Search

ስብከቶች፤

ርዕስ 3፡ የውሃውና የመንፈሱ ወንጌል

[3-8] የኢየሱስ ጥምቀት ለቤዛነት አስፈላጊ የሆነ ሒደት ነው፡፡ ‹‹ ማቴዎስ 3፡13-17 ››

የኢየሱስ ጥምቀት ለቤዛነት አስፈላጊ የሆነ ሒደት ነው፡፡
‹‹ ማቴዎስ 3፡13-17 ››
‹‹ያን ጊዜ ኢየሱስ በዮሐንስ ሊጠመቅ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ መጣ፡፡ ዮሐንስ ግን፡- እኔ በአንተ ልጠመቅ ያስፈልገኛል፤ አንተም ወደ እኔ ትመጣለህን? ብሎ ይከለክለው ነበር፡፡ ኢየሱስም መልሶ፡- አሁንስ ፍቀድልኝ፤ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና አለው፡፡ ያን ጊዜ ፈቀደለት፡፡ ኢየሱስም ከጠመቀ በኋላ ወዲያው ከውሃ ወጣ፡፡ እነሆም ሰማያት ተከፈቱ፡፡ የእግዚአብሄርም መንፈስ እንደ ርግብ ሲወርድ በእርሱ ላይም ሲመጣ አየ፡፡ እነሆም ድምጽ ከሰማያት መጥቶ በእርሱ ደስ የሚለኝ ልጄ ይህ ነው አለ፡፡››   
 
 

የአጥማቂው ዮሐንስ ጥምቀት፡፡ 

 
ንስሐ ምንድነው?
ለመቀደስ በሐጢያት ከተሞላ ሕይወት መመለስና በኢየሱስ ማመን ማለት ነው፡፡ 

በዓለም ላይ የሚኖሩ ብዙ ሰዎች ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም ለምን እንደመጣና በአጥማቂው ዮሐንስ እንደተጠመቀ አያውቁም፡፡ ስለዚህ ስለ ኢየሱስ ጥምቀት ዓላማና ኢየሱስን ስላጠመቀው አጥማቂው ዮሐንስ እናውራ፡፡
በመጀመሪያ አጥማቂው ዮሐንስ ሕዝቡን በዮርዳኖስ እንዲያጠምቅ ስለመራው ጉዳይ እናስብ፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ ሕዝቡን ያጠመቀው ሐጢያቶቻቸውን በመናዘዝ ከሐጢያቶች ወደ እግዚአብሄር እንዲመለሱ ለማድረግ እንደሆነ በማቴዎስ 3፡1-12 ላይ የተብራራ ነው፡፡   
‹‹እኔ ለንስሐ በውሃ አጠምቃችኋለሁ፡፡›› (ቁጥር 11) ‹‹የጌታን መንገድ አዘጋጁ፤ ጥርጊያውንም አቅኑ እያለ በምድረ በዳ የሚጮህ ሰው ድምጽ፡፡›› (ቁጥር 3) አጥማቂው ዮሐንስ የግመል ጠጉር ለብሶና የአንበጣ መንጎችን ተሸክሞ ለሐጢያቶች የንስሐ ጥምቀትን እየሰበከ በምድረ በዳ ይጮህ ነበር፡፡
ለሕዝቡም ‹‹ንስሐ ግቡ የሰው ዘር አዳኝ እየመጣ ነው፡፡ የእርሱን የደህንነት መንገድ አዘጋጁ፡፡ የአሕዛቦችን አማልክቶች ማምለክ አቁሙና ጌታን በልባችሁ ተቀበሉ›› እያለ ይሰብክ ነበር፡፡    
ከምን መመለስ? ጣዖታትን ከማምለክና በሐጢያት የተሞላው ሕይወት ከሚሰራቸው ሌሎች ክፉ ድርጊቶች ሁሉ፡፡ ስለዚህ እኛ ማድረግ ያለብን ነገር ምንድነው? ለመቀደስ በኢየሱስ ውስጥ መጠመቅ አለብን፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ በምድረ በዳ ሲጮህ ‹‹ኑና በእኔ ተጠመቁ፤ ሐጢያቶቻችሁንም አንጹ፡፡ አዳኙ መሲሃችሁ እየመጣ ነው፡፡ እንደ ብሉይ ኪዳን የመስዋዕት በግ ሐጢያቶቻችሁን በሙሉ ይወስድና ሐጢያቶቻችሁን በሙሉ ያነጻላችኋል›› እያለ ጮኸ፡፡ 
በብሉይ ኪዳን የዘወትር ሐጢያቶች በእጆች መጫን አማካይነት ወደ ሐጢያት ቁርባኑ ይተላለፉ ነበር፡፡ የእስራኤሎች ሁሉ አመታዊ ሐጢያቶችም እንደዚሁ በየዓመቱ በሰባተኛው ወር በአስረኛው ቀን በሚውለው የስርየት ቀን በሊቀ ካህኑ አማካይነት ወደ ፍየሉ ይተላለፉ ነበር፡፡ (ዘሌዋውያን 16፡29-31)
በተመሳሳይ መንገድ የሰው ዘር ሐጢያቶች በእርሱ በኩል ይደመሰሱ ዘንድ በጥምቀቱ አማካይነት በአንድ ጊዜ ወደ ኢየሱስ መሻገር ነበረባቸው፡፡ ስለዚህ ዮሐንስ ሕዝቡን ወደ ኢየሱስ እንዲመለሱና እንዲጠመቁ ወተወታቸው፡፡    
በአጥማቂው ዮሐንስ የተፈጸመው ጥምቀት የመጀመሪያ ጠቀሜታው የእስራኤልን ሕዝብ በኋላ ሊመጣ ወደነበረው ኢየሱስ የመለሰው ንስሐ ነበር፡፡ ንስሐ ማለት ከሐጢያት ሕይወት መመለስና የሐጢያቶች ይቅርታን ለማግኘት በመሲሁ ማመን ማለት ነው፡፡ 
የእስራኤል ሕዝቦች ሐጢያቶቻቸውን ለማንጻት በኋላ  የሚመጣውን መሲህ ተስፋ በማድረግ ከሐጢያቶቻቸው መቤዠት ይችሉ ነበር፡፡ በተመሳሳይ መንገድ እኛም ከ2,000 ዓመታት በፊት በወረደውና የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለማንጻት በመጣው በኢየሱስ ቤዛነትን አግኝተናል፡፡ ነገር ግን በብሉይ ኪዳን የነበሩት እስራኤሎች የእግዚአብሄርን ሕግ ትተው የተሳሳቱ መስዋዕቶችን አቀረቡና መሲሁን ረሱት፡፡  
አጥማቂው ዮሐንስ የእግዚአብሄርን ሕግና በኋላ የሚመጣውን መሲህ ሊያስታውሳቸው ስለፈለገ ሰዎችን ማጥመቅ ጀመረ፡፡ ውሎ አድሮም ኢየሱስን በዮርዳኖስ አጠመቀው፡፡  
ብዙ ሰዎች ጣዖታትን ከማምለክና የእግዚአብሄርን ሕግ ከመተዋቸው ንስሐ እየገቡ ወደ ዮሐንስ መጡና ተጠመቁ፡፡ በአንድ ተገቢ መስዋዕት ውስጥ ሦስት አስፈላጊ ፍሬ ነገሮች --በሕይወት ያለ እንስሳ፣ እጆችን መጫንና ደሙ-- አሉ፡፡ የዓለም ሕዝብ በሙሉ በኢየሱስ በማመን ድኖዋል፡፡
ፈሪሳውያንና ሰዱቃውያን ሊጠመቁ በመጡ ጊዜ ዮሐንስ እንዲህ ሲል ጮኸባቸው፡፡ ‹‹እናንተ የእፉኝት ልጆች ከሚመጣው ቁጣ እንድትሸሹ ማን አመለከታችሁ? እንግዲህ ለንስሐ የሚገባ ፍሬ አድርጉ፡፡ በልባችሁም፡- አብርሃም አባት አለን እንደምትሉ አይምሰላችሁ፡፡›› (ማቴዎስ 3፡7-9)
የፖለቲከኞችና የጣዖት አምላኪዎች ቡድኖች የሆኑ እነዚህ ፈሪሳውያንና ሰዱቃውያን ምንም እንኳን በእግዚአብሄር ቃል የማያምኑ ቢሆኑም የእግዚአብሄር ልጆች እንደነበሩ አሰቡ፡፡ እነርሱ በሌሎች አማልክቶችና በራሳቸው አስተሳሰቦች አመኑ፡፡  
እነርሱ ለመጠመቅ ወደ አጥማቂው ዮሐንስ በመጡ ጊዜ ‹‹የተሳሳቱ መስዋዕቶችን ማቅረብ አይገባችሁም፡፡ ነገር ግን ከሐጢያት ተመለሱና መሲሁ እንደሚመጣና ከሐጢያቶቻችሁ እንደሚያነጻችሁ ከልባችሁ እመኑ፡፡ ይህንን በልቦቻችሁ ማመን ይገባችኋል›› ብሎ ነገራቸው፡፡    
ንስሐ መግባት ማለት ከስህተት መንገድ መመለስ ማለት ነው፡፡ እውነተኛ ንስሐ ከሐጢያትና ከሐሰት አመኔታዎች ወደ ኢየሱስ መመለስ ነው፡፡ ይህም በጥምቀቱ ቤዛነትና በመስቀል ላይ ፍርዱ ማመንን ማለት ነው፡፡  
ከዚህ የተነሳ አጥማቂው ዮሐንስ ወደ እግዚአብሄር እንዲመለሱ ለማሳመን የእግዚአብሄርን ሕግና የመስዋዕት ስርዓት ችላ ላሉት የእስራኤል ሕዝቦች ተማህጽኖውን አቀረበ፡፡ በእርሱ እንዲያምኑና ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ እንዲድኑ ሕዝቡን ወደ ኢየሱስ ማቅረብ የአጥማቂው ዮሐንስ ሚና ነበር፡፡  
 
 

በኢየሱስ ጥምቀት አማካይነት በሆነው ቤዛነት ታምናላችሁን?  

 
ሰዎች ሁሉ በእግዚአብሄር ፊት ማድረግ ያለባቸው ምንድነው?
ከሐጢያቶቻቸው ሁሉ ለመዳን በእርሱ ማመን አለባቸው፡፡ 

ኢየሱስ በይፋ በጀመረው አገልግሎቱ ያደረገው የመጀመሪያው ነገር በአጥማቂው ዮሐንስ መጠመቅ ነበር፡፡ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ በዚህ መንገድ ወደ እርሱ ተሻግረዋል፡፡  
ስለዚህ የኢየሱስ ጥምቀት እግዚአብሄር የሰውን ዘር ከሐጢያት ለማንጻት የጀመረው የመጀመሪያው ተግባር እንደዚሁም ይህም የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ የወሰደበት የኢየሱስ የጽድቅ ተግባር ነበር፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱ አማካይነት የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በመውሰዱ እውነት  የሚያምኑትን ሁሉ ተቤዣቸው፡፡   
ኢየሱስ ወደዚህ ምድር በመጣና በአጥማቂው ዮሐንስ በተጠመቀ ጊዜ የመንግሥተ ሰማይ ወንጌል ጀመረ፡፡ በእርሱ ጥምቀት ሰማያት ተከፈቱ፡፡ በማቴዎስ 3፡15 ላይ እንደተገለጠውም ይህ በብሉይ ኪዳን በዘሌዋውያን 1፡1-5፤4፡27-31 ላይ በትክክል እንደተብራራው የስርየት መስዋዕትን ይመስላል፡፡   
በብሉይ ኪዳን ውስጥ ያለው እያንዳንዱ ነገር በአዲስ ኪዳን ውስጥ ባልንጀራ አለው፡፡ በግልባጩም እንደዚሁ ነው፡፡ ‹‹በእግዚአብሄር መጽሐፍ ፈልጉ አንብቡም፡፡ አፌ አዝዞአልና፤ መንፈሱም ሰብስቦአቸዋልና፡፡ ከእነዚህም አንዲት አትጠፋም፡፡ ባልንጀራውንም የሚያጣ የለም፡፡›› (ኢሳይያስ 34፡16) 
 
 

ብሉይና አዲስ ኪዳናት ስርየትን ስላገኙት የሕዝቡ ሐጢያቶች በሙሉ ይናገራሉ፡፡ 

 
ለዘወትር ሐጢያቶቻችን በየቀኑ ንስሐ መግባት ይኖርብናልን?
አይኖርብንም፡፡ እውነተኛ ንስሐ ሐጢያቶችን በሙሉ ማመንና ቤዛነትን ለማግኘት ልቡናን ወደ ኢየሱስ ጥምቀት መመለስ ነው፡፡ 

በብሉይ ኪዳን የቀኑ ሐጢያት በእጆች መጫን አማካይነት ወደ ሐጢያት ቁርባኑ ይሻገራል፡፡ ከዚያም ቁርባኑ በሐጢያተኛው ምትክ ይደማና ይፈረድበታል፡፡ ሕዝቡ ሁሉ ለዓመቱ ሐጢያት ይቅርታን ያገኝ ዘንድም የተከማቹት የዓመቱ ሐጢያቶች በሙሉ በእጆች መጫን ወደ ሐጢያት ቁርባኑ ይሻገሩ ነበር፡፡ 
በአዲስ ኪዳን ኢየሱስ ትክክለኛ በሆነ ተመሳሳይ መንገድ ወደዚህ ዓለም መጣና የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ለመውሰድ በዮርዳኖስ ተጠመቀ፡፡ በዚህም በብሉይ ኪዳን የተተነበየው የእግዚአብሄር ቃል ተፈጸመ፡፡ 
ኢየሱስን ያጠመቀው አጥማቂው ዮሐንስ ከኢየሱስ 6 ወር አስቀድሞ የመጣ የእግዚአብሄር አገልጋይ ነበር፡፡ በዮሐንስ 1፡29 ላይ ‹‹እነሆ የዓለምን ሐጢያት የሚያስወግድ የእግዚአብሄር በግ›› በማለት ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ እንደወሰደ መሰከረ፡፡ 
አጥማቂው ዮሐንስ ኢየሱስን በዮርዳኖስ ወንዝ በማጥመቅ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወደ እርሱ አስተላልፎዋል፡፡ በዚህ መንገድ ጌታ ለሰው ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ስርየትን አደረገ፡፡ አሁን እኛ ማድረግ ያለብን በዚህ ማመን ነው፡፡ 
የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ ተላልፈዋል፡፡ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት በሐዋርያት ሥራ 3፡19 ላይ እንዲህ አሉ፡- ‹‹እንግዲህ ከጌታ ፊት የመጽናናት ዘመን እንድትመጣላችሁ አስቀድሞም ለእናንተ የመረጠውን ኢየሱስ ክርስቶስን እንዲልክላችሁ ሐጢአታችሁ ይደመሰስ ዘንድ ንስሐ ግቡ ተመለሱም፡፡›› 
እነርሱ ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ ለምን እንደተጠመቀ ሰዎች እንዲከተሉት ለምን እንደነገራቸው እንድናስተውል እየወተወቱን ነው፡፡ እርሱ እንዲህ አለ፡- ንስሐ ግቡና ተመለሱ፡፡ በኢየሱስ ጥምቀት ቤዛነት እመኑ፡፡ ከሐጢያቶቻችሁም ታጠቡ፡፡›› 
መሲሁ መጣና በመጠመቅ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በአንድ ጊዜ ወሰደ፡፡ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ የተላለፉት በዚህ መንገድ ነበር፡፡ በዚህም በማቴዎስ 3፡13-17 ላይ እንደተጻፈው የእግዚአብሄር ኪዳን በኢየሱስ ጥምቀት ተፈጸመ፡፡ 
‹‹ያን ጊዜ ኢየሱስ በዮሐንስ ሊጠመቅ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ መጣ፡፡ ዮሐንስ ግን፡- እኔ በአንተ ልጠመቅ ያስፈልገኛል፤ አንተም ወደ እኔ ትመጣለህን? ብሎ ይከለክለው ነበር፡፡ ኢየሱስም መልሶ፡- አሁንስ ፍቀድልኝ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና አለው፡፡ ያን ጊዜ ፈቀደለት፡፡ ኢየሱስም ከተጠመቀ በኋላ ወዲያው ከውሃ ወጣ፡፡ እነሆም ሰማያት ተከፈቱ፡፡ የእግዚአብሄርም መንፈስ እንደ ርግብ ሲወርድ በእርሱ ላይም ሲመጣ አየ፡፡ እነሆም ድምጽ ከሰማያት መጥቶ በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው አለ፡፡›› 
የእግዚአብሄርን የደህንነት ቃል ለመፈጸም ኢየሱስ ወደ ዮሐንስ በመሄድ ተጠመቀ፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ የእግዚአብሄር ልዩ አገልጋይ ነበር፡፡ ሉቃስ ምዕራፍ 1 ዮሐንስ የመጀመሪያው ሊቀ ካህን የአሮን ዘር መሆኑን ይናገራል፡፡ እግዚአብሄርም ከአሮን ዘር የሆነውን ዮሐንስን የመረጠው ምክንያቱም የሰው ዘር ሁሉ ወኪል ጽድቅን ሁሉ እንዲፈጽም በመፈለጉ ነበር፡፡
ስለዚህ እግዚአብሄር ዮሐንስ ኢየሱስ ከመወለዱ ከ6 ወራቶች በፊት በሊቀ ካህን ቤት እንዲወለድ አደረገ፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ ኢየሱስ ከመምጣቱ አስቀድሞ በምድረ በዳ ‹‹እናንተ የእፉኝት ልጆች ንስሐ ግቡና ተመለሱ፡፡ መሲሁ ይመጣል፡፡ ወደ እርሱ ተመለሱ፤ አለበለዚያ ይቆርጣችሁና ወደ እሳት ይወረውራችኋል፡፡ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ደሙ እመኑ፡፡ ንስሐ ግቡና ተጠመቁ፡፡ ያን ጊዜ ቤዛነትን ታገኛላችሁ›› ብሎ እየጮኸ ለኢየሱስ መንገድን ሲጠርግ ነበር፡፡    
የቤዛነት ወንጌል በሐዋርያት ሥራ 3፡19 ላይ በግልጽ ተብራርቶዋል፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ ስለ ሰው ዘር ሐጢያት በተናገረና በጮኸ ጊዜ ብዙዎች ተለወጡ፡፡  
አጥማቂው ዮሐንስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ በማሻገሩ የሰው ዘር ሐጢያቶች በሙሉ በአንድ ጊዜ ተደምስሰዋል፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንደወሰደ ስለመሰከረ የውሃና የመንፈስ ወንጌል በሆነው የቤዛነት ወንጌል በማመን መዳን እንደምንችል እናውቃለን፡፡  
 
 

አጥማቂው ዮሐንስ ከኢየሱስ በፊት የመጣበት ምክንያት፡፡ 

 
‹‹እንዲህ›› የሚለው ቃል ያሉት ትርጉሞች ምንድናቸው? 
1. በጣም ተገቢ=
2. በጣም ተስማሚ
3. የግድ በዚህ መንገድ ብቻ (ሌላ መንገድ የለም፡፡)  

በአዳኙ ኢየሱስ በማመን ሐጢያቶቻቸው የተወሰዱላቸው ደህንነታቸውን ማቴዎስ ለኢየሱስ ጥምቀተ ወንጌል በሰጠው ምስክርነት አማካይነት ማረጋገጥ ይችላሉ፡፡ በማቴዎስ 3፡15-16 ላይ ኢየሱስ ወደ ዮሐንስ መጣና ‹‹አጥምቀኝ›› አለው፡፡ ዮሐንስም ‹‹እኔ በአንተ ልጠመቅ ያስፈልገኛል፤ አንተም ወደ እኔ ትመጣለህን?›› ብሎ መለሰ፡፡  
አጥማቂው ዮሐንስ የእርሱን ማንነት በማወቁ ኢየሱስን አጠመቀው፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ እንዲያስተላልፍ የተላከ የእግዚአብሄር አገልጋይ ነበር፡፡ ኢየሱስ የብሉይ ኪዳንን ትንቢት ለመፈጸም አዳኝ ሆኖ ስለመጣ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በራሱ ላይ ይሸከም ዘንድ አጥማቂው ዮሐንስ እንዲያጠምቀው አዘዘው፡፡    
ለምን? ምክንያቱም ኢየሱስ የእግዚአብሄር ልጅ፣ ፈጣሪና አዳኝ ነው፡፡ ወደ እኛ የመጣውም ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ሊያነጻን ነው፡፡ ስለዚህ ሰዎችን በሙሉ ለማዳን መጠመቅ ነበረበት፡፡
‹‹እንዲህ›› ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ አነጻ፡፡ በመስቀል ላይም በእኛ ምትክ ተፈረደበት፡፡ የኢየሱስ ጥምቀት ለደህንነታችን ምስክር ነበር፡፡ እግዚአብሄር በብሉይ ኪዳን ሐጢያቶች በሙሉ መስዋዕት ሆኖ ወደቀረበው በግ እንደሚሻገሩ ቃል እንደገባ ሁሉ የእግዚአብሄር ልጅም በግ ሆነና ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በራሱ ወሰደ፡፡  
ስለዚህ በብሉይ ኪዳን የእጆችን መጫንና በአዲስ ኪዳን የኢየሱስ ጥምቀት ሐጢያቶች የሚሻገሩበትና በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ለሚያምኑ ደህንነትና የዘላለም ሕይወት የተሰጠባቸው ናቸው፡፡  
 
 

የኢየሱስ ጥምቀት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ አነጻ፡፡ 

 
ክርስቶስን መልበስ የምንችለው እንዴት ነው? 
በክርስቶስ በመጠመቅ ነው፡፡  

ኢየሱስ መጠመቅ በፈለገ ጊዜ አጥማቂው ዮሐንስ ‹‹እኔ በአንተ ልጠመቅ ያስፈልገኛል፤ አንተም ወደ እኔ ትመጣለህን?›› ብሎ ሊከለክለው ሞክሮ ነበር፡፡ 
ኢየሱስ ግን እንዲህ ሲል መለሰ፡- ‹‹አሁንስ ፍቀድልኝ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና፡፡›› አሁንስ ፍቀድልኝ፤ ፍቀድልኝ፡፡ ዮሐንስን ‹‹በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል የሚያምኑትን እንዳድናቸውና ወደ እኔ እንደመልሳቸው አንተ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወደ እኔ ማስተላለፍ አለብህ፡፡ በእኔ ጥምቀትና ደም ለሚያምኑት በሙሉ ለሐጢያቶቻቸው ፍርድን እቀበላለሁ፡፡ ስለዚህ አሁን ፍቀድልኝ፡፡›› 
ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ ተጠመቀ፡፡ የኢየሱስ ጥምቀት ጻድቅ ከሆነው የእግዚአብሄር የቤዛነት ሕግ ጋር የተስማማ ነበር፡፡ ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ እርሱ በመተላለፋቸው የተነሳ እኛም በኢየሱስ ስናምንና ስንጠመቅ ለአንዴና ለመጨረሻ ቤዛነትን ልናገኝ እንችላለን፡፡ እርሱ እጆችን በመጫን ሥርዓትም ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ስለወሰደ፣ በእኛ ፋንታም በመስቀል ላይ ስለሞተና አሁንም በእግዚአብሄር ቀኝ ስለተቀመጠ በውሃውና በመንፈሱ ቤዛነት በማመን ልንድን እንችላለን፡፡
ከዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ያዳነን ኢየሱስ ነው፡፡ ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ እንደወሰደና የሐጢያቶችንንም ደመወዝ መስቀል ላይ እንደከፈለ በማመን ልንድን እንችላለን፡፡ የኢየሱስ ጥምቀት የቤዛነት ወንጌል መጀመሪያ ነበር፡፡  
ቤዛነትን የሚያስገኘው ጥምቀት በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በተደጋጋሚ ተጠቅሶዋል፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ በገላትያ ላይ  በክርስቶስ ስለተጠመቀና ክርስቶስን ስለለበሰ ከክርስቶስ ጋር መሰቀሉን ይናገራል፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ሞቱ አማካይነት በተሰጠው ቤዛነት ላይ ያለውን እምነቱን ይናገራል፡፡    
 
 
‹‹አሁንስ ፍቀድልኝ፡፡›› 
 
የአጥማቂው ዮሐንስ ሚና ምን ነበር?
የእርሱ ሚና የነበረው የሰው ዘር ሁሉ ሊቀ ካህን በመሆን የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ ማስተላለፍ ነበር፡፡ 

ኢየሱስ እንዲህ አለ፡- ‹‹እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና፡፡›› ጽድቅን ሁሉ ማለት ሐጢያቶችን በሙሉ በጥምቀቱ መደምሰስና ሰዎችን ሁሉ በልቦቻቸው ሐጢያት አልባ ማድረግ ነው፡፡ ‹‹ያን ጊዜ ፈቀደለት፡፡›› ኢየሱስ በዮርዳኖስ ተጠመቀ፡፡ 
ሊቀ ካህኑ እጆቹን በሕያው ፍየል ራስ እንደጫነ ሁሉ አጥማቂው ዮሐንስም እጆቹን በኢየሱስ ራስ ላይ በመጫን የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወደ እርሱ አስተላለፈ፡፡ አጥማቂው ዮሐንስ ተግባሩ የሰዎች ወኪል በመሆን የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ የሚያስተላልፍ ሊቀ ካህን ነበር፡፡ ‹‹እግዚአብሄር እኔ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወደ በግህ ኢየሱስ አስተላልፋለሁ፡፡›› በዚህም የሰው ዘር ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ ተላለፉ፡፡   
አጥማቂው ዮሐንስ እጆቹን በኢየሱስ ራስ ላይ ጫነ፤ ወደ ውሃው ውስጥ አጠለመው፤ ኢየሱስ ከውሃው ሲወጣ ዮሐንስ እጆቹን አነሳ፡፡ የኢየሱስ ጥምቀት ለጽድቅ ደህንነት የተበጀ ነበር፡፡ በዚህም ኢየሱስ በጥምቀቱ የሚያምነውን የሰው ዘር በሙሉ አዳነ፡፡ 
 
 
ሰማያት ተከፈቱና ድምጽ ከሰማይ መጣ፡፡  
 
መንግሥተ ሰማይ የተከፈተው ከመቼ ጀምሮ ነበር?
ከአጥማቂው ዮሐንስ ዘመን ጀምሮ ነበር፡፡ (ማቴዎስ 11፡12)  

‹‹ኢየሱስም ከተጠመቀ በኋላ ወዲያው ከውሃ ወጣ፡፡ እነሆም ሰማያት ተከፈቱ፡፡ የእግዚአብሄርም መንፈስ እንደ ርግብ ሲወርድ በእርሱ ላይም ሲመጣ አየ፡፡ እነሆም ድምጽ ከሰማያት መጥቶ በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው አለ፡፡›› (ማቴዎስ 3፡16-17) 
ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በጥምቀቱ በወሰደ ጊዜ ሰማያት ተከፈቱ፡፡ በዚህም እግዚአብሄር ከብዙ ሺህ ዓመታት በፊት የገባው ቃል ኪዳን በዮርዳኖስ በኢየሱስ ጥምቀት ተፈጸመ፡፡  
በዚህም የእግዚአብሄር በግ የሆነው ኢየሱስ የዓለምን ሕዝብ በሙሉ ከሐጢያቶቻቸው አዳነ፡፡ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ ተላለፉ፡፡ እርሱም የእግዚአብሄርን ፈቃድ ፈጸመ፡፡    
ይህም በዮሐንስ 1፡29 ላይ ተመስክሮዋል፡- ‹‹እነሆ የዓለምን ሐጢያት የሚያስወግድ የእግዚአብሄር በግ፡፡›› የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ የእግዚአብሄር በግ ወደሆነው ኢየሱስ በመሻገራቸው ከሦስት ዓመታት በኋላ ሸክሙን በጫንቃው ተሸክሞ በጎልጎታ ወዳለው መስቀል ሄደ፡፡ ሐጢያቶችን በሙሉ በጥምቀቱ ከወሰደ በኋላ በሄደበት ቦታ ሁሉ እርሱን በእምነት ለተቀበሉት ሐጢያቶቻቸው በሙሉ ይቅር መባላቸውን ነገራቸው፡፡    
በዮሐንስ 8፡11 ላይ በምንዝር ተግባር ላይ የተገኘችን ሴት ‹‹እኔም አልፈርድብሽም›› አላት፡፡ ያልኮነናት ሊፈረድበት የሚገባው ሐጢያትን በሙሉ የወሰደው ራሱ ኢየሱስ በመሆኑ ነበር፡፡ በዚህም ለሰዎች ሁሉ የሐጢያተኞች ሁሉ አዳኝ መሆኑን ነገራቸው፡፡ 
የእግዚአብሄር ልጅ የሆነው እርሱ ሐጢያቶቻችንን   በሙሉ ስለወሰደ በዓለም ላይ ያለ እያንዳንዱ ምዕመን መቀደስ ይችላል፡፡ እርሱ በተጠመቀ ጊዜ ሰማያት ተከፈቱ፡፡ የመንግስተ ሰማይ በሮችም ተከፍተዋል፤ በኢየሱስ ጥምቀት ያመነ ሁሉ በነጻ ሊገባ ይችላል፡፡  
 
 

ኢየሱስ የተሰቀለው የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በጥምቀቱ ከወሰደ በኋላ ነበር፡፡ 

 
ኢየሱስ የሰይጣንን ራስ የቀጠቀጠው እንዴት ነበር?
ለሐጢያቶቻችን በሙሉ ፍርድን ከተቀበለ በኋላ ከሞት በመነሳት ነው፡፡ 

የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ራሱ ስለተሻገሩ ኢየሱስ በመስቀል ላይ ሊፈረድበት ይገባ ነበር፡፡ በመስቀል ላይ የሚቀበለውን ስቃይ ባሰበ ጊዜ በጣሙን አዝኖና ታውኮ ነበር፡፡ ላቡ እንደ ደም ነጠብጣቦች እስኪወርድ ድረስ ጸለየ፡፡ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ጌቴሴማኔ ወደተባለ ስፍራ በሄደ ጊዜ እንዲህ ሲል ጮኸ፡- ‹‹አባት ሆይ ቢቻልስ ይህች ጽዋ ከእኔ ትለፍ፡፡›› (ማቴዎስ 26፡39) ‹‹እኔ በጥምቀት የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወስጃለሁ፡፡ ለዚህ ግን አልሙት፡፡›› እግዚአብሄር ግን ምላሽ አልሰጠም፡፡ 
በብሉይ ኪዳን በነበረው የስርየት ቀን ደሙ በሊቀ ካህኑ አማካይነት በስርየት መክደኛው ላይ ይረጭ ዘንድ የሐጢያቱ ቁርባን መታረድ ነበረበት፡፡ ኢየሱስም በተመሳሳይ መንገድ መሰቀል ነበረበት፡፡ እግዚአብሄርም ይህንን በሌላ መንገድ ሊያደርገው እንደማይችል ወስኖ ነበር፡፡  
መሰዊያው የእግዚአብሄርን ፍርድ ሲያመላክት የቁርባኑ ደም ደግሞ ሕይወትን ያመላክታል፡፡ በስርየት መክደኛው ላይና ፊት ለፊት ደሙን ሰባት ጊዜ መረጨት ማለት ፍርዱ ሁሉ ተሻግሮዋል ማለት ነው፡፡ (ዘሌዋውያን 16፡1-22)  
ኢየሱስ ጽዋው እንዲያልፈው ወደ እግዚአብሄር ጸለየ፡፡  አባቱ ግን አልፈቀደለትም፡፡ በመጨረሻም ኢየሱስ እንዲህ አለ፡- ‹‹አንተ እንደምትወድ ይሁን እንጂ እኔ እንደምወድ አይሁን፡፡›› (ማቴዎስ 26፡39) ወደ እግዚአብሄር ሲጸልይ እርሱ እንደወደደው እንዲሆን ተናገረ፡፡ ጸሎቱንም ጨረሰና የአባቱን ፈቃድ ተከተለ፡፡  
ኢየሱስ የራሱን ፈቃድ ጣለና አባቱን ታዘዘ፡፡ ለምን? ምክንያቱም እርሱ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ከወሰደ በኋላ ፍርድን ባይቀበል ኖሮ ደህንነት አይጠናቀቅም ነበር፡፡ የተሰቀለው የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ በጥምቀቱ በመውሰዱ ምክንያት ነው፡፡ ‹‹የሐጢአት ደመወዝ ሞት ነው፡፡ የእግዚአብሄር የጸጋ ስጦታ ግን በኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን የዘላለም ሕይወት ነው፡፡›› (ሮሜ 6፡23)   
እግዚአብሄር አዳኙን እንደሚልክና የኢየሱስን ጥምቀት በሚያሳየው እጆች መጫን አማካይነት ሰዎችን እንደሚያድን የሚናገረውን ኪዳን ፈጸመ፡፡ ኢየሱስ የእግዚአብሄርን ፈቃድ ታዘዘና ስለ እኛ ፍርድን ተቀበለ፡፡ 
ይህም በዘፍጥረት 3፡15 ላይ የተተነበየው ትንቢት ፍጻሜ ነበር፡፡ ‹‹በአንተና በሴቲቱ መካከል በዘርህና በዘርዋም መካከል ጠላትነትን አደርጋለሁ፡፡ እርሱ ራስህን ይቀጠቅጣል፤ አንተም ሰኮናውን ትቀጠቅጣለህ፡፡›› እግዚአብሄር የሔዋን ዘር የሆነውን መሲህ እንደሚልክና እርሱም የሰውን ዘር ሐጢያተኛ እንዲሆንና ወደ ሲዖል እንዲወርድ ያደረገውን ሰይጣንን እንደሚረታው ለአዳም ተስፋ ሰጠው፡፡   
የኢየሱስን ጥምቀትና የመስቀሉን ደም ስናውቅና ስናምን ሐጢያቶቻችን በሙሉ ይነጹና ከፍርድ እንድናለን፡፡ 
የኢየሱስን ጥምቀትና የመስቀል ላይ ደሙን በምናስብበት ጊዜ በልቦቻችን ውስጥ እውነተኛ አመኔታ ሊኖረን ይገባል፡፡ ይህንን በልቦቻችሁ እመኑት፡፡ ያን ጊዜ ትድናላችሁ፡፡ 
 
 

የኢየሱስ ጥምቀት የሰማያዊው ወንጌል መጀመሪያ ነው፡፡ 

 
ጌታ ወደ ሰማይ ከመሄዱ በፊት የመጨረሻው ትዕዛዙ ምን ነበር?
ደቀ መዛሙርቱን አሕዛብን ሁሉ በአብ፣ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም በማጥመቅ  ደቀ መዛሙርቱ እንዲያደርጓቸው አዘዛቸው፡፡

የኢየሱስ ጥምቀት የወንጌል መጀመሪያ ነበር፡፡ እርሱ በጥምቀቱና በደሙ ሐጢያተኞችን በሙሉ አዳነ፡ በማቴዎስ 28፡19 ላይ እንዲህ ተጽፎዋል፡- ‹‹እንግዲህ ሂዱና አሕአዛብን ሁሉ በአብ፣ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው፡፡›› ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ አብ፣ ወልድና መንፈስ ቅዱስ የሰውን ዘር ከሐጢያቶች ሁሉ እንዳዳኑና በጥምቀቱና በደሙ አማካይነት ሁሉንም እንዳነጹ ይመሰክሩ ዘንድ ነገራቸው፡፡    
ኢየሱስ ከአሕዛብ ሁሉ ደቀ መዛሙርት እንዲያደርጉ፣ ስለ ኢየሱስ ጥምቀት፣ ስለ ቤዛነት ጥምቀት፣ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ስላስወገደው ጥምቀት እንዲያስተምሩዋቸው ስልጣንን ሰጣቸው፡፡ 
ከ2,000 ዓመታት በፊት ኢየሱስ ሥጋን ለብሶ ወደ ምድር መጣና በአጥማቂው ዮሐንስ ተጠመቀ፡፡ በኢየሱስ ጥምቀትም የእኛን ሐጢያቶች በሙሉ ጨምሮ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ እርሱ ተሻገሩ፡፡ 
ወደ እርሱ የተላለፈው ሐጢያት ምን ያህል ነው? የነገዎቹ ሐጢያቶችስ? እርሱ የነገዎቹ ሐጢያቶችም እንኳን ወደ እርሱ መተላለፋቸውን ይነግረናል፡፡ የልጆቻችን ሐጢያቶች፣ የትውልዶቻችን ሐጢያቶች፣ ያለፉት፣ የአሁንና የወደፊት  የአዳምም ሐጢያት እንኳን ሳይቀር ወደ ኢየሱስ ተላልፈዋል፡፡
እንዴት ሐጢያት ላይኖር ይችላል? እንዴት ያለ ሐጢያት መሆን እንችላለን? ምዕመናን በሙሉ ራሳቸውን ከሐጢያት ነጻ አድርገው ወደ እግዚአብሄር መንግሥት ይገቡ ዘንድ ኢየሱስ በጥምቀቱ የእኛን ሐጢያቶችና የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ ወሰደ፡፡ 
‹‹እውነትን የሚያደርግ ግን ሥራው በእግዚአብሄር ተደርጎ እንደሆነ ይገለጥ ዘንድ ወደ ብርሃን ይመጣል፡፡›› (ዮሐንስ 3፡21) 
ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ፣ በመስቀል ላይ ደሙ፣ በሞቱና በትንሳኤው ሐጢያቶቻችንን በሙሉ አነጻ፡፡ ስለዚህ በእርሱ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ሞቱ ማመን ከሐጢያት ሁሉ መዳን ማለት ነው፡፡ ይህ የቤዛነት እምነት ነው፡፡  
በኢየሱስ ጥምቀትና በክርስቶስ ደም ስናምን ድነናል፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ በትክክል የምናምን ከሆነ ጻድቃን ነን ወይስ ሐጢያተኞች? ጻድቃን ነን፡፡ ጎዶሎ ፍጥረታት ብንሆን እንኳን ሐጢያት አልባ ነን? አዎ ሐጢያት አልባ ነን፡፡ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ፍርዱ ማመን ምሉዕና ተገቢ እምነት መያዝ ነው፡፡   
 
 
በኢየሱስ ስም ማጥመቅና መጠመቅ፡፡ 
 
የሰማያዊው ወንጌል መጀመሪያ ምንድነው?
የኢየሱስ ጥምቀት ነው፡፡  

ሰዎች ጎዶሎ ፍጥረታት ስለሆኑ አገልጋዮች በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ የሚያምኑትን እምነታቸውን ያጸኑ ዘንድ ያጠምቁዋቸዋል፡፡ ዳግም የተወለዱት የእምነት ማረጋገጫ አድርገው ኢየሱስ በተጠመቀበት ተመሳሳይ መንገድ በመጠመቃቸው መዳናቸውን ያረጋግጣሉ፡፡ 
በመጀመሪያ አገልጋዩ ዳግም በሚወለደው ግለሰብ ራስ ላይ እጆቹን በመጫን ግለሰቡ እስከ ዕድሜው ፍጻሜ ድረስ እግዚአብሄርን ያመልክ ዘንድ የአምላክን በረከት ይለምንለታል፡፡ ከዚያም በአብ፣ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም ያጠምቀዋል፡፡  
እኛ በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ላይ ባለን እምነታችን መሰረት  ተጠምቀናል፡፡ ይህ ጥምቀት ዓላማው ሐጢያት በሙሉ ወደ ኢየሱስ መሻገሩን፣ የተጠመቀው ግለሰብም ከኢየሱስ ጋር መሞቱንና ከእርሱም ጋር መነሳቱን ማሳየት ነው፡፡  
መጠመቅ የአንድ ሰው ሐጢያቶች በሙሉ በጥምቀት ወደ ኢየሱስ መተላለፋቸውን ከኢየሱስ ጋር አብሮ ለሐጢያቶች የተፈረደበት መሆኑንና ከእርሱ ጋር አብሮ መነሳቱን ማወጅ ነው፡፡ የአንድን ሰው እምነትም በአብ፣ በወልድ፣ በመንፈስ ቅዱስ፣ በሰይጣንና በወንድሞችና በእህቶች ፊት ማወጅ ነው፡፡ ሰው ከውሃና ከመንፈስ መወለዱን መናዘዝ ነው፡፡ 
የኢየሱስን ጥምቀትና የመስቀል ላይ ደሙን ትክክለኛ ትርጉም የሚያውቁና የሚያምኑ በሙሉ ከዓለም ሐጢያቶች  በሙሉ ድነዋል፡፡ ስለዚህ በአብ፣ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም ይጠመቃሉ፡፡ 
‹‹አሮጌው ነገር አልፎዋል፡፡ እነሆ ሁሉ አዲስ ሆንዋል፡፡›› (2ኛ ቆሮንቶስ 5፡17) አሮጌ ነገሮቻችን በሙሉ አልፈዋል፡፡ እኛም የእምነት ሰዎች ሆነን ዳግም ተወልደናል፡፡ ይህንንም በልቦቻችን ለማረጋገጥ እንጠመቃለን፡፡ በኢየሱስ ጥምቀት በማመን በኢየሱስ ተጠምቀናል፡፡   
 
 
በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደም ዳግም ከተወለዱ በኋላ የሚኖረው ሕይወት፡፡ 
 
ዳግም የተወለዱት የሚኖሩት ለምንድነው? 
እነርሱ ወንጌልን በዓለም ሁሉ በመስበክ ለእግዚአብሄር መንግሥትና ለጽድቁ ይኖራሉ፡፡  

ቤዛነትና ዳግም ውልደት ከተገኘ በኋላ ያለው ሕይወት በእግዚአብሄር ቃል ማመንን ማካተት አለበት፡፡ ይህ ሕይወት  አንድ ሰው በየቀኑ ለሚሰራው ሐጢያት በየዕለቱ እየጸለየ እንደሚኖረው አይነት ስሜታዊ ሕይወት መሆን የለበትም፡፡ ይልቁንም በየቀኑ ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በጥምቀቱ የወሰደልን ለመሆኑ እርግጠኛ የሆንበት የታመነ ሕይወት መሆን ይኖርበታል፡፡    
ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ ሐጢያቶቻችን በሙሉ ወደ ኢየሱስ ተሻግረዋል፡፡ ከዚያም ለሐጢያቶቻችን በሙሉ ፍርድን እስኪቀበልና እስኪሰቀል ድረስ ለሦስት ዓመታት ከዚህ  ሸክም ጋር ኖረ፡፡  
ስለዚህ እኛ አማኞች እምነት ሊኖረን የሚገባው በውስጥ ተራ በሆኑ ስሜቶቻችን ሳይሆን በተጻፈው የእግዚአብሄር ቃል መሆን አለበት፡፡ ይህንን ማድረግ ከተሳነን ቤዛነትን ካገኘንና ዳግም ከተወለድን በኋላም በየዕለቱ ለምንሰራቸው ሐጢያቶች ብቻ እንጨነቃለን፡፡  
ከግል ስሜት ጋር የተያያዘውን የሐጢያት ምልከታ አስወግደን በውሃውና በደሙ ወንጌል ብቻ ማመን ይኖርብናል፡፡ ቤዛነትን ያገኘ ግለሰብ ሊመራው የሚገባው ሕይወት ይህ ነው፡፡  
አጥማቂው ዮሐንስ ስለ ኢየሱስ የተናገረው ነገር ምንድነው? ‹‹እነሆ የዓለምን ሐጢያት የሚያስወግድ የእግዚአብሄር በግ፡፡›› (ዮሐንስ 1፡29) እርሱ የዛሬውን፣ የነገውን፣ የትናንቱን እንደዚሁም የአዳምን ሐጢያት መውሰዱን መሰከረ፡፡ 
እነዚያን ሐጢያቶች በሙሉ አልወሰደምን? እነዚያ ሐጢያቶች በሙሉ ወደ ኢየሱስ አልተላለፉምን? የዓለም ሐጢያቶች ያለፉትን፣ የአሁኖቹንና የወደፊቶቹን ሐጢያቶቻችንን በሙሉ ይጨምራሉ፡፡ በኢየሱስ ጥምቀት አማካይነት የቤዛነትን ወንጌል ማረጋገጥ ይኖርብናል፡፡  
በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ እውነት የሚያምኑ ይድናሉ፡፡ በኢየሱስ ጥምቀት ያመነ ሁሉ በልቡ ውስጥ ሐጢያት የለበትም፡፡ 
ሆኖም ብዙ ሰዎች ሐጢያቶቻቸው በሙሉ በጥምቀቱ አማካይነት አስቀድሞ ወደ ኢየሱስ መሻገራቸውን ባለማወቃቸው ገናም ሐጢያት እንዳለባቸው ያስባሉ፡፡ እነርሱ በሰይጣን ተታለዋል፡፡ ሰይጣን በሥጋዊ አስተሳሰቦቻቸው ‹‹በየቀኑ ሐጢያት ትሰራለህ፡፡ እንዴት ሐጢያት አልባ ልትሆን ትችላለህ?›› ሲል ያንሾካሹክላቸዋል፡፡   
እነርሱ ሐጢያት አልባ ለመሆን ማድረግ የሚጠበቅባቸው በእግዚአብሄር ማመን ነው፡፡ ነገር ግን አሁንም ሐጢያት ስለሚሰሩ ሐጢያተኞች መሆናቸውን እንዲያስቡ አታለላቸው፡፡ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ የሚያምን ሰው ሐጢያት የለበትም፡፡ 
እኛ በዚህ ዓለም ላይ ብቁ ያልሆንንና ደካሞች ሆነን ስለምንኖር በሥራዎቻችንና በምግባሮቻችን ብቻ ጻድቃን እንሆናለን ማለት በጭራሽ አንችልም፡፡ ነገር ግን በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደሙ እውነት መዳናችንን በእምነት መናገር እንችላለን፡፡ በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ በማመን ልቦቻችን እንደተቀደሱ ከተረዳን በኋላ ሐጢያት እንደሌለብን በእርግጠኝነት እናውቃለን፡፡    
‹‹♫ተዋጅቻለሁ፡፡ አንተም ተዋጅተሃል፡፡ ሁላችንም ተዋጅተናል፡፡♫›› ወንጌልን ለሁሉም ከመስበክና በመንፈስ እየተመራን መሆኑን ከማወቅ ጋር መኖር የደስታና የሐሴት ስሜት ነው፡፡  
በእርግጥ እኛ አማኞች በየቀኑ ሐጢያትን እንሰራለን፤ ነገር ግን ሐጢያት የለብንም፡፡ በልቦቻችን ውስጥ የኢየሱስ ጥምቀትና ደሙ አለን፡፡ ልቦቻችን በሐጢያት መሞላት ልማዳቸው ነው፡፡ ነገር ግን አሁን በኢየሱስ ጥምቀት ስላመንን እንዴት ሐጢያተኞች ሆነን ልንቀር እንችላለን፡፡ 
‹‹ከዚያ ወራት በኋላ ከእነርሱ ጋር የምገባው ኪዳን ይህ ነው ይላል ጌታ፡፡ በልባቸው ሕጌን አኖራለሁ፡፡ በልቡናቸውም እጽፈዋለሁ፡፡›› (ዕብራውያን 10፡16) 
ልቦቻችን ከሐጢያት ነጻ ናቸው፡፡ ኢየሱስ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ደሙ አማካይነት ሙሉ በሙሉ ከሐጢያት  እንድንድን አስችሎናል፡፡ ከሐጢያት መዳን የሚመነጨው በእግዚአብሄር ቃል ከማመን ነው፡፡  
 
 
በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀሉ ደም የሚያምን ሁሉ በጭራሽ ሐጢያተኛ ሊሆን አይችልም፡፡   
 
ሐጢአትን ስንሰራ እንደገና ሐጢያተኞች እንሆናለን?
አንሆንም፡፡ ዳግመኛ በጭራሽ ሐጢያተኞች አንሆንም፡፡  

በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ስላመንን ይቅርታን ለማግኘት ደጋግመን ብንጸልይም ሐጢያት በልቦቻችን ውስጥ ይኖራል፡፡ ነገር ግን በእውነተኛው ወንጌል ስናምን ሐጢያቶቻችን በሙሉ ይነጻሉ፡፡ 
‹‹ሃይ በእነዚህ ቀናት ብሩህና ደስተኛ የሆንከው እንዴት ነው?›› 
‹‹አየህ ከእንግዲህ ወዲያ በልቤ ውስጥ ሐጢያት የለብኝም፡፡ ለዚያ ነው፡፡››  
‹‹እውነትህን ነው? እንደዚያ ከሆነ አሁን እንደፈለግህ ሐጢያት መስራት ትችላለህ ማለት ነዋ?›› 
‹‹የሰው ዘር ሐጢያትን ከመስራት ውጭ ምንም ሊያደርግ እንደማይችል ታውቃለህ፡፡ ሰው ማለት እንደዚያ ነው፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በጥምቀቱ ወሰደና በመስቀል ላይ የእነርሱን ፍርድ ተቀበለ፡፡ በዚህ ምክንያት አሁን በቤተክርስቲያን ውስጥ ወንጌልን ለማገልገል ራሴን ሰጠሁ፡፡ ሁላችንም በዚህ መልኩ መኖር እንደሚገባን ሮሜ ምዕራፍ 6 ይናገራል፡፡ በልቤ ውስጥ ሐጢያት ስለሌለብኝ የጽድቅ ነገር ማድረግ እፈልጋለሁ፡፡ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደሙ ማመንና ወንጌልን በመላው ዓለም መስበክ አለብን! የቤዛነታችን አለቃ በሆነው በኢየሱስ ስናምን ዳግመኛ በጭራሽ ሐጢያተኞች አንሆንም፡፡ በኢየሱስ ጥምቀት በመስቀል ላይ ደሙ በተገኘው ዘላለማዊ ደህንነትና ማመን ይኖርብናል፡፡ በምስጋና ተሞልቻለሁ!››    
 
 

መንፈስ ቅዱስን የሚቀበለው ማነው?  

 
አጥማቂው ዮሐንስ ስለ ኢየሱስ የመሰከረው ምንድነው?
እርሱ የዓለምን ሐጢያቶች ማለትም ያለፉትን፣ አሁን ያሉትንና ወደፊት የሚሰሩትን ሐጢያቶችና የአዳምንም ሐጢያት ሳይቀር የወሰደው የእግዚአብሄር በግ ኢየሱስ እንደሆነ መሰከረ፡፡   

በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደሙ የሚያምን በሙሉ ደህንነትን ያገኛል፡፡ መንፈስን ማግኘት የምንችለው እንዴት ነው? የሐዋርያት ሥራ 2፡38-39 መልሱን ይነግረናል፡- ‹‹ጴጥሮስም፡- ንስሐ ግቡ፤ ሐጢአታችሁም ይሰረይ ዘንድ እያንዳንዳችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተጠመቁ፡፡ የመንፈስ ቅዱስንም ስጦታ ትቀበላላችሁ፡፡ የተስፋ ቃል ለእናንተና ለልጆቻችሁ ጌታ አምላካችንም ለሚጠራቸው በሩቅ ላሉ ሁሉ ነውና አላቸው፡፡››    
በኢየሱስ ክርስቶስ ስም መጠመቅ ማለት በኢየሱስ ጥምቀት ማመንና ቤዛነትን ማግኘት ማለት ነው፡፡ ያን ጊዜ መንፈስ የእግዚአብሄር ስጦታ ሆኖ ይሰጣል፡፡  
በኢየሱስ ክርስቶስ ስም መጠመቅ ማለት በክርስቶስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደሙ በማመን መቀደስ ማለትም ጭምር ነው፡፡ ይህን እምነት ስንቀበል ቤዛነትን እናገኝና ጻድቃን እንሆናለን፡፡ አማኞች በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀሉ ላይ ደሙ አማካይነት እንደ በረዶ የነጡ ይሆናሉ፡፡
‹‹የመንፈስ ቅዱስንም ስጦታ ትቀበላላችሁ፡፡›› ሐጢያቶቻችን በሙሉ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ እንደተላለፉና ለእነዚህም ሐጢያቶች ሲል በመስቀል ላይ ሞት እንደተፈረደበት ስናምን  ልቦቻችን ይነጻሉ፡፡ በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ስናምን መንፈስ ቅዱስን ስንቀበልና የእግዚአብሄር ልጆች ስንሆን አዲስ ሕይወትን እንጀምራለን፡፡ 
‹‹እውነትንም ታውቃላችሁ፤ እውነትም አርነት ያወጣችኋል፡፡›› (ዮሐንስ 8፡32) የጌታን የመስቀል ላይ ፍርድ ትክክለኛ ትርጉም ልናውቅ ይገባናል፡፡ እውነቱ ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ደሙ ሐጢያቶቻችንን መደምሰሱ ነው፡፡ ቤዛነት የሚሰጠን እውነቱን ስናምን ነው፡፡ 
 
 

የኢየሱስ ጥምቀት ያድነናል፡፡ 

 
መንፈስ ቅዱስን የሚቀበለው ማነው? 
በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደሙ ያመነና ከሐጢያቶቹ ሁሉ ቤዛነትን ያገኘ ሰው ነው፡፡ 

በብሉይ ኪዳን የመስዋዕት ስርዓት አማካይነት የሚገኘው የሐጢያት ስርየት በአዲስ ኪዳን የኢየሱስን ጥምቀት ያመላክታል፡፡ የኢየሱስ ጥምቀት በብሉይ ኪዳን ላሉ ትንቢቶች በሙሉ መሰረት ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን እጆችን የመጫኑ እኩያ በአዲስ ኪዳን በኢየሱስ ጥምቀት ውስጥ ሊገኝ ይችላል፡፡   
የእስራኤል ሐጢያቶች በእጆች መጫን አማካይነት ወደ አዛዜሉ ፍየል እንደተሻገሩ ሁሉ የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ በጥምቀቱ አማካይነት ወደ ኢየሱስ ተሻግረዋል፡፡
ከሐጢያቶቻችን ሁሉ ለመዳን በኢየሱስ ጥምቀት ማመን አለብን? አዎን በዚህ ማመን አለብን! ኢየሱስ በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ የመውሰዱን እውነት መቀበል አለብን፡፡ በኢየሱስ ጥምቀት የማናምን ከሆነ ሐጢያቶቻችን ወደ እርሱ ሊተላለፉ አይችሉም፡፡ ደህንነታችንን ሙሉ ለማድረግ በዚህ ማመን አለብን፡፡ አለበለዚያ ጻድቃን ልንሆን አንችልም፡፡  
ኢየሱስ በጥምቀቱ የዓለምን ሐጢያተኞች በሙሉ እጅግ ተስማሚና ጻድቅ በሆነ መንገድ አዳናቸው፡፡ ይህ ከዚህ በበለጠ ተስማሚ መንገድ ሊደረግ አይችልም ነበር፡፡ የኢየሱስ ጥምቀት ሐጢያቶች ሁሉ ወደ እርሱ የተሻገሩበት ሒደት በመሆኑ ልቦቻችን ለዘለቄታው ከሐጢያት ይነጹ ዘንድ ልናምንበት ይገባናል፡፡   
የኢየሱስ ደም ለሐጢያቶቻችን ሁሉ የተሰጠ ፍርድ እንደነበር ማመን ይገባናል፡፡ ስለዚህ በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደሙ የሚያምኑ ሁሉ ከሐጢያት ድነዋል፡፡  
መንግሥት ሰማይ ለመግባት በኢየሱስ ጥምቀት ማመን ይገባናል፡፡ ይህ ከሐጢያት አርነት መውጣትና ቅን የሆነውን ቅጣት ማምለጥ የምንችልበት ብቸኛው መንገድ ነው፡፡   
በአዲስ ኪዳን ያለው የኢየሱስ ጥምቀትና በብሉይ ኪዳን ያለው እጆችን መጫን አንዳቸው ለሌላቸው መስተዋት ናቸው፡፡ እነዚህም በብሉይ ኪዳንና በአዲስ ኪዳን መካከል ያሉ ማያያዣ ቀለበቶች ናቸው፡፡ 
በአዲስ ኪዳን አጥማቂው ዮሐንስ ወደ ምድር የመጣው ከኢየሱስ 6 ወር ቀደም ብሎ ነበር፡፡ ኢየሱስ በተጠመቀ ጊዜ ‹‹የእግዚአብሄር ልጅ የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል መጀመሪያ፡፡›› (ማርቆስ 1፡1) ነበር፡፡ ወንጌሉ የሚጀምረው ኢየሱስ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ በጥምቀቱ በወሰደ ጊዜ ነው፡፡  
ለሰው ዘር ደህንነት የተደረገው አገልግሎት እንደ ሰንሰለት በተያያዙ ክስተቶች አማካይነት ተግባራዊ ተደርጓል፡፡ ይህም የኢየሱስ መወለድ፣ የእርሱ ጥምቀት፣ የመስቀል ላይ ሞቱና ትንሳኤው እንደዚሁም ወደ ሰማይ ያደረገው ዕርገቱ ናቸው፡፡ በዚህ የክስተቶች ሰንሰለት ውስጥ ያለውን የደህንነት ሒደት ስናውቅ ስንረዳና ስናምን ከሐጢያቶቻችን ሁሉ እንድናለን፡፡ የኢየሱስ ጥምቀት የወንጌል መጀመሪያ ሲሆን በመስቀል ላይ ያፈሰሰው ደሙ ደግሞ መደምደሚያው ነው፡፡
 ‹‹የእግዚአብሄር ልጅ የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል መጀመሪያ፡፡›› (ማርቆስ 1፡1) የጽድቅ ምግባሮቹን -- ጥምቀቱን፣ በመስቀል ላይ ያፈሰሰውን ደሙን፣ ትንሳኤውን፣ ዕርገቱንና ዳግም ምጽአቱን--አንዳቸውንም ከእግዚአብሄር ልጅ ወንጌል መግደፍ አንችልም፡፡    
ኢየሱስ ሥጋን ለብሶ ወደዚህ ዓለም መጣና የሰውን ዘር ሐጢያቶች በሙሉ በጥምቀቱ ወሰደ፡፡ የሰማያዊው ወንጌል ጅማሬ ይህ ነው፡፡ ከእነዚህ አንዱ እንኳን ጎድሎ ቢሆን ኖሮ ሰማያዊው ወንጌል የተሟላ ባልሆነም ነበር፡፡  
ስለዚህ አንድ ሰው ዳግም መወለድ ቢፈልግ በክርስቶስ ጥምቀትና በደሙ እውነት ማመን ይኖርበታል፡፡ በዚህ ዘመን ብዙ ሰዎች በኢየሱስ ጥምቀትና ደም እውነት አያምኑም፡፡  የኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀት ሃይማኖታዊ ስርዓት ብቻ እንደሆነ ያስባሉ፡፡ ይህ ከበድ ያለ የተሳሳተ እሳቤ ነው፡፡ በኢየሱስ የሚያምን ማንኛውም ሰው በጥምቀቱና በደሙም ደግሞ ማመን አለበት፡፡  
ለይቅርታ በመጸለይ ብቻ ሐጢያቶቻችን እንዴት ሊነጹ ይችላሉ? ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ ሲጠመቅ ሐጢያቶቻችን በሙሉ ወደ እርሱ ተሻገሩ፡፡ ከዚህ ሌላ የሰውን ዘር ሐጢያቶች ሊወስድ የሚችልበት ሌላ መንገድ አልነበረውም፡፡   
መንግሥተ ሰማይ ለመግባት ከውሃና ከመንፈስ ዳግም መወለድ ይኖርብናል፡፡ ሰው ያለ ጥምቀት ያለ መስቀሉ ደምና ቤዛነት ሊኖር አይችልም፡፡ ኢየሱስ ለኒቆዲሞስ በዮሐንስ 3፡5 ላይ እንደነገረው እግዚአብሄርን ማየት የሚችለው ዳግም የተወለደ ሰው ብቻ ነው፡፡ እውነተኛ ደህንነት የምናገኘው በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ስናምን ነው፡፡ 
 
 

ያለ ኢየሱስ ጥምቀት መዳን እንችላለን? 

 
ኢየሱስ አዳኛችን የሆነው እንዴት ነው?
በጥምቀቱ ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በመውሰዱ ነው፡፡ 

ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም መጥቶ በጥምቀቱ አማካይነት ሐጢያቶቻችንን በሙሉ የመውሰዱን እምነት ከይፋ አገልግሎቱ ከገደፍን ወይም ከድንግል ማርያም የተወለደውን የኢየሱስን ቅድስና ቸል ካልን ወይም በክርስቶስ መስቀል ለማመን ግድ የለሾች ከሆንን ክርስትና ልክ ቡዲስቶች በመቅደሶቻቸው ውስጥ እንደሚያደርጉት ምዕመናን ‹‹ይቅር በለኝ! ይቅር በለኝ! ይቅር በለኝ!›› ብለው እንዲጮሁ የሚመራ ተራ የሆነ ባዕድ አምልኮአዊ ሃይማኖት ይሆናል፡፡ 
የኢየሱስን ጥምቀት መግደፍ ማለት ሐጢያቶቻችን ወደ እርሱ አልተላለፉም ማለት ነው፡፡ እምነታችን ከንቱ ይሆናል፡፡ በተጨባጭ ምንም የከፈለው ነገር ሳይኖር ዕዳዎቹን ሁሉ እንደከፈለ ከሚናገረው ባለ ዕዳም የተለየን አንሆንም፡፡ ዋሾዎች ያደርገናል፡፡ ባለ ዕዳው በተጨባጭ ምንም የከፈለው ነገር ሳይኖር ዕዳዎቹን ሁሉ መክፈሉን ከተናገረ በተግባርም በሕሊናም ገና ባለ ዕዳ ነው፡፡  
ኢየሱስ በጥምቀቱ ውሃ ምዕመናንን አነጻና የእግዚአብሄር ልጆች አደረጋቸው፡፡ አማኞች በሙሉ ይጸድቁ ዘንድ ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ በመጠመቅ ሐጢያቶቻቸውን በሙሉ ወሰደ፡፡ ይህንን ስናውቅና ስናምን ልቦቻችን ለዘላለም  ይነጻሉ፡፡   
ለጸጋው እግዚአብሄር የተመሰገነ ይሁን፡፡ ሉቃስ 2፡14 እንዲህ ይላል፡- ‹‹እግዚአብሄርንም እያመሰገኑ ክብር ለእግዚአብሄር በአርያም ይሁን፡፡ ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ አሉ፡፡›› በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ላይ ያለን እምነት ምሉዕ ደህንነትን አመጣልንና የእግዚአብሄር ልጆች እንድንሆን አደረገን፡፡ የኢየሱስ ጥምቀትና ደሙ አዳነን፡፡ በእነዚህ ሁለት ነገሮች ያመነ ሁሉ ይድናል፡፡ 
ከእርሱ ሥራዎች ምንም የሚገደፍ ነገር የለም፡፡ አንዳንዶች ሐዋርያው ጳውሎስ ስለ መስቀሉ እንጂ በሌላ አልተመካም ብለው ያምናሉ፡፡ ነገር ግን የኢየሱስ ጥምቀት በመስቀሉ ውስጥ ተካቶዋል፡፡ 
በሮሜ 6 ላይ ጳውሎስ በክርስቶስ እንደተጠመቀና ከክርስቶስ ጋር እንደሞተ እናያለን፡፡ በገላትያ 2፡20 ላይም፡- ‹‹ከክርስቶስ ጋር ተሰቅዬአለሁ፤ እኔም አሁን ሕያው ሆኜ አልኖርም፡፡ ክርስቶስ ግን በእኔ ይኖራል፡፡ አሁንም በሥጋ የምኖርበት ኑሮ በእግዚአብሄር ልጅ ላይ ባለ እምነት የምኖረው ኑሮ ነው›› ተብሎ ተጽፎዋል፡፡  
በገላትያ 3፡27-29 ላይም እንዲህ ተጽፎዋል፡- ‹‹ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና፡፡ አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፡፡ ባርያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፡፡ ወንድም ሴትም የለም፡፡ ሁላችሁም በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁ፡፡ እናንተም የክርስቶስ ከሆናችሁ እንኪያስ የአብርሃም ዘር እንደ ተስፋውም ቃል ወራሾች ናችሁ፡፡››  
በኢየሱስ ክርስቶስ መጠመቅ ማለት ኢየሱስ በዚህ ምድር ላይ እያለ በሰራቸው ነገሮች በጥምቀቱና በደሙ ማመን ማለት ነው፡፡ በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ማመን ማለት ኢየሱስ ከ2,000 ዓመታት በፊት ሐጢያቶቻችንን ደመሰሰልን በሚለው እውነት ማመን ነው፡፡ ደህንነትን የሚያመጣልን ሌላ መንገድ የለም፡፡  
 
 
በኢየሱስ ጥምቀትና በመስቀል ላይ ደሙ ስናምን በእግዚአብሄር ድነናል፡፡ 
 
ለይቅርታ በመጸለይ ብቻ ሐጢያቶቻችን ሊነጹ ይችላሉን? 
አይችሉም፡፡ ለሐጢያቶቻችን ይቅርታን የምናገኘው ሐጢያቶቻችን በሙሉ ኢየሱስ በአጥማቂው ዮሐንስ በተጠመቀ ጊዜ ወደ እርሱ መተላለፋቸውን ስናምን ብቻ ነው፡፡   

‹‹ሰው በልቡ አምኖ ይጸድቃል፤ በአፉም መስክሮ ይድናልና፡›› (ሮሜ 10፡10) 
‹‹ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና፡፡›› (ገላትያ 2፡27) እምነታችን በክርስቶስ እንድንጠመቅ፣ ክርስቶስን እንድንለብስና የእግዚአብሄር ልጆች እንድንሆን ይመራናል፡፡ ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም በመጣና በተጠመቀ ጊዜ የእኛ ሐጢያትና የዓለም ሐጢያቶች በሙሉ ወደ እርሱ ተላልፈዋል፡፡   
እምነታችን ከክርስቶስ ጋር አንድ እንድንሆን መርቶናል፡፡ እርሱ በሞተ ጊዜ እኛም ሞተናል፡፡ እርሱ በተነሳ ጊዜ እኛም ተነስተናል፡፡ አሁን እኛ በኢየሱስ ጥምቀት፣ በደሙ፣ በትንሳኤው፣ በዕርገቱና በምጽአቱ ስለምናምን መንግሥተ ሰማይ መግባትና ለዘላለም መኖር እንችላለን፡፡  
ሰዎች በኢየሱስ ደም ብቻ የሚያምኑ ከሆኑ በልቦቻቸው ውስጥ ባለው ሐጢያት ከመሰቃየት ውጪ ምንም ሊያደርጉ የሚችሉት ነገር የለም፡፡ ለምን? ምክንያቱም እነርሱ የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ የወሰደውንና በሐጢያት የተሞሉትን ልቦች አንጽቶ ለዘላለም እንደ በረዶ ነጭ ያደረጋቸውን የኢየሱስን ጥምቀት ትርጉም አያውቁትም፤ አይቀበሉትምም፡፡
ከሐጢያቶቻችሁ በሙሉ ለዘላለም ባዳናችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀትና ደም ታምናላችሁን? እባካችሁ በዚህ በማይለወጥ እውነት እመኑ፡፡ በኢየሱስ ጥምቀት የማታምኑ ከሆነ እምነታችሁ ከንቱ ነው፡፡ በኢየሱስ ጥምቀት እምነት ከሌላችሁ ለሐጢያቶቻችሁ ቤዛነትን ልታገኙ አትችሉም፡፡
እነዚያ በመስቀሉ ብቻ የሚያምኑ ሰዎች ‹‹ኢየሱስ ጌታዬ በመስቀል ላይ ለእኔ የሞተልኝ አዳኜ ነው፡፡ እንደገናም ለትንሳኤው ምስክርነት ተነስቶ ለ40 ቀናት ያህል ቆይቶ ወደ ሰማይ አረገ፡፡ አሁን በእግዚአብሄር ቀኝ ተቀምጦዋል፡፡ እኛን ሊፈርድ ለሁለተኛ ጊዜ እንደሚመጣ አምናለሁ፡፡ ኢየሱስን ልገናኘው እንድችልም ሙሉ በሙሉ እንዲለውጠኝ እጸልያለሁ፡፡ ኦ የምወድህ ኢየሱስ ጌታዬ!›› ይላሉ፡፡
እነርሱ ለሐጢያቶቻቸው ይቅርታን ይጠይቁና ያለ ሐጢያት ለመሆን ተስፋ ያደርጋሉ፤ ነገር ግን በልቦቻቸው ውስጥ ሐጢያት አለ፡፡ ‹‹በኢየሱስ አምናለሁ፤ ነገር ግን በልቤ ውስጥ ሐጢያት አለ፡፡ ኢየሱስን ብወደውም በውስጤ ሐጢያት አለ፡፡ በልቤ ውስጥ ሐጢያት ስላለና ስለ ደህንነቴ እርግጠኛ መሆን ስለማልችል ‹ሙሽራዬ እባክህ ወደ እኔ ና› ማለት አልችልም፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ የሚመጣው እኔ በደምብ ስዘጋጅና ጠንክሬ ከጸለይሁና በርትቼ ንስሐ ከገባሁ በኋላ እንደሆነ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ኢየሱስን በሙሉ ልቤ ብወደውም በልቤ ውስጥ ባሉት ሐጢያቶች ምክንያት ልጋፈጠው አልደፍርም፡፡››
ኢየሱስ እነዚህን ሰዎች ‹‹ሙሉ አይደለንም ብላችሁ ለምን ታስባላችሁ?›› ብሎ ቢጠይቃቸው፤ 
‹‹ጌታ ሆይ በየዕለቱ ሐጢያትን ስለምሰራ ጻድቅ አለመሆኔን አውቃለሁ፡፡ ስለዚህ እባክህ ሐጢያተኞችን በምትጠራ ጊዜ ጥራኝ›› ብለው ይመልሱ ነበር፡፡    
እነርሱ የሁሉም ነገር ፈጣሪና ፈራጅ የሆነው እግዚአብሄር ሐጢያተኞችን እንደማይቀበልም ሆነ ልጆቹ እንደማያደርጋቸው አያውቁም፡፡ 
ሙሽራው መጣና የሙሽራይቱን የሐጢያት ችግር በሙሉ ፈታላት፡፡ ሙሽራይቱ ግን ይህንን እውነት ስላላወቀች ተሰቃየች፡፡ በሥጋ ሐጢያትን ስለሰራን ሐጢያተኞች  እንደሆነን በምናስብበት ጊዜ በእግዚአብሄር እምነት የለንም፡፡ የእግዚአብሄርን የእውነት ቃል ካላወቅንም ሆነ ካላስተዋልን ሐጢያት በልቦቻችን ውስጥ መብዛቱን ይቀጥላል፡፡    
 
አንዳንድ ሰዎች በልቦቻቸው ውስጥ በቀረ ሐጢያት የሚሰቃዩት ለምንድነው? 
የዓለምን ሐጢያቶች በሙሉ የወሰደውን የኢየሱስን ጥምቀት ትርጉም ስለማያውቁም ሆነ  በልቦቻቸው ስለማይቀበሉ ነው፡፡  

ሙሽራው የዓለምን ሐጢያት በሙሉ ወሰደ፡፡ የት? በዮርዳኖስ በተጠመቀ ጊዜ፡፡ ይህንን የማያምኑ ሰዎች አሁንም ሐጢያተኞች ናቸው፡፡ የረከሱ ሙሽሮች ሆነው ይቀራሉ፡፡  
ሙሽራው ሙሽራይቱን ‹‹የእኔ ሙሽራ ሳትሆኝ እንዴት ልታፈቅሪኝ ትችያለሽ? እኔን ሙሽራዬ ብለሽ ከመጥራትሽ በፊት ሐጢያቶችሽ በሙሉ መንጻት አለባቸው፡፡›› 
ያለ ኢየሱስ ጥምቀት ቤዛነትን ልናገኝ እንችላለን? አንችልም፡፡ እኛ የተፈጠርነው በእግዚአብሄር አምሳል ስለሆነ በልቦቻችን ፍትህን እንሻለን፡፡ ሕሊናዎቻችንም ቀና ሊሆኑ ይሞክራሉ፡፡ ነገር ግን ልቦቻችን ሳይነጹ ሐጢያት አልባ ነን ብለን ማሰባችን የሚቻል አይደለም፡፡ በትክክል ሐጢያት አልባና ጻድቃን ነን ማለት የምንችለው በኢየሱስ ጥምቀት ስናምንና ይህንን ስንቀበል ብቻ ነው፡፡  
በልቦቻችን ውስጥ በተጨባጭ ሐጢያት እያለ ራሳችንን ያለ ሐጢያት እንደሆንን አድርገን የምንመለከት ከሆነ ሕሊናዎቻችን በጭራሽ ሊቀደሱ አይችሉም፡፡ በዚህ አይነት ሁኔታዎችም እግዚአብሄር አይቀበለንም፡፡ እግዚአብሄር ከቶውኑም አይዋሽም፡፡ 
እግዚአብሄር የእስራኤልን ልጆች እንዲቆጥርና ለሕይወታቸው ቤዛነትን እንዲከፍሉ ለሙሴ ነገረው፡፡ ባለጠጋው ከግማሽ ሰቅል በላይ አይሰጥም፡፡ ደሃውም ከዚያ ያነሰ አይሰጥም፡፡ እያንዳንዱ ሰው ቤዛ ይከፍላል፡፡  
ስለዚህ አንድ ሰው ለሕይወቱ ቤዛነትን በከፈለለት በኢየሱስ ካላመነ እንዴት ሊቀደስ ይችላል? እንደዚህ ያለ ሰው በልቡ ውስጥ ሐጢያት መኖሩን ይቀጥላል፡፡  
በኢየሱስ ደም ብቻ ስንምን በልቦቻችን ውስጥ ሐጢያት እንዳለና ሐጢያተኞች እንደሆንን መናዘዝ ይኖርብናል፡፡ ነገር ግን በውሃውና በመንፈሱ ወንጌል ስናምን በትክክል ሐጢያት እንደሌለብን መናገር እንችላለን፡፡ ደህንነትና የዘላለም ሕይወት የእኛ ይሆናሉ፡፡  
 
 

መንፈስ ቅዱስን መሳደብ፡፡  

 
ሰውን ለሲዖል የሚኮንነው ምን አይነት ሐጢያት ነው? 
በመንፈስ ቅዱስ ላይ የሚሰራ ሐጢያት ማለትም በኢየሱስ ጥምቀት አለማመን ነው፡፡ 

ሮሜ 1፡17 እንዲህ ይላል፡- ‹‹የእግዚአብሄር ጽድቅ ከእምነት ወደ እምነት በእርሱ ይገለጣልና፡፡›› የእግዚአብሄር ጽድቅ በወንጌል ውስጥ ተገልጦዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም መጣና ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በጥምቀቱና በመስቀል ላይ ሞቱ አነጻቸው፡፡ የኢየሱስ ጥምቀትና ደሙ የወንጌል ሐይል ነው፡፡ ኢየሱስ ሐጢያቶቻችንን ለአንዴና ለመጨረሻ አነጻ፡፡  
ማመን መዳን ሲሆን አለማመን የዘላለም ሲዖል ነው፡፡ በሰማይ ያለው አባታችን አንድያ ልጁን ወደዚህ ዓለም ላከና ስለ እኛ ሐጢያት እንዲጠመቅ አደረገው፡፡ ስለዚህ በእርሱ የሚያምን ከመተላለፎቹ ሁሉ መንጻት ይችላል፡፡ 
በዚህ ዓለም ላይ የቀረው ብቸኛው ሐጢያት በእርሱ ጥምቀትና ደም የአለማመን ሐጢያት ነው፡፡ አለማመን መንፈስ ቅዱስ መሳደብና በእግዚአብሄር የሚፈረድበት ሐጢያት ነው፡፡ የማያምነውን ለሲዖል ይኮንነዋል፡፡ ይህ ከሁሉም እጅግ የከፋ ሐጢያት ነው፡፡ ይህንን ሐጢያት የሰራችሁ ማናችሁም ንስሐ መግባትና በኢየሱስ ጥምቀት በማመን ቤዛነትን ማግኘት አለባችሁ፡፡ እንደዚያ ካልሆነ ለዘላለም ትጠፋላችሁ፡፡  
በእርሱ ጥምቀትና በደሙ አማካይነት በሆነው የቤዛነት ምስክርነት ድናችኋልን? በዮሐንስ 1፡29 ላይ እንደተጻፈው የዮሐንስን ምስክርነት ተቀብላችሁታልን? ‹‹እነሆ የዓለምን ሐጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሄር በግ›› በዕብራውያን 10፡18 ላይ እንደተጻፈው በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ታምናላችሁን? ‹‹የእነዚህም ስርየት ባለበት ዘንድ ከዚህ ወዲህ ስለ ሐጢአት ማቅረብ የለም፡፡››  
እግዚአብሄር በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ለሚያምኑት በልቦቻቸው ውስጥ ማረጋገጫን ይሰጣቸዋል፡፡ እግዚአብሄር ልጆቹ ያደርጋቸዋል፡፡ በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ የሚያምኑ ሰዎች ጻድቅ በሆነው የኢየሱስ ፍቅር ቤዛነትን ያገኙ ናቸው፡፡  
እግዚአብሄር የላከው የእግዚአብሄርን ቃል ይናገራል፡፡ ነገር ግን ከምድር የሆኑና በእግዚአብሄር ያልተላኩ ከራሳቸው አስተሳሰቦች ጋር የሚጣጣሙትን ይሰብካሉ፡፡ በዚህ ምድር ላይ የእግዚአብሄርን ቃል የሚሰብኩ ብዙዎች ናቸው፡፡ በእግዚአብሄር የተላኩ የኢየሱስን ጥምቀትና የደሙን ወንጌል ይሰብካሉ፡፡
ነገር ግን የራሳቸውን ቃሎች የሚሰብኩ የራሳቸውን አስተሳሰቦች ብቻ እያብራሩ ነው፡፡ ‹‹ከአዳም ሐጢያት ድነናል፡፡ ነገር ግን እያንዳንዱ ሰው ለዘወትር ሐጢያቶቹ ንስሐ መግባት ይኖርበታል›› ብለው ይሰብካሉ፡፡ ቀስ በቀስም እንደምንቀደስ ይናገራሉ፡፡   
ነገር ግን ሰው በራሱ ሊቀደስ ይችላልን? በራሳችን ትሩፋቶች ብርታትና በጥረቶቻችን መቀደስ እንችላለን? የተቀደስነው እግዚአብሄር ሐጢያቶቻችንን በሙሉ በማንጻቱ ነው ወይስ በራሳችን ቤዛነት ላይ በመድረሳችን?   
እውነተኛ እምነት ይቀድሰናል፡፡ ከሰልን አንድ ሺህ ጊዜ በማጠብ ነጭ ልናደርገው ይቻለናልን? ጥቁር ቆዳንስ ነጭ ማድረግ ይቻለናልን? ምንም ያህል ሳሙና ወይም በረኪና  ሐጢያቶቻችንን ሊያነጻ አንችልም፡፡ ጽድቃችን የመርገም ጨርቅ ነው፡፡ የምንጸድቀው በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ በማመን ነው ወይስ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ በማመን ብቻ?   
እውነተኛ እምነት የሚመጣው በኢየሱስ የጥምቀቱ ውሃና በመስቀል ላይ ካፈሰሰው ደም ነው፡፡ ደህንነት ከራሳችን ጥረቶች ሊመጣ አይችልም፡፡ ከሐጢያት ሊያነጻንና ጻድቃን ሊያደርገን የሚችለው በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ያለን እምነት ብቻ ነው፡፡  
አብ ሰዎችን ሁሉ በልጁ እጅ አሳልፎ ሰጥቶታል፡፡ በእርሱ የሚያምኑ ሰዎችም የዘላለም ሕይወትን ያገኛሉ፡፡ በልጁ ማመን ማለት በጥምቀቱና በደሙ በማመን በሚገኘው ቤዛነት ማመን ማለት ነው፡፡ በዚህ የሚያምን የእግዚአብሄር ልጅ ይሆንና የዘላለምን ሕይወትን ያገኛል፡፡ የዳኑትም ለዘላለም በእግዚአብሄር ቀኝ ይኖራሉ፡፡   
በኢየሱስ ጥምቀትና ከእግዚአብሄር ጋር ባለው አንድነቱ ማመን በመንፈሱም ማመን ነው፡፡ የእውነት ቃል ዳግም እንድንወለድ ይፈቅድልናል፡፡ በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ማመን ድነናል፡፡ 
እምነት ይኑራችሁ፡፡ በኢየሱስ ጥምቀትና በደሙ ማመን ማለት ዘላለማዊ ቤዛነትን ማግኘት ማለት ነው፡፡ በእውነተኛው ወንጌል በማመን የሐጢያት ይቅርታን አግኙ፡፡