስፈሪ መከራም እንደሚያድነኝ አምናለሁ፡፡ አብረውኝ ያሉትንም ቅዱሳኖች እንደሚያድን አምናለሁ፡፡ የመጨረሻው ዘመን ከመምጣቱም በፊት ቢሆን የእኔ ደህንነት በዙፋኑ ላይ የተቀመጠው የአምላካችንና የበጉ እንደሆነም አምናለሁ፡፡ የእናንተም ደህንነት እንደዚሁ የሚገኘው በእግዚአብሄር እንደሆነ አምናለሁ፡፡
 
ታላቁ መከራ ሲመጣ ዓለም ፈጥኖ በመቅሰፍቶችና በጥፋቶች ይሞላል፡፡ ነገር ግን ዓለም ምንም ያህል አስቸጋሪ ቢሆንም አምላካችን ከዘመኑ መከራዎችና መቅሰፍቶች ከጠላቶቻችንም ስደት እንደሚያድነን አምናለሁ፡፡ እግዚአብሄር ከሐጢያቶቻችን ሁሉ አድኖን የእርሱ ልጆች እንሆን ዘንድ እምነትን ሰጥቶናል፡፡ እንዲህ እንድንሆንም አድርጎናል፡፡
 
ዳግመኛ ያልተወለዱ ሰዎች ከእኛ ይበልጥ በጣም ምስኪኖች ናቸው፡፡ ሁሉም ነገር በሚቃጠልበትና ጥፋት በሚገኝበት ጊዜ ፍጹም የሆነ መታመንን የሚያኖሩበት አምላክ የሌላቸው ሰዎች ምንኛ ምስኪኖች ናቸው? አንዳንድ ሰዎች ቡዲዝምም ይሁን እስልምና በሞት ሽረት ውስጥ ተስፋን አያገኙም ይላሉ፡፡ የሚጠብቃቸው ተስፋ መቁረጥና መሸበር ብቻ ነው፡፡ እንዲህ ባለ ተስፋ አስቆራጭ ሁኔታ ውስጥ መጨረሻቸውን የሚጋፈጡ ብዙ ሰዎች ይኖራሉ፡፡ እኛም እንደዚሁ እነዚህ ሰዎች የሚገጥሙዋቸው ተመሳሳይ ሽብር ተመሳሳይ ችግሮች ይገጥሙናል፡፡ ነገር ግን ልባችን ከእነርሱ ልብ የተለየ ነው፡፡ አሁን እምነታችን የምናዘጋጅ ሰዎች ከሌሎቹ የተለየን ሰዎች ነን፡፡ እግዚአብሄር በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ሐጢያት አልባ አድርጎናልና፡፡
 
ዮሐንስ 1፡12 እንዲህ ይነግናል፡- ‹‹ለተቀበሉት ሁሉ ግን በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሄር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው፡፡›› በሌላ አነጋገር እግዚአብሄር ‹‹ልጆቼ ናችሁ›› በማለት የእርሱ ልጆች በምንሆንበት መብት አትሞናል፡፡ ይህንን ታላቅና ክቡር መብት ሰጥቶናል፡፡ እኛ የእግዚአብሄር ልጆች ነን፡፡ በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ስናምን በልባችን ውስጥ የቀረ አንዳች ሐጢያት አለን? በእርግጥ የለም! የእግዚአብሄር ልጆች አልሆንምን? በእርግጥ ሆነናል! የእግዚአብሄር ልጆች የመጽሐፍ ቅዱስ ዕውቀት የሚጎድላቸውና በብዙ ጉድለቶች ውስጥ ያሉ ከሆኑ ይህ ማለት እግዚአብሄር የእነርሱ አባት ሆኖ አይጠብቃቸውም ማለት ነውን? በእርግጥ አይደለም! ወላጆች ዕውቀት የሚጎድላቸውን ልጆቻቸውን እንደሚጠብቁና እንደሚንከባከቡ ሁሉ እግዚአብሄርም ደካሞች ለሆንን ሰዎች ብዙ ጉልበትንና ብዙ ጥበቃን ያደርግልናል፡፡
 
በጸረ ክርስቶስ መገለጥ ሁከት ሲበዛ እግዚአብሄር በመንፈስ ቅዱስ አማካይነት ልጆቹን ያጠነክራቸዋል፡፡ እምነትን፣ ተስፋንና ድፍረትንም ይሰጣቸዋል፡፡ እርሱ ድፍረትን ስለሚሰጠን አንፈራም፡፡ በልባችን ውስጥ ከሚነሳው ከራሱ ከፍርሃት በቀር የምንፈራው ምንም ነገር የለንም፡፡ ሰዎች በዙሪያቸው የሆነውን ነገር በመሸሽ ሊያስወግዱት ይችላሉ፡፡ ነገር ግን የትም ቦታ ቢሄዱ በልባቸው ውስጥ ያለ ፍርሃት ሊወገድ አይችልም፡፡ በመኝታ ቤቶች ውስጥ በመደበቅ፣ ከወለል በታች በመደበቅ፣ በቦምብ መጠለያዎች ውስጥ በመጠለል ልባቸውን አንቆ ከያዘው ከዚህ ፍርሃት ማምለጥ ከያዘው አይችሉም፡፡
 
በአንጻሩ የቅዱሳን ልብ ድፍረት እንጂ ፍርሃት የለበትም፡፡ በዚህም ለራሳቸው ‹‹በመጨረሻ የተጠበቀው ደረሰ፡፡ ይህ ጌታ የሚመጣበት ዘመን ነው! በቅርቡ ይወስደናል!›› በማለት ሰማዕትነታቸውን በድፍረት ይቀበሉታል፡፡ ንጥቀት የሚሆነው እንዲህ ነው፡፡ ንጥቀት የሚሆነው የዓለም ሲሶ በሚነድበት ጊዜ ነው፡፡ ነገር ግን መከራው ይበልጥ አስከፊ ከመሆኑ በፊት እግዚአብሄር ቅዱሳንን ይነጥቃቸዋል፡፡
 
አሁን እግዚአብሄር በእርግጥም ሰባት ዘመኖችን እንደወሰነላችሁ ታምናላችሁን? ራዕይ 6 ይህንን እንዳደረገ ይነግረናል፡፡ እግዚአብሄር በቅዱሳን ላይ እንደሚመጣ የተናገረውን ነገር ሁሉ በተጻፈው መሰረት ይፈጽማል፡፡ ስለዚህ የሐጢያቶቻቸውን ስርየት ያገኙ ሰዎች በአያሌው ተባርከዋል፡፡ ነገር ግን ያመነቱና በወንጌል ያላመኑ ሰዎች መጨረሻቸው ሲዖል የሚሆን ዕድለ ቢሶች ናቸው፡፡ እግዚአብሄር ወደፊት አስከፊ መቅሰፍቶች እንደሚመጡ ነግሮናል፡፡ እነዚህ መቅሰፍቶች ሲጠናቀቁ ዳግመኛ ያልተወለዱ ሰዎች ወደ ዘላለም የእሳትና ዲን ባህር ይጣላሉ፡፡ እግዚአብሄር አሁን ሰላማዊ ዓለም የሰጠንና በዚህ ሰላማዊ ዘመን ወንጌሉን በሐላፊነት ያስረከበን ለዚህ ነው፡፡
 
እግዚአብሄር ከ2,000 ዓመታት በፊት የሰው ሥጋ ለብሶ ወደዚህ ምድር መጣ፡፡ ለእኛ ሲልም ሐጢያቶቻችንን ሁሉ ለመውሰድ ተጠመቀ፡፡ በመስቀል ላይ በመሞትም ከዓለም ሐጢያቶች ሁሉ አዳነን፡፡ አዳኛችን በመሆኑም አዳነን፡፡ በእግዚአብሄርና በማዳኑ በማመን እንድንድን የፈቀደልንን በረከቱንም ለግሶናል፡፡ ይህ የእግዚአብሄር ጸጋ ነው፡፡ የእግዚአብሄርን አንድያ ልጅ ወደ እኛ በመላክ፣ ሐጢያቶቻችንንም ወደ እርሱ በማስተላለፍ፣ በእኛ ፋንታም ልጁን በመኮነን ከሐጢያቶቻችን ሁሉና ከእግዚአብሄር ፍርድ ያዳነን ወንጌል ይህ ነው፡፡ አሁን በዚህ በማመን የእግዚአብሄርን ጸጋ ለብሰናል፡፡ ከእርሱ ዘንድም የዘላለምን ሕይወት ተቀብለናል፡፡ እኛ በዚህ ስለምናምን የእግዚአብሄር ልጆች ሆነናል፡፡ አሁን የእግዚአብሄር ልጆች ስለሆንን የዘመኑ መጨረሻ መከራ እጅግ አስከፊ ወደሆነ ደረጃ ሲደርስ ይነጥቀናል፤ ይጠብቀንማል፡፡ 
 
በዚህ ጊዜ የእግዚአብሄር ልጆችና የሰይጣን ልጆች አንዳቸው ከሌላቸው በግልጽ ይለያሉ፡፡ የማያሳስቱት ልዩነቶቻቸው በግልጽ ይለያሉ፡፡ ይህ ወደ በኋላ በጣም ዘርዘር ባለ መልኩ ይብራራል፡፡ አሁን ልታስታውሱት የሚገባችሁ ነገር ቢኖር ታላቁ መከራ ሲመጣብንና እኛም ሰማዕት ስንሆን በእግዚአብሄር ፊት ትንሳኤ እንደምናገኝና እንደምንነጠቅ ነው፡፡ ይህንን የሚያምን ወይም የማያምን ሰው ቢኖር ምንም ማለት አይደለም፡፡ ይህ መሆኑ አይቀርም፡፡ እግዚአብሄር ነፋሳቶቹን እንደሚለቅና እነዚህም ነገሮች ሁሉ እንደሚመጡ ተናግሮዋል፡፡
 
ቁጥር 1 እንዲህ ይነግረናል፡- ‹‹ከዚህ በኋላም በአራቱ የምድር ማዕዘን ቆመው አራት መላዕክት አየሁ፡፡ እነርሱም ነፋስ በምድር ቢሆን ወይም በባሕር ወይም በማንም ዛፍ እንዳይነፍስ አራቱን የምድር ነፋሳት ያዙ፡፡›› እግዚአብሄር እነዚህ ነፋሳቶች አሁን እንዳይነፍሱ ይዞዋቸዋል፡፡ በሌላ አነጋገር ይህ ማለት እግዚአብሄር ሲፈቅድ እነዚህ ነፋሳቶች በአራቱ የምድር ማዕዘናት ይነፍሳሉ ማለት ነው፡፡ እግዚአብሄር ሲፈቅድላቸው የእግዚአብሄር መላዕክቶች እነዚህን ነፋሳት ይለቁዋቸውና የሐመሩ ፈረስ ዘመን ይመጣል፡፡ የታላቁ መከራ ነፋስ እንዲህ መንፈስ ሲጀምር በዓለም ላይ በየስፍራው የተፈጥሮ ጥፋቶችንና ጦርነቶችን ስለሚያመጣ ሰው ሁሉ በጥፋቶች ውስጥ ያልፋል፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር እስከ አሁን ድረስ እነዚህን ነፋሳቶች ይዞዋቸዋል፡፡
 
በዓለም ዙሪያ ያሉ አገሮች የጦር መሳርያዎችን ለማምረት ገንዘባቸውን ያውላሉ፡፡ ታላላቅ ሐያላን መንግሥታቶች ከዓመታዊ ገቢያቸው 30 እጅ የሚሆነውን ለወታደራዊ አቅም የሚያውሉበት ጊዜ ይመጣ ይሆናል፡፡ አሁንም እንኳን ብዙ መጠን ያላቸው አዳዲስና ይበልጥ ገዳይ የሆኑ የጦር መሳሪያዎችን ማለትም ሕዝብ ጨራሽ መሳርያዎችን በማምረት ጥረት ውስጥ እጅግ ከፍተኛ የሆነ የገንዘብ መጠን በወታደራዊ አቅም ላይ እየዋለ ነው፡፡ ኢኮኖሚው በሚያገግምበት ጊዜ ሁሉ ትርፉ የሚውለው ወታደራዊ ወጭዎችን በማስፋት ነው፡፡
 
ለምሳሌ አሜሪካ በአሁኑ ጊዜ ‹‹የከዋክብት ጦርነት ዕቅድ›› ተብሎ የሚጠራውን የሚሳኤል መከላከያ ሲስተም ለመገንባት እየተገፋፋች ነው፡፡ ይህ ሲስተም ሙሉ በሙሉ ሲመረት ጦርነት በምድር ላይ ብቻ ሳይሆን በሕዋ ላይም ይካሄዳል፡፡ የጦር መሳርያ የታጠቁ ሳተላይቶች ከከባቢ አየር ውጭ ያሉ ተምዘግዛጊ ባለስቲክ ሚሳኤሎችን በራሳቸው ሚሳኤሎች መትተው ይጥላሉ፡፡ ያን ጊዜ የአየር ላይ ጦርነት ሙሉ በሙሉ አዲስ ትርጉም ይኖረዋል፡፡ ስለዚህ አሁን የሚነሳው ጥያቄ ተጨማሪ ሥነ ከባቢ አየራዊ የጦር መሳሪያዎችን ቀድሞ የሚያመርተውና ሕዋውን ለወታደራዊ ጥቅም የሚያውለው ማነው የሚለው ነው፡፡
 
እንደዚህ ያሉ ዝግጅቶችን ስንመለከት እግዚአብሄር ሲፈቅድና አስፈሪ መቅሰፍቶች በምድር ላይ ሲወርዱ ትንቢት የተነገረለት መሪ አምባገነን ሥልጣኑን ይዞ ብቅ ይላል፡፡
 
ነገር ግን እነዚህ ነገሮች ሁሉ ሊሆኑ የሚችሉት እግዚአብሄር ሲፈቅድላቸው ብቻ ነው፡፡ ዓለም ምንም ያህል አስቸጋሪ ሆና ብትለወጥም እግዚአብሄር እረኛችን እንደሚሆን፣ ወደ ሕይወት ውሃ ምንጮች እንደሚመራንና ከዓይኖቻችንም ዕንባዎችን ሁሉ እንደሚያብስ እናምናለን፡፡ የዳኑት እንዲህ በአያሌው የተባረኩት ለዚህ ነው፡፡
 
በኢየሱስ ስታምኑ በእርሱ የምታምኑት እናንተ በተሰማችሁ በማናቸውም መንገድ አይደለም፡፡ እውነተኛ እምነት በእግዚአብሄር ቃል የሚያምኑ ሰዎች እምነት ነው፡፡
 
ዮሐንስ ራዕይ 7፡14 እንዲህ ይነግረናል፡- ‹‹እኔም፡- ጌታ ሆይ አንተ ታውለህ አልሁት፡፡ አለኝም እነዚህ ከታላቁ መከራ የመጡ ናቸው፡፡ ልብሳቸውንም አጥበው በበጉ ደም አነጹ፡፡›› ‹‹ልብሳቸውን በበጉ ደም አጥበው አነጹ›› ማለት በጌታ ባላቸው እምነት ሰማዕት ሆነዋል ማለት ነው፡፡ ይህንን ቁጥር ስትተረጉሙት ተጠንቀቁ፡፡ ይህ በመስቀሉ ደም በማመን ብቻ መዳንን አያመላክትም፡፡
 
ነገር ግን በልባቸው ውስጥ መንፈስ ቅዱስ የሌላቸው ሰዎች የእግዚአብሄር ልጆች እንዳልሆኑና በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የማያምኑ ሰዎችም ፈጽሞ በወንጌል የማያምኑ ሰዎች መሆናቸውን መገንዘብ አለባችሁ፡፡ ሰማዕትነታቸውን መቀበል የሚችሉት፣ መከራውን የሚያሸንፉትና ለጌታም ታላቅ ክብርን የሚያቀርቡት በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑ ሰዎች ብቻ ናቸው፡፡
 
እኛ በእግዚአብሄር ስለምናምን ታላቅ የችግርና የመከራ ዘመን ሲመጣ እምነታችንን አናጣም፡፡ ለሰይጣንም አናጎበድድም፡፡ ከእግዚአብሄር በተቀበልነው ጉልበት ሰማዕትነታችንን እንቀበላለን፡፡ ያን ጊዜ ጌታ ያስነሳንና ይጠብቀናል፡፡ በጉም እረኛችን ይሆናል፡፡ ዕንባዎችንም ከዓይኖቻችን ያብሳል፡፡ ዳግመኛም አንራብም፤ አንጠማም፡፡ በትኩሳትም አንቃጠልም፡፡ ፈጽሞም በማናቸውም ሌላ ነገር አንቸገርም፡፡ ለምን? ቀድሞውኑም በታላቅ መከራ ውስጥ ስላለፍን እግዚአብሄር መከራን ለዘላለም ያስወግደዋልና፡፡ ሰማይ የሚባለው የእግዚአብሄር ዓለም ይህን ያህል ድንቅ ነው፡፡ እንዲህ ያለ ግሩም ስፍራ ስለሆነ ሰዎች የመልካም ነገር ሁሉ ምሳሌ አድርገው ገነት ወይም ሰማይ ብለው ይጠሩታል፡፡
 
ገነት ማለቂያ የሌለው ደስታ ስፍራ ነው፡፡ በቡዲዝም ሐይማኖት ገነት አማልክት ቡድሃ ለሚሆኑ ሰዎች ብቻ የተወሰነ ስፍራ ነው፡፡ ወደ ቡድሃነት መለወጥ የሚችል አማልክት መሆን የሚችል ሰው በእርግጥ ይኖራልን? አይኖርም! ሲድሃርታ ራሱ በሞት አፋፍ ላይ ሳለ ‹‹አማልክት ሁኑ፡፡ ከዓለም አሰቃቂ ነገሮች ሁሉ ማምለጥ የምትችሉት አምላክ ስትሆኑ ብቻ ነው›› በማለት ተናግሮዋል፡፡ ነገር ግን ማንም ሰው በራሱ ከሐጢያት ማምለጥና ገዳይ የሆኑትን የሐጢያት አሰቃቂ ነገሮች ማሸነፍ አይችልም፡፡ ሲድሃርታ ራሱ ማምለጥ አልቻለም፡፡ ሌላውም ሰው ሁሉ ማምለጥ አይችልም፡፡ ቃሉ እንዲህ ይነግረናል፡- ‹‹መዳን በሌላ በማንም የለም፡፡ እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች የለምና፡፡›› (የሐዋርያት ሥራ 4፡12) ደህንነታችንን ያገኘነው ዩኒቨርስንና እኛን በፈጠረው በእግዚአብሄር በኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ከአስፈሪዎቹ መቅሰፍቶች የሚያድነን አዳኝ እንደሆነ የሚናገረው ይህ እውነት እግዚአብሄር በመንፈስ ቅዱስ አማካይነት እያስተማረን ያለው ትምህርት ነው፡፡
 
ሰማይ እጅግ ግሩም ስፍራ ነው፡፡ ለዘላለም በክብርና በሞገስ በደስታ መኖር ትፈልጋላችሁን? አንዳች ነገር ሳይጎድላችሁ በዘላለም ደስታ ውስጥ ለመኖር ትፈልጋላችሁን? አንዳች ነገር ሳይጎድላችሁ በፍጹማዊነትና በሙላት መኖር ትፈልጋላችሁን? እግዚአብሄር እንድንኖርበት የጠራን ስፍራ እንዲህ ያለ ስፍራ ነው፡፡ ሰማይ ነው፡፡ አንዳች የሚጎድለው ነገር የለውም፡፡ አንዳች ዕጦትም አይገኝበትም፡፡ ዳግመኛ አትታመሙም፡፡ በትኩሳትም አትሰቃዩም፡፡ አንዳች ዕንባም አታፈሱም፡፡
 
ኢየሱስ በተሰቀለ ጊዜ ከጎኑ ተሰቅሎ ለነበረው ወንበዴ ‹‹እውነት እልሃለሁ፤ ዛሬ ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ›› አለው፡፡ ‹‹ገነት›› ማለት ቃል በቃል የደስታ አጸድ ማለት ነው፡፡ ሰው በደስታና በሐሴት የሚፈነጥዝበት ስፍራ ነው፡፡ በዚህ ምድር ላይ እንድንደሰትና እንድንፈነድቅ የሚያደርጉን ሁሉ እግዚአብሄር እኛን በሚጠራበት በዚህ ስፍራም ከመጠን በላይ ይተረፈረፋሉ፡፡ በዚህ እመኑ፡፡ ይህንን ሰማይ፣ ይህንን ገነት፣ ይህንን የእግዚአብሄር መንግሥት የራሳችሁ አድርጉት፡፡ የእግዚአብሄር መንግሥት ፍጹምና በጎ ነው፡፡ በዚህ ምድር ላይ ያሉት መንግሥታቶች ያሉባቸው ሕጸጾች በእርሱ ውስጥ ሊገኝ አይችልም፡፡
 
እግዚአብሄር ሁሉን ቻይ ስለሆነ ይህንን መንግሥት ይሰጠናል፡፡ ጌታችን ሁሉን ቻይ ጌታ ስለሆነ የራሱን ሕዝብ ያድናቸዋል፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ ምንም ዕንባ እንዳያፈስሱና በምንም ነገር እንዳይጨነቁ ያደርጋቸዋል፡፡ ወደ ሕይወት ውሃ ምንጭም ይመራናል፡፡ በዘላለም ሕይወት፣ በዘላለም ሐሴትና በዘላለም ደስታ ውስጥ እንድንኖር ይመራናል፡፡ እነዚህ ነገሮች በሙሉ እንደሚቻሉ አምናለሁ፡፡ ምክንያቱም የእርሱ ሐይል ሁሉን የሚችል ነውና፡፡
 
ያዳነን እግዚአብሄር አቅም አልባ ቢሆን ኖሮ እኛም እንደዚሁ አቅም አልባ በሆንን ነበር፡፡ እርሱ ፍጹማዊ በሆነ ሐይሉ ሐጢያት አልባ አድርጎናል፡፡ እኛም የእግዚአብሄር ቅዱሳን ተብለን ተጠርተናል፡፡
 
በዚህ ምድር ላይ ያለን ሕይወት ምን ዓይነት መሆኑ ያን ያህል ከቁም ነገር የሚገባ አይደለም፡፡ ምንም እንኳን ሕይወታችን እስከ አሁን ድረስ ዳግመኛ ካልተወለዱት ሰዎች የከፋ ቢሆንም የእግዚአብሄር ልጆች ስለሆንንና የነገሥታት ንጉሥ ሐይል ስላለን የሐመሩ ፈረስ ዘመንና የጌታችን ምጽዓት ሲቃረብ በእርግጠኝነት ወደ ራሱ ይጠራንና በገነቱ ውስጥ እንድንኖር ይፈቅድልናል፡፡ አንዳች አይጎድለንም፡፡ መላዕክቶችም እንኳን አገልጋዮቻችን እስኪሆኑ ድረስ ፍጹማዊ በሆነ ሥልጣን እንነግሳለን፡፡ ቅዱሳን በግርማና በክብር ሁሉ ለዘላለም ይኖራሉ፡፡
 
ቅዱሳን ዳግመኛ በፍጹም አይሞቱም፡፡ ሐይማኖቶች ሁሉ የሚያልሙት ይህንን ነው፡፡ ለዘላለም መኖር፣ መንገሥና ሰማይ መግባት፡፡ ይህ በረከት ለእኔ ብቻ የተሰጠ አይደለም፡፡ እግዚአብሄር ግን በእኩል ደረጃ ለእናንተም ደግሞ ለግሶችኋል፡፡
 
ጊዜው ሲደርስ እግዚአብሄር የመከራዎችን ነፋስ እንደሚያስነሳ አምናለሁ፡፡ ይህ የመከራ ነፋስ ሲነፍስ ዲያብሎስን የምንቋቋምበትን ጉልበት ይሰጠናል፡፡ በመጨረሻም ይነጥቀናል፡፡ ለዘላለምም በደስታ እንድንኖር እንደሚፈቅድልንም አምናለሁ፡፡
 
እግዚአብሄር እነዚህን ነገሮች ሁሉ ተስፋ አልሰጠንምን? በእርግጥም ሰጥቶናል! እንዲህ በማለት ነግሮናል፡- ‹‹ልባችሁ አይታወክ፡፡ በእግዚአብሄር እመኑ፤ በእኔም ደግሞ እመኑ፡፡ በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ፡፡ እንዲህስ ባይሆን ባልኋችሁ ነበር፡፡ ሥፍራ አዘጋጅላችሁ ዘንድ እሄዳለሁና፡፡ ሄጄም ሥፍራ ባዘጋጀሁላችሁ እኔ ባለሁበት እናንተ ደግሞ እንድትሆኑ ሁለተኛ እመጣለሁ፤ ወደ እኔም እወስዳችኋለሁ፡፡›› (ዮሐንስ 14፡1-3) ጌታችን ተስፋ የሰጠን ይህንን ነው፡፡ በራዕይ 20-22 ላይ የእግዚአብሄር ቃል በሙሉ እርሱ ለእኛ የሰጠን የተስፋ ቃሉ ነው፡፡
ሐሌሉያ! ምስጋናዬን ሁሉ ለእግዚአብሄር አቀርባለሁ፡፡